Sunday, February 24, 2013

ደግመን ደጋግመን የምንቃወመው ነገር ዐድማና ዘመቻው ለቤተክርስቲያን ሳይሆን ለግለሰቦች ጥቅም የሚውል በመሆኑ ነው!


የአቡነ ማትያስን ፓትርያርክ መሆን ኅሊና እንዳለው ሰው ምልከታ በራሱ ጉዳት አለው ብለን አስበን አናውቅም። ችግሩ የሚመጣው አቡነ ማትያስን ፓትርያርክ ለማስደረግ የሚደረገውን ሩጫ ስንመለከትና ሯጮቹን ስንመረምር እጅግ ያሳስበናል፤ ያስፈራናልም። የአቡነ ማትያስን ፓትርያርክነት የሚፈልጉ ቡድኖች ሁለት ስልት ይዘው የሚንቀሳቀሱትን  እነማን መሆናቸውን ስናይ ምርጫውን አጥብቀን ለመቃወም እንገደዳለን። በምርጫ ሚዛን ከአቡነ ሳሙኤል ይልቅ አቡነ ማትያስ የተሻለ ኳሊቲ ሊኖራቸው ይችላል። ይሁን እንጂ አቡነ ሳሙኤልን የሚጠሉ ቡድኖች በአንድ በኩል የጥቅሞቻችን ጠላት የሚሏቸው አቡነ ሳሙኤልን ለመጣልና በሌላ በኩል የራሳቸውን ጥቅሞች ለማስከበር ሲሉ ለአቡነ ማትያስ መመረጥ ዐመጽና ዘመቻ ውስጥ መግባት ለቤተ ክርስቲያን ከጉዳት በስተቀር ትርፍ ካለማምጣቱም በላይ ተገቢም፤ መንፈሳዊም አይደለም። እንደዚሁ ሁሉ የአቡነ ማቴዎስ መመረጥ በብዙ ሚዛን ቢለካ ፓትርያርክ ለመሆን የሚያስችል ብቃት እንዳላቸው እናምናለን። ይህን ብቃት ለማግኘት የግድ የቡድንና የዐድማ ዘመቻ ውስጥ መገባት አለበት ብለንም አናስብም። የአቡነ ማቴዎስን ፓትርያርክ መሆን የሚፈልጉ ቡድኖች አቡነ ማቴዎስ ለቤተ ክርስቲያን እንዲሰሩ ፈልገው ሳይሆን በር ከፋችና ዘጊ ሆነው በቤተ ክርስቲያን ጉያ ዐቃቤ ኆኅት አድርገው ራሳቸውን ለመትከል ከመፈለግ የመነጨ በመሆኑ አሁንም እንቃወማለን። የአቡነ ሕዝቅኤልንም ፓትርያርክነት እንዳንቀበል የሚያደርገን ጉልህ ችግር አለ ብለን አስበን አናውቅም። ችግሩ ያለው አቡነ ሕዝቅኤል ፓትርያርክ እንዲሆኑ የሚፈልጉ ወንዘኞች የመራወጣቸው ነገር ነው።  ምንም እንኳን ከሰው ልጅ ጉድለት የመኖሩ ነገር ጠባይዓዊ መሆኑ ባይካድም ከጉድለታቸው ይልቅ ብቃታቸው ያመዝናልና ፓትርያርክ ሆነው ሁሉም መታጨታቸው በራሱ ችግር ላይኖረው ይችላል። ችግሩ የሚነሳው እነሱን ፓትርያርክ ለማድረግ የሚራወጡት ኃይሎችና ቡድኖች እያደረጉት ያለው ጉዞ ነው። የማያውቋት ቤተ ክርስቲያን አሳስቧቸው ሳይሆን በዚህም ይሁን በዚያ ጥቅሞቻቸውን ለማስከበር ከታቀደ ዓላማ የመነጨ በመሆኑ ድርጊታቸውን አጥብቀን እንጸየፈዋለን። በሌላ መልኩም ራሳቸው እጩዎቹ እነዚህን ዙሪያቸው ተሰልፈው እናነግስዎታለን ባዮችን በመቃወም ምርጫው በመንፈሳዊ ዓይን ተካሂዶ የሚመጣውን ውጤት በቅንነት ከመጠበቅ ይልቅ ከተሰላፊዎቹ ጋር መቆም ወይም ሰልፉን በዝምታ መቀበላቸው በራሱ ፓትርያርክ የመሆን ብቃታቸውን ያወርደዋል። በዚህም የተነሳ ለፓትርያርክነት የቆሙበትን መንገድ አጥብቀን እንቃወመዋለን።
 በዐድመኞቹና ሰልፈኞቹ የተቀነባበረ መንገድ ለምርጫው ይቀርባሉ የተባሉ የ880 የመራጮች ድምጽ ጥራት እንደሌለው የቻይና እቃ በርካሽ ዋጋ ገዝተው ወይም እጅ ጠምዝዘው ሲያበቁ አስቀድሞ የታወቀውን የራሳቸው ፓትርያርክ በምርጫ አሸንፈዋል ለማለት መዘጋጀት እንኳን እንደ ሃይማኖት ሰዎች ይቅርና ኅሊና እንደፈጠረበት ኢአማኒ ለመቀበል  የሚያስቸግር አሳፋሪም፤ አሳዛኝም  ነገር ነው። አቅማቸው ፈቅዶ ዐድመኞችን ማስተባበር የማይችሉት እነ አቡነ ኤልሳዕ እና አቡነ ዮሴፍ የመሳሰሉት አንድም እንደ ሕጻን ፓትርያርክ ልናደርጋችሁ አጭተናችኋል ብሎ ማታለል ነው፤ አለያም መራጭ እንደሌላቸው በማስላት ለጫወታ ሜዳው ውበት ለመስጠት የተፈለጉ አዳማቂዎች  አድርጎ ማቅረብ ነው። እኛ አጫዋች አንሆንም ብለው ራሳቸውን ቢያገሉ ቢያንስ ለፓትርያርክ መወዳደር ማለት ምን ማለት እንደሆነና ዋጋ እንዳለው ማሳየታቸው ነው፤ ቢበዛም የነጋዴዎቹን የኮንትሮባንድ መንገድ ወደሕግ መስመር እንዲገባ ጫና መፍጠራቸው ስለሆነ ውሳኔአቸውን እናደንቃለን።

Saturday, February 23, 2013

ምረጡኝ ብዬ አላልኹም፤ ምረጡኝ ብዬ አላውቅም

 (አዲስ አድማስ፤ ቅዳሜ የካቲት 16/ 2005)
አምስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሞተ ሥጋ ከተለዩ ስድስት ወራት ተቆጠሩ፡፡ ከፓትርያርኩ ኅልፈት በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን በተደነገገው መሠረት ስድስተኛው ፓትርያርክ እስኪመረጥ ድረስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክነት ተሠይመው ቤተ ክርስቲያኒቱን በማገልገል ላይ ናቸው፡፡
የስድስተኛውን ፓትርያሪክ ምርጫ ለማስፈጸም ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ የተቋቋመው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ጥር 30 ቀን 2005 ዓ.ም ለብዙኀን መገናኛ ይፋ ባደረገው የምርጫ መርሐ ግብር መሠረት፤ ከየካቲት 9 - 14 ቀን 2005 ዓ.ም አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ሲመርጥና ሲያጣራ ቆይቶ በዛሬው ዕለት ለቅዱስ ሲኖዶሱ እንደሚያርቀርብ ታውቋል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤም ከዛሬ ጀምሮ በሚያካሂደው ውይይት የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ለሚከናወነው ምርጫ በዕጩነት በሚቀርቡት አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ላይ የመጨረሻ ውሳኔ አሳልፎ የዕጩዎቹን ዝርዝር ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡
የምርጫው ሂደት በይፋ ከተጀመረ አንሥቶና ከዚያም በፊት ቀጣዩ ፓትርያሪክ እንደሚኾኑ ብዙ ከተነገረላቸው ሊቃነ ጳጳሳት መካከል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አንዱ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው በፓትርያሪክነት ምርጫው ከሚሳተፉ ከ800 በላይ መራጮች የምርጫ ድጋፍ ለማሰባሰብ በሥልጠና ስም በርካታ ገንዘብ ማውጣታቸውን፤ በሕንፃ ኪራይ፣ በሥራ ምደባ፣ በውጭ ተልእኮና በሹመት አሰጣጥ ለብዙዎች ቃል መግባታቸውን፤ ከዚህም አልፎ ቀጣዩ ፓትርያሪክ እርሳቸው እንደሚኾኑ ራሳቸውን ለመንግሥት አካላት ስለ ማስተዋወቀቸው በአንዳንድ ሚዲያዎች ተዘግቧል፡፡
በእኒህ ጉዳዮች ላይ የብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን አስተያየት ከራሳቸው አንደበት ለመስማት የአዲስ አድማስ ሪፖርተር ሰላም ገረመው ከብፁዕነታቸው ጋር አጭር አጠር ያለ ቆይታ አድርጋለች፡፡

በያዝነው ዓመት በኮሚሽኑ ድጋፍ ለአህጉረ ስብከት ሓላፊዎች የተሰጡ ሥልጠናዎች፣ በአዲስ አበባ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጋር የተደረጉ የልምድ ልውውጦች ከፓትርያሪክ ምርጫው ጋር በተያያዘ ለብፁዕነትዎ ድጋፍን የመሸመት ዓላማ እንደነበራቸው ይነገራል፡፡ የተሰጠው ሥልጠና ምን ነበር? ዓላማውና የበጀት ምንጩስ?
ከግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከመጡ ልኡካን ጋር የተደረገው የልምድ ልውውጥና የተሰጠው ሥልጠና፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከግብጹ ፖፕ አቡነ ሺኖዳ ጋር ቀድሞ በደረሱበት ስምምነት መሠረት የተፈጸመ፣ ነገር ግን ዘግይቶ የተፈጸመ ስለኾነ እንጂ ከፓትርያሪኩ ኅልፈት በኋላ የታቀደና ለምርጫ ድጋፍ ቅሰቀሳ የታሰበ አይደለም፤ በቀጣይም ከሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት ለምሳሌ ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በተመሳሳይ መድረኮች የመገናኘት ዕቅድ አለን፡፡
ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና ሌሎች ሓላፊዎች በጥቅምት ወር ከሀገር አቀፉ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጋር ተያይዞ የተሰጠው ሥልጠና አምናም በተመሳሳይ ወቅት የነበረ ነው፡፡ በ2004 ዓ.ም ጥቅምት ወር ፓዝፋይንደር ኢትዮጵያ በሰጠው የገንዘብ ድጋፍ በሥነ ተዋልዶና የሴት ልጅ ግርዛት ላይ ያተኮረ ሥልጠና ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች ተሰጥቷል፡፡

አማኝ እንጂ አክራሪ አትሁን!


አማኝ ያመነውን የሚኖር በፍቅርም የሚማርክ ጀግና ነው። አክራሪ ግን ጥቂት እውቀቱን ከዱላ ጋር ለማስከበር የሚሞክር ነው። የከረረ ነገር መበጠሱ አይቀርም። የከረረ ነገር ሲከርም ሲበጠስም ስጋት ነው። አክራሪነት የአለሙ ልከኛ ሰው እኔ ነኝ። ከኔ በቀር በአለም ላይ ማንም መኖር የለበትም። ከምስራቅ ስገላበጥ ምእራብ እደርሳለሁ። ከሰሜን ስራመድ ባንድ ስንዝር ደቡብን እረግጣለሁ። ስለዚህ ከኔ ውጪ ማንም መኖር የለበትም ብሎ እንደማሰብ ነው። የአክራሪነት ምንጩ አለማወቅ ነው። አክራሪ ሰው በከሳሽነት መንፈስ የተያዘ እንጂ የሚያሳየው ማራኪ ስራ የሌለው ነው። ጥቂት እውቀቱ ከሰፋች የካደ ስለሚመስለው ላለማወቅ ተጠንቅቆ የሚጓዝ ነው። እርሱ ካለበት ገድጓድ ውጪ አለም ያለ የማይመስለው ። የለመድኩት ሰይጣን ይሻላል ብሎ ከመቃብር ጋር በኪዳን የሚኖር ተስፋ የሌለው ሳይሞት መኖር ያቆመ ሳይቀበር እውቀቱን የጨረሰ ሰው ነው። የአክራሪነት ወንድሙ አለማወቅ ነው።