Friday, November 1, 2013

አባ እስጢፋኖስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ላይ እየፈጸሙ ያለው ሙስናና እየነፈጉ ያለው ፍትሕ ብዙዎችን እያማረረ ነው!


 
ከመግቢያችን ለጥቆ ያለው ርዕሱን ገላጭ የሆነው ጽሁፍ የተገኘው ከአባ ሰላማ ብሎግ ነው።

(እንደመግቢያ፤ ከደጀብርሃን)

ቅድሚያ ይድረስ ለፓትርያርክ ማትያስ!!

 ብዙ ጊዜ አስነዋሪ ገመና የተሸከሙ ሰዎች ገመናቸውን በንስሐ ማጠብ እርም ሆኖባቸው መቆየቱ ሳያንስ  ገመናቸውን ተሸክመው አርፈው እንደመቀመጥ ወደአደባባይ ይወጡና ጭራሹኑ የገመናቸውን መጠን ሲያሳድጉ ይታያሉ። አደባባይ ያወቀውን ገመና ተሸክመው ይኖሩ የነበሩትና ተሸፍኖላቸው እንደትልቅ ሰው የጅማ መሪ የሆኑት አባ እስጢፋኖስ የገመናውን ደረጃ ወዳሳደጉበት አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመልሰው ሲመጡ «ድመት መንኩሳ አመሏን ላትረሳ» ያሉ ብዙዎች ነበሩ። በእርግጥም እስከመቃብር አብሯቸው የሚዘልቀው ገመና ከሥጋ አልፎ አጥንታቸው ላይ የተጣበቀው አባ እስጢፋኖስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን ከማኅበረ ቅዱሳን ነፍሰ በላዎች ጋር በመተጋገዝ እያጠቡት ይገኛሉ።   ማንም ሳይነካቸውና ገመናቸው ከሰፈር ወሬ ባለፈ የተናገረ ማንም ሳይኖር በራሳቸው ጊዜ  ገመናዬን አደባባይ አውጡልኝ፤ በሚዲያም ተናገሩልኝ ሲሉ በሥራቸው አላፊ አግዳሚውን ተጣሩ፤ እያፈናቀሉና ወሮ በላውን እያሳደጉ የማን ወዳጅ መሆናቸውን በተግባር አሳዩ።   አለመታደል ሆኖ እንጂ ሊቀ ጳጳሱ መልካም አስተዳደርና ሙስናን ተከላክለው ቢሆኑ ኖሮ ገመናቸውን በማውጣት ማንም ድካማቸውን ለመተረክ ጊዜውን ባላጠፋ ነበር። ይሁን እንጂ «ያዳቆነ ሰይጣን » እንዲሉ ክፉ ተግባራቸውን ለመተው መቼም ቢሆን ያልታደሉት የጥፋት ሰው አባ እስጢፋኖስ ደሃውን አስለቀሱ፤ ከስራ አፈናቀሉ፤ በአየር ላይ አንሳፈው ለረሃብና ለመከራ አጋልጠው ሰጡ፤ የሚሸጡትን ሰው ሸጡ፤ የሚገድሉትንም በደብዳቤ እንዳይነሳ አድርገው ጣሉ።  ከዚህ ሁሉ የከፋውና የሚያሳዝነው ደግሞ ፓትርያርክ ማትያስም ለዚህ ወንጀልና ለመጥፎ ድርጊት ተባባሪ ሆነው መገኘታቸው ነው።                                  
ዋናው ምክንያት ፓትርያርክ ማትያስን ላስመረጡበት ውለታ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት የተበረከተ ክፍያ ሲሆን በሌላ መልኩም «ግም ለግም አብረህ አዝግም»  የሚለው የብሂል ገመድ እየሳበ ፓትርያርኩን ስላስቸገረ ነው።  አባ ማትያስ ከፓትርያርክነታቸው በፊት የጵጵስና ዘመናቸውን የሚያጋልጥ ከወራት በፊት በእጃችን ላይ የደረሰው አስደማሚ መረጃ ቢኖርም አደባባይ ላይ ማውጣት ያልፈለግነው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብር ነበር። ቤተክርስቲያኒቱን አክብረው ማስከበር ሲገባቸው ቤተ ክርስቲያኒቱን ለችግርና ለሰቆቃ አጋልጠው ለሚሰጡ አባ እስጢፋኖስን ለመሰሉ የዘመኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ እርግማን ለሆኑ ሰዎች ጥላና ከለላ መሆናቸው  ግምት ውስጥ የሚያስገባቸው ብቻ ሳይሆን የኔንም እንደውዴ አባ እስጢፋኖስ አደባባይ አውጡልኝ እያሉ በሰጡት የዐመጻ ድጋፍ አርፎ የተቀመጠውን ፋይል እየቀሰቀሱት መሆኑን ሊያውቁት ይገባል። ከዚያም በተረፈ የነማን ወዳጅ ምን ይመስላል? ለሚለው የሰዎች የጥያቄ እንቆቅልሽ መልስ እንዲያገኝ በር እየከፈቱ መሆንዎን ለፓትርያክነትዎ እንናገራለን። በዚህ ዘመን የተከደነ የማይገለጥ እንደሌለም ይወቁ። የአባ እስጢፋኖስ የገመና ሰማዕት መሆን ከፈለጉ ምርጫው የእርስዎ ብቻ ነው። እኛም ለእንደዚህ ዓይነት ሰዎች የሚኖረን ትዕግስት እስከመቼ ነው? አርፈው እንዲቀመጡ ሊነገራቸው ይገባል? ወይስ እነሱ የዐመጻቸውን ቆሻሻ ሲደፉብን ዝም ብለን እንሸከም? ብለን ራሳችንን እንጠይቃለን።
  በመጨረሻም ለፓትርያርክ ማትያስ የምናቀርበው ልመናና ተማጽኖ ሀገረ ስብከቱን እያወኩ የሚገኙት ሊቀ ጳጳስ ተብዬ ሰው ከቦታው ያንሱልን!!  ጳጳሱ ለዋሉት ውለታቸው ቤተ ክርስቲያንን በመሸጥ ሳይሆን  አሜሪካ ከሚከፈልዎ የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ደመወዝዎ ላይ ቀንሰው በዶላር ይስጡ። ያለምንም ማስፈራራት ቀጣዩ የአደባባይ ገመና የእርስዎ ይሆናል። ከዚያ በኋላ የትም ሄደው ቢደሰኩሩ እመራዋለሁ ከሚሉት ሕዝብ ፊት የሚታየው እርስዎ ያልተጸየፉትና ተከድኖ ሳይገለጥ የቆየው ገመናዎ ለአባ እስጢፋኖስ የቀረበ መስዋዕት ይሆንልዎታል።  ኃጢአትን የተለማመደ ሰው ይህ ምንም ስሜት ባይሰጠውም፤ ኃጢአታቸውን ለመሸፈን ሲሉ መልካም ለመሥራት ቃል ያልገቡ መሪዎች ሁሉ የሚከተላቸው የኃጢአታቸው ደብዳቤ መሆኑን ስለምንረዳ በመጨረሻው ዘመን የመንፈሳዊ ሰዎች መታጣት ስለሚታወቅ ብዙም አያስገርመንም።
                                                                  
«የአንዳንዶች ሰዎች ኃጢአት የተገለጠ ነው ፍርድንም ያመለክታል፥ ሌሎችን ግን ይከተላቸዋል» 1ኛ ጢሞ 5፤24

የአባ ሰላማ ብሎግ የአባ እስጢፋኖስን ተግባር ያጋለጠበት ጽሁፍ ይህንን ይመስላል።
አባ ገብረ ሚካኤል ለጵጵስና ሲታጩ የዑራኤል አስተዳዳሪ የነበሩት አባ ላእከ የተባሉ አባት ለአቡነ ጳውሎስ “ምነው አባታችን የምናውቃቸውን አባ ገብረ ሚካኤልን ልንድራቸው ሲገባ እንዴት ያጰጵሳሉ? እነዚህ በሚመሯት ቤተክርስቲያን ውስጥ በኀላፊነት መሥራት አልፈልግም” ብለው “ኢታርእየኒ ሙስናሃ ለኢየሩሳሌም” ወይም “የኢየሩሳሌምን ጥፋቷን አታሳየን” እንዳለው ነቢይ የኦርቶዶክስን ጥፋት ላለማየት በመወሰን ወደ መርጡለማርያም ገዳም እንደገቡ ይነገራል፡፡ መልአከ ገነት አባ ኀይለ ማርያም የተባሉ አራዳ ጊዮርጊስ አለቃ የነበሩ አባትም በጊዜው በጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን የነበረውን ገንዘብ ለመዝረፍ ታስቦ እርሳቸው ለጵጵስና ሲታጩ (ከእነአባ ገብረሚካኤል ጋር)፣ “ወቅብዐ ኃጥኣንሰ ኢይትቀባዕ ርእስየ” እና “ወኢይደመር ውስተ ማኅበሮሙ ለእኩያን” የሚሉትን የቅዱሳት መጻሕፍት ቃል በመጥቀስ የሚያስተዳድሩትን ደብር ለቀው ገዳም ሊገቡ ሲሉ በፓትርያርኩ ተለምነው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሆነው ነበር፡፡ ነገር ግን የአባ ገብረሚካኤል የድራፍት ቡድን አላላውስ አላንቀሳቅስ ስላላቸው የሚወዷትን አገራቸውንና ቤተክርስቲያናቸውን ጥለው በመሰደድ በብስጭትና በንዴት በስደት አገር ሳሉ ዐርፈዋል፡፡ እነዚህ አባቶች ያኔ የተናገሩት ቢሰማና አባ ገብረሚካኤል ወደ ጵጵስና ሳይሆን ወደ ትዳር እንዲገቡ ቢደረግ ኖሮ ዛሬ በእርሳቸው እየደረሰ ያለው ጥፋት በቤተክርስቲያን ላይ ባልደረሰ ነበር የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም፡፡

በአባ ገብረሚካኤል እጩነት ላይ አባ ላእከ እና መልአከ ገነት አባ ኃይለ ማርያም ያቀረቡት ቅሬታ ሰሚ ሳያገኝ እነርሱ ወደገዳምና ስደት በኋላም ወደሞት፣ አባ ገብረ ሚካኤልም “አባ እስጢፋኖስ” ተብለው ወደ ጵጵስና መጡ፡፡ አባ እስጢፋኖስን “አባ” ከማለት ይልቅ “አቶ” ማለት ይቀላል ይላሉ የሚያውቋቸው፡፡ በቆብ ውስጥ ትዳር ከመሰረቱና ባለትዳር መሆናቸው ከሚነገርላቸው ጳጳሳት መካከል አባ እስጢፋኖስ አንዱ ሲሆኑ የቆብ ውስጥ ትዳር በመመስረታቸው ብዙዎች የእሳቸው ይሻላል ቢሉም፣ ብዙ ውሽሞች ያሏቸው መሆናቸው እየተጋለጠ ሲመጣ ግን “እኛስ በአንድ በመወሰናቸው ደስ ብሎን ነበር ግን ምን ያደርጋል …” ወደማለት መጥተዋል፡፡
አባ እስጢፋኖስ ሊቀጳጳስነት እንደ ተሾሙ ከሌሎቹ ጳጳሳት ጋር አባ ጳውሎስ አክሱም ይዘዋቸው ሄደው የነበረ ሲሆን፣ ሌሎቹ ጳጳሳት ወደ ጽላት ቤት ይዘዋቸው ሲገቡ ለዚህ ጉዳይ እንጅግ የሚጠነቀቁት አክሱማውያን ካህናት ከጳጳሳቱ መካከል አባ አስጢፋኖስን የጽላት ቤቱን ያረክሱብናል በሚል “አሥመራ የወለድካቸውን ልጆች አሳድግ እንጂ አንተ እዚህ አትገባም” ብለው አግደዋቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ በወቅቱ ሊቄ ብርሃኑ “ሊቀጳጳስ  ናቸው እኮ” ብለው ሊከራከሩላቸው ቢሞክሩም ካህናቱ በአቋማቸው ጸንተው እንዳይገቡ አግደዋቸው ከደጅ ተመልሰዋል። ቀደም ብሎም ናዝሬት ላይ ሳሉም ሴት በመድፈር ተከሰው የነበረ መሆኑን በቅርብ የሚያውቋቸው ይናገራሉ፡፡ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ መጋቢ እያሉም በአባ ሳሙኤል አምሳል ሴት ያስገቡ ያስወጡ እንደነበር በጊዜው ጥበቃ ከነበሩት አንዳንዶቹ ይመሰክራሉ፡፡

ሁሉ የሚያውቃቸው የትዳር አጋራቸው የዑራኤል ቤተክርስቲያን ጸሓፊ የሆኑት ወ/ሮ ትዕግሥት ሲባሉ አባው ከእርሳቸው ሦስት ወይም አራት ልጆችን አፍርተዋል ይላሉ ምንጮቻችን፡፡ የዚያው ቤተክርስቲያን ሒሳብ ሹም የኾኑትን ወ/ሮ መናንም ወሽመዋል እየተባለ በስፋት ይወራል፡፡ ወ/ሮ መና በሂሳብ ሹምነታቸው ብዙ ሙስና ቢፈጽሙም “ዋ እንዳላወጣው” እያሉ አባ እስጢፋኖስን በማስፈራራት በሀገረ ስብከቱ ያለመከሰስ መብታቸውን አስከብረዋል ነው የሚባለው፡፡ ከእዚህ በተጨማሪ በሙስናው መዋቅር ውስጥ ገንዘብ በማቀባበልና የጉቦን መጠን ደረጃ በማውጣት ከሚደልሉላቸው ደላሎቻቸው መካከል የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ያደረጉት የዮናስ እናትና ሌሎችም ውሽሞቻቸው እንደሆኑ በካህናቱ መካከል የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የየካ ሚካኤል ቁጥጥር የሆነ ኢያሱና የአቡነ ጢሞቴዎስ ሾፌር የሆነው የልቤ ነጋም ልጆቻቸው መሆናቸውን ምንጮቻችን በእርግጥኝነትና በካህናቱ መካከል ሁሉም የሚያውቀው ሐቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተለይ የልቤ የተባለው ልጅ “ነጋ” በሚባል የአባት ስም ይጠራ እንጂ ቁርጥ አባቱን አባ እስጢፋኖስ እንደሚመስል ይናገራሉ፡፡
አባ እስጢፋኖስ በፓትርያርክ ማትያስ ዘመን የመጀመሪያው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስና የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀጳጳስ ሆነው ሲሾሙ፣ በፓትርያርክ ምርጫው ላይ በነበራቸው የአስመራጭነት ሥልጣን አባ ማትያስ እንዲመረጡ ለማድረግ በተጫወቱት ሚና በጅማ ሀገረ ስብከት ላይ አዲስ አበባ እንደተጨመረላቸው የሚናገሩ አሉ፡፡ ከመጰጰሳቸው በፊት በተለይ በ1988 – 89 ዓ.ም ድረስ በነበሩት ዓመታት ውስጥ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ እያሉ በሀገረ ስብከቱ ውስጥ ሕገወጥ የድራፍትና የጉቦ ቡድኖችን በማደራጀት ቅጥርና ዝውውር በጉቦ እንዲፈጸም መሠረት በመጣል ተጠቃሽ ስለነበሩ፣ ሊቀጳጳስ ሆነው ሲመጡ ብዙዎች “የጀመሩትን የሙስና መንገድ እንዲያጠናክሩት ነው የተሾሙት ሲሉ” ስጋታቸውን ገልጸው ነበር፡፡
እርሳቸውም የቀድሞ ክፉ ስማቸው ዳግም እንዳይነሳ በመስጋት ስለሙስና አብዝቶ ማውራት ከሙስና ነጻ የሚያደርግ ስለመሰላቸው በየተገኙበት ሙስናን ሲኮንኑ ቢሰሙም እንደአሁኑ ጊዜ ሙስናና የፍትሕ እጦት የተስፋፋበት እንደ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ያለ ስፍራ የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ ስለሙስና አብዝተው እያወሩ በኃይለኛ ሙስና ውስጥ ተዘፍቆ መገኘት የዘመኑ ፋሽን ሆኗል፡፡ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ኃላፊ እንደ ነበረው እንደ ገብረዋሕድ ስለሙስና አብዝቶ ያወራ በሙስናም ተዘፍቆ የተገኘ ስለሌለ የገብርኤልን መገበሪያ የበላ ሳይነኩት ይለፈልፋል እንደሚባለው ሙስና ውስጥ የሚገኝ ስለ ሙስና አብዝቶ ማውራቱ እየተለመደ መጥቷል፡፡ እንዲህ ስንል ሁሉም ስለ ሙስና የሚያወራ ሙሰኛ ነው እያልን አይደለም፡፡ - በፍጹም! ሙስናን በቁርጠኝነት ለመታገል የተሰለፉ፣ ሙስናን የሚኮንኑ እውነተኛ የቤተክርስቲያን ልጆችም እንዳሉ እናውቃለን፡፡
አባ እስጢፋኖስ በጅማ ሀገረ ስብከት ላይ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ከተጨመረላቸው ወዲህ ሙስናና ብልሹ አሰራር ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ እየተስፋፋና በርካታ አገልጋዮች የሙሰኞች ሰለባ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ ለዚህም በሀገረ ስብከቱ ውስጥ ቁልፍ ቦታዎችን የያዙት ማለትም አስተዳደር ላይ የተቀመጠው ዮናስ፣ ደብዳቤ መሪ ተብሎ የተሰየመው ታዴዎስና ስብከተ ወንጌል ክፍሉን የሚመራው ዳዊት ቅጥርና ዝውውር ላይ ኃይለኛ ደላሎች በመሆን ጉቦ እየተቀበሉ አንዱን እየሾሙ ሌላውን በአየር ላይ እያንሳፍፉ ይገኛሉ፡፡ አለቃቸው አባ እስጢፋኖስም ምናልባት ተገኝተው አቤቱታ ሲሰሙ በተለይ ዮናስን በአቤቱታ አቅራቢው ፊት ሰድበውና ሞልጨው ይናገሩትና ከመጋረጃ በስተጀርባ የሚተገበረው ግን ዮናስ ያለው ነው፡፡
በአሁኑ ጊዜ ጉቦው ወደ 30 እና 40 ሺህ ብር ከፍ ያለ መሆኑን እየተነገረ ነው፡፡ ጉቦ ለመብላት የተነደፈው ስልትም በየደብሩ በሐቅ የሚሰሩና ለዘራፊዎቹ ያልተመቹ አገልጋዮችንና በልዩ ልዩ ምክንያት የተጋጯቸውን አገልጋዮች አንዳንድ የደብር አስተዳዳሪዎች ከደላሎቹ ጋር በመነጋገርና በመደራደር እገሌን ቀይርልኝና ይህን ያህል እሰጥሃለሁ ይላሉ፡፡ በዚህ መካከል ደላሎቹ ከአስተዳዳሪውም በዝውውር የተሻለ ቦታ ከተገኘላቸው ሟሳኝ አሟሳኝ ሰራተኞችም ዳጎስ ያለ ጉቦ ይቀበላሉ፡፡ ከፍለው ለሚዛወሩት ነገሩ አልጋ ባልጋ ሲሆንላቸው ያለበደላቸው ከሚያገለግሉበት ደብር እንዲዛወሩ ለሚደረጉት የደላላ ሰለባዎች ግን አባጣ ጎርባጣ ነው የሚሆንባቸው፡፡ ሀብታም ከሆነና መሀል ከተማ ከሚገኝ ደብር ከከተማ ወጣ ብሎ ወደሚገኝና ገቢው አነስተኛ ወደሆነ ደብር እንዲዛወሩ፣ የዝውውር ደብዳቤ ከተጻፈላቸውና የነበሩበትን ደብር ከለቀቁ በኋላ የተዛወሩበት ደብር እንዳይቀበላቸው የማድረግና አየር ላይ የማንሳፈፍ የቀድሞው የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ የአባ ሳሙኤል ስልትም ተግባራዊ ይሆንባቸዋል፡፡
ለመጥቀስ ያህል እንኳ የ1500 ብር ደሞዝተኛ የነበረ አገልጋይ ጉቦ ለዮናስ ሰጥቶ በ2400 ብር በቅርቡ ዝውውር ተፈጽሞለታል፡፡ ቦታውን እንዲለቅ የተደረገው ደግሞ ደሞዝ ቀንሶ ነው የተዛወረው፡፡ እንዲሁም የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ቤተክርስቲያን ሒሳብ ሹም የነበረውን አገልጋይም በቅርቡ አዲስ ተሹሞ የመጣው አለቃ (አባ ነአኩቶ ለአብ) አላስበላ ብሎኛል በሚል ከአባ እስጢፋኖስ ደላሎች ጋር በመመሳጠር ከሚያገኘው ደመወዝ 400 ብር ቀንሶ ወደ ጠሮ ሥላሴ እንዲዛወር ያደረገው ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ወደተዛወረበትም ተቀባይ ሳያገኝ አየር ላይ ተንሳፎ ይገኛል፡፡ ሌላው አገልጋይ ደግሞ የተሻለ ገቢ ከነበረው ከኩርፎ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ከኮተቤ አለፍ ብሎ ወደሚገኘው ገጠር ቀመስ ቤተክርስቲያን ያዛወረው ሲሆን፣ ደብሩ ደሃና ወርሃዊ ደሞዝ እንኳን በቅጡ የማይከፈልበት፣ በየወሩ አንዳንድ ጊዜ የደሞዝ ግማሽ፣ አንዳንዴ ደግሞ ሩቡን ካልሆነም እስከ 20 ከመቶ ያህል የሚከፈልበት ደሃ ቤተክርስቲያን መሆኑ ይነገራል፡፡
ቄስ ለይኩን የተባለ አገልጋይ ደግሞ በደላላው ዳዊት አማካይነት ለአባ እስጢፋኖስ 40 ሺህ ብር ከፍለው ከኮተቤ ሩፋኤል ቤተክርስቲያን የ1600 ብር ደሞዝ ወደ ሰዋስወብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ቤተክርስቲያን 2999 ብር ደሞዝ ከነአበሉ እንዲያገኙ ተደርጎ ተዛውረዋል፡፡ በቅርቡም በተመሳሳይ ተልእኮ ከአራዳ ጊዮርጊስ ወደ መካኒሳ ሚካኤል የተዛወረ አንድ ሰራተኛ የመንግስት ባለስልጣን የሆነ ዘመድ ስለነበረው በተጽእኖ ከመካኒሳ ሚካኤል ወደቅድስተ ስላሴ ካቴድራል እንዲዛወር ተደርጓል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ የሙሰኞች ሰለባ ሆነው ከደሞዛቸው ቀንሰው ተዛውራችኋል የተባሉና አየር ላይ ተንሳፈው የሚገኙ አገልጋዮች ጥቂት አይደሉም፡፡ አባ እስጢፋኖስ ደላሎቻቸውና በጉቦ ወደሚዘረፍበት ደብር ዓይናቸውን የጣሉ ሙሰኞች የከፈቱት “የዝውውር መስኮት” መቼ እንደሚዘጋ አንድዬ ነው የሚያውቀው፡፡
አባ እስጢፋኖስ በዚህ ብቻ ሳይገቱ አንድ እግራቸውን ጅማ አንድ እግራቸውን አዲስ አበባ ላይ የተከሉ እንደመሆናቸው በአብዛኛው አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በደላሎቹ በኩል ካልሆነ በቀር የማይገኙ ከመሆናቸውም በላይ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ለጅማ ሀገረ ስብከት በሚል ከአንዳንድ የደብር አስተዳዳሪዎች ጋር በመመሳጠር ገንዘብ እየጠየቁና እየተሰጣቸው መሆኑን ምንጮችን ይናገራሉ፡፡ በቅርቡ እንኳ ከአስኮ ገብርኤል 34 ሺህ ብር መውሰዳቸው ታውቋል፡፡ በጅማ ሀገረ ስብከት ስም ለአባ እስጢፋኖስ ፈሰስ የማያደርጉ አለቆች ግን ጥርስ ውስጥ ገብተው የዝውውር ሰለባ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰሞኑን እየተካሄደ ባለው የሲኖዶስ ስብሰባ ላይ የአባ እስጢፋኖስ ጉዳይ ተነስቶ በሲኖዶስ አባላት ከሀገረ ስብከቱ ይነሱ የሚል ውሳኔ በጳጳሳቱ ሁሉ የተላለፈ ቢሆንም ፓትርያርክ ማትያስ ግን “ሀገረ ስብከቱ የእኔ ነው አይነሱም ይቀጥላሉ” ብለው መቃወማቸው ተሰምቷል፡፡ ጳጳሳቱ ግን በግልም ለአባ እስጢፋኖስ “ሳይዋረዱ ቀድመው ቢወርዱ ይሻላል” ብለው ምክር የሰጧቸው መሆናቸውን እየተናገሩ ነው፡፡ በተያያዘም ከድለላው ክበብ ውጪ ያሉ የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች በሌሎች የአድባራትና ገዳማት ሠራተኞች ላይ የሚፈጸምውን ግፍና በደል፣ አቤቱታ ሰሚም በመታጣቱና ፍትሕ እየተዛባ በመሆኑ ምክንያት ከአባ እስጢፋኖስ ጋር አንሰራም በሚል ውስጥ ውስጡን ከፍተኛ ተቃውሞ እያሰሙ ይገኛሉ፡፡

ይህ ሁሉ ሲሆን አብሯቸው እየሠራ ያለውና በሀገረ ስብከቱ እያዘዘ የሚገኘው ማቅ ለምን ዝም አለ? ዝርዝሩን በሌላ ጊዜ እንመለስበታለን፡፡