Saturday, October 18, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የሚፈርሰው በራሱ ተግባር ነው፤ ኢሕአዴግ ላለፉት 22 ዓመታት መቼ ነካው?

ይህን ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2006 ዓ/ም በመካነ ጦማራችን ላይ አውጥተነው ነበር።። ዳግመኛ ማውጣት ያስፈለገን ጉዳይ ሰሞኑን በፓትርያርክ አቡነ ማትያስና በማኅበረ ካህናቱ በኩል ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን በቅኝ ገዢነት የመቆጣጠር ስልቱና ይህንን ስለማስቆም በአንድ ድምጽ የተናገሩትን አቋም በመጻረር የማኅበረ ቅዱሳን ቀኝ ክንፍ የሆኑት አባ ማቴዎስ የሰጡትን  ማስጠንቀቂያ መነሻ በማድረግ ለማስታወስ የምንፈልገው ቁም ነገር ስላለ ነው።
 ዛሬ አባ ማቴዎስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስን « እንደአቡነ ጳውሎስ በሞት ይወገዳሉ» በማለት የተናገሩትን ቃል ከስምንት ወራት በፊት ማኅበሩ ራሱ በአሉላ ጥላሁን መካነ ጦማር በኩል ተናግሮት ነበር። ያንኑ የእናስወግዳለን ዛቻ አባ ማቴዎስ ሲደግሙት በቤተ ክህነቱ ውስጥ በተቃርኖ የቆሙ አካሎች ስውር መጠፋፋት እንደሚፈጽሙ ማሳያ ምስክር ነው።  በሌላ መልኩም ማኅበሩ ሊታረም የሚችል አካል ስላይደለ እየታየ ባለው የምድራዊ ሥልጣን ግብግብ ውስጥ ማኅበሩ በያዘው መንገድ ከቀጠለ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር መጥፋቱ የማይቀር መሆኑንም አስረግጠን ገልጸን ነበር። መቅኖ አጥቶና ባክኖ እንዲቀር ባንፈልግም አንዴ «ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ነው፤አንዴ አቡነ ማትያስ ሊበሉኝ ነው» የሚለው ጩኸት የራሱን ሥፍራ ቆም ብሎ እንዳያይ እያደረገው ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ቢጠፋ፤ መጥፋቱ በሌላ በማንም ሳይሆን በራሱ ተግባር መሆኑን ጠቁመን ነበር።
 መልካም ንባብ ይሁንላችሁ!!

ይህ ሕንጻ የማነው? የቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን? የመንበረ ፓትርያርክ? የአስመጪና ላኪ? የበጎ አድራጊ ድርጅት?

 የሀገሬ ሰው «ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል» ይላል። ይህ አባባል ለሰሞነኛው የማኅበረ ቅዱሳን የጅቡ በላኝ ጩኸት ይስማማል። ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ነው ሲል በየግል ጋዜጣው ማስወራቱ 22 ዓመታት ኢህአዴግ በሚመራት ሀገር ውስጥ ያልነበረ ይመስላል። ሲነግድ፤ ሲያስነግድ፤ ሲሸጥ ሲለውጥ፤ከግብርና ታክስ ተከልሎ በሚሊዮኖች ብር ህንጻ ሲገነባ በሀገሪቱ ኢህአዴግ ያላየው ወይም የማያውቀው ይመስላል። ኢህአዴግ ማኅበረ ቅዱሳንን በአስማት ይሁን በምትሃት እስከዛሬ ሳያየው ቆይቶ አሁን ለማየት ዓይኑን ሲከፍት ማኅበረ ቅዱሳንን አገኘውና ሊበላው ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ለምን ፈለገ ሲል ለመጠየቅ የተገደደ ይመስላል። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ያለው ተግባሬ ከማኅበረ ካህናቱ ጋር አጋጨኝ፤ በማያገባኝ አስተዳደር ውስጥ እጄን ሳስገባ ተገኘሁ እንዳይል ከመሬት ተነስቶ ኢህአዴግ ሊውጠኝ ነው ወደሚል ቅስቀሳ መግባቱን  ከመምረጡ በስተቀር በምድር ላይ ያለው እውነታ ግን የምርጫ ዘጠና ሰባት ውጤትና ተከትሎ የመጣው ፖለቲካዊ ቀውስ ስንቱን ፓርቲና የተቃዋሚ መሪዎች እየደፈጠጠ ሲያልፍ ማኅበረ ቅዱሳን ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ታዛ ተጠልሎ አልፏል።ኢህአዴግ ቢያጠፋው ኖሮ ያኔ ባጠፋው ነበር። 

ከዚህ በፊት ማኅበሩ እንደጥራጊ አውጥቶ የጣለው ዳንኤል ክብረት ይህን ኢህአዴግ ሊበላኝ ነው የሚለውን የማኅበረ ቅዱሳንን ዘፈን እንዲህ ሲል በደጀሰላም ብሎግ ላይ አውጥቶ ነበር።
«እኔ እንደምገምተው የማኅበሩ አባላት መንግሥትን እንዲፈሩ እና እንዲጠሉ የሚፈልጉ አካላት በአመራሩ ውስጥ ሳይኖሩ አይ ቀርም፡፡ ምንጊዜም አንዳች ከባድ ነገር ሲነሣ መንግሥት እንዲህ ብሎናል፣ በዚህ ስብሰባው እንዲህ ብሏል፣ ሊዘጋን ነው፣ ሊያስረን ነው፣ ሊጨርሰን ነው ከማለት ያለፈ አንድም ቀን በጎ ነገር ስለ መንግሥት የማያነሡ አካላት አሉ»
 ስለዚህ ከዚህ አባባል ተነስተን ልንል የምንችለው ነገር ይህ መንግሥት ሊበላን ነው የሚለው ዜማ እንደስልት የተያዘና መንግሥት በአባላቱ ዘንድ እንዲጠላ የተዘየደ መሆኑ ነው። ከዚያም ባሻገር መሰሪ ስራውን ለመደበቅ ራሱን ጻድቅ አድርጎ በሌሎች ሰዎች ዘንድ ለመሳል የታቀደ ጥበብ ሲሆን ጻድቁ ማኅበረ ቅዱሳንን ኢህአዴግ ሊያጠፋው ስለሆነ ኦርቶዶክሳውያን የሆናችሁ ሁሉ የዚህን መንግሥት መሠሪነት ተመልከቱ ብሎ ክፉ ስዕል ለመስጠት የተፈለገ ብልጠት ነው።
እውነቱ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ነጋዴ ድርጅት መሆኑ ማንም ያውቃል። የግል ይሁን የአክሲዮን ማኅበር መሆኑ ያልታወቀና የራሱን ሀብት የፈጠረ ተቋም ስለመሆኑም ስራው ምስክር ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ከንግድ ተቋማቱና ከልዩ ልዩ የገቢ ምንጮቹ ባሻገር የራሱ የሆኑ አባላት ያሉትና የአባልነት መዋጮ የሚሰበስብ ድርጅት ነው። ከዋናው ማዕከል ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ ቁመት የራሱ የሆነ መዋቅርና  ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ነገር ግን አደረጃጀቱ በየትኛው የሀገሪቱ  የአደረጃጀት ፈቃድ ላይ እንደቆመ ያልታወቀ መሆኑም እርግጥ ነው። ይህንን የራሱ ተቋማዊ ኅልውና ያለውን ማኅበር በሀብቱ፤ በንግድ ተቋማቱ፤ በመዋቅራዊ አካላቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመቆጣጠርና የማዘዝ ምንም ሥልጣን የላትም።  በአንጻሩም ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስር ተሸፋፍኖ እንደመጠለሉ መጠን ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ ላይ የመቆጣጠርና የማዘዝ ሥልጣን እንዳላት ግምት ያለው በመሆኑ መንግሥት ይህን ድርጅት ነክቶት አያውቅም። ስለዚህ ይህንን ማኅበር ቤተ ክርስቲያኒቱም፤ መንግሥትም ሳይመለከቱት ከሁለት ወገን ቁጥጥር ነጻ ሆኖ 22 ዓመት ዘልቋል። 
 «ለሁሉም ጊዜ አለው» እንዲሉ ሆኖ ማኅበሩን ማነህ? ምንድነህ? የት ነህ? ምን አለህ? ምን አገባህ? የሚሉ ካህናትና የአመራር አካላት ተባብረው በመነሳት መጠየቅ ሲጀምሩ ጥቂት ሟሳኞችና አሟሳኞች ወደሚል ሃሳብ ለመውረድ ተገዷል።  በምንም ደረጃ ያሉ ሰዎች ማኅበረ ቅዱሳንን መክሰስ መቻላቸው የማኅበሩን ማንነት ማሳያው ተግባሩ እንጂ ክሱ አይደለም።  እየተከሰሰ ያለው ማኅበር በተግባሩ ያልታወቀ ማኅበር ባለመሆኑ በሟሳኞችና አሟሳኞች የቃላት ጫወታ እየፈጸመ የቆየውን ሸፍጥ ሸፍኖ ማስቀረት አይቻልም።
ማኅበረ ቅዱሳን በተግባር በሌለው ሥልጣንና መብት መናፍቃን ናቸው ያላቸውን ኢትዮጵያውያንን በራሱ ጥቁር መዝገብ አስፍሮ አስደብድቧል፤ ሰልሏል፤ ስም አጥፍቷል፤ አስፈራርቷል፤ እንዲሰደዱ አድርጓል። ማኅበረ ቅዱሳን በቤተክርስቲያኒቱ ስም መጽሔትና መጻሕፍትን፤ ካሴትና ቪዲዮ፤ አልባሳትና ንዋየ ቅድሳትን ከታክስና ከቀረጥ ነጻ ሆኖ ነግዷል። የማኅበረ ቅዱሳን አቋም የሚቃወሙ ሁሉ ጠላቶቹ ናቸው። የሚደግፉት ደግሞ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ ወንጀል ቢኖርባቸው እንኳን የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ አገልጋይ ተደርገው ዜና ይሰራላቸዋል፤ ሙገሳ ይሰጣቸዋል። አባ እስጢፋኖስን ማንሳት ይቻላል። ጠላቶቼ ከሚላቸውና ስማቸውን ሌሊትና ቀን ሲያጠፋቸው ከቆዩት ጳጳሳት ውስጥ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ደግሞ የጥላቻ የአፍ መፍቻው ናቸው። ሌሎቹም ፈርተው አንገታቸውን ደፍተውለታል። የተገዳደረውን አንገት ያስደፋል፤ አለያም ቀና ካለ አንገቱን ይሰብራል።  ሌላው ቀርቶ ሲያመሰግናቸው የነበሩትን አዲሱን ፓትርያርክ ጠላቶቼ የሚላቸውን ሰዎች ሲቀጣ በቆየበት መልኩ በስም ማጥፋት ቅጣት ናዳውን እያወረደባቸው ይገኛል። ለራሱ ኅልውና ብቻ የሚጨነቅ፤ ካልመሰለው ደግሞ ሲያወድሳቸው ለነበሩት ሳይቀር ግድ የሌለው ማኅበር ስለመሆኑ ከድርጊቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።  ወትሮውንም ሸፋጭ ነጋዴ ገንዘቡን እንጂ ወዳጅና እውነት በእሱ ዘንድ ዋጋ የሌላቸው ስለሆኑ የሚያስበው ጊዜያዊ ትርፉን ብቻ ነው። በዚህ ዙሪያ ማኅበሩ አሸንቅጥሮ የጣለውና ለተቀበለው የእጅ መንሻ በውጪ እንዳለ የሚለፈልፈው ዳንኤል ክብረት ማኅበሩ ስለግለሰቦችና ስለቤተ ክርስቲያኒቱ ደንታ ቢስ እንደሆነ ያጋለጠው እንዲህ ሲል ነበር።
«ዲያቆን በጋሻው ማስተማር የጀመረው መቼ ነው? ማኅበሩ በነዲያቆን በጋሻው ላይ ሃሳብ ዛሬ መሠንዘር ለምን ጀመረ? በጋሻው ለቤተ ክርስቲያን አደጋ ነው ብሎ ስላሰበ አይደለም፡፡ በጋሻው ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ ስለ ተናገረ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ምንም ያልተናገረው ማኅበር ስሙ ሲነሣ ቤተ ክርስቲያን ተነካች ብሎ ተነሣ፡፡ ማኅበሩ አቡነ ጳውሎስን በተመለከተ የተለየ አቋም መያዝ የጀመረው መቼ ነው? «እርሳቸው ማኅበሩን ሊያፈርሱ ነው» ብሎ መሥጋት ከጀመረ በኋላ፡፡ አባ ሠረቀንም ቢሆንኮ ዛሬ ዛሬ በእምነት ችግር ይከሳቸዋል እንጂ፣ ከእርሳቸው ጋር ያለው ዋናው ችግሩ ማኅበሩ መነካቱ ነው፡፡ አባ ሠረቀ ማኅበረ ቅዱሳንን ሳይነኩ የፈለጉትን ቢሆኑ ኖሮ አይናገራቸውም ነበር፡፡ ባለፈው ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ ችግር ሲፈጠር፣ ዝምታን መርጦ የነበረው አመራር የመንግሥት አካላት ከቤተ ክህነቱ ባለሥልጣናት ጋር ሆነው ስለ ማኅበሩ ሲያወያዩት ግን አገር ይያዝልኝ አለ፡፡ የአዋሳ ምእመናንን ችግር በዝምታ ያለፈው አመራር አባ ሠረቀ አንዳች ነገር ተናገሩ ብሎ ድምፁን አሰምቶ ተናገረ፡፡ እነዚህ እና መሰል ሁኔታዎች አመራሩ የሚቆረቁረው ማኅበሩ ሲነካ እንጂ ቤተ ክርስቲያኒቱ ስትነካ አለመሆኑን ያመለክታሉ» ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ከራሱ በላይ ማንንም እንደማይወድ እርግጥ ነው። የራሱን ድክመት ቆም ብሎ በመገምገም ለመስተካከል ከመሞከር ይልቅ አንገቱን በማደንደን ወደ ስድብ፤ ዛቻ፤ ማስፈራራትና ስም ማጥፋት ይሮጣል። ይህም በመሆኑ ማኅበሩ የሚጠፋው በራሱ ተግባር እንጂ በቅንነቱ ወይም በቀናዒነቱ አይደለም። ይህም ማለት ግን ቀናዒና ቅን አባላት የሉትም ማለት እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። ቅን አባላቱ ጠማማውን አመራር ማስተካከል የሚችል አቅም የላቸውም። ማኅበሩ ራሱ የሚመራው በቡድናዊ ስልት ስለሆነ በቡድን ይመታሉ፤ በቡድን ይወገዳሉ። 
ማኅበረ ቅዱሳን በፖለቲካው ዙሪያ ከምርጫ 97 በፊትም ሆነ በኋላ ስላለው ሁኔታ መንግሥት በቂ መረጃ እንዳለው ይሰማል። በዚህ ዙሪያ መንግሥት ያለውን መረጃ እስኪያወጣ ድረስ የምንለው ነገር የለም። ነገር ግን ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያምሳት መቆየቱን፤ እጁን እያስገባ ሲኖዶሱን ሳይቀር እንደሚጠመዝዝ እናውቃለን። ማኅበሩ ደፋርና የልብ ልብ የተሰማው አንዳንድ የሲኖዶስ አባላት ተጠግቶ የጉባዔ ሃሳብ በራሱ መንገድ እስከመጠምዘዝ የመድረሱን አቅም እየለካ በመሄዱ ነው። ዛሬ ላይ ያ ነገር የለም። ፓትርያርክ ማትያስ ለዚህ የማኅበሩ ሃሳብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ገና አንድ ዓመት ሳይሞላቸው ከኢህአዴግ ጋር ተመሳጥረው ሊያጠፉኝ ነው እያለ ስም ወደማጥፋት ወርዷል። በተቃራኒው ደግሞ ማንም እንደማያጠፋው በሚገልጽ ጀብደኝነቱ ፓትርያርክ ጳውሎስም እንደዚሁ ሊያጠፉኝ ሞክረው እንደማያዋጣቸው አውቀው አጃቸውን ከእኔ ላይ ለማንሳት ተገደዋል በማለት ለፓትርያርክ ማትያስ የማስጠንቀቂያ ማስታወቂያ እየሰራ ይገኛል። እጅዎን ከእኔ ላይ የማንሳትን ጉዳይ ችላ ሳይሉ ከቀድሞው ፓትርያርክ ትምህርት ውሰዱ በማለት ማሳሰቢያ እየሰጠ መሆኑ ነው። 
የሚፈራው ከተገኘ ጥሩ ጀብደኝነት ነው፤ ነገር ግን ባለቀ ጊዜ ማላዘን ዋጋ የለውም። ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያኒቱ ስንት ችግር ባለባት ሰዓት ራሱ ችግር ፈጣሪ ሆኖ ካለቦታው የተገኘ ማኅበር ስለሆነ ተገቢ ቦታውን መያዝ ካለበት ሰዓቱ አሁን ነው። ማኅበረ ካህናቱና የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር አባላት ጠንክሮ መታገል የሚገባችሁ ወቅት ቢኖር ዛሬ ነው። ማኅበሩ ቁጭ ብሎ አዋጭ የሆነውን መንገድ መቅረጽ ካለበት ቶሎ ብሎ ይህንኑ እንዲፈጽም ምክር እንለግሰዋለን። የአክሲዮን ማኅበር፤ የሃይማኖት ተቋም፤ በጎ አድራጊ ድርጅት ወይም የተሻለ ነው ብሎ የደረሰበትን ውሳኔ ወደተግባር መቀየር ካለበት ቀኑ ሳይመሽ በብርሃኑ ይሆን ዘንድ ልናሳስበው እንወዳለን። ሲሆን ዘንድሮ፤ ካልሆነም በቀጣዩ ዓመት፤ ቢረዝም፤ ቢረዝም አንድ ቀን ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጉያ እንደመዥገር የተጣበቀበት ቀን እንደሚያበቃ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ምክንያቱም ማኅበሩና ተግባሩ፤ ካህናቱና አስተዳደሩ መቼም ቢሆን አሁን ባለው መንገድ አብረው መጓዝ አይችሉምና ነው።  ከዚህ ሁሉ ፓትርያርኩም፤ ካህናቱም፤ አመራሮችም፤ መንግሥትም ይህንን ማኅበር ቦታ የማስያዙን ጉዳይ ችላ ሊሉት አይገባም። ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖር ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖርም ትኖራለች!!!  «ማኅበረ ቅዱሳን ከሌለ ቤተ ክርስቲያን ትጠፋለች» የሚለው ራሱ ማኅበረ ቅዱሳን ብቻ ነው።

Friday, October 17, 2014

ካሕናቱና ማኅበሩ…እንዴት ተጃመሩ(ተጀማመሩ)???…

 ( በአማን ነጸረ )

 - ልክ የዛሬ አመት በተካሄደው አመታዊው የሰበካ ጠቅላላ ጉባኤ የምዕራብ ሸዋዎቹ አቡነ ሳዊሮስና ስ/አስኪያጆቻቸው “ማኅበሩ በሀገረ ስብከታችን ጣልቃ እየገባ አላሰራን አለ” የሚል ሪፖርት አቀረቡ፡፡ጉባኤው ለሪፖርቱ ያለውን ድጋፍ በእጁ ብቻ ሳይሆን በእግሩ ጭምር መሬት እየደበደበ በድምድምታ ታግዞ ገለጸ፡፡የዚህ ትርጉም ‘መናገር ፈርተን እንጅ በሁላችንም ሀገረ ስብከት ጣልቃ እየገባ ነው’ የሚል ነበር፡፡መፍትሄውም የራሱን የማኅበሩን አካሄድ መፈተሽ ነበር፡፡ማኅበሩ ያደረገው ግን በኅቡዕ ሚዲያዎቹ ጳጳሱንና ስ/አስኪያጆቹን ማብጠልጠል ሆነ፡፡የእነሱ ኃጢኣት የማኅበሩን ጥፋት ይሸፍነው ይመስል ጳጳሱን ‘ሺበሺ’፣መነኩሴውን ‘ዘማዊ’፣ካሕኑን ‘ካንድ በላይ ያገባ’ እያለ በኅቡዕ መዝለፉን ቀጠለ፡፡

2 - በሂሳብ ሙያ 25 አመታት ልምድ አለን ያሉ የጠቅላይ ቤተክሕነቱ ሰዎች ማኅበሩ በቤተክሕነት ስር እስከሆነና ተጠሪነቱም ለኛ እስከሆነ ድረስ በራሳችን ሰዎች ኦዲት ይደረግ፣የራሳችንን ደረሰኝ ይጠቀም የሚል ጥያቄ አቀረቡ፡፡ጉባኤው አሁንም ድጋፉን ገለጸ፡፡የማኅበሩ ተወካዮች ግን ጉባኤውን ረግጠው ወጡና በተለመዱት ኅቡዕ ሚዲያዎቻቸው የቤተክሕነቱን የአቅም ውሱንነትና የደረሰኞቹን ለሂሳብ አያያዝ ምቹ አለመሆን በመግለጽ ጥያቄውንና ጠያቂዎቹን ለማንኳሰስ ተሽቀዳደሙ፡፡ ‘እንዲህ አይነቱን አሰራር እኮ ማስተካከል የሚቻለው ከአስተዳደሩ በመራቅና እሱን በማራከስ ሳይሆን ውስጥ ገብቶ ራሱን ተቋሙንም አግዞ ከችግሩ ለመውጣት ያብሮነት ተጋድሎ በማድረግ ነው’ ብሎ ለመናገር ይቅርና ይሄን ሀሳብ ማሰብም ኑፋቄ ነው ተባለ፡፡

3 - ቀጠሉና ቤ/ክ ትዘምናለች፤አስተዳደሯ ይስተካከላል የሚል መፈክር አነሱ፡፡መፈክሩ ሁላችንንም አማለለን፡፡በገዳማውያን ጸሎት በመታገዝ 3 ሚሊዮን የፈጀ ጥናት አቅርበናል ‘ወንዶች በጭብጨባ ሴቶች በእልልታ’ ተባልን፡፡ከማኅበራዊ ሚዲያ እስከ ዐለማዊ ጋዜጦችና የዲያስፖራው ሚዲያ ተቀባበለው፡፡ይሄ ሁሉ ሲሆን ግን ጥናቱ ለሚመለከተው አካል ደርሶ ገና አልጸደቀም፤ካሕናቱም አልመከሩበትም፡፡ቀጠለ፡፡ካሕናቱና ምዕመናኑ ስለ ጥናቱ ስልጠና ተብሎ አራት ኪሎ ላይ ከተሙ፡፡ጉዳዩ ግን ስልጠና ሳይሆን ራስን መስበኪያና ጥያቄዎችን ማፈኛ ወደ መሆን አዘነበለ፡፡

4 - ከአጥኚው ክፍል ውስጥ ከ12ቱ 8ቱ የማኅበሩ አባላት ሲሆኑ በቋሚ ትክለኛ አገልጋይ ደረጃ ደግሞ አንድ ጸሐፊ መሀላቸው ጣል ተደርጓል፡፡ካሕናቱ እዚህ ላይ ጥያቄ አነሱ “በጥናቱ ውስጥ እኛን የሚወክል ሰው የታለ?” አሉ፡፡ “ጉዳያችሁ ከጥናቱ ጠቀሜታ ነው ወይስ ከአጥኚው?” እየተባለ ትርፍ ንግግርና አፈና ተጀመረ፡፡ነገርየው “እኛ ስለናንተ ጥቅም ስለምናውቅ ባትሳተፉ ምን ቸገራችሁ--እናውቅላችኋለን” በሚል እንደሚተረጎም ማን አስቦት!!እነሱ እንደሆነ ቀናኢነታቸው ከማንም በላይ ነው!!ጥያቄው ቀጥሏል!! “ያጠናችሁት ጥናት የቤ/ክ የበላይ ሕግ በሆነው ቃለዐዋዲ የታቀፉ ነባር የስራ መደቦች ላይ ሽግሽግ የሚያደርግና የተወሰኑ ኃላፊነቶችን ጨምሮ እንደ አዲስ የሚደለድል ስለሆነ ቃለዐዋዲውን ቀድሞ መመሪያው መምጣቱ ከፈረሱ ጋሪው (በሐጋጊዎች አነጋገር against hierarchy of law) ሆነሳ?” ቢባል!! እረ ወዲያ!!ማን ሰምቶ!! አማሳኝ፣ ዘረኛ፣ ተሐድሶ፣ ካድሬ፣ ወያኔ፣ ሌባ፣ ሙሰኛ፣ምንደኛ፣ተላላኪ፣ደደብ፣ምቀኛ፣ሸረኛ…..የስድብ ሜኑ ተደረደረ!!

5 - አሁን ፅዋው ሞላ!!የአድባራትና ገዳማት አለቆችና ፀሐፊዎች መጋረጃውን ገልጠው ወጡ!!በይፋ ተሰባስበው በቤ/ክሕነቱ አዳራሽ አጀንዳቸውን ቀርጸው ፊርማ ማሰባሰብ ጀመሩ፡፡ገና በጠዋቱ መንገዳቸው ላይ ያለውን ፈተና ተገንዝበውት ነበር፡፡የማኅበሩ ኅቡዕ ሚዲያ የ30 እና 40 አመት አገልግሎታቸውን አፈር አስግጦ ዛሬ እሱ ላይ ጥያቄ ስላነሱ ብቻ ስማቸውን ጭቃ ከመቀባትም አልፎ በራሳቸውና በሚቀርቧቸው ሰዎች ጭምር እንደሚመጣባቸው እንደሚጠብቁ በአደባባይ ተናገሩ፡፡እነ ፋክት መጽሔት፣እነ ‘ቀናኢ ነን’ ብሎጎች የአደባባዩን አቋም “ጥብቅ ምስጢር” እያሉ ቲፎዞ ማንቀሳቀሳቸውን ቀጠሉ፡፡አልገረመንም!!ብሎግን ከግል ኅትመት ሚዲያ አቀናጅቶ በማኅበሩ አካሄድ ጥያቄ ባነሱ ሁሉ መዝመት ከሚሊኒየሙ ማግሥት ጀምሮ እንደ መልካም ትውፊት ስለተያዘ!!

6 - የካሕናቱ በአለቆችና በፀሐፊዎች መያዝ ባሰጋው ማኅበር ቀስቃሽነት ጉዳዩን የምዕመናንን መብት የማስከበር አስመስሎ ከ40 አመት በፊት በሰበካ ጉባኤና በልማት ኮሚቴ እየተመረጠ ከካሕናቱ ጎን ለጎን በቤ/ክ ጉዳይ ውሳኔ ሰጭ የሆነውን ምዕመን ሆድ ለማስባስ ተሞከረ፡፡ “መሬት አንቀጥቅጥ ሰልፍ እንጠራለን፣የአማሳኞችን ገመና እናወጣለን” ተባለ!!ተፎከረ!! ‘እረ ቀስ’ የሚል አልነበረም!! ‘ገመና-ገመና የሚባለው አካሄድ የሚሰራው ሰዎቹ ያጠፉ እለት እለቱን እንዲታረሙና ማስረጃውም ገና ትኩስ እያለ ቢሆን እንጅ ማኅበሩን ሲያነሱ ብቻ ከሆነማ ማኅበሩን ሳያነሱ ስለሚያጠፉት ሰዎች ደንታ የላችሁም፤ስለዚህ እናንተ ቤ/ክ ተጎዳች ምትሉት ማኅበሩ ላይ ጥያቄ ከተነሳ ብቻ ነው’ ያሰኝብናል የሚል ይሉኝታ እንኳ የለም!!ወደ ፊት ብቻ!!በዚህ መሀል ካሕናቱ በጥናቱ ይዘት፣በአጥኚው ስብጥር፣በጥናቱ የስልጠና ሂደት ያላቸውን ቅሬታ በመጠኑ ፈንገጥ ካለና ስሜታዊነት በታከለበት አኳኋን የማኅበረቅዱሳንን ሥም እየጠሩ አስረዱ--ለቅ/ፓትርያርኩ፡፡

7 - ‘የለውጥ አራማጅ ነኝ፣ተነቃናቂ ኃይል አለኝ፣ተወደደም ተጠላም ጥናቱ ሳይሸራረፍ ይተገበራል’ የሚለው ቡድንም በጋዜጣና በብሎግ ተጠራርቶ ፓትርያርኩ ላይ ገብቶ አጀንዳውን አስረዳ፡፡ፓትርያርኩም “ጥናቱ በሊቃውንት ክለሳ ተካሂዶበት ለቤ/ክ በሚበጅ መልኩ ይተገበራል፤ቀደም ሲል የመጡት ካሕናትም ጉዳያቸውን ማስረዳት መብታቸው ቢሆንም ዳኅፀ - ቃል (የምላስ ወለምታ) አድርገዋል” ብለው በአባታዊ መንገድ አስተናገዱ፡፡እዚህ ላይ ጨዋታው ፈረሰ!! ‘ጥናቱ አሁኑኑ’ የሚለው ኃይል የጭቃ ጅራፉን ያጮኸው ጀመር!!ጮኸ-ጮኸ-ጮኸ!!ይሄን ጩኸት ከኋላ ሆኖ ይዘውረው የነበረው ማኅበርም በጩኸቱ ተበረታቶ ነው መሰለኝ መጋረጃውን ገልጦ ወጣና ልሳኔ-የግሌ በሚል ስሜት ሐመር መጽሄቱን መዶሻ፣አቤቱታ አቅራቢዎቹን ካሕናት ደረቅ የማገዶ ግንድ አድርጎ አማሳኝ፣ተሐድሶ…እያለ ፈለጣውን ቀጠለ!!

8 - ካሕናቱ ግን ወይ ፍንክች!!ከነብር ተፋዞ (ተፋጦ) ማን እንቅልፍ ያበዛል!!እስከ በታች ሰራተኛ ወርደው 5ሺህ የሚገመት ፊርማ አሰባሰቡ፣ኮሚቴ አዋቀሩ፣መንግሥት እንዳይገላምጣቸው አሳወቁ (በመንግሥትም ተሰግስግንበታል እየተባለ ማስፈራሪያ ሆኗላ)፣ዐላማቸው ማኅበሩ ቤ/ክ ባሰመረችለት ልክ ከመጓዝ አልፎ ጣልቃ መግባቱን እንዲያቆም እንጅ ማኅበሩን ለማፍረስ አንዳች ፍላጎት እንደሌላቸው ተናገሩ፣የተላተምነው አድማሳትን የሚያቋርጥ የሚዲያ መረብ ከዘረጋ አካል ነውና በአስተዳደር ላይ ያላችሁ ራሳችሁን ካላስፈላጊ ምግባርና ከተበላሸ አስተዳደር ጠብቁ፣በተቻለ መጠን አባቶችን ሰድቦ ለሰዳቢ ከሚሰጠው የተሐድሶዎች እንቅስቃሴ አጀንዳችንን እንጠብቅ…የሚሉ መርሆዎች ተቀመጡ፡፡

9 - እንቅስቃሴው ከላይኛው የቤተክሕነት አካልም ቀላል የማይባል ድጋፍ አገኘ፡፡በፓ/ኩ ዕለተ - ሲመት የካቲት 24 በተደረጉ ቅኔያት ይሄው ሀሳብ…ወቤቴል አሀቲ ኢትኩን ዝርውተ፣አኃዝ ማኅበራተ፣መዋግደ ብዙኅ ፀጋከ ወአስተናድፍ ሥርዓተ…በሚሉ የሊቃውንት ቅኔያት ተንፀባረቀ፡፡ማኅበሩ ግን ይሄንን ከቅርቡ ያሉ ሊቃውንት ውትወታ ከመስማት ይልቅ ለሚመለከተው መምሪያና ላሉበት ሀገረ ስብከት ሳያሳውቅ የጠረፎቹን እየጠራ “ለማናውቀው ስብሰባ ኃላፊነት አንወስድም” ሲባል….የኛ ቤት እንደምታውቁት…እያለ የአዞ እንባውን መርጨት ጀመረ፡፡ታዲያ ሚዲያው አልሰነፈም!!ጉዳዩን ሲፈልግ ከወያኔ አነሳስ፣ሌላ ጊዜ ደግሞ ከተሐድሶ እንቅስሴ ጋር እያገናኘ ማኅበሩ ራሱን የሚያይበትን ውስጣዊ ዐይን ዐውሮ በትምክሕቱ እንዲጀቦን የውዳሴ ከንቱ ቡልኮ አጎናጸፈው፡፡ “አንድ ለእናቱ” እያሉ የቤተክርስቲያኒቱን የ2ሺህ አመት ታሪክ ለ20 አመቱ ማኅበር አሸክመው አንገዳገዱት፡፡ውስጡን እንዳይመለከት ጋረዱት!!

10 - እናም ይሄው አባላቱ ማኅበሩን የበጎነት እና የክፋት፣የጽድቅና የኩነኔ መለኪያ አድርገው ኮሽ ባለ ቁጥር ፡- ራሳቸውን መድኅን ቅሬታ አቅራቢዎችን ሰቃልያነ - እግዚእ፣ራሳቸውን ድመት ሌላውን አይጥ፣እነሱ ርቱዕ ኦርቶዶክሳዊ ሌላው መናፍቅ፣እነሱ ለነፍስ ያደሩ ሌላው ለሆዱ….እያሉ እያስመሰሉ የልዩነት መስመር ሲያሰምሩ ይውላሉ፡፡የሚበዙት አባላቱም ማኅበራቸውን ከመፈተሸ ይልቅ ዕቡያን ክሶቹን ተቀብው አሜን-አሜን ይላሉ!!ይህ የማኅበሩ ከመዋቅር እና ከማዕከላዊ አስተዳደር የማፈንገጥ ዝንባሌ፣ስሙን ባነሱ የቤ/ክ ልጆች ላይ ሁሉ ከቅ/ሲኖዶስና ከፍርድ ቤት ውሳኔ በፊት የሚያደርገው “የተሐድሶ እና አማሳኝ” የውንጀላ ዘመቻ ለቀሳጥያን ተሐድሶዎችና የእነሱ ልሳናት ለሆኑ ብሎጎች ምን ያህል መንገዱን ጨርቅ እንዳደረገላቸው አልተረዱም!!እነዚህ በቁም ያሉትን፣እነዛ ደግሞ በቅድስና ያረፉትን ክብር በማጉደፍ ምዕመኑ ላይ የእጓለማውታነት ስሜት ለመፍጠር ይታትራሉ!!ከንቱ መታተር!!ፍኖተ ሐኬት--የክፋት መንገድ!!

Wednesday, October 15, 2014

«እርስዎም በአማካሪዎችዎ የተነሳ ዕድሜዎ እንዳያጥር ያስቡበት!» ያሉት አባ ማቴዎስ ጠንቅ ዋይ ወይስ የሞት መንፈስ?



ዋና ሥራ አስኪያጁ ‹‹ውድቀት እንዳይደረስብዎ አማካሪዎችዎ ሊያዝንልዎ ይገባል፤›› ማለታቸውን የገለጹት የስብሰባው ተሳታፊዎች አያይዘውም ‹‹ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በአማካሪዎቻቸው ክፋት ከዕድሜያቸው ዐሥር ዓመት አሳጥረዋል፤ እርስዎም በአማካሪዎችዎ የተነሣ ዕድሜዎ እንዳያጥር ያስቡበት፤›› ሲሉ መምከራቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ( ሐራ)

«እርስዎም በአማካሪዎችዎ የተነሳ ዕድሜዎ እንዳያጥር ያስቡበት!» ያሉት አባ ማቴዎስ ጠንቅ ዋይ ወይስ የሞት መንፈስ ናቸው?

የሁላችንም ዕድሜ ያለው በእግዚአብሔር እጅ ነው። ማንም የማንንም ዕድሜ አያውቅም። ነገር ግን የሰውን ዕድሜ እናውቃለን የሚሉ ጠንቅ ዋዮችና መናፍስት ጠሪዎች ቢኖሩም አታላዮችና አጭበርባሪዎች ናቸው። ታዲያ አባ ማቴዎስ የፓትርያርክ አቡነ ማትያስን እድሜ በዐሥር ዓመት ማሳጠር የሚችሉት በምን ጥበባቸው ነው? ደግሞስ ነፍስ ኄር አቡነ ጳውሎስ ሊቆዩ ከሚችሉበት ዕድሜ በዐሥር ዓመት ያሳጠሩትስ በምን ኃይል ነው? አባ ማቴዎስ ስለሟቹ ፓትርያርክ አሟሟት የሚያውቁትን ምሥጢር በፓትርያርክ ማትያስ ላይ ለመድገም እንደሚችሉ «እርስዎም ዕድሜዎ በዐሥር ዓመት እንዳያጥር ያስቡበት!» ሲሉ ማስጠንቀቃቸው የሚነግረን አንድ ምሥጢር አለ። እግዚአብሔር ማኅበረ ቅዱሳንን የማይወደውን ሁሉ ይገድላል እያሉን ነው ወይም ማኅበረ ቅዱሳንን የማይወደውን ሁሉ እኛ እንገድላለን ማለታቸው ነው። እንደዚያ ካልሆነ ማኅበረ ቅዱሳንን ባለመውደድና በሞት መካከል ምን ግንኙነት አለ?

    አባ ማቴዎስ በግልጽ ቋንቋ የተናገሩት ዐረፍተ ነገር እንደሚያስረዳው ስለፓትርያርክ ጳውሎስ አሟሟት በትክክል እንደሚያውቁ ነው። ይህንኑ ዕውቀት በፓትርያርክ ማትያስ ላይ እንደሚደግሙት ማስጠንቀቂያቸው ያስረዳናል።
«የአቦን ግብር የበላ ይለፈልፋል» እንዲሉ በማኅበሩ ላይ የደረሰው የማኅበረ ካህናቱና የፓትርያርኩ ግልጽ አቋም ያበሳጫቸው ሸዌው እጩ ፓትርያርክ አባ ማቴዎስ በንዴት ሳያውቁት ድብቁን አደባባይ ላይ አዋሉት። «አቡነ ጳውሎስን የገደልናቸው እኛ ነን» ሲሉ ራሳቸው መሠከሩ። እኛም በመጠየቅ ጨምረን እንዲነግሩን የምንፈልገው እንዴት አድረገው እድሜአቸውን ማሳጠር እንደቻሉ ምስጢሩን ከቻሉ በጀመሩበት መንገድ በፈቃዳቸው እንዲነግሩን፤ እምቢ ካሉ ደግሞ በሕግ ፊት እንዲዘከዝኩልን ለሚመለከታቸው ክፍሎች እናሳስባለን። 

በአንድ ከፍተኛ የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር ላይ «ዕድሜህን በዐሥር ዓመት እናሳጥራለን!» የሚለው ዛቻ «ልብስ አጥበን እንተኩሳለን» እንደሚባለው የሠፈር ማስታወቂያ ተነቦ በቀላሉ የሚታለፍ ጉዳይ አይደለም። በተዘዋዋሪ «እንገድልሃለን» ማለት ነው። የግድያ ዛቻ ደግሞ በምድራዊው ሕግ ወንጀል ነው።  በሰማያዊውም ቃል ዐመጻና ክፋት ነው።

«አስበው ክፉ ነገርን ተናገሩ። ከፍ ከፍ ብለውም በዓመፃ ተናገሩ» መዝ 73፤8 

አስበው የተናገሩት ቃል ከፍ ያለ የግድያ ዐመጻ ነው። አባ ማቴዎስ ቀድመው እንደማይሞቱ ያረጋገጡ ይመስል የአቡነ ማትያስን በፍጥነት በሞት መወገድ በአደባባይ እንደማወጅ ነውረኛና የከፋ አነጋገር ይኖር ይሆን? እግዚአብሔር አምላክነቱ ለአባ ማቴዎስና ለማኅበረ ቅዱሳን ብቻ የሆነ ያህል አቡነ ማትያስን ቶሎ እንደሚገድል መናገር አሳፋሪ ነው። እንግዲህ እነዚህ ናቸው፤ ቤተ ክርስቲያንን የሚመሩት!

በማኅበረ ካህናቱ ስብሰባ ላይ የነበሩ አንድ ካህን ከተናገሩት አንድ ቃል እዚህ ላይ ልዋስ። « እነዚህ እኮ መንግሥትን ከአንድ ክ/ሀገር ወደሌላ ክ/ሀገር ያመጡ ሰዎች ናቸው እኮ፤ በዚያን ዘመን እንዲህ ማድረግ የቻሉ ዛሬ «አቢሲዲ ቆጥረውማ ማን ይችላቸዋል?» ማለታቸው አንድ ነገር ያሳስበናል። ለሥልጣን ሲሉ ሰው እስከመግደል ሊደርሱ መቻላቸውን ይገልጻል። እንደዚያ ካልሆነ አባ ማቴዎስ እስከዕድሜ ማሳጠር እብደት ቀመስ ንግግር ባልደረሱም ነበር። ምንም እንኳን የሰው ልጅ ዕድሜ በእግዚአብሔር እጅ ያለ ስለሆነ ሁሉም ሰው መሞቱ ባይቀርም አሟሟቱ ግን ልዩ ልዩ ነው።

 በጎርፍ፤ በመሬት መንቀጥቀጥ፤ በመኪና አደጋ፤ ገደል በመውደቅ፤ ውሃ ውስጥ በመስመጥ፤ በሕመም፤ በሰው እጅ በመገደል ወዘተ መንገድ ሕይወቱ ሊያልፍ ይችላል። የአቡነ ማትያስ አሟሟት በእነ አባ ማቴዎስ እጅ ይፈጸም ዘንድ ከፈጣሪ የታዘዘ ካልሆነ በስተቀር ካልጠፋ ወቀሳና ሌላ የማሳሰቢያ ንግግር «እንደአቡነ ጳውሎስ ዕድሜዎት በዐሥር ዓመት ያጥራል» ባለሉም ነበር። እግዚአብሔር የነፍሳት ሁሉ ጌታ ስለሆነ  አሟሟታቸውን ልዩ ልዩ አድርጓል።  በእርግጥም የሰውን ነፍስና ሥጋ ይለዩ ዘንድ ምክንያት ከሚሆኑት መካከል ክፉ መናፍስቶች አንዱ ናቸው። አባ ማቴዎስን ከክፉው መንፈስ እንደአንዱ እንቁጠራቸው? ሞትን ያህል ዜና በአደባባይ ያወሩት የክፉው መንፈስ መልዕክት ቢደርሳቸው ይሆናል። እውነታው ግን እግዚአብሔር ለአባ ማቴዎስና ለማኅበራቸው ብቻ የቆመ አምላክ አይደለም። ኃጢአተኞችን ሁሉ በመታገስ ዕለትን በዕድሜአቸው ላይ የሚሰጥ ሁሉን ቻይ አምላክ ነው።
ነገር ግን አባ ማቴዎስ እንደጻድቅ ራሳቸውን ቆጥረው በሌላው ሰው ላይ ሲፈርዱ ለዚህ ክፉ አሳባቸው የሞት መልአክ ቀድሞ ወደእርሳቸው ቢመጣስ?

«ክፉ ሰው ዓመፃን ብቻ ይሻል ስለዚህ ጨካኝ መልአክ ይላክበታል» መዝ 17፤11 ይላልና መጽሐፉ።

አቡነ ማትያስም ከክፉ ሰዎች እጅ እንዲድኑ አብዝተው መጸለይ የሚገባቸው ይመስለናል። ዳዊት በዝማሬው እንዳለው

 « አቤቱ፥ ከክፉ ሰው አድነኝ፥ በልባቸውም ክፉ ካሰቡ ከዓመፀኞች ሰዎች ጠብቀኝ ቀኑን ሁሉ ለሰልፍ ይከማቻሉ» መዝ 140፤1

የዕድሜ ወሰን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።

«የሰው ዕድሜ የተወሰነ ነው፥ የወሩም ቍጥር በአንተ ዘንድ ነው፥ እርሱም ሊተላለፈው የማይችለውን ዳርቻ አደረግህለት» ኢዮ 14፤5
አባ ማቴዎስ ማኅበረ ቅዱሳንን የሚነካ ሁሉ ይሞታል እያሉ ይናገራሉ።  ታዲያ አባ ማቴዎስ ጠንቅ ዋይ ናቸው ወይስ የሞት መንፈስ???? የምታውቁ ንገሩን!!