Monday, January 7, 2013

«በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም» ፩ኛ ቆሮ ፭፤፰


ጨለማ አስቸጋሪ ነገር ነው። የሰው ልጆች የሌሊቱን ጨለማ ማሸነፍ ባይችሉ ማየት የተከለከለ የዓይናቸውን ብርሃን ለማገዝ የተለያዩ የብርሃን ምንጮችን ሰርተዋል። እንደዚያም ሆኖ የሰው ልጆች የብርሃን ምንጮች  ጨለማን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠር አይችሉም። ይልቁንም በእንከንና በችግር የተሞሉ በመሆናቸው በሌሊቱ ጨለማ ውስጥ አንዳንዴ በጨለማው ሊሸነፉ ይችላሉ። እንኳን የሰው ልጆች የብርሃን ስሪቶች ይቅርና የሰማይ አምላክ የፈጠራት የፀሐይ ብርሃን እንኳን ዓለሙን ሙሉ በአንድ ጊዜ እንድትሸፍን ተደርጋ አልተስራችም። ከዚህም የተነሳ በክልል ያልተወሰነ፤ ብቃቱ ምሉዕ የሆነና በጨለማ መተካት የማይችል ብርሃን እስከዛሬ ዓለማችን አልተሰራላትም።   ስለዚህ ለዓይናችን የሚታየው የብርሃን ምንጭ ውሱንነት የዚህን ያህል ግልጽ ከሆነ በሰዎች ውስጣዊ ሕይወት ውስጥ ያለውን የማንነት ብርሃን ከጨለማ ማውጣት የሚችል ማነው?  

 ይህንን የሕይወት ጨለማ፤ በብርሃን መሙላት የሚቻለው ከሰው ልጆች መካከል አንድም ቅዱስና ጻድቅ የሆነ፤ ከሰማያት መላእክት መካከል  ማንም የለም።  ይህንን የሰው ልጆች ሕይወት በጨለማ ውስጥ ከመኖር ወደብርሃን መቀየር የግድ ያስፈለገው ጉድለቱን መሙላት የሚችል ባለመኖሩ ነበር። እሱም ጨለማ የማያሸንፈው፤ ብርሃኑን ለተቀበሉ ሁሉ በውስጣቸው ዘላለማዊ ብርሃን ማኖር የሚችል፤ የብርሃናት ሁሉ ጌታ ለመሆን  የተገባው  መገኘት ነበረበት። በጨለማ የሚሄድን ሕዝብ ወደብርሃን እንዲመጣና በሞት ጥላ ስር የወደቁ ሁሉ ዘላለማዊ ሕይወትን እንዲያገኙ፤ ነፍስና ሥጋን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር ሌላ ማን ይችላል? ፍጹም የሆነ መታመኛ እርሱ ብቻ ነውና! ዳዊት በዝማሬው « እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው» እንዳለው መዝ ፳፯፤፩ ይህንን የሕይወት ጨለማ በብርሃን መግለጥ የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነበር።

የሰው ልጆች ብርሃን የጨለማ  ዓለምን በሙላት መግለጥ የማይችል ከመሆኑም በላይ የነፍስን ጨለማ ደግሞ በብርሃን መሙላት ይችላል ተብሎ ስለማይታሰብ፤  መታመኛ ብርሃን የሆነው እግዚአብሔር፤ ከዘላለማዊ ብርሃኑ የወጣ ብርሃን፤ ከአምላክነቱ የወጣ አምላክ፤ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፤ ጨለማን በመግለጥ ብርሃንን  የሚሰጥ፤ በሞት ጥላ ስር ላሉ ሕይወትን የሚያድል፤ አንድያ ብርሃን ልጁን ለጨለማው ዓለም ላከ። ይህም ብርሃን ወደዓለም መጣ።
«በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ»  ዮሐ ፲፤፵፮ በማለት እውነተኛው ብርሃን እንደተናገረው።
ይህ ብርሃን ወደዓለም የመጣው ጨለማውን ዓለም በማይጠፋ ብርሃን ሊሞላ ነው። በሞት ጥላ ስር ላሉትም ሕይወትን ሊሰጥም ጭምር ነው።«በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው» ኢሳ 9፤2 እንዳለው።  የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ለዓለሙ ሁሉ ሆነ።
«ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል» ኢሳ ፱፤፮

Saturday, January 5, 2013

ምንኩስናና ጋብቻ!

በንጽህናና በድንግልና እየኖሩ የክርስቶስን የማዳን ሥራ ዘወትር እያሰቡ መኖር የእውነተኛ ክርስቲያን አንዱ ገጽታ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስም ይህንን ሲገልጸው  «ነገር ግን ያለ አሳብ ልትኖሩ እወዳለሁ። ያላገባው ጌታን እንዴት ደስ እንዲያሰኘው የጌታን ነገር ያስባልና» በማለት ሳያገቡ የክርስቶስን  መከራ ሞት እያሰቡና የሕይወታቸው መመሪያ አድርገው ለሚኖሩ ትልቅ ሥፍራ ሰጥቷቸው ይገኛል። (1ኛ ቆሮ 7፤32)

ይህ ማለት ግን ያገቡ ሰዎች ክርስቶስን ማገልገል አይችሉም  ማለት አይደለም። እንዲያውም  የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲሉ በትግልና በትልቅ ፈተና ስር ራሳቸውን ጥለው ሥጋቸውን በመጨቆን የሚያሰቃዩትን ሰዎች በድንግልና ያለመቀጠል ብቃታቸውን እንዲህ ሲል ከፈተናቸው እንዲላቀቁ በጌታ መንፈስ ይመክራቸዋል።
«ነገር ግን በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ» 1ኛ ቆሮ 7፤ 9
ክርስቲያን መኖር የሚገባው በተሰጠው ጸጋ እንጂ የሌለውንና ያልተጠራበትን ጸጋ በጥረቱ ለማግኘት በመፈለግ ባለመሆኑ አንዳንዶች በድንግልና እንኖራለን ብለው ሲያበቁ አዳማዊ ማንነታቸው ከሔዋን ጋር የሚያጣምር ሲሆንባቸውና ከቁጥጥር ውጪ በሆነ ምኞት ስር ሲጥላቸው የሥጋ ብልቶቻቸውን በቢላዋ ጎምደው እስከመጣል ይደርሳሉ። ይሁን እንጂ የሥጋ ብልታቸው መቆረጡ የልብ ምኞታቸውም ቆርጦ ሊያስቀረው የማይችል ስለሆነ ዘወትር እንደተቅበዘብዙ ይናራሉ።
«ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፥ አንዱ እንደዚህ ሁለተኛውም እንደዚያ»  1ኛ ቆሮ 7፤7

ሐዋርያው እንዳለው በድንግልና የጌታን ነገር ብቻ እያሰቡ መኖር የተሻለ መሆኑ አይካድም።  ይህ ጸጋ ለሁሉም የሚሰጥ ባለመሆኑ አንዳንዶች ጸጋቸውን ሳያውቁ ሰዎች በደነገጉት የድንግልና ሕግ ሥር ወድቀው የራሳቸውን የጽድቅ መንገድ ለማቆም እየታገሉና  እየተቃጠሉ መኖራቸው እርግጥ ነው። የሥጋ ብልቶቻቸውን ከመቁረጥ አንስቶ አስገድዶ እስከመድፈር ፤ እንስቶችን አባብሎ ከመዳራትና የስርቆሽ ዝሙት እስከመፈጸም መድረሳቸው  የሰውኛ ጥረት ውጤት ነው። አንዳንዶቹ የሥጋው ፈተና የመጨረሻው ጣሪያ ላይ ሲደርስባቸው ለክፉ መንፈስ ተጋልጠው ግብረ ሰዶም እስከመፈጸም ይደርሳሉ።
«የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም» ሮሜ 10፤3
 የተባለው  የእግዚአብሔርን ጽድቅ  ሳያውቁ ለመጽደቅና የራሳቸውን ጽድቅ ለማቆም  ሲታገሉ ከጽድቁ ሥራ ወጥተው የቀሩትን ይህ ቃለ እግዚአብሔር ተፈጽሞባቸዋል ማለት ይቻላል።

ከዓለማውያን ሰዎች ባልተሻለ መልኩ አባ እገሌ እገሊትን ደፍረው ተያዙ፤ አቡነ እገሌ ልጅ ወለዱ፤ እነአባ እገሌም  ግብረ ሰዶም ፈጸሙ እየተባለ ለሰሚ የሚቀፍ ዜና የሚሰማው እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲታገሉ ቆይተው የጭናቸው እሳት እየፈጀ መቆሚያና መቀመጫ ስለሚያሳጣቸው ነው። በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ በሰው ሚስት ላይ የተያዙ፤ አስገድደው የደፈሩ፤ አልፎ ተርፎም ግብረ ሰዶም ፈጽመው የተገኙ የብዙ አባዎች ጉዳይ አሳሳቢነት ለሲኖዶስ ጉባዔ መወያያ  ሆኖ  መቅረቡ አይዘነጋም።
ይህ እንግዲህ የምናውቃቸውንና የምንሰማቸውን አስጸያፊ ተግባራት ሳይጨምር መሆኑ ነው። ይህን ማንሳት በሥጋ ድካም መነኮሳት የሰሩትን ኃጢአት ለማውራት ሳይሆን የጋብቻን ክቡርነት የሚናገረውን የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የራሳቸውን ሕግ ለማቆም በመታገል መካከል በሚፈጠረው ሽንፈት የተነሳ ኢ-ሞራላዊ፤ ኢ- ምግባራዊና ጸረ ሃይማኖታዊ አድራጎት እየተስፋፋ በመገኘቱ ምክንያት እንደሆነ መታወቅ አለበት። የማይቻለውን ለመቻል ሲታገሉ ሽንፈታቸው መረን የለሽ ወደመሆን አድርሷቸው  የመገኘታቸው ነገር ግልጽ ወጥቶ በመነጋገር  አንድ  እልባት ላይ መድረስ ካልተቻለ ድርጊቱ ማቆሚያ የሌለው ሆኖ ይቀጥላል። ይህም በተጎጂው ላይ፤ በእምነቱ ተከታይ ውስጥ እና በማኅበረሰቡ ውስጥ አሉታዊ አስተሳሰብ እንዲኖር የማድረጉ ነገር ማብቂያ የለውም።

Friday, January 4, 2013

«የሦስት ልጆች አባት የሆነው አምላክ፤ የኢሬቻ በዓል»



12, 000 ሺህ ዓመት በፊት የኩሾች ፈርዖን፤ የሰማይና ጸሐይ   «አስራ» የተባለው አምላክ ሦስት ልጆችን ወለደ።  የመጀመሪያ ወንድ ልጁ «ሴቴ»፤ ሁለተኛው ልጁ ደግሞ «ኦራ» ሲባል የመጨረሻ ሴት ልጁ ደግሞ «አቴቴ» ወይም አድባር የምትባል ነበረች። ከጸሐይና ከሰማይ አምላክ «አስራ»  ልጆች መካከል ሴቴ የተባለው የመጀመሪያ ልጁ ታናሽ ወንድሙን ኦራን በድንጋይ ገደለው። በወንድሟ ሞት እጅግ ያዘነችው «አቴቴ»  ዐባይ ወንዝ ዳርቻ ባረፈው በሟች በወንድሟ መቃብር ላይ «ኦዳ» የተባለውን ዛፍ ለመታሰቢያነት ተከለች።
አቴቴ (አድባር) በመቀጠልም ያደረገችው ነገር በገዳይና በሟች ወንድሞቿ ቤተሰቦች መካከል በቀልና ጥላቻ እንዳይኖር ወደሰማይና ጸሐይ አምላክ አባቷ  ወደ አስራ በማመልከቷ የሰላም ምልክት እንዲሆን ከሰማያት ዝናብ ዘንቦ የተከለችውን «ኦዳ» የተባለውን በማለምለም ሰላም እንዲሰፍን አድርጎላታል።

ሟች ኦራም በኦዳ ዛፍ ልምላሜ የተነሳ በጸሐይና በሰማይ አምላክ አባቱ ሥልጣን ምክንያት ከሞት የተነሳና ያረገ ሲሆን ይኸው በኦዳ ዛፍ ስር ሟች ኦራን በማስታወስ የሚደረገው የሰላምና የምህረት አከባበር ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ ቀጥሏል። በቀደምት ኑቢያውያን የሚደረገው አከባበር  በጥንታውያን የአክሱም ስርወ መንግሥትም ዘመን የኦራ መታሰቢያን የሚያመለክት ቋሚ ድንጋዮችን በመትከል ሲታሰብ ኖሯል።