Wednesday, June 22, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጌልን ማቆም ያልቻለው ለምንድነው?


ከዙፋን (ተስተካክሎ የቀረበ)
ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሰረተ 25 አመት ሞላው። ድርጅቱ ከተመሰረተ ጀምሮ የፕሮቴስታንት፣ የካቶሊክና ሌሎች የክርስትና ክፍሎች የወንጌል ስብከት በፊት ከነበራቸው ውስንነት በበለጠ ሲሰፉ እንጂ ሲጠፉ አልታየም።
 በተለይም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች የሆኑና ቤተክርስቲያኒቱ ከወንጌል ጋር አንዳንዴም ከወንጌል በላይ ስፍራ የምትሰጣቸው ትውፊቶች፣ ድርሳናት፣ ገድላት ከዚያም ባለፈ ልዩ ልዩ አስማትና ተረቶች የእግዚአብሔርን የክብር ስፍራ ወስደውና ጋርደው መገኘታቸውን ያስተዋሉና ከውስጥ የተነሱ የተሃድሶ እንቅስቃሴዎች ከነበሩበት ሁኔታ እየሰፉና እያደጉ መጥተዋል። ግንዛቤያቸውን በሁሉም ዘንድ በማዳረስ ረገድ ሰፊ ተቀባይነት በማግኘታቸው ከነበሩበት የተወሰነ ሁኔታ ወጥተው ዛሬ ከማኅበሩ የ25 ዓመታት ቁጥጥር ውጪ ናቸው። ማኅበሩ የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመጨፍለቅ ያልቆፈረው ጉድጓድ፣ ያልፈነቀለው ድንጋይ አልነበረም። ከንግድ ድርጅቶቹ የሚያገኘውን ግዙፍ ገንዘብ፣ የሰው ኃይልና ማቴሪያልም ጭምር ለዚህ ስራ ያውላል። በተሐድሶ ላይ ግንዛቤ ማስጨበጫ፣ ዐውደ ርእይ፣ ስብሰባ፣ ወርክሾኘ፣ በንግሥ በዓላት፣ በዐውደ ምሕረት፣ በፅሑፍ፣ በምስል ወዘተ ልዩ ልዩ መንገዶች ህዝቡን ያስተምራል፣ ያስጠነቅቃል ቪዲዮ ይበትናል፣ ካሴት ይለቃል፣ በራሪ ወረቀቶችን ያሰራጫል። በዩኒቨርሲቲዎች፣ በኮሌጆች፣ በሕጻናት፣ በወጣቶች፣ በጎልማሶች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ባሉ ሰንበት ት/ ቤት ተማሪዎች ላይ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ሰርቷል። ተጽእኖውና መልእክቱ ያልገባበት ቤት የለም። ተሐድሶ፣ ሃራጥቃ፣ መናፍቃን፣ የአውሬው ተከታዮች፣ ፀረ ማርያሞች፣ ጠላቶች፣ ነካሾች፣ ቡችሎች…ወዘተ ብዙ ስም አውጥቶ ለማስጠላት ሞክሯል። በስለላ፣ በክትትል፣ በጥርጠራና በድጋፍ አብሮት ያልቆመውን ሁሉ ስም እየለጠፈ በማባረርና በማስፈራራት ብዙ ቢጓዝም ትምህርተ ተሐድሶ ግን ሊቀንስ አልቻለም። ከዚህ ሁሉ ልፋት በኋላ በውጤቱም በ25 አመት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማታወቅ መልኩ 15 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ከኦርቶዶክስ አካውንት ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ጎርፏል።
ብዙ ሚሊዮን ኦርቶዶክሳዊያን ምእመናን፣ መምህራን፣ ሊቃውንት፣ ቀሳውስት፣ መነኮሳት፣ ጳጳሳት ሳይቀሩ ባሉበት ቤታቸው ሆነው የተሐድሶ እንቅስቃሴን ደጋፊና አራማጅ ሆነዋል። የተሐድሶ እንቅስቃሴ መጀመር ወደሌላ የእምነት ድርጅት የሚኮበልለውን ምዕመን ቁጥር መቀነስ ችሏል። ችግሩ ያለው ከኦርቶዶክስ መሠረታዊ አስተምህሮ ሳይሆን በጊዜ ብዛት በገቡ የስህተት ትምህርቶችና የፈጣሪን ሥፍራ የተረከቡ የክህደቶች አምልኰዎች የተነሳ መሆኑን ተሐድሶዎች ማሳወቅ በመቻላቸውና ይህንን ለማስወገድ ደግሞ እዚያው ሆኖ በማስተማርና በመለወጥ እንጂ በመኮብለል አለመሆኑን ብዙ በመሥራታቸው የተነሳ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ የሱን የኑፋቄ ጽዋ ለመጨለጥ ያልፈለጉት እዚያው ከሚቆዩ ይልቅ ኮብልለው የትም ገደል ቢገቡለት ይመርጣል። በጀትና ኃይል መድቦ ተሐድሶዎችን ከመከታተል ይልቅ ከበረት አስወጥቶ፣ በረቱ ውስጥ የቆዩለትን በጎች የራሱ የግል ንብረት አድርጎ ለመቆጣጠር ያመቸዋል። ያስቸገረውና ብዙ ድካሙን መና ያስቀረው ነገር የተሐድሶ ኃይል በእውቀት፣ በጥበብና በተዋሕዶ ቀደምት እውነት ሁሉን ማዳረስ መቻሉ ነው።
የማኅበረ ቅዱሳን ትልቁ ችግር ራሱን የእውነትና የእምነት ጫፍ አድርጎ መመልከቱ አንዱ ጉዳይ ሲሆን ሌላው ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተምህሮ ጥግ ላይ ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ያለው ለማስተማር መሞከር ማለት አፍን ማሞጥሞጥ እንደሆነ አድርጎ ማሰቡ ነው። እውነታው ግን በተሐድሶ ምሁራንና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለው የእውቀት ልዩነት የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ተሐድሶ አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ይቀመጥ ሲል ማኅበሩ ደግሞ በአሮጌው አቁማዳ አዲሱን የወይን ጠጅ ማስቀመጥ ይቻላል በሚለው የእምነት አስተሳሰብ ልዩነት የተነሳ በተደራጀ አቅምና ሥልጣን በሚያደርገው ሩጫ ተሐድሶን ማስቆም አልቻለም። ተሐድሶ የግለሰቦች አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔር አሰራር መገለጫ በመሆኑ ማንም ድርጅት በትግል ሊያቆመው አይችልም።
“ወልበስዎ ለሐዲስ ብእሲ ዘሐደሶ እግዚአብሔር በጽድቅ፣ ወበርትዕ፣ ወበንጽሕ” ኤፌ 4:24
“ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ” የሚለን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ነው። በተረታ--ተረትና በእንቶ ፈንቶ ጩኸት በመባከን ፈንታ የወንጌልን እውነት መጨበጥ፣ ባዶ ተስፋ ከሚያስጨብጡ ዝናብ አልቦ ደመናዎች ዝናብ ከመጠበቅ ይልቅ ባለቤቱ ራሱ የሕይወት ውሃ ምንጭ እኔ ነኝ ካለው እውነት ቃሉ በመጠጣት መርካት መቻል ማለት መታደስ፣ መለወጥ፣ አዲስ ሰው መሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ሁሉም ሰው እንዲታደስለት ይፈልጋል። የተሰራነው አንድ ጊዜ ተሞልቶ ፈፅሞ ከማይደክም የባትሪ ኃይል አይደለም።
“ወዘንተ ውስጥነሰ ይትሔደስ ኩሎ አሚረ”
“... የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” 2ኛ ቆሮ 4:16 እንዳለው መታደስ በመንፈሳዊነት ኃይል እግዚአብሔር እንደሚወደው ሆኖ መሰራት ማለት ነው።
በዚህም የተነሳ ማኅበረ ቅዱሳን የሚታገለው የእግዚአብሔርን ሃሳብ ለማስቆም ነው። ነገር ግን እስካሁንም አልቻለም፣ ወደፊትም አይችልም። ምክንያቱም ተሐድሶ፣

1. የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው።

 በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ወንጌል በምድር ሁሉ ሊሰበክ ግድ ነው። ሉቃ 12:49 “በምድር ላይ እሳት ልጥል መጣሁ “ እንደሚለው ጌታ የጣለው እሳት ይነዳል እንጂ አይጠፋም። ሐዋ 5-38
  “ይህ አሳብ ከሰው እንደ ሆነ ይጠፋልና፤ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ግን ታጠፉአቸው ዘንድ አይቻላችሁም፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ” እንዳለው ከእግዚአብሔር ስለሆነ ሊጠፉ አልቻሉም፣ አይጠፉምም ።

2. የአብርሖት (enlightenment) ዘመን በመሆኑ፣

ይህ ዘመን ትምህርት የተስፋፋበት ብዙዎች ከመሃይምነት ነጻ የወጡበት መረጃ የበዛበት ነው። የሰዎች መንፈሳዊ ረሃብ በማይረዱት ግእዝ የማያውቁትን ነገር ተቀብለው ወደቤት ከመሄድ ባለፈ መጽሐፍ ቅዱስና መንፈሳዊ ፅሑፎችን በማንበብ ማብራሪያና መልስ የሚፈልግበት ዘመን ነው። ትውልዱ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ልምምድን በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ይፈትሻል። ለእምነቱ በቂ ማብራሪያ ይሻል። ያነጻጽራል። መጽሐፍ ቅዱስን በሞባይሉ አስጭኖ የትም ቦታ ያነባል። እንደ መጨረሻ ባለሥልጣን ቃልም ያየዋል። ከዚህ ቃል ጋር የሚጋጭ ወይም ለማስታረቅ የሚሞክርን ማንኛውንም ውሸት ለመቀበል አይፈልግም። ይህንን ዘመነ አብርሖት ከእውነት ጋር በመስማማት እንጂ በመሸፋፈን ወይም ትቀሰፋለህ፣ በሰይፍ ትቆረጣለህ በሚል ማስፈራራት ማስቆም አይቻልም።

3. ዛሬም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መዳንና ፈውስ ስላለ፣

 እግዚአብሔር በአንድ ቃልና በጸሎት በአንዴ መፈወስ ያቃተው ይመስል ለሥጋዊ ፈውስ ሸንኮራ፣ ጻድቃኔ፣ግሼን፣ሚጣቅ፣ ሺፈጅ፣ ኩክየለሽ፣ ግንድአንሳ፣ ከድንጋይ አጣብቅ፣ መሿለኪያ፣ መንከባለያ፣ ገልብጥ፣ ሰንጥቅ ወዘተ አዳዲስ የፈውስ መደብር እየፈጠሩ የአንዱ ወረት ሲያልቅ ሌላ እየፈለሰፉ ገንዘብ ጉልበት ጊዜ ጨርሶ መፍትሄ በማሳጣት ተራራ ለተራራ መንከራተት ስለሰለቸው ሰው ከዚህ እንግልት ማረፍ ፈልጓል። ከ 5 ትውልድ ወደ10 ትውልድ፣ ወደ 30 የማይጨበጥ ቃል ኪዳን ለመጨበጥ ሲያበላልጥ በክርስቶስ ላይ ብቻ አንዴ ታምኖ በመኖር ዕረፍትን ፈልጓል።

4. ትውልዱ ከሱስ መፈታትን ስለሚፈልግ

የጫት፣ የሲጋራ፣ የሺሻ፣ የሃሺሽና የመጠጥ ሱስ በየመንደሩ ብዙ ወጣቶችን ተብትቧል። ሴተኛ አዳሪነት፣ ስርቆትና ዝሙት አንገቱ ላይ ያሰረው ክር ወይም መስቀል ነፃ ሊያወጡት አልቻሉም። የጠለንጅ ወይም የጊዜዋ ቅጠል ማጫጫስ መፍትሄ አልሆኑትም።
 44 ታቦት ባነገሠ ማግሥት ከነበረበት ሕይወት ሊፈታ ባለመቻሉ ከተስፋ መቁረጥ የሚያድነውን ይፈልጋል። ይኼውም ያልተቀላቀለበት የእውነት ወንጌል መስማት መቻሉ ነው።
2 ቆሮንቶስ 4፣2
“ነገር ግን የሚያሳፍረውን ስውር ነገር ጥለናልና በተንኮል አንመላለስም፣ የእግዚአብሔርንም ቃል በውሸት አንቀላቅልም፤ እውነትን በመግለጥ ግን በእግዚአብሔር ፊት ለሰው ሕሊና ሁሉ ራሳችንን እናመሰግናለን”

5. ለሥራ ስለሚያነሳሳ፣

 እምነቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያስተካከለ ሁሉ ለበጎ ሥራ የተነሳሳ ሰው ነው። ከወንጌል ሥራን እንጂ ስንፍናን አይማርም። ዐባይን ብቻዋን እንድትጠቀም ግብጽ በሕዝባችን ላይ የጫነችው የስንክሳር የበዐላት ሸክሟን ከራሱ ላይ አራግፎ በመሥራት ራሱንና ወገኖቹን የሚጠቅም ትውልድ እንጂ ስለአባ እገሌ እያለ የሚለምን ዜጋ ሊኖር አይችልም። ትንሽ ሠርቶ ያገኛትን ደግሞ በፍትሃት ድግስ እያራገፈ፣ ብዙውን ጊዜ ደግሞ ዛሬ መልአከ እገሌ፣ ነገ አባ እገሌ፣ በዓታ፣ ጸአታ፣ ፍልሰታ፣ ልደታ፣ ግንቦታ፣ እያለ አበሻ ሥራ ቢሰራ የተለየ ቀሳፊ የተመደበበት ይመስል ዐዛሬ ቅጠል አልበጥስም” እያለ ይኖርበት ከነበረው ዘመን ተፈትቶ በዘመነ ተሐድሶ ነፃ እየወጣ የዕለት እንጀራውን ለማግኘት ሌሊትና ቀን እየሰራ ነው። በዐል ሳያከብር ፈረንጅ ያመረተውን ስንዴና ዘይት በእርዳታ የሚለምን በዐል አክባሪ እንደአበሻ ግብዝ የት ይገኛል?

ስለዚህ የዘመነ ተሐድሶ የክርስቶስን ወንጌል የሚቋቋም ማንም አይኖርም። የክርስቶስን ወንጌል የሚያቆም ከሰማይ በታች ምንም ዓይነት ኃይል ወይም ማኅበር የለም። ይሁን እንጂ ወርክሾፕ፣ ስልጠና ፣ አቅም ግንባታ፣ ሕንጻ ግንባታ፣ ኤግዚብሽን ግንባታ፣ ዐውደ ርእይ ወዘተ መደረጉ አይቀርም፣ ይኽ መደረጉ የእግዚአብሔርን የተሐድሶ ሐሳብ አያቆመውም። ማኅበረ ቅዱሳን የብር ኢዮቤልዩውን እንዲህ ካሳለፈ ዕድሜው ከሰጠው የወርቁን ደግሞ አመራሩ ራሱ ከኑፋቄ ወጥቶ ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ በማምለክ ያከብረው ዘንድ የእግዚአብሔር የተሐድሶ እቅድ መሆኑን አንጠራጠርም።

Wednesday, June 15, 2016

በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው!!


የቁልቁለት መንገድ ተጀምሯል!

ይህ ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2004 በመካነ ጦማራችን ላይ የወጣ ነው። ደግመን ማውጣት ያስፈለገን፤ ሞት የሁሉም ሰው ጽዋ ቢሆንም ማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ ጳውሎስን በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል እስከሞት እያዋከበ መቆሚያና መቀመጫ እንዳያሳያቸው እነሆ ፓትርያርክ ማትያስን በተራቸው እስከሞት እየተዋጋ ለመቆየት መቁረጡ በዳበረ ልምዱ ሲሰራበት መቆየቱን ለማሳየት ነው። እንዲህ ብለናቸው ነበር። አንዳች ነገር ሳያደርጉ ሞት ወሰዳቸው፤ ማኅበሩም ሰፋለት። (አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው) ዛሬም ፓትርያርክ ማትያስን ለተመሳሳይ ጽዋ  በወከባና በአድማ እያንደረደረ ይገኛል። ማኅበሩ የሚተዳደርበት አዲስ ሕግ ሳይጸድቅ፤ በዐቃቤ መንበርና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሥልጣን ነጠቃውን ጀምሯል። ወደፊትስ?

በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ማኅበረ ቅዱሳን ከተራ ማኅበርነት ወደ ሀገረ ስብከትነት  አደገ። በዚህም የተነሳ ሲኖዶሱ ሙሉ በሙሉ በማኅበረ ቅዱሳን እጁን ተጠምዝዞ እንደሚሰራ አስመሰከረ። የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ  የየሀገረ ስብከቶቹ  ጠቅላይ ጽ/ቤት ሆኖ ያገለግላል። ይህ ጽ/ቤት ደግሞ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ በየ3 ዓመቱ በሚያደርገው ምርጫ በሚመድበው ሊቀጳጳስ ነው። እንግዲህ ማኅበረ ቅዱሳን ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና አሥኪያጅ ሆነ ማለት ራሱን የቻለ ሀ/ስብከት  ሆነ ማለት ነው። የጠቅላይ ቤተክህነቱ መምሪያዎች ሊያዙት አይችሉም። ከዚያም በላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ ሊያዙት፤ ሊናገሩትና ሊቆጡት አይችሉም ማለት ነው። በቀጥታ በቅዱስ ሲኖዶስ በሚመደበው ሊቀጳጳስ በኩል ግንኙነቱ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋር ብቻ ይሆናል ማለት ነው። እንዲህ ነው እንጂ ሹመት፤ መሾም ካልቀረ!! አንድ ማኅበር ባንድ ጊዜ እመር ብሎ አናት ላይ ፊጢጥ ብሎ ከመቀመጥ ወዲያ ሹመት ከወደየት ይገኛል? ከእንግዲህ  ከተቀመጠበት ደረጃ አንጻር ማኅበር መባሉ ዝቅ የሚያደርገው ስም ስለሆነ የቅዱሳን መምሪያ ወይም የወጣቶች ሀ/ስብከት እንዲባል ሲኖዶሱ በነካካው እጁ ስሙንም ማሻሻል ይገባዋል። ከዚያም አያይዞ ለዚሁ አዲስ ሀ/ስብከት አንድ ሊቀጳጳስ እንዲመድቡለትም ጥቆማውን እናቀርባለን። አንድ ነገር ታዘብን። ቤተክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ የሚባል አካል እንደሌላት ተረዳን። በአንድ ተራ ማኅበር እየተመሩ የእሱን ጉዳይ ብቻ ሲያነሱና ሲጥሉ ሦስትና አራት ቀናት ስብሰባ መወዘፍን ምን ይሉታል? ስንት ስራ መስራት እየቻሉ ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አጀንዳ ይዞ መከራከርን እውነት ሰዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ነው የሚመሩት እንድንል ያደርገናል። ይህ ማኅበር ባይኖር ኖሮ ስለምን ጉዳይ ሊሰበሰቡ ነበር፤፤
ይህ ማኅበር እስካሁን እየታዘዘ እንዳልቆየ የተጻፉለት ደብዳቤዎች አረጋጋጮች ናቸው። እሱ ራሱ አልቀበልም ብሎ በደብዳቤ አረጋግጧል። አንዴ ከኢህአዴግ፤ አንዴ ደግሞ ከተቃዋሚ ነኝ እያለ፤ ሌላ ጊዜ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለልተኛ እየመሰለ የተጓዘበትን ሁላችንም እናውቃለን። የወንድሞች ከሳሽና አሳዳጅ ስለመሆኑም ግፉን የቀመሱ ሁሉ ይመሰክራሉ። የተጓዘባቸውን ስልቶች ሁሉ ያጠናው መንግሥት ከሽብር አቀንቃኝ  ከሰለፊያ ጋር በአንድ ረድፍ አንዳስቀመጠው ነግሮናል። ስለሆነም አቡነ ጳውሎስ ይህንን የአድማና በጥቅም የተሳሰረ ውሳኔ አልፈርምም በማለት ውድቅ ሊያደርጉት ይገባል። ማኅበሩ አስቀድሞ ከሰለፊያ ተግባር ነጻ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ማምጣት ይጠበቅበታል። ደጋፊዎቹ ጳጳሳትን በማስረጃና በሰው ምስክር ተጠንተው ብቁ ሆነው ያልተገኙ ካሉ ከማዕርጋቸው መሰናበት አለባቸው።  ቄስ የነበሩ፤ ልጆች የወለዱ፤ ቅምጥ ያላቸው እንዳሉ ይወራል፤ የአንዳንዶቹም ይታወቃል።  እየተሸፋፈነ መቀመጡ ለቤተክርስቲያን ጠንቅ የሆነ ውሳኔ ለማስወሰን ያልተመለሱ ሰዎች ስብስብ መሆኑ ከታየ ውሎ አድሯል።  ነውራቸውን ለመሸፈን እንኳን ከድመት አንሰዋል።
በአንድ ወቅት አባ ገብርኤል፤ አቶ ኢያሱ ተብለው ከማዕርጋቸው ተገፈው እንደነበረው፤ ማንነታቸው እንደገና ተመርምሮ  አስቸጋሪ በሆኑት ላይ ዛሬም ተመሳሳይ ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል። ጨከን ያለ የሥርዓት ማስከበር አካሄድ መውሰድ ካልተቻለ ሲኖዶሱን በነሱ በኩል እያወከ ነገ ፓትርያርክነቱን አስቀድሞ ከዚያም ቤተመንግሥቱን እንደሚረከብ የሚጠራጠር ካለ የማኅበሩን አካሄድ የማያውቅ ብቻ ነው። አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው። ከሆነለት ፓትርያርክነቱን ለሚታዘዝ  ሰው  ሰጥቶ ወደ ቤተመንግሥት ሰተት ብሎ ለመግባት ከጽዋ ማኅበርነት ወደ መምሪያ ተገዳዳሪነት፤ አሁን ደግሞ ወደ ሀገረ ስብከትነት ማደጉ ከምንም በላይ ማሳያ ነው።  ታዲያ ከእንግዲህ የቀረው ምንድነው? ይህ ሁሉ ለጽድቅ ነው እንዳይትሉንና እንዳንስቅ ጥቂት እዘኑልን። ነጋዴና  ሸቃጭ የሆነ  ቅዱስ ማኅበር  አራት ኪሎ የለም ። እያየነው በትንሽ በትንሹ የወጣው ይህ ሐረግ ቤተ ክህነቱን አንቆ ወዳሰበበት በመጓዝ ላይ ነው። እግዚአብሔር ለዚህ ክፉ ማኅበር አሳልፎ ከሰጠ በእውነትም ቤተክርስቲያኒቱ ለፈተናና ለውድቀት ተመርጣለች ማለት ነው። ተወደደም፤ ተጠላ ሲኖዶስ በየዓመቱ ያለህውከት ማለፍ አይችልም።
ሰውዬው «ሁሉን ለማየት መቆየት»እንዳለው የሚሆነውን ለማየት ከዕድሜው አይንፈገን!

Monday, June 13, 2016

"ፓ" ይላል ምዕመኑ!!!



«በዘውድአለም ታደሰ»
ነብይ ነኝ ባዩ የቤተክርስቲያን ደላላ!

ይሄ ሰውዬ "ጎሳ" ይባላል። በተለያየ ጊዜ የተለያዩ ቸርቾች ሲሰብክ አይቼዋለሁ። (ጎፋ መድሃኒአለም ፣ ዘፀአት ፣ FBI ፣ ወዘተ... ) የሚደክም አይነት ሰው አይደለም። ውሃ ሳይጎነጭ በተከታታይ ለሶስት ሰአታት የማውራት አቅም አለው! የምእመኑን ሳይኮ በልቶታል። ህዝቤን ምን እንደሚያስጮሀት ስለሚያውቅ አዳራሹን በጩኸት መናጥ ለነብይ ጎሣ ቀላል ነው!
ብዙ ግዜ ቸርቾች ይህን ሰውዬ ሚጋብዙት ገንዘብ ክፉኛ ሲያስፈልጋቸው ነው። ወይ መሬት ሊገዙ ሲያስቡ ... አሊያም የተሻለ አዳራሽ ሊከራዩ ሲፈልጉ ... ብቻ የሆነ የፈንድ ሬይዚንግ ጉዳይ ሲኖር ጎስሻን ይጠሩትና በዚያች ጮሌ ምላሱ የራሱንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ታሪክ እያጋነነ በመስበክ የዚህን ምስኪን ምእመን ኪስ ያራቁትላቸዋል!
«ነኝ ያልኩ ኮንትራክተር ነበርኩ፣ ነፍፍ መኪኖችና ብዙ ሰራተኞች ነበሩኝ፣ ጌታ ሲገባኝ ግን ንብረቶቼን ሸጬ ለቸርች ሰጠሁ» ብሎ ይጀምራል ተረት ተረቱን።
«ፓ» ይላል ምእመኑ!
«ከዛ ክፉኛ ተቸገርኩና፣ ምልስ ምቀምሰውን አጣሁ፣» ብሎ ለፅድቅ ሲል የከፈለውን መከራ እያጋነነ ያወራል!
«በከተማዋ ስሜ የተጠራ ኮንትራክተር እንዳልነበርኩ ምልስ ምቀምሰውን አጥቼ ተቸገርኩ» ሲል ረሃብን የሚያውቀው የዚህ ህዝብ አንጀት በሀዘኔታ ይላወሳል።
የሰዉን አቴንሽን ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ታዲያ ... እንዴት ተአምራዊ በሆነ ሁኔታ እግዜር ሀብታም እንዳደረገው፣ እንዴት እንዳበለፀገው ትረካ በሚመስል ሁኔታ ያወራ ያወራና የህዝቡን አእምሮና ስሜት በሚገባ እንደተቆጣጠረ ሲረዳ እንዲህ ይላል ..
«ጌታ እንዲህ ሲል ተናግሮኛል» ብሎ ይጀምራል ነብይ ጎሳ። (ማን ነብይ እንዳረገው እንጃለቱ)
«ጌታ ዛሬ በዚህ አዳራሽ ውስጥ ያላችሁትን ሁላችሁን እባርካለሁ ብሎኛል» ሲል እቺ በረከቷን ከአርያም ሳይሆን መድረክ ላይ ከቆመው አረም የምትጠብቅ ምእመን አዳራሹን በጩኸት ታቀልጠዋለች! በጭብጨባው የሚሟሟቀው ጎሲሻም «አንዳንዶቻችሁ ከዚህ አዳራሽ ስትወጡ ከበረከታችሁ ጋር ትገናኛላችሁ» ሲል አዳራሹ በአንድ ድምፅ «አሜን» ይላል።
«አንዳንዶቻችሁ ደግሞ ቤታችሁ ስትገቡ በረከታችሁ ቁጭ ብሎ ይጠብቃችኋል»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ ስራ ቦታችሁ ላይ»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ሳምንት»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ወር»
«አሜን»
«እግዜር በተራራው ላይ ሙሴን ሲያገኘው በእጅህ ላይ ምን አለ? ብሎ ነው የጠየቀው ወገኖቼ። እግዜር እጃችን ላይ ባለ ነገር ነው ሚሰራው። ዛሬ በእጃችሁ ላይ ምን አለ?» ይላል ብልጣብልጡ ጎሳ!
ይሄ የዋህ ሁን ሲባል ሞኝ የሆነ ህዝብም እውነት መስሎት እጅና ኪሱን ያያል! ከዛማ በቃ አዋራው ይጨሳል .... ፒፕሉ በረከቱን በስጦታው ለመግዛት ይጋፋል! አዳሜ ወርቋን ከአንገቷ ላይ እየበጠሰች፣ ገንዘቧን ከቦርሳዋ እያራቆተች፣ ምንም የሌላት ደግሞ የእጅ ስልኳን ሳይቀር መባ እቃ ውስጥ እየጨመረች የማይፈፀም ትንቢት ታቅፋ እርቃኗን ከአዳራሹ ትወጣለች ... ልትባረክ ነዋ ሃሃሃሃ
ከላይ እንዳልኩት ነብይ ጎሳ ነብይነቱን ከየት እንዳገኘው ማንም አያውቅም። የሚያወራው ታሪክም እውነት ስለመሆኑ ምንም ማረጋገጫ የለም። ይህን ሰውዬ የሚጋብዙት ስግብግብ የቤተክርስቲያን አገልጋዮችም የሰውየው ምስክርነት እውነት የተፈፀመ ይሁን አይሁን ለማረጋገጥ ምንም አይነት ጥረት አያደርጉም! እነሱ ሚፈልጉት በሱ ጅንጀና የሚዘንበውን የገንዘብ ዶፍ ነው። የስብከቱ መለኪያ በሱ ስብከት አማካኝነት የገባው የገንዘብ መጠን ነው እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም!
አሁን ቤተክርስቲያን በጎሳና ጎሳን በሚመስሉ መንፈሳዊ ደላሎች እየታመሰች የምትገኝበት ሰአት ላይ ትገኛለች። መፅሀፉ ጎሳንና መሰል አገልጋዮችን «ለመንጋው የማይራሩ» ይላቸዋል!
እንዲጠብቁት የተሰጣቸውን ምእመንና እረኛ የሆኑለትን መንጋ ስጋ እየበሉ ሰብተው ቆዳውን ገፍፈው ይለብሳሉ! በአስራትና በበኩራት፣ በመባና በፍቅር ስጦታ ስም፣ ገንዘቡ ወደካዝናቸው ይጋዝ እንጂ የገንዘቡ አመጣጥ እነሱን አያስጨንቃቸውም። በምእመኑ ፍራንክ ትልልቅ እቅዶች ያቅዳሉ፣ የህዝቡን መሶብ አራቁተው ሰማይ ጠቀስ ፎቆችን ይገነባሉ፣ በሊትር ሶስት ኪሎሜትር የሚሄዱ ላግዥሪ መኪኖችን ይነዳሉ። ይሄ ተስፈኛ ምእመን ግን ከሰማይ መና እየጠበቀ በደረቅ ምድረ በዳ ደረቅ ትንቢታቸው ታቅፎ ከቃዴስ ቃዴስ ሲንከራተት ይኖራል።
በአብዛኞቹ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያኖች ዘንድ ምድር ምድር የሚሸት ስብከት በዝቷል። ሰባኪው ሁሉ የ prosperity Gospel (የብልፅግና ወንጌል) አቀንቃኝ ሆኗል፣ ምእመኑም በረከቱን የሚለካው በምድራዊና ቁሳዊ ሀብት ብቻ ነው! «ሀገሬ በሰማይ ነው» አይነት ንግግሮች ከምእመኑ አንደበት መደመጥ አቁመዋል። ኢየሱስ የሞተው ለቼቭሮሌት መኪናና ለግራውንድ ፕላስ ስሪ ፎቅ ይመስል ወሬው ሁሉ ቤት ስለመስራትና ቤት ስለማፍረስ ሆኗል ... እንደ ዊነርስ ቻፕል አይነት ቸርቾችማ ወሬው ሁሉ ሱሪ ስለመቀየርና መኪና ስለመንዳት ከሆነ ቆየ። «በመንፈስ መኪና የመንዳት» ፕሮግራም ሁሉ ያካሂዳሉ አሉ! ሃሃሃ
ነብያቶች በዝተዋል። ነብይነት ግን ከሞተ ቆየ! ሰባኪዎችም አሸን ናቸው። ስብከት ግን ስልሳዎቹ ላይ ቆሟል! በየመድረኩ ተኳኩለው እንጣጥ እንጣጥ የሚሉ (ባለብዙ ሚስት ዘማሪዎች እልፍ ናቸው) መንፈሳዊ ማንነትን የሚያንፅ መዝሙር ግን ከመድረኩ ነጥፏል!
በፅድቅና በቅድስና የሚያገለግሉ አንዳንድ አገልጋዮች እንዳሉ አይጠፋኝም። ግን እነዚህ አገልጋዮች ከጎሳውያኑ ጋር ሲተያዩ በገምቦ ውስጥ እንዳሉ ጥቂት ጠብታዎች ናቸው! ስለዚህ ባህር ውስጥ እንዳሉ አይቆጠሩም። እኔ ማወራው ባህሩን ስለሞሉት የተበከሉ አሳዎች ነው!
 ቸርቾች በየመቶ ሜትሩ ከተማ ውስጥ ፈልተዋል። ደቀመዝሙር ማፍራት የማይችሉ ውሀ አልባ ምንጮች ናቸው እንጂ! ክርስቲያን ያልሆኑ የክርስቶስ ሰባኪዎችና ክርስቶስን የማያውቁ አገልጋዮች ይሄን ምስኪን ምእመን እንደአሻንጉሊት እየተጫወቱበት ነው! አገልግሎታቸው ያከበራቸውን ህዝብ በመናቅና በማስፈራራት ላይ የተመሰረተ ነው! «ለምን?» ብሎ ጥያቄ የሚያነሳ ሲመጣ «ጌታ በቀባው ላይ እጅህን አታንሳ» በማለት በጥቅስ ያስፈራሩታል። በፅድቅ ለማገልገል ከላይ እታች እያሉ የጅብ ድግሳቸው ላይ የማይሳተፉትን ንፁሀን ደግሞ የተለያየ ስም ጀርባቸው ላይ በመለጠፍ ከአገልግሎት ያግዷቸውና የሚከተላቸውን ምእመን ኑሮ እየቀሙ ይኖራሉ! ሳቁን መንትፈው ይስቃሉ! ደስታውን አራቁተው ይደሰታሉ! እውነትም ለመንጋው የማይራሩ ሆዳሞች!
ዘመኑ የባቢሎናውያኑን ዘመን ይመስላል። ትርምስ እንጂ መረጋጋት የለም! ጩኸት እንጂ መግባባት ጠፍቷል። ግራ የተጋቡ ባለራእዮችና ያልተማሩ አስተማሪዎች መሬት ባልረገጠ የትምህርት ወጀብ ህዝቡን እየናጡት ነው። በተቀየጠ ዶክትሪንና በስህተት አስተምህሮ ምእመኑን ከወንጌል አርቀው አይኑን በማሰር ወደቁልቁለት እየነዱት ነው! ነብያት ነን ባዮቹ ወንዝ በማያሻግር ትንቢት ሲወራጩ መድረኮቻችን ላይ ውለው ያድራሉ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች በተራ ፉከራና ሽለላ የተሞሉ ፍሬ አልባ ደረቅ መሬቶች ናቸው!
በተለያዩ ቤተክርስቲያኖች እየተጋበዘ ህዝቡን የሚያራቁተው ደላላው ነብይ .... «ነብይ ጎሳም» ከላይ ለጠቀስኳቸው ሆዳም አገልጋዮች እውነተኛ ምልክት ሊሆን ይችላል ባይ ነኝ!

እቀጥላለሁ!‎