Showing posts with label ታሪክ. Show all posts
Showing posts with label ታሪክ. Show all posts

Thursday, August 28, 2014

«ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ የተሰወረ ሊሆን አይችልም» አምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ለአፄ ኃ/ሥላሴ በ1957 ዓ/ም ከጻፉት ደብዳቤ







ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ

አዲስ አበባ

ግርማዊ ሆይ፣

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት የሚታየውን ምሬትና ግፍ፣ የፍትሕም መጓደል ምክንያት በማድረግ ወደ አገሬ ለመግባት ያለኝን አሳብ ማቆየት ግድ እንደሆነብኝ ለግርማዊነትዎ መግለጥ አስፈላጊ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ይህ ሁኔታ የሚታረምበትን በኅብረት ለመሥራት ባንሞክር ታላቅ ብጥብጥ እንደሚያስከትልብን ከታሪክ መማር ካልቻልን፣ ከተከታዩ መቅሰፍት የምናመልጥበትና የምንከለልበት ሰው ሠራሽ ዘዴ ይገኝለታል ብሎ ራስን መደለል በሕልም ዓለም ውስጥ ለመኖር እንደ መፈተን ይቆጠራል፡፡
ከዚህም በቀር ለተተኪው ትውልድ አቋም ይሆናሉ ብለን ተከባክበን ልናሳድጋቸው አላፊነት ያለብንን ሕፃናትና ውለታ ትተው ለማለፍ የተደራጁትን ሽማግሎቻችንንም ደህና ዕረፍት እንዳያገኙ ከአገሪቱ በተፈጥሮ ያገኙትን ዕድል መንፈግ ያሰኛል፡፡ በዚህም ምክንያት በፈጸምነው ስህተት ታሪክ ምሕረት ሊያደርግልን በፍጹም አይችልም፡፡
ይህን የመሳሰለው ሁኔታ በብርቱ የሚያሳስበን መሆኑን ስንገልጥ ምንም እንኳ አንዳንድ ሰዎች ‹‹አንተ ምን አገባህ?›› በማለት በጉዳዩ ባለቤትነት ክፍያ ድርሻችንን ለማሳነስ ቢሞክሩም በኢትዮጵያዊነት ትክለኛ መብት ላይ አጥብበው ያሰመሩትን የወሰን ክልል አሜን ብሎ ለመቀበል ከቶ ስለሚያስቸግር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አላፊነቱን የማስወረድ ተግባር እንዳለበት አይካድም፡፡ እኔም ይህን ምክንያት አድርጌ በአሁኑ የመንግሥት አስተዳደር የደረሰውን ሕገ ወጥ አፈጻጸም ሁሉ ለማረምና ፍትሕን ለማደላደል የሚቻልበትን አሳብ በነፃ ለመግለጥ ስል እውጭ አገር መቆየትን መረጥሁ፡፡
በአሁኑ አያያዝ እንዲቀጥል የተተወ እንደሆነ በኢትዮጵያ የወገን መለያየትና የደም መፍሰስ እንደሚያሠጋ የመላው ኢትዮጵያውያን ግምት የወደቀበት ነው፡፡ ዋናው አላማ ይህ እልቂት የሚወገድበት መድኃኒቱ ምንድነው? ለተባለው ጥያቄ ለመመለስ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ መቸም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በሚመስለውና በሚያምንበት ረገድ መልሱን ለመስጠት ሞክሯል፡፡ አሁን የጐደለ መስሎ የሚታየው ከዙፋኑ በኩል የሚጠበቀው ይሁንታ ብቻ ነው፡፡ ነገሩን በመጠኑ ለማብራራት ያህል በሚከተሉት መስመሮች አስተያየቴን ለመግለጥ እሰነዝራለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዙፋኑ የሰጠው ልባዊ አክብሮት ዘላቂ ሆኖ በታሪካዊ ቅርስነት እንዲጠበቅ በቤተ መንግሥቱ በኩል አልታሰበበትም ለማለት ያስደፍራል፡፡ ባለፈው ‹‹መለኮታዊ መብት›› የተባለው የዘውድ ቴዎሪ የተሳሳተ መሆኑን ቢረዳውም፣ ሕዝቡ፣ ዘውዱን ታሪካዊ ሲምቦል ወይም ምሳሌ አድርጐ በክብር ሊያኖረው ሲፈቅድ ወደ መለኮታዊ መብት አስተያየት እንደገና እንዲመለስና ጣኦታዊ ስግደት እንዲያደርግ ማስገደድ፣ በእልህ ዘውዱን ለማስረገጥ ካልሆነ በቀር ለሌላ አያገለግልም፡፡
ጃንሆይ፣ ባለዘውድ፣ አስተዳዳሪ፣ ሕግ አውጭ፣ ዳኛ፣ ምስለኔ፣ ፖሊስ፣ ጭቃ ሹም ሆኜ ልሥራ ሲሉ፣ በ፳ኛው [20ኛው] ክፍለ ዘመን የሚገኝ ሕዝብ ይህን መብት አጠቃሎ በፈቃዱ ለዘውዱ ብቻ ይለቃል ማለት የማይታመን ነው፡፡ መቸም እየተደጋገመ የሚሰጠው ምክንያት ‹‹ሕዝቡ ኃላፊነትን ለመቀበል አልደረሰም›› የሚል መሆኑን በየጊዜው ሰምተናል፡፡ በውነቱ ከአፍሪካና ከኤሻ ሕዝብ መካከል አልደረሰም ተብሎ በኢትዮጵያ ሕዝብ መፍረድ ይገባልን? ደግሞስ ያለመድረስ ትርጓሜው ምንድነው? ምናልባት የማሰብ፣ የመምረጥ፣ የማመዛዘን፣ የመፍረድ ሴንስ አልተፈጠረለትም ማለት ነው? እንደዚህማ ከሆነ በ፫ሺሕ [በ3 ሺሕ] ዘመን ውስጥ ለዚህ ሕዝብ ጭንቅላት ሆኖ ያሰበለት፣ ዓይን ሆኖ ያየለት፣ ጆሮ ሆኖ የሰማለት የዛሬው ዘውድ ነው ማለት ነዋ! የሚፈተነው ይህን የመሰለ አስተያየት ለማቅረብ እንደሆነ ምሕረት የሌለው በደል ነው፡፡
ይልቁንስ ጃንሆይ የሕግ ጠባቂነትን ልብስ ተጐናጽፈው በዚህ መንፈስ ፍትሕን ከሚያጓድሉ፣ ሥልጣኑን ለሕዝብዎ ሰጥተው እርሱ ቢጨነቅበት እንደሚሻል ጥርጥር የለውም፡፡ ያለዚያ ከዚህ ማስታወሻዬ ውስጥ ለስማቸው እንኳ ሥፍራ ለመስጠት ዋጋ የሌላቸውና ሕሊና ቢሶች የሚያቀርቡልዎትን ‹‹ደህና ታይቷል›› እያሉ ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ እንደሚኖር የተሰወረ ሊሆን አይችልም፡፡
ይህን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ለማሻሻል የሚቻለው ጃንሆይ ዘውዱን ለራስዎ አስቀርተው አስተዳደሩን ለሕዝብ በመስጠትና የዴሞክራሲን መንፈስ በማስገባት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አስተያየት ለግርማዊነትዎ ሰውነት አለርጂ ሆኖ ቢያስቸግርም እንኳ ሌላ ማማረጫ ይኖራል፡፡ ይኸውም ዘውዱን ለልዑል አልጋ ወራሽ ማስተላለፍና አብዲኬት ማድረግ ነው፡፡ እርሳቸው ሕገ መንግሥት ጠብቀው ለመኖር ፈቃደኛ እንደሆኑ አያሌ ሰዎች ሲመሰክሩላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ያለዚያ ተከታዩ ትርምስና ደም መፋሰስ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡
ይህ አቤቱታ ከኔ ብቻ የቀረበ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍርኃት ታፍኖ ነጋም መሸም የሚያጕተመትመው ይህንኑ ነው፡፡ ድምፁን ከፍ ለማድረግ ግን አካባቢው አልፈቀደለትም፡፡ እኔም ከርሱ የተለየሁ መስዬ ታይቼ እንደሆነ ያጋጣሚ ነገር ብቻ ነው፡፡ አዲስ አበባ የታፈንኩትን ያህል እዚህ ከተነፈስሁ በኋላ ወደ አገሬ እንድመለስ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምናልባት ይህን አቤቱታ በመጻፌ እወነጀል ይሆናል፡፡ ግድ የለም፡፡ የሆነ ሆኖ በትእዛዝ ሳይሆን በነፃ የሚፈርድና በግልጽ የሚያስችል ፍርድ ቤት ተቋቁሞ ራሴን በሕጋዊ ጠበቃ አማካይነት ለመከላከል ጃንሆይ የሚፈቅዱልኝ ከሆነ በአገሬ ውስጥ ለመተንፈስ ዕድል ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡
ከዚህም ሁሉ ጋር ላስታውሰው የምፈቅደው፣ ይህን ማስታወሻ በመጻፌ ተቀይመው የእኔን ሕይወት ለማስጠፋት በሺሕ የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚወጣ ጥርጥር የለውም፡፡ አዝናለሁ፡፡ እኔ ለሞት የተዘጋጀሁ ስለሆነ ገንዘቡ ባይባክንና ለነፍሰ ገዳይ በመስጠት ፈንታ ለጦም አዳሪ ችግረኛ ቢውል የበለጠ እንደሚጠቅም ጥርጥር የለውም፡፡ በበኩሌ በአገራችን ሬሾሉሽን እንዲነሣና የማንም ደም እንዲፈስ አልፈቅድም፡፡ በዚህ ባቤቱታዬ የምወተውተውም ሰላማዊ ለውጥ እንዲሆንና የምንፈራው ደም መፋሰስ እንዳይደርስ ስለሆነ ጃንሆይ አንድ ቀን ‹‹ለካ ብርሃኑ ውነቱ ኖሯል!›› ሳይሉ አይቀርም፡፡
እንኳን ዘውድ የጫነ ሰውነትንና ማናቸውንም ሰው የማክበር ልምድ ስላለኝ፣ ይህ አቀራረቤ ክብርን ለመድፈር እንደማያስቆጥርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ውነት ሁል ጊዜ መራራ ናት፡፡ የመድኃኒት ፈውሱ እንጂ ምሬቱ አይታሰብም እንደተባለው ይህ በቅን ልቡና የቀረበው ውነተኛ አቤቱታዬ የግርማዊነትዎን ልብ አራርቶ ለኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት አንድ ፈውስ እንዲያመጣለት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ጃንሆይ! በኢትዮጵያ ወጣቱ ሽማግሌው ሴቱ ወንዱ የአኗኗሩ ዘዴ ውሉ ተዘባርቆበታል፡፡ አምላካችን፣ ፈጣሪያችን እያለ ቢደልልዎት አይመኑት፡፡ ጨንቆት ነው፡፡ ከልብ የሚመርቅዎት ግን ራስህን አስተዳድር ብለው አርነት ሲያወጡትና ወደ ዴሞክራሲ ሲመሩት ነው፡፡ ይህንንም ስል ሕዝብ በራሱ ሲተዳደር ችግር አይገጥመውም ማለቴ አይደለም፡፡ እስከዚህ አልሳሳትም፡፡ ነገር ግን ሌላው ለፍቶ ከሚጥለውና ላንሣህ ከሚለው፣ ራሱ ወድቆ በራሱ መነሣትን ይመርጣል፡፡ ይኽም በሥሕተት መማር ይባላል፡፡ ስለዚህ ጃንሆይም ተሳሳቱ እያለ ከሚከስዎት እርሱ ለሥሕተት እንዲጸጸትና እንዲማር ቢያደርጉት ትልቅ ውለታ ይቆጠራል፡፡
የዛሬው ሕገ መንግሥት ዴሞክራሲን ለማስገንባት የሚረዳ ካለመሆኑም በላይ ያንኑም ቅሉ አክብሮ ለመጠበቅ በአንቀጽ ፳፩ [21] እንደተመለከተው ከንጉሠ ነገሥቱ በመሐላ የተሰጠው ቃል ፈርሷል እያሉ አያሌ ኢትዮጵያውያን እንደሚያማርሩ ግርማዊነትዎ ሳይሰማው አይቀርም፡፡ መቸም ሕገ መንግሥቱን፣ ለመጣስ አንድ የጽሕፈት ሚኒስቴር ደብዳቤ ይበቃል፡፡ እንግዴህ ሕዝቡ ወይም ሹማምቱ ለንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ነኝ እያሉ ቢምሉም፣ ንጉሠ ነገሥቱ በበኩሉ መሐላውን የሚጠብቅ ካልሆነ በመሐላቸው ታስረው እንደማይኖሩ በልጅ ኢያሱ ጊዜ የደረሰው ሁኔታ ምሳሌ ሊሆን ይችል ይመስለኛል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የገጠመንን ፕሮብሌም እንደ መጠኑ ለመግለጥ ‹‹በግርማዊነታቸው መንግሥት ያገኘሁት ኤክስፔሪያንስ›› የሚለው መጽሐፌ በሙሉ ታትሞ እስከወጣ ድረስ ፲፪ኛውን [12ኛውን] ምዕራፍ ከዚህ ጋር አያይዤ ለግርማዊነትዎ በትህትና አቀርባለሁ፡፡

                          ዋሽንግተን ግንቦት ፳፭/፶፯ [ግንቦት 25/57]
                                ከታላቅ አክብሮታዊ ፍርሐት ጋራ
                                          ብርሃኑ ድንቄ


Friday, August 22, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

 (ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ

ስለ አምላክ  ሕግና ስለ ሰው ሕግ

እግዚአብሔር  የገዛ  ሕዝቡን  እንዲያስቷቸው  ስለምን  ዋሾ  ሰዎችን  ይተዋል  ብዬ  አሰብኩ፡፡  እግዚአብሔር  ግን  ለሁሉም
ለእያንዳንዱ  እውነትንና  ሐሰትን  እንዲያውቅ  ልቦና  ሰጥቶናል፡፡  እውነት  ወይም  ሐሰት እንደፈቃዱ  የሚመርጥበት
መምረጫም ሰጠው፡፡ እውነትን ብንወድ ለፍጥረት ሁሉ አስፈላጊና ተገቢ የሆነውን እርሱም እንድናይበት እግዚአብሔር
በሰጠን ልቦናችን ውስጥ እንፈልጋት፡፡ ሰው ሁሉ ዋሾ ነውና እውነትንም በሰዎች ትምህርት አታገኟትም፡፡ ከእውነት ይልቅ
ሐሰትን ብንመርጥ ስለዚህ እኛ በስህተታችን እንጠፋለን እንጂ ለፍጥረት ሁሉ የተሰራው የፈጣሪ ሥርዓትና ሕግ አይጠፋም፡፡
እግዚአብሔር ማንንም በሠራው ሥራ ይጠብቀዋል፡፡ ከሰው ሥራ ግን የእግዚአብሔር ሥራ ይጸናል፡፡ የሰው ሥራ ሊያጠፋው
አይችልም።  ስለዚህም  ከጋብቻ  ይልቅ  ምንኩስናን  ይበልጣል  ብለው  የሚያምኑ  እነርሱ  በፈጣሪ  ሥራ  ጽናት  ወደ  ጋብቻ
ይሳባሉ፡፡ ፆም ነፍስን እንደሚያፀድቅ የሚያምኑ እነርሱ ደግሞ ረሃብ በበዛባቸው  ጊዜ ይበላሉ፡፡ ገንዘቡን የተወ ፍፁም
እንዲሆን  የሚያምኑ በገንዘብ  ለሚያገኙት   ጥቅም  ወደ  ገንዘብ  መፈለግ  ይሳባሉ፡፡  ብዙዎች  የሀገራችን  መነኩሴዎችም
እንደሚደርጉት ከተዉት በኋላ እንደገና ይፈልጉታል፡፡ እንደዚሁ ዋሾዎች ሁላቸው የተፈጥሮን ሥራ ሊያፈርሱ ይፈልጋሉ፡፡
ነገር ግን ደካማነታቸውን ያሳያሉ እንጂ አይችሉም፡፡ ፈጣሪም ይስቅባቸዋል፡፡ የፍጥረት ጌታም በላያቸው ይሳለቅባቸዋል፡፡
እግዚአብሔር የእግዚአብሔርን ፍርድ ማድረግ ያውቃልና ኃጥአንም በእጁ ሥራ ወጥመድ  ተጠመደ፡፡ ስለዚህም የጋብቻን
ሥርዓት የሚያስነውር መነኩሴ በክፉ በሽታና ፍጥረቱ ባልሆነ በሌላ የሴት አበሳ በዝሙት ተጽዕኖ ይጠመዳል፡፡ ገንዘባቸውን
የሚንቁ  ገንዘብ  እንዲያገኙ  በሀብታሞችና  በነገሥታት  ዘንድ  ግብዞች  ይሆናሉ፡፡  ለእግዚአብሔር  ብለው  ዘመዶቻቸውንም
በሽምግልናቸውና በችግራቸውም ረዳት ባጡ ጊዜ የተዉ በነሱ ሽምግልና ጊዜ ሰውና እግዚአብሔርን ወደ ማማት፤ መሳደብ
ይደርሳሉ፡፡  እንደዚሁም  የፈጣሪን  ሥርዓት   የሚያፈርሱ  ሁሉ  በእጃቸው  በሰሩት  ወጥመድ  ይወድቃሉ፡፡  እንደገናም
እግዚአብሔር  ክፋትን፤ ስህተትን  በሰው  መካከል  ይተዋል፡፡  ነፍሶቻችን  በዚህ  ዓለም  የእግዚአብሔር ጥበብ  የፈጠረውን
የፈተና ቀን ይኖራሉ፡፡

ጠቢቡ ሰለሞን

"እግዚአብሔር  ፃድቃንን  ፈተናቸው፡፡  ወርቅ  በእሳት  እንደሚፈተን  ይፈትናቸዋል፡፡  ለእርሱ  የተዘጋጁ  ሆነውም
አግኝቷቸዋልና፡፡ እንደተወደደ ዕጣን መዐዛም ይቀበላቸዋል" ይላል፡፡
ከሞታችን በኋላም ቢሆን ወደፈጣሪያችን በገባን ጊዜ እግዚአብሔር በእውነትና በትልቅ በጥበብ ከሠራው ሁሉ እውነትና ቅን
የሆነውን መንገድ ሁሉ እንለያለን፡፡ ነፍሳችንም ከሥጋዊ ሞታችን በኋላ እንደምትድን ይታወቃል፡፡ በዚህ ዓለም ውዴታችን
አይፈፀምምና የሌላቸው ይፈልጋሉ፤ ያላቸው ባላቸው ላይ እንደገና ሊጨምሩ ይፈልጋሉ፡፡ሰው በዚህ ዓለም ያለው ሁሉ
እንኳን  ቢኖረው  እንደገና  ይወዳል  እንጅ  አይጠግብም፡፡  ይህም  የፍጥረታችን  ጠባይ  ለሚመጣው  ንብረት  እንጂ  ለዚህ
ዓለም ንብረት ብቻ እንዳልተፈጠርን ያመለክታል፡፡ በዚያውም የፈጣሪያቸውን ፈቃድ የፈፀሙ ነፍሳት ፍፁም ይጠግባሉ
እንጂ ከእንግዲህ ሌላ አይወዱም፡፡ አለዚያ ግን የሰው ፍጥረት አስፈላጊውን ሁሉ አላገኝምና ጎዶሎ በሆነ ነበር፡፡ እንደገናም
ነፍሳችን  እግዚአብሔርን  ማሠብ  ትችላለችና  በሃሳቧም  ታየዋለች፡፡  እንደገናም  ለዘላለም  መኖር  ማሰብ  ትችላለች፡፡
እግዚአብሔርም ይህን ማሰብ በከንቱ አልሰጣትም፡፡ ነገር ግን እንደሰጣት ልታስብና  እንድታገኝም ሰጣት፡፡ ደግሞ በዚህ
ዓለም ፅድቅ ሁሉ አይፈፀምም፡፡ ክፉ ሰዎች ከዚህ ዓለም መልካም ይጠግባሉ፡፡ ደጋጎች ይራባሉ፡፡ የሚደሰት ክፉ አለ፣
የሚያዝን ደግ አለ፣ የሚደሰት ዐመፀኛ አለ፣ የሚያለቅስ ፃድቅም አለ፣ ስለዚህም  ከሞታችን በኋላ ለሁሉ እንደየምግባሩ
የሚከፍለው  ሌላ  ኑሮና  ፍፁም  ፅድቅ  ያስፈልጋል፡፡  በብርሃን  ልቦናችን  ተገለፀላቸው፡፡  የፈጣሪን  ፈቃድ  የፈፀሙና
በተፈጥሯቸውም ፀባያዊ ህጉን የጠበቁ ዋጋቸው ይከፈላቸዋል፡፡ የተፈጥሮን ሕግ ከመረመርን የተረጋገጠ መሆኑን ልቦናችን
በግልፅ  ይነግረናል፡፡  ነገር  ግን ሰዎች  ሊመረምሩ  አልፈለጉምና  የፈጣሪያቸውን  ፈቃድ በእውነት  ከመፈለግ  የሰዎችን  ቃል
ማመን መረጡ፡፡

 ስለ ባህሪያዊ ዕውቀት

የፈጣሪ ፈቃድ ግን ለእግዚአብሔር ለፈጣሪህ ስገድ ፣ ሰውንም ሁሉ እንደነፍስህ አፍቅር ይላል፡፡ ይህ በልቦናችን እውነት
መሆኑ  ይታወቃል፡፡  እንደገናም  በልቦናችን  እውነትነቱ  የሚታወቅ  ሌላ  እውነት  "ሊያደርጉብህ  የማትፈልገውን  በሰው
አታድርግ፡፡  ላንተ  ሊያደርጉልህ  የምትፈልገውን  አድርግላቸው"  ይላል፡፡  የሰንበትን  ማክበር  የሚለው  ካልሆነ  በቀር  ዐሥሩ
የኦሪት  ትዕዛዛት  የፈጣሪ  ናቸው፡፡  ሰንበትን  ለማክበር  ግን  ልቦናችን  ዝም  ይላል፡፡ ልንገድልና  ልንሰርቅ፣  ልንዋሽና  የሰው
ሚስት  ልንሰርቅ  ይህን  የሚመስለውን  ልናደርግ  እንደማይገባን  ልቦናችን  ይነግረናል፡፡ እንዲሁ  ስድስቱ  የወንጌል  ቃላት
የፈጣሪ  ፈቃዶች  ናቸው፡፡  እኛ  ይህን  የምህረት  ሥራ  ሊያደርጉልን  እንፈልጋለን፡፡  በሚቻለን  ለሌሎች  ልናደርግላቸው
ይገባናል፡፡ ደግሞም በዚህ ዓለም ሕይወታችን፣ ንብረታችን እንድንጠብቅ የፈጣሪ ፈቃድ ነው፡፡ ከፈጣሪ ፈቃድ ወጥተን
በዚህ ሕይወት እንኖራለን፡፡ በተቀደሰ ፈቃዱ ካልሆነ በቀር ልንተወው አይገባንም፡፡እርሱ ፈጣሪያችን ለሁሉ ልቦናና ችሎታ
ስለሰጠ ኑሯችንን በዕውቀትና በሥራ እንድናሳምረው ይፈቅድልናል፡፡ ይህ ካልሆነ በቀር የሕይወታችን ፍላጎት አይገኝም፡፡
እንዲሁ  አንዱ  ካንዷ  ጋር  መጋባትና  ልጆች  ማሳደግን  ፈቅዷል፡፡  ደግሞም  ከልቦናችን  ጋር  የሚስማማ  ለህይወታችንም
ለሁሉም  የሰው  ልጆች  ኑሮ  የሚያስፈልጉ  ሌሎች  ብዙ  ሥራዎች  አሉና  የፈጣሪ  ፈቃድም  እንዲሁ  ስለሆነ  ልንጠብቀው
ይገባናል፡፡ እግዚያብሔር ፍፁማን አድርጎ እንዳልፈጠረን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ለመፈፀማችን የተዘጋጀን አዋቂዎችና በዚህም
ዓለም  እስካለን  ድረስ  እንድንፈፅምና  ፈጣሪያችን  በጥበቡ  ላዘጋጀልን  ዋጋ  የተዘጋጀን እንድንሆን  አድርጎ  ፈጠረን፡፡  በዚህ
ምድር ፍፁማንና ብፁዓን አድርጎ ሊፈጥረን ለእግዚአብሔር ይቻለው ነበር፡፡ ነገር ግን ለመፈፀማችን የምንዘጋጅ አድርጎ
ፈጠረን እንጅ እንዲሁ ሊፈጥረን አልፈቀደም፡፡ ከሞታችን በኋላ ፈጣሪያችን ለሚሰጠን ዋጋ የተዘጋጀን ፍፁማን እንድንሆን
በዚህ የፈተና ዓለም መካከል አኖረን፡፡ በዚህ ዓለም እስካለንም ወደ እርሱ እስኪወስደን ድረስ እየታገስን ፈቃዱን እየፈፀምን
ፈጣሪያችን  ልናመሰግነው  ይገባል፡፡  የፈተናችንንም  ጊዜያቶች  እንዲያቀልልን  ባለማወቃችን  ሠራነውን  የእብደት  አበሳ
እንዲተውልን የተፈጥሮ ሕግጋትን አውቀን እንድንጠብቃቸው ልቦና እንዲሰጠን ወደቸርነቱ እንለምን፡፡ ፀሎት ደግሞ ላዋቂ
ነፍስ  አስፈላጊ  ነውና  ዘወትር  ልንፀልይ  ይገባናል፡፡  አዋቂ  ነፍስ  ሁሉን  የሚያውቅና ሁሉን  የሚጠብቅ  ሁሉን  የሚገዛ
እግዚአብሔር እንዳለ ታውቃለች፡፡ ወደ እርሱ እንድትፀልይም ከእርሱ መልካም እንድትለምን፣ ከክፉ እንድትድንና ሁሉን
ወደሚችል እጅ እንድትማፀን ወደ እርሱ ትሳባለች፡፡ እግዚአብሔር ምሁርና ትልቅ ነው፡፡ የሚሳነውም የለም፡፡ ከበታቹ
ያለውን ያያል፣ ሁሉንም ይይዛል፣ ሁሉን ያውቃል ፣ ሁሉን ይመራል፣ ሁሉን ያስተምራል አባታችን ፈጣሪያችን ጠባቂያችን
ነው፡፡  የነፍሳችን  ዋጋ  ቸርና  ይቅር  ባይ  ችግራችንን  ሁሉ  የሚያውቅ  ነው፡፡  ለሕይወት  እንጂ  ለጥፋት  አልፈጠረንም፡፡
በትዕግስታችን ይደሰታል፡

Friday, August 1, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

(ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ) ክፍል ሁለት

የሰው  ፍጥረት  ታካችና  ደካማ  መሰለኝ፡፡ ሰው  ግን ፍቅርን  ቢወዳትና  በጣም  ቢያፈቅራት  የተሸሸገውንም  ፍጥረትን  ቢያውቅ ይወዳል፡፡ ይህም  ነገር  እጅግ  ጥልቅ  ነውና  በትልቅ  ድካምና  ትዕግስት  ካልሆነ  በስተቀር  አይገኝም፡፡ ጠቢቡ ሰለሞን፡ “ከፀሐይ  በታች  ስለተደረገው  ሁሉ  ጥበብን  ለመፈለግና  ለመመርመር  ልቤን  ሰጠሁ፡፡  እግዚአብሔር  ለሰው  ልጆች  እንዲደክሙበት የሰጣቸውን  ክፉ  ስራ  አየሁ”ይላል፡፡

   ስለዚህ  ሰዎች  ሊመረምሩት  አይፈልጉም፡፡  ሳይመረምሩ  ከአባቶቻቸው  የሰሙትን  ማመን  ይመርጣሉ፡፡  ነገር  ግን እግዚአብሔር  ሰውን  የምግባሩ  ጌታ  ክፉ  ወይም  መልካም  የፈለገውን  እንዲሆን  ፈጠረው፡፡  ሰውም  ክፉና  ዋሾ  መሆንን  ቢመርጥ ለክፋቱ የሚገባውን  ቅጣት  እስኪያገኝ  ድረስ  ይችላል፡፡ ነገር  ግን  ሰው ሥጋዊ  ነውና  ለሥጋው  የሚመቸውን  ይወዳል፡፡ ክፉ  ይሁን  መልካም  ለስጋው  ፍላጎት የሚያገኝበትን  መንገድ  ሁሉ  ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር  ሰው  የፈለገውን  እንዲሆን  ለመምረጥ  መብት  ሰጠው  እንጂ  ለክፋት  አልፈጠረውም፡፡ ስለዚህ  መምረጥ  ክፉ  ቢሆን  ለቅጣት  መልካም  ቢሆን  ደግሞ  የመልካምነት  ዋጋ  ለመቀበል  የተዘጋጀ  እንዲሆን  እድል  ሰጠው፡፡

  በሕዝብ  ዘንድ  ክብርና  ገንዘብ  ለማግኝት  የሚፈልግ  ዋሾ  ሰው  ነው፡፡  ዋሾ  ሰው  ይህን  በሐሰተኛ  መንገድ  ሲያገኝ  እዉነት አስመስሎ ሀሰት  ይናገራል፡፡ ሊመረምሩ  የማይፈልጉ  ሰዎች  እውነት  ይመስላቸውና  በእርሱ  በጽኑ  ሃይማኖት  ያምናሉ፡፡ እስኪ  ሕዝባችን  በስንት  ውሸት  ያምናል?  በጽኑ  ሃይማኖት  ያምናል፡፡  በሃሳበ  ከዋክብትና  በሌላም  አስማት፣  አጋንንት  በመሳብና በመርጨት፣ አስማት በማድረግ፣ በጥንቆላ  ሁሉ  ያምናሉ፡፡ ይህንን  ሁሉ  መርምረው  እውነቱን  አግኝተው  አያምኑም፡፡ ነገር  ግን  ከአባቶቻቸው  ሰምተው ያምናሉ፡፡ እነዚያስ  የፊተኞቹ  ገንዘብና  ክብር ለማግኝት  ካልሆነ በቀር ስለምን  ዋሹ?  እንዲሁ  ህዝብን  ሊገዙ  የሚፈልጉ  ሁሉ  እውነት  እንነግራቸኋለን  እግዚአብሔር  ወደናንተ  ላከን  ይሏቸዋል፡፡  ሕዝቡም  ያምናሉ፡፡
ከነርሱም  በኋላ  የመጡት  እነርሱ  ሳይመረምሩ  የተቀበሏትን  የአባቶቻቸውን  እምነት  አልመረመሩም፡፡  ከዚያ  ይልቅ  ለእውነትና ለሃይማኖታቸው  ማስረጃ  ታሪክን፣ ምልክቶችን ፣ ተዓምራትን  እየጨመሩ እውነት  አስመስለው  አጸኑት፡፡  በነገሩ ሁሉ እግዚአብሔርን  ስም ጨመሩ።  እግዚአብሔርንም የሐሰኞች ተካፋይና  የሐሰት  ምስክር  አደረጉት፡፡

  ጥልቅ   ምርመራ  ስለ  ሙሴና  መሐመድ  ሕግጋት

 ለሚመረምር  ግን  እውነት  ቶሎ  ይገለፃል፡፡  ፈጣሪ  በሰው  ልብ  ያስገባውን  ንጹህ  ልቦና  የፍጥረት  ሕግጋትና  ስርዓትን  ተመልክቶ የሚመረምር  እርሱ  እውነትን  ያገኛል፡፡ ሙሴ  ፈቃዱንና  ሕጉን  ልነግራችሁ  ከእግዚአብሔር  ዘንድ  ተልኬ  መጣሁ  ይላል፡፡ ከሆነ ታዲያ «ሴት በወር አበባ ወቅት የረከሰች ናት» ለምን ይላል? የሙሴ  መጽሐፍ  ከፍጥረት  ሕግ  ሥርዓትና  ከፈጣሪ  ጥበብ  ጋር  አይስማማም፡፡  ከውስጡ  የተሳሳተ  ጥበብ  ይገኛል፡፡ ለሚመረምር  ግን  እውነት  አይመስለውም፡፡  በፈጣሪ  ፈቃድና  በፍጥረት  ህግ  የሰው  ልጅ  እንዳይጠፋ  ልጆችን  ለመውለድ  ወንድና  ሴት  በፍትወተ  ሥጋ  እንዲገናኙ  ታዟል፡፡  ይህም  ግንኙነት  እግዚአብሔር  ለሰው  በሕገ  ተፈጥሮ  የሰጠው  ነው፡፡ እግዚአብሔርም  የእጁን  ሥራ  አያረክስም፡፡ እግዚአብሔር  ዘንድ  እርኩሰት  ሊገኝ  አይችልም፡፡  ፈጣሪ የፈጠረውን መልሶ አያረክሰውም እላለሁ። 

  እንደገናም  የክርስቲያን  ሕግ  ለማስረጃዋ  ተአምራቶች ተገኝተዋልና  ከእግዚአብሔር  ናት  ይላሉ፡፡  ነገር  ግን  የወሲብ  ሥርዓት  የተፈጥሮ  ሥርዓት  እንደሆነ  ምንኩስና  ግን  ልጆች ከመውለድ  ከልክሎ  የሰውን  ፍጥረት  አጥፍቶ  የፈጣሪን  ጥበብ  የሚያጠፋ  እነደሆነ  ልቦናችን  ይነግረናልና  ያስረዳናል፡፡ የክርስቲያን  ሕግ  ምንኩስና  ከወሲብ  ይበልጣል  ብትል  ሐሰት  ትናገራለችና  ከእግዚአብሔር  አይደለችም፡፡  የፈጣሪን  ሕግ  የሚያፈርስ  እንዴት  ከጥበብ በለጠ ?  ወይስ  የእግዚአብሔርን  ስራ  የሰው  ምስክር ሊያስተካክለው ይቻለዋልን ? ሰዎች ግን ሳይመረምሩ ምንኩስና ከጋብቻ ትበልጣለች ይላሉ። ዘርን የሰጠ ፈጣሪ ዘር አያስፈልግም አይልም። ቀጣፊዎች በእግዚአብሔር ስም  እውነት አስመሰሉት እንጂ።

እንዲሁም  መሐመድ  የማዛችሁ  ከእግዚአብሔር  የተቀበልኩትን  ነው  ይላል፡፡  መሐመድን  መቀበል  የሚያስረዱ  የተዓምራት  ፀሐፊዎች  አልጠፉምና  ከሱም  አመኑ፡፡ እኛ  ግን  የመሐመድ  ትምህርት  ከእግዚአብሔር  ሊሆን  እንደማይችል  እናውቃለን፡፡ የሚወለዱ  ሰዎች  ወንድና  ሴት  ቁጥራቸው  ትክክል  ነው፡፡ በአንድ  ሰፊ  ቦታ  የሚኖሩ  ወንድ  ሴት ብንቆጥር  ለእያንዳንዱ  ወንድ አንዲት  ሴት  ትገኛለች  እንጂ  ለአንድ  ወንድ  ስምንት  ወይም  ዐሥር  ሴቶች  አይገኙም፡፡ የተፈጥሮ  ህግም  አንዱ  ከአንዲት  ጋር እንዲጋቡ  አዟል፡፡ አንድ  ወንድ  ዐሥር  ሴት  ቢያገባ  ግን  ዘጠኝ  ወንዶች  ሴት  የሌላቸው  ይቀራሉ፡፡ ይህም  የፈጣሪን  ስርዓትና  ሕገ ተፈጥሮን  የጋብቻንም  ጥቅም  ያጠፋል፡፡ አንድ  ወንድ ብዙ ሴቶች ሊያገባ  ይገባዋል  ብሎ  በእግዚአብሔር  ስም  ያስተማረ  መሐመድ  ግን  ትክክል  ነው አልልም፡፡ ከእግዚአብሔር  ዘንድ  አልተላከም፡፡  ጥቂት  ስለጋብቻ  ሕግ  መረመርኩ  ፡፡ ከመጀመሪያም  ለአዳም አንድ ሴት ከመፍጠር ይልቅ ዐሥር ሴት ያልፈጠረለት ለምንድነው? ይህን የፈጣሪ ሕግ  ሳይመረምሩ የመሐመድን  ሕግ መቀበል ስህተት ነው። ከእግዚአብሔር እንደተገኘ  ብመረምርም  በህገ  ኦሪትና  በክርስትናና  በእስልምና  ሕግ  ፈጣሪ  በልቦናችን  ከሚገልጽልን  እውነት  እና  እምነት ጋር የማይስማማ ብዙ ነገር አለ  አልኩ።

    ፈጣሪ  ለሰው  ልጅ  ክፉና  መልካም  የሚለይበት  ልቦና  ሰጥቶታል፡፡  «በብርሃንህ  ብርሃንን  እናያለን»  እንደተባለውም  የሚገባውን  የማይገባውን  ሊያውቅ፣  እውነትን  ከሐሰት እንዲለይ ነው፡፡ ስለዚህ የልቦናችን  ብርሃን  እንደሚገባ  በእርሱ  ብናይበት  ሊታይልን አይችልም፡፡ ፈጣሪያችን ይሄን ብርሃን  የሰጠን  በርሱ  እንድንድን  ነው እንጂ  እንድንጠፋ  አይደለም። የልቦናችን  ብርሃን  የሚያሳየን  ሁሉም  ከእውነት  ምንጭ  ነው፡፡ ሰዎች  ከሐሰት  ምንጭ  ነው  ቢሉን ግን  ሁሉን  የሰራ  ፈጣሪ  ቅን እንደሆነ  ልቦናችን  ያስረዳናል፡፡ ፈጣሪ  በመልካም ጥበቡ  ከሴት  ልጅ  ማህጸን  በየወሩ  ደም  እንዲፈስ አዟል፡፡  ሙሴና  ክርስቲያኖች  ግን  ይህን የፈጣሪ  ጥበብ  እርኩስ  አደረጉት፡፡
እንደገና  ሙሴ  እንዲህ  ያለችው  ሴት ከተቀመጠችበት የተቀመጠውንም፤ የተገናኛትንም  ያረክሳል፡፡  ይህም  የሙሴ  ህግ  የሴትን  ኑሮ  በሙሉና  ጋብቻዋን  ከባድ አድርጎታል፡፡ የመራባትንም  ህግ  አጥፍቷል፡፡ ልጆችንም  ከማሳደግ  ከልክሎ  ፍቅርንም  ያፈርሳል፡፡ ስለዚህ ይህ  የሙሴ  ሕግ  ሴትን  ከፈጠረ  ሊሆን  አይችልም  እላለሁ፡፡ «ሞተውን ሰው በድን የነካ ሁለመናውን ባያጠራ የእግዚአብሔርን ማደሪያ ያረክሳል ያ ሰው ከእስራኤል ዘንድ ተለይቶ ይጠፋል » የምትለው የሙሴ ሕግ ሞትን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር አይደለችም። እንደገናም  የሞቱትን  ወንድሞቻችንን  ልንቀብራቸው  ተገቢ መሆኑን ልቦናችን  ይነግረናል፡፡ በድኖቻቸውም  በሙሴ  ጥበብ  ካልሆነ  በስተቀር  ከመሬት  የተፈጠርንበት  ወደ መሬትም  ልንገባበት  በፈጣሪያችን  ጥበብ  እርኩሳን  አይደሉም፡፡ ነገር  ግን  ለፍጥረት  ሁሉ  እንደሚገባ  በትልቅ  ጥበብ  የሰራ  እግዚአብሔር ሥርዓቱን  አያረክሳውም፡፡ ሰው  ግን  የሐሰትን  ቃል  እንዲያከብር  ብሎ  ሊያረክሰው ይፈልጋል፡፡

  እንደዚሁም  እግዚአብሔር  የከንቱ  ነገር  አያዝም፡፡  «ጥረህ ግረህ በላብህ ወዝ ብላ» ያለው አምላክ ይህን  ብላ፣ ይህን  አትብላ፣ ዛሬ ብላ፣ ነገ  አትብላ  አይልም፡፡ ለክርስቲያኖች  እንደሚመስላቸውና  የጾም  ሕግጋት  እንደሚጠብቁ  ሥጋን  ዛሬ  ብላ፤  ነገ  አትብላ  አይልም፡፡  ለክርስቲያኖች እንደሚመስላቸውና  የጾም  ሕግጋት  እንደሚጠብቁ  ሥጋን  ዛሬ ብላ ነገ ግን  አትብላ  አይልም፡፡  እስላሞችንም  እግዚአብሔር  ለሊት  ብሉ  ቀን  አትብሉ  ብሎ  ይሄንና  የመሳሰሉትን  አይላቸውም፡፡ የፍጥረታችንን  ጤና  የማያውክ ነገር ሁሉ  ልንበላ  እንደሰለጠንን  ልቦናችን  ያስተምረናል።  አንድ  የመብል ቀን፤ አንድ  የጾም  ቀን ግን  ጤናን  ያውካል፡፡ የጾም ህግ መብላትን  ለሰው  ሕይወት  ከፈጠረና  ልንበላቸው  ከፈቀደ  ፈጣሪ የወጣ  አይደለም፡፡ በልተን ልናመሰግነው  እንጂ  በረከቱን  ልናርም አይገባንም፡፡ ሕገ  ፆም  የሥጋን  ፍትወት ለመግደል  የተሰራ  ነው  የሚሉም  ቢኖሩ  ፍትወተ  ሥጋ  ወንድ  ወደ ሴት  ሊሳብ  ሴትም ወደ  ወንድ  ልትሳብ  የፈጣሪ ጥበብ  ነውና  እርሱ  ፈጣሪ  በሰራው  በታወቀ  ማጥፋት  አይገባም  እላለሁ፡፡  ፈጣሪያችን  ይህን ፍትወት ለሰው፤  ለእንስሳት  ሁሉ  በከንቱ  አልሰጠም፡፡ ነገር ግን  ለዚህ  ዓለም  ሕይወትና  ለፍጥረት  የተሰራለት  መንገድ  ሁሉ  መሠረቱ  ሆኖ እንዲቆይ  ይህ  ፍትወት  ለሰው  ልጅ  ተሰጠ፡፡ አስፈላጊያችንን ልንበላ  ይገባናል፡፡ በእሁድ  ቀንና  በበዓል  ቀናት  በአስፈላጊው  ልክ  የበላ  እንዳልበደለ  እንዲሁ  በአርብ  ቀንና  ከፋሲካ  በፊት  ባሉት  ቀናት  ለክቶ  የሚበላ  አልበደለም፡፡  እግዚአብሔር  ሰውን  በሁሉ  ቀንና  በሁሉ  ወራት  ካስፈላጊ  ምግብ  ጋር  አስተካክሎ  ፈጥሮታል፡፡  አይሁድ፣  ክርስቲያንና  እስላም  ግን  የፆምን  ሕግ  ባወጡ  ጊዜ ይህን  የእግዚአብሔር  ሥራ  ልብ  አላሉም፡፡ እግዚአብሔር  ፆምን  ሰራልን፤  እንዳንበላም  ከለከለን  እያሉ ይዋሻሉ፡፡ እግዚአብሔር ፈጣሪያችን  ነው፡፡ ግን  የምንበላውን  ምግባችንን   እንድንመገበው ሰጠን  እንጂ  እርሱን  ልናርም  አይደለም፡፡  በሚያስተውል ልቡናችን  ለክተን  መኖር የኛ ፈንታ ነው።

 ስለ  ሃይማኖቶች    መለያየት

 ሌላ ትልቅ  ምርመራ  አለ፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በእግዚአብሔር  ዘንድ  ትክክል  ናቸው፡፡ እርሱም  አንድ  ሕዝብ ለሕይወት፤  አንድ  ሕዝብ ለሞት፤  አንድም  ለምህረት፤  አንድም  ለኩነኔ  አልፈጠረም፡፡  ይህም  አድሎ  በስራው  ሁሉ  ጻድቅ  በሆነ  በእግዚአብሔር  ዘንድ እንደማይገኝ  ልቦናችን  ያስተምረናል፡፡ ሙሴ  ግን  አይሁድን  ለብቻቸው  እንዲያስተምራቸው  ተላከ፡፡ ለሌሎች  ሕዝቦች  ፍርዱ አልተነገረም፡፡  እግዚአብሔር  ስለምን  ለአንድ  ሕዝብ  ፍርድ  ሲነግር  ለሌላው  አልነገረም፡፡  በዚህም  ጊዜ  ክርስቲያኖች  የእግዚአብሔር  ትምህርት  ከኛ  ጋር  ካልሆነ  በስተቀር  አይገኝም  ይላሉ፡፡ አይሁድና  እስላም  የህንድ  ሰዎችም  ሌሎችም  ሁሉ እንደነሱ  ይላሉ፡፡ እንዲሁ  ደግሞ  ክርስቲያኖች  እርስ  በርሳቸው  አይስማሙም፡፡ ካቶሊኮች  እግዚአብሔር  ከኛ  ጋር  ነው  ያለው እንጂ ከናንተ  ጋር አይደለም  ይሉናል፡፡ እኛም  እንዲሁ  እንላቸዋለን፡፡ ሰዎች  እንደምንሰማቸው  ግን  የእግዚአብሔር  ትምህርት  እጅግ  ጥቂቶች  ወደ ሆኑት  እንጂ  ለብዙዎቹ  አልደረሰም፡፡  ከእነዚህ  ሁሉ  ደግሞ  ወደ  ማን  እንደደረሰ  አናውቅም፡፡ እግዚአብሔር  ከፈቀደ ቃሉን  በሰው  ዘንድ  ማጽናት ተስኖት  ነውን?  ሆኖም  ግን  የእግዚአብሔር  ጥበብ  በመልካም  ምክር  ይህ  ነገር  እውነት እንዳይመስላቸው  ሰዎች  በሐሰት  ሊስማሙ  አልተወም፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በአንድ  ነገር  በተስማሙ  ጊዜ  ይህ  ነገር እውነት ይመስላል፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በሃይማኖታቸው  ምንም  እንደማይስማሙ  በሃሳብም  ሊስማሙ  አይችሉም፡፡
    እስኪ  እናስብ  ሰዎች  ሁሉ  ሁሉን  የፈጠረ  እግዚአብሔር  አለ  በማለታቸው  ስለምን  ይስማማሉ?  ፍጡር  ያለ  ፈጣሪ  ሊገኝ  እንደማይችል፤ ስለዚህም  ፈጣሪ  እንዳለ እውነት  ነውና  ነው፡፡ ይህ  የምናየው  ሁሉ  ፍጡር  እንደሆነ  የሰው  ሁሉ   ልቦና  ያውቃል ፡፡ ሰዎች ሁሉ በዚህ  ይስማማሉ፡፡  ነገር  ግን  ሰዎች  ያስተማሩትን  ሃይማኖት  በመረመርን  ጊዜ  በውስጡ  ሐሰት  ከእውነት  ጋር  ተቀላቅሎበታል፡፡  ስለዚህ  እርስ  በርሱ አይስማማም፡፡ ሰዎች  እርስ በርሳቸው  አንዱ  ይህ  እውነት  ነው ሲል፤ ሁለተኛው  አይደለም፤  ሐሰት  ነው  ሲል  ይጣላሉ፡፡ ሁሉም  የእግዚአብሔርን  ቃል  የሰው  ቃል  እያደረጉ  ይዋሻሉ፡፡  እንደገናም  የሰው  ሃይማኖት  ከእግዚአብሔር  ብትሆን  ክፉዎችን   ክፉ  እንዲያደርጉ  እያስፈራራች  መልካም  እንዳያደርጉ ትፈቅድላቸው  ነበር፡፡ ደጎችንም በትዕግስታቸው ታጸናቸው ነበር፡፡

  ለኔም እንዲህ ያለው  ሃይማኖት  ባሏ  ሳያውቅ  በምንዝርና  የወለደች ሴትን ትመስለኛለች፡፡ ባሏ ግን  ስለመሰለው  በሕፃኑ  ይደሰታል፡፡ እናቲቱንም ይወዳታል፡፡ በዝሙት  እንደወለደችው  ባወቀ  ጊዜ  ግን  ያዝናል፡፡ ሚስቱንም  ልጅዋንም  ያባርራል፡፡ እንዲሁም  እኔም  ሀይማኖቴን አመንዝራና  ዋሾ  መሆኑዋን  ካወኩ  በኋላ  ስለርሷ  በዝሙት  ስለተወለዱ   ልጆቿ አዘንኩ ፡፡ እነሱ  በጠብ፣ በማሳደድ፣ በመማታት፣ በማሰር፣ በመግደል  ወደዚህ  ዋሻ  ያባረሩኝ  ናቸው፡፡  ከውሸታቸው ጋር ስላልተባበርኩ ጠሉኝ። ነገር  ግን  የክርስቲያን  ሃይማኖት  ሀሰት  ናት እንዳልል  በዘመነ  ወንጌል  እንደተሰራ  ክፉ  አልሆነችም፡፡  የምህረትን  ሥራ  በሙሉ  እርስ   በርስ መፋቀርን ታዛለች፡፡  እነሱ ግን ፍቅርን ፈጽሞ አያውቋትም። በዚህ ዘመን  ግን  የሀገራችን  ሰዎች  የወንጌልን  ፍቅር  ወደ ጠብና  ኃይል  ወደ  ምድራዊ  መርዝ  ለወጡት፡፡  ሃይማኖታቸውን  ከመሰረቱ  ዐመጻ  እየሰሩ  ከንቱ  ያስተምራሉ፡፡  በሐሰትም  ክርስቲያኖች ይባላሉ፡፡

Wednesday, July 30, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

 ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ (ክፍል አንድ)

እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሁሉ ለነፍስ ያደረጋችሁትን መናገር እጀምራለሁና ኑ ስሙኝ፡ ሁሉን በፈጠረ መጀመሪያና መጨረሻ በሆነ ሁሉን በያዘና የሕይወትና የጥበብ ሁሉ ምንጭ በሆነ እግዚአብሔር በሰጠኝ ረዥም እድሜየ ትንሽ እጽፋለሁ፡፡ ነፍሴ በእግዚአብሔር ዘንድ የተከበረች ትሁን ጆሮዎችም ሰምተው ይደሰቱ፡፡ እኔ እግዚአብሔርን ፈለኩት መለሰልኝ፡፡ አሁንም እናንተ ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችሁማል፤ ፊታችሁንም አያሳፍርም፡፡ እግዚአብሔርን ከኔ ጋር ከፍ ከፍ አድርጉት አብረን ስሙን እናንሳ፡፡

  እኔ የተወለድኩት በአክሱም በካህናት ሀገር ነው፡፡ ነገር ግን እኔ በአክሱም አውራጃ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ በነገሠ በሦስተኛው ዓመት በ1592 ዓ/ም ከ አንድ ገበሬ ቤተሰብ ተወለድሁ፡፡ በክርስትና ጥምቀት ዘርዓ ያዕቆብ ተብየ ተሰየምኩ፡፡ ሰዎች ግን ወርቄ ይሉኛል፡፡ ካደኩ በኋላ ትምህርት እንድማር አባቴ ወደ ትምህርት ቤት ላከኝ፡፡ ዳዊትም ከደገምኩ በኋላ መምህሬ አባቴን ይህ ህፃን ልጅህ ልቦናው የበራ በትምህርት ታጋሽ ነውና ወደ ትምህርት ቤት ብትልከው ሊቅና መምህር ይሆናል አለው፡፡ አባቴም ይህን ሰምቶ ዜማ እንድማር ላከኝ፡፡ ሆኖም ድምጼ ሸካራ ሆኖ አላምር አለኝ፡፡ በዚህ ምክንያት ጓደኞቼ መሳቂያና መዘባበቻ አደረጉኝ፡፡ እዚያም ሦስት ወር ያህል ቆየሁ፡፡ ስላልተሳካልኝ ከልቤ አዘንኩ፡፡ ተነስቼ ሰዋስውና ቅኔ ለመማር ወደ ሌላ አስተማሪ ሄድኩ፡፡ ከጓደኞቼ ፈጥኜ እንድማርም እግዚአብሔር ጥበቡን ሰጠኝ፡፡ ይህም የመጀመሪያ ሃዘኔን አስረሳኝ ፡፡ በጣም ተደሰትኩ፡፡ እዛም አራት አመት ቆየሁ፡፡ በነዚያ ቀኖች እግዚአብሔር ከሞት አዳነኝ፡፡ ከጓደኞቼ ጋር ስጫወት ወደገደል ወደቅሁ፡፡ እግዚአብሔር በታምራቱ አዳነኝ እንጅ ፈጽሞ ልድን አልችልም ነበር፡፡ ከዳንኩ በኋላ ገደሉን በረዥም ገመድ ለካሁት፡፡ ዐሥራ ሦስት ሜትር ሆኖ ተገኝ፡፡ እኔም ድኜ ያዳነኝን እግዚአብሔርን እያመሰገንኩ ወደ መምህሬ ቤት ሄድኩ፡፡ ከዚያም ተነስቼ የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜ ለመማር ሄድኩ፡፡

 በዚያም ዐሥር ዓመት ቆየሁ፡፡ መጻሕፍትን ፈረንጆች እንዴት እንደሚተረጉሟቸው፤ የኛም ምሁራን እንዴት እንደሚተረጉሟቸው ተማረኩ፡፡ ትርጓሜያቸው ግን ከኔ ልቡና ጋር የሚስማማ አልነበረም፡፡ ሆኖም ይህን ስሜቴን፤ ሃሳቤን ለማንም ሳልገልጽ በልቤ ይዠው ቆየሁ፡፡ ከዚያም ወደሃገሬ ወደ አክሱም ተመለስኩ፡፡ በአክሱም ለአራት አመት መጽሐፍ አስተማረኩ፡፡
ይህ ዘመን ክፉ ዘመን ሆነ፡፡ አፄ ሱስንዮስ በነገሠ በ 19ኛው ዓመት የፈረንጆች ተወላጅ አቡነ አልፎንዝ መጣ፡፡ ከ2 ዓመት በኋላም ንጉሡ የፈረንጆቹን ሃይማኖት ስለተቀበለ በኢትዮጵያ ትልቅ ስደት ሆነ፡፡ ይህን ሃይማኖት ያልተቀበለ በሙሉ ግን እጣው ስደት ሆነ፡፡

 አፄ ሱስንዮስ፣ አልፎንዝና ጠላቴ ወልደ ዮሐንስ

እኔ በሃገሬ መጻሕፍት ሳስተምር ብዙዎቹ ጓደኞቼ ጠሉኝ፡፡ በዚህ ዘመን የባልንጀራ ፍቅር ጠፍቶ ነበርና ቅናት ያዛቸው፡፡ በትምህርትና ጓደኛን በመውደድ ከነርሱ እበልጣለሁ፡፡ ከሁሉ ሰው፤ ከፈረንጆቹና ከግብጻውያን ጋር እስማማለሁ፡፡
መጻሕፍትን ሳስተምርና ስተረጉም እንዲህ እንዲህ ይላሉ፤ ግብጻዊያኖች ደግሞ (ኦርቶዶክሶች) እንዲህ እንዲህ ይላሉ እላለሁ፡፡ እኛም ብንመረምር ይህን ሁሉ እናውቃለን እላለሁ እንጅ ይህ መልካም ነው፤ ይህ ደግሞ ክፉ ነው አልልም፡፡ ግብጾቹ የፈረንጅ፣ ፈረንጆቹ ደግሞ የግብጻውያኖቹ እመስላቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ሁሉም ጠሉኝ፡፡ ብዙ ጊዜም ወደንጉሡ ከሰሱኝ፡፡ እግዚአብሔር ግን አዳነኝ፡፡ ከዚህም በኋላ ከአክሱም ካህናት አንድ ወልደ ዮሐንስ የተባለ ጠላቴ፤ የንጉሥ ወዳጅ ስለነበረ፣ የነገሥታት ፍቅር በሽንገላ ምላስ ስለሚያገኝ ወደ ንጉሡ ሄደ፡፡ ወደ ንጉሡም ገብቶ እንደዚህ አለው ፡፡
“ይህ ሰው ህዝብን ያሳስታል፡፡ ስለሃይማኖታችን እንነሳና ንጉሡን እንግደለው፣ ፈረንጆቹንም እናባራቸው ይላል” እያለ ይሄንና ይሄን በመሰለ ውሸት ከሰሰኝ፡፡ እኔም ይህን አውቄ ገና ለገና ይገድለኛል ብዬ ፈርቼ የነበረኝን ሶስት ወቄት ወርቅና የምጸልይበትን መዝሙረ ዳዊት ይዠ በሌሊት ሸሸሁ፡፡ ወዴት እንደምሄድ ለማንም አልተናገርኩም፡፡ ወደተከዜ በረሀ ገባሁ፡፡ በነጋታውም ራበኝ፡፡

  ከሀብታሞች ገበሬዎች እንጀራ ለመለመን እየፈራሁ ወጣሁ፡፡ ሰጡኝና በልቼ እየሮጥኩ ሄድኩ፡፡ እንዲህ እያልኩ ብዙ ቀን ቆየሁ፣ በኋላ ወደ ሽዋ ግድም ስሄድ ሰው የሌለበት በርሃ አገኘሁ፡፡ ከገደሉ በታች መልካም ዋሻ ነበርና ሰው ሳያየኝ በዚህ ዋሻ እኖራለሁ ብየ ወሰንኩ፡፡ ሱስንዮስ እስኪሞትም ድረስ በዚያ 2 ዓመት ቆየሁ፡፡ አንዳንዴ ወደገበያ እየወጣሁ ወይም ወደ አምሐራ ሀገር እሄድ ነበር፡፡ ለአምሐራ ሰዎች የምበላው እንዲሰጡኝ የምለምን ባህታዊ መነኩሴ እመስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከየት እንደምወጣና ወዴት እንደምገባ አያውቁም፡፡ ከዋሻየ ለብቻየ በሆንኩ ጊዜም በመንግሥተ ሰማያት የምኖር መሰለኝ፡፡ ቁጥር የሌለው ክፋታቸውን አውቄ ከሰዎች ጋር መኖር ጠላሁ፡፡ ሌሊት መጥተው የበርሃ አራዊት እንዳይበሉኝም በድንጋይና በአሽዋ አጥር ዋሻየን አጠርኩ፡፡
እሚፈልጉኝ ሰዎች ወደኔ ቢመጡ የማመልጥበት መውጫም አዘጋጀሁ፡፡ እዚያ በሰላም ኖርኩ፡፡ በሚሰማኝ በእግዚአብሔር ተስፋ አድርጌ በሙሉ ልቤ በመዝሙረ ዳዊት ጸለይኩ፡፡

ስለአምላክ መኖርና የሐይማኖት መለያየት

ከጸሎት በኋላም ስራ ስለሌለኝ ሁልጊዜ ስለሰዎች ክፋትና ሰዎች በእርሱ ስም ሲበድሉ፣ ወንድሞቻቸውን ጓደኞቻቸውን ሲያባርሩ እና ሲገድሉ ዝም በማለቱ ስለፈጣሪ ጥበብ አስብ ነበር፡፡ በዚህም ጊዜ ፈረንጆቹ አየሉ፡፡ ነገር ግን ያገሩ ሰዎችም ከነሱ የባሰ ክፋት ሰሩ እንጅ ፈረንጆቹ ብቻቸውን አልነበረም የከፉት፡፡ የካቶሊክ ሃይማኖት የተቀበሉት፤ ኦርቶዶክሶች የመንበረ ጴጥሮስን እውነተኛዋን ሃይማኖት ክደዋልና የእግዚአብሔር ጠላቶች ናቸው አሉ፡፡ ስለዚህም አሳደዱአቸው፡፡
ኦርቶዶክሶችም ለሃይማኖታቸው እንዲሁ አደረጉ፡፡ እግዚአብሔር የሰዎች ጠባቂ ከሆነ ለምን ፍጥረታቸው እንዲህ ከፋ ብየ አሰብኩ፡፡ በአርያም የሚያውቅ አለን ? ኧረ እግዚአብሔርስ ያውቃልን ? በቅዱስ ስሙ ሲበድሉና ሲረክሱ የሚያውቅ ከሆነ እንዴት የሰዎችን ክፋት ዝም ይላል? አልኩ፡፡
ምንም ልብ አላደረኩም ብዙ አሰብኩ፡፡ የፈጠርከኝ ፈጣሪየ ሆይ አዋቂ አድርገኝ፤ የተደበቀውን ጥበብህን ንገረኝ ብየ ጸለይኩ፡፡ ለሞት እንዳይተኙ አይኖችህን አብራቸው፤ እጆችህ አደረጉኝና ሰሩኝ፡፡ ትዕዛዝህን እንድማር ልብ ስጠኝ፡፡ ለኔ ግን እግሮቼ በተፍገመገሙ፤ ተረከዞቼም በተንሸራተቱ ነበር ፡፡ ይህም በፊቴ ስላለው ድካም ነው፡፡ ይህንን እና ይህን የመሰለ ፀሎት አደርግ ነበር፡፡
 አንድ ቀን እኔ ወደ ማን ነው የምፀልየው? አልኩ፡፡ በእውነት የሚሰማኝ እግዚአብሔር አለን? በዚህም አሳብ በጣም አዝኜ እንዲህ አልኩ፡፡ዳዊት እንዳለ እንዴት ምንኛ ልቤን አጸደኳት፡፡ ኋላም አሰብኩ።ይህ ዳዊት እንዲህ የሚለው «ጆሮን የተከለ አይሰማምን ?»  በእውነት እንድሰማበት ጆሮ የሰጠኝ ማነው? አዋቂስ አድርጎ የፈጠረኝ ማነው? በዚህስ ዓለም እኔ እንደምን መጣሁ? ከዓለም በፊት ብኖር የሕይወቴ መጀመሪያና የእውቀቴ መጀመሪያን ባወቅሁ፡፡ እኔ በገዛ እጄ ተፈጠርኩን ? ነገር ግን እኔ በተፈጠርኩ ጊዜ አልኖርኩም፡፡ አባት እናቴ ፈጠሩኝ ብልም እንደገና ወላጆችና የወላጆችን ወላጅ፣ወላጅ የሌላቸው በሌላ መንገድ ወደዚህ ዓለም የመጡትን እንደኛ ያልተወለዱትን የፊተኞቹ ድረስ ፈጣሪያቸውን እፈልጋለሁ፡፡ እነርሱም ቢወለዱ የፈጠራቸው አንድ ህላዌ አለ ከማለት በቀር የጥንት መወለጃቸውን አላውቅም፡፡ ያለና በሁሉም የሚኖር የሁሉ ጌታ ሁሉን የያዘ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው ዓመቱ እማይቆጠር እማይለወጥ ያልተፈጠረ ፈጣሪ አለ አልኩ፡፡ ፈጣሪስ አለ፡፡ ፈጣሪ ባይኖር ፍጥረት ባልተገኘ አልኩ፡፡ እኛ ብንኖር ፍጡራን እንጅ ፈጣሪዎች አይደለንም፡፡ የፈጠረ ፈጣሪ አለ እንል ዘንድ ይገባናል፡፡ ይህም የፈጠረን ፈጣሪ አዋቂና ተናጋሪ ካልሆነ በቀር ከዕውቀቱ በተረፈ አዋቆዎችና ተናጋሪዎች አድርጎ ፈጥሮናል፡፡ ሁሉን ፈጥሯል ሁሉን ይይዛልና እርሱ ሁሉን ያውቃል፡፡ ፈጣሪየ ወደ እርሱ ስጸልይ ይሰማኛል ብየ ሳስብ ትልቅ ደስታ ተደሰትኩ፡፡ በትልቅ ተስፋም እየጸለይኩ ፈጣሪየን በሙሉ ልቤ ወደድኩት፡፡ ጌታየ ሆይ፤ አንተ ሃሳቤን ሁሉ ከሩቅ ታውቃለህ አልኩት፡፡ አንተ የመጀመሪያየ ነህ፡፡ የመጨረሻየን ሁሉን አወቅህ፡፡ መንገዴንም ሁሉ አንተ አስቀድመህ አወቅህ፡፡ ስለዚህም ከሩቅ ታውቃለህ ይሉሃል፡፡ እኔ ሳልፈጠር ሀሳቤን ያውቃልና ፈጣሪየ ሆይ እውቀትን ስጠኝ አልኩ፡፡

ስለ ሃይማኖት ምርመራና ፀሎት

በኋላም ይህ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጻፈ ሁሉ እውነት ይሆን? ብየ አሰብኩ፡፡ በጣም አላወቅሁምና የተማሩና ተመራማሪ ሰዎች እውነቱን እንዲነግሩኝ ሄጄ ልጠይቃቸው ብዬ ብዙ አሰብኩ፣ እንደገናም ሰዎች በየልባቸው ያለውን ካልሆነ በቀር ሌላ ምን ይመልሱልኛል ብየ አሰብኩ፡፡ ሰው ሁሉ የኔ ሃይማኖት እውነተኛ ናት ይላል፡፡ በሌላ ሃይማኖት የሚያምኑ ሐሰተኞች
የእግዚአብሔር ጠላቶች ናቸው፡፡ ዛሬም ቢሆን ፈረንጆች ሃይማኖታችን መልካም ናት፣ ሃይማኖታችሁ ግን መጥፎ ናት ይሉናል፡፡ እኛም መልሰን እንዲዚህ አይደለም፤ የናንተ ሃይማኖት መጥፎ፤ የኛ ሃይማኖት ግን መልካም ናት እንላቸዋለን፡፡
እንደገናም የእስልምና፣ የአይሁድ አማኞችን ብንጠይቃቸው እንዲሁ ይሉናል፡፡ በዚህም ክርክር ፈራጅ ማን ይሆናል? ሰዎች ሁሉ እርስ በእርሳቸው ወቃሾችና ተወቃሾች ሆነዋል፡፡ አንድ እንኳን ከሰው ልጅ የሚፈርድ አይገኝም፡፡ እኔ መጀመሪያ ስለብዙ ሃይማኖቶች ጉዳይ አንድ የፈረንጅ መምህር ጠየኩ፡፡ እሱ ግን ሁሉን እንደራሱ ሃይማኖት አድርጎ ፈታው፡፡ ኋላም አንድ ትልቅ የኢትዮጵያ መምህር ጠየቅሁ ፡፡ እርሱም ሁሉን እንደ ሃይማኖቱ አድርጎ ተረጎመው፡፡ እስልምና እና አይሁድንም ብንጠይቅ እንዲሁ እንደ ሃይማኖታቸው ይተረጉማሉ፡፡ ታዲያ እውነት የሚፈርድ የት አገኛለሁ? የኔ ሃይማኖት ለኔ ትክክል እንደሚመስለኝ እንዲሁ ለሌላውም ሃይማኖቱ እውነት ይመስለዋል፡፡ ነገር ግን ጽድቅ አንዲት ብቻ ናት፡፡

 እንደዚህ እያልኩ አሰብኩ፡፡ ጠቢብና የእውነተኞችም እውነተኛ እኔን የፈጠርክ ሆይ አዋቂ አድርገህ የፈጠርከኝ ሆይ፤ ዳዊት ሰው ሁሉ ዋሾ ነው ካለው በስተቀር በሰው ዘንድ ጥበብና እውነት አይገኝምና አንተ አዋቂ አድርገኝ ብዬ ጸለይኩ፡፡ ሰዎች በዚህ ትልቅ ነገር ነፍሳቸውን ለማጥፋት ስለምን ይዋሻሉ? ብየ አሰብኩ፡፡ የሚዋሹም መሰለኝ፡፡ የሚያወቁ እየመሰላቸው ምንም አያውቁምና የሚያውቁ ይመስላቸዋል፡፡ ስለዚህ እውነትን ለማግኝት ብለው አይመረምሩም፡፡ ዳዊት እንዳለው ልባችን እንደወተት ረካ፡፡ ከአባቶቻቸው በሰሙት ልባቸው ረክቷል፡፡ እውነት ወይም ሀሰት ሊሆን ይችላል ብለው አልመረመሩም፡፡ እኔም ጌታ ሆይ ፍርድህን እንዳውቅ ያሳመንከኝ ይገባኛል አልኩ፡፡
አንተ በእውነት ቅጣኝ፣ በምህረትህም ገስጸኝ፡፡ አንተ አዋቂ አድርገህ የፈጠርከኝ ጥበበኛ አድርገኝ እንጅ የዋሾ መምህራንና የኃጢአት ቅባት እራሴን አልቀባም፡፡
እኔ አዋቂ ብሆን ምን አውቃለሁ ብየ አሰብኩ፡፡ ከፍጥረት ሁሉ የሚልቅ ፈጣሪ እንዳለ አውቃለሁ፡፡ ከታላቅነቱ የተረፈ ታላላቅን ፈጥሯልና፡፡ ሁሉንም የሚያውቅ ነውና፡፡ ከአዋቂነቱ በተረፈ አዋቂዎች አድርጎ ፈጥሮናልና፡፡ ለርሱ ልንሰግድለት ይገባል፡፡ እርሱ የሁሉ ጌታና ሁሉንም የያዘ ነውና ወደርሱ በጸለይን ጊዜ ይሰማናል፡፡ እግዚአብሔር አዋቂ አድርጎ የፈጠረኝ በከንቱ አይደለም፡፡ እንዲህ አድርጎ የፈጠረኝ እንድፈልገውና እርሱ በጥበቡ በፈጠረኝ መንገድ እንዳውቀው እስካለሁም ድረስ እንዳመሰግነው ነው ብየ አሰብኩ፡፡ ሰዎች ሁሉ ሀሰት ካልሆነ በስተቀር ስለምን እውነት አይናገሩም ብየ አሰብኩ፡፡

Monday, March 3, 2014

ግብፅ ስትደነፋ መለስ ዜናዊ ናፈቁኝ!! When I hear Egypt's Rhetoric over Nile, I miss Meles Zenawi


ፎቶ፦ ናሳ ሳተላይት    
  ጽሁፍ በአማኑኤል ዊንታ
በሌሊት የተነሱ የግብፅ የሳተላይት ፎቶዎችን በአትኩሮት ብታዩ ፍንትው ያለና የማያወላዳ እውነትን ይጋፈጣሉ ከታላቁ የአስዋን ግድብ በካይሮ አድርጐ እስከ ሜዲትራንያን ባህር ድረስ 84 ሚሊዮን የሚጠጋው አጠቃላይ የግብፅ ህዝብ በጣም በሚገርም ሁኔታ የአባይን ዳር ለዳር ተጠግቶ ይኖራል፡፡ ይህም ግብፅን በአለም ላይ ካሉ ሀገራት ሁሉ እራሷን ሙሉ በሙሉ ለጥፋት አደጋ ያመቻቸች ብቸኛ ሐገር ያሰኛታል፡፡
ታላቁ የአስዋን ግድብ ያቋተው ውሃ የናስር ሐይቅ የሚባለውን ሰው ሰራሽ ሐይቅ ለመፍጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ የናስር ሰው ሰራሽ ሐይቅ 547 ኪ.ሜ ርዝመት 35 ኪ.ሜ ስፋትና 110 ሜ ከፍታ አለው፡፡ ይህ የተፈጥሮ ሐይቅ ቢመታና ውሃው ቢፈስ በሰዓታት ውስጥ ግብፅ ያለምንም ጥርጥር ከጫፍ እስከ ጫፍ ተጥለቅልቃ ትጠፋለች ይህ ሳይንሳዊ ሐቅ ነው፡፡

በቅርቡ የካይሮና የአዲስ አበባ መሪዎች የተለያዩ የተካረሩ ቃላቶችን ሲወራወሩ አይተናል ሰምተናል፡፡ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ውስጤን ቆፍጠን! በሸቅ! ነደድ! የሚያደርግ ነገር ወረረኝ፡፡ አይ ወይኔ ይሄኔ ነበር የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ በኖሩልን ብዬ  የተመኘሁት በደንብ አርገው ግብፅን ያቀምሱልኝ ነበራ፡፡ አሐ እሳቸው እንዲሁ ነብሳቸውን ይማርና እንኳን የግብፅን የአሜሪካና የአውሮፓ ድንፋታንም ከቁብ አይቆጥሩት እኔ በግሌ የእሳቸው ፓርቲ አባል አይደለሁም ፓለቲካም አልወድም አባቴ ይሙት! ጀግና ናቸው እረ በጣም አዋቂም ናቸው፡፡ ናፈቁኝ ከምር ናፈቁኝ፡፡ ምን ዋጋ አለው “የማንም ልቅምቅም የሰው ልክ አያውቅም!” አለ ያገሬ ሰው፡፡ ግብፆች ደነፋብን የግብፅ ኘሬዝዳንት ሙሐመድ ሙሪሲ ለህዝባቸው የሚከተለውን ድስኩር አሰሙ፡፡
“በእውነቱ እኔ ጦርነት ይጀመር እያልኩ አይደለም ግን በእርግጠኝነት ቃል እገባላችኋለው የግብፅ የውሃ ፍላጐት በማንም በምንም አደጋ ላይ አይወድቅም! አሉ ቀጠሉናም
“የግብፅ የውሃ ፍላጐትና ደህንነት መቸም ቢሆን ጥያቄ ውስጥ አይገባም በማንም አይሞከርም እንደ ግብፅ ኘሬዝዳንትነቴ እማረጋግጥላችሁ ነገር ቢኖር ሁሉም አማራጮች ክፍት ናቸው ይተገበራሉም!” አሉ
ከዛም ቀጠሉና ተረት ተረት የሚመስለውን ግን እርር ድብን ያረገኝን ቀጣዮቹን ሁለት ንግግሮች ቀጠሉ “ግብፅ የአባይ ስጦታ ናት ካልን አባይም የግብፅ ስጦታ ነው!” በማለት ከድሮ ጀምሮ ሲባል የነበረውን አባባል በቴሌቪዥን ሕዝባቸውን ሆ አስባሉበት ቀጠሉናም ደነፉ፡፡
“የግብፃውያን ሕይወት ከአባይ ጋር ብቻ የተያያዘ ነው…. እንደ አንድ ታላቅ ህዝብ ደግሞ አንዲት ጠብታ ውሃ ከአባይ ላይ ሳትመጣ ብትቀር አማራጫችን አንድና አንድ ነው ደማችን ይፈሳል!” አሉና ፈገግ ጀነን ደንደን አሉ፡፡
እኔም እርር ድብን! ቆጣ! በስጨት! አልኩና ለማን ልተንፍሰው? ኮከቤ ደግሞ ታውረስ በሬው ነውና ለመዋጋትም፣ ይለይልን ኑ ውጡ! ለማለትም አማረኝ ግን አንድ ኢትዮጵያዊ ግለሰብ መሆኔ ሁሉንም አገደኝ ግን ከምር አንድ ግብፃዊ መንገድ ዳር ላይ ባገኝ ያን ቀን በስሱ በቴስታ ነበር አፍንጫውን ብየ ደም እያሉ ኘሬዝዳንት ሙርሲ የደነፉበትን ደም የማየው በእውነት ምን ችግር አለው በስሱ አንድ ቴስታ ባቀምሰው? ምንም፡፡
ኘሬዝዳንት ሙርሲም ሲያጠቃልሉ “ግብፅ ሁሉንም የአባይ ተፋሰስ ሐገራት ኢትዮጵያንም ጨምሮ በወንዙ ላይ ለሚሰሩት የልማት ኘሮጀክቶች ተቃውሞ የላትም፡፡ ነገር ግን የልማት ኘሮጀክቶች የግብፅን ህጋዊም ሆነ ታሪካዊ መብቶች የሚነኩም የሚያስተጓጉሉም መሆን የለባቸውም፡፡” አሉና ፖለቲካቸውን ቦተለኩ፡፡
የግብፅ የተለያዩ ፖለቲከኞችም የሙርሲን አባባል እያነሱ እያወደሱ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ብቅ እያሉ እንዳውም ታላቁን የኢትዮጵያ የሕዳሴ ግድብ ከፍ ሳይል ባጭር እንቅጨው የጦር እርምጃ እንውሰድበት እያሉ ቀባጠሩ፡፡
ታዲያ መለስ ዜናዊ ቢናፍቁኝ ትፈርዱብኛላችሁ? አሃ ሌሎችንማ አየናቸው እኛ ላይ ሲሏችሁ ነው እንጂ የምትደነፉት ጠላት ሲመጣማ ጭጭ ምጭጭ፡፡ ባይሆን በኢቲቪ ወጣ ብላችሁ “ግብፅ ብትደነፋም በኩርኩም ነው የምንላት!” ምናምን እያላችሁ አታፅናኑንም? ድንቄም ፖለቲከኛ! እኔ በእውነት በጣም ተሰምቶኛል ወይ ደግሞ አንዳንድ ጊዜ ፖለቲከኞቻችን መድረሱን ለጀግኖች ለመከላከያ ሰራዊታችን ለቀቅ አድርጉላቸውና በሚዲያችን ዛቻና ድንፋታ እንስማበትና ወንዱ! አንበሳው! እንባባል፡
እውነቱን እንነጋገር ከተባለ ይህንን ሁሉ ችግር የፈጠረው የእኛ የፖለቲከኞች ችግርና ጥበብ ማነስ ነው ግድቡ የኢህአዴግ ብቻ ይመስል ለግንቦት 20 በአል አከባበር ታላቅ ድምቀት ብላችሁ የልደት ኬክ ይመስል አባይን ቦታውን አስቀይሳችሁ በሌላ አቅጣጫ እንዲፈስ አደረጋችሁ ወይም በሳይንሳዊ አገላለፁ (Diversion) ተሰራ፡፡ ግን ይሄ መሆን ያለበት የግብፅም ሆነ ሌሎች የአባይ ተፋሰስ ሐገራት ቅድሚያ አውቀውትና ተስማምተው መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም ግድቡ ሲጀመርም እኮ አብዛኞቹ ሐገራት ተስማምተዋል፡፡ መመካከር ማንን ይጐዳል? ነው ወይስ አባይን ለፖለቲካ ቅስቀሳ ጥቅም ብቻ ነው የገነባችሁት? አባይ የዚህ ወይም የዛ ፓርቲ አባል ነው የሚል ፓርቲ ካለ ከግብፅ ጐን መሰለፍ ይችላል፡፡ አባይ በተለይም ጥቁር አባይ የኢትዮጵያዊያን በሙሉ ነው፡፡ ለዛም ነው ህዝቡ በጉልበቱም በገንዘቡም ሆ ብሎ እየገነባው ያለው የሚገነባውም! እና እንደ ምክር ወይ እንደተግሳፅ ፖለቲከኞቻችን እዩትና እባካችሁ ለሐገራችን የሚጠቅመውን አድርጉ አዋቂና ጥበበኞችም ሁኑ አንብቡ ተማሩ ተመራመሩ፡፡ መለስ የናፈቁኝ አንባቢ መሪና ተመራማሪ ስለነበሩ ነው፡፡ እንደውም አሁን አሁን በየቀበሌው በየቢሮው የመለስን ራዕይ እናሳካለን እያላችሁ በለጠፋችሁት ወረቀት ስር ይህንንም የምንተገብረው እንደሳቸው በማንበብና በመፃፍ በመማርና በመመራመር ነው በሉበት፡፡ በእውነት እውነቴን ነው፡፡ እኔ ይህንን ጽሑፍ ለመፃፍ ያነሳሳኝ የፖለቲካ ፓርቲ አባል ወይም ስልጣን ፈላጊ ሆኘ አይደለም ሐገሬን አንድ ግብፃዊ ስነ-ህዝቡ በአደባባይ ሲዘልፋት ሰምቸ ተናድጀና ተቆጥቸ እንጅ አንድ ተራ ሰላማዊ ዜጋ ነኝ ግን እንደኔ ይህንን ስሜት የሚጋሩ ብዙ ኢትዮጵያዊያን አይጠፉምና አስቡበት፡፡
ከዚህ ቀጥሎ ግብፅ በ2011 ላይ ደርሶባት ስለነበረው የእርስ በእርስ ግጭትና የግብፅን የአሁን ሁኔታ በመላው አለም ላይ ተሰራጭቶ የተለያዩ ኤክስፐርቶች አስተያየት የሰጡበትን መረጃ በመመርኮዝ ለሐገራችን ሕዝቦች ለመንግስታችንና ለሐገር መከላከያ ሰራዊታችን አቀርባለሁ፡፡
ልብ በሉ ግብፅ በታሪኳ ብዙ ጦርነቶችን አድርጋለች ታላላቅ ጦርነቶችን ግን ተሸንፋለች፡፡ በአሁኑ ሰዓት የጦር ኃይሏ በአፍሪካ አንደኛ በአለም አስረኛ ነው፡፡ በአሜሪካ የጦር መሳሪያ ድጋፍ ከሚያገኙ ሐገራት ከእስራኤል ቀጥሎ ሁለተኛ ናት፡፡ አሜሪካ የእኔ ብቻ ናቸው ሌላ ሐገራት ቴክኖሎጂውን እንዳይሸጡት በሽያጭ አላቀርባቸውም የምትላቸው የብቻዋ ቴክኖሎጂ የሆኑ የተለያዩ ቀላልና ከባድ የጦር መሳሪያዎች ሄልኮኘተርና ጀቶችን ጨምሮ ግብፅን አስታጥቃታለች፡፡ በአጭሩ ግብፅ በአፍሪካ ቁንጮ ላይ ከአቅሟ በላይ የታጠቀች ጉረኛ ሐገር ናት ማለት ይቻላል፡፡
በአንድ ቀላል ምሳሌ እንኳን ለማስረዳት እስራኤልን ከምድረ ገፅ አጠፋለሁ ብላ ከሶስት ሐገራት ጋር ተባብራ በታሪክ የ“6 ቀኑ ጦርነት” የሚባለውን ልትተገብር ስትነሳ፣ ገና ሳይነሱ እስራኤል አጋየቻቸው እንጅ 300 የጦር አውሮኘላኖችን ቦምብና ሚሳኤል አስታጥቃ እስራኤልን ልትወርና ልታጠፋ የሞከረች ሐገር ናት፡፡ ይህም ምን ያህል ድንፋታም ነገር ግን ጥበብ የጐደላት ሀገር መሆኗን በቀላሉ ያስረዳል፡፡
ብዙ አወራሁ ወደ ተሰራጨ ያልኳችሁ ፅሑፍ ልግባና በመፅሐፍ ቅዱስ ትንቢተ ሕዝቅኤል ምዕራፍ 29 እና 30 ላይ የግብፅን ቅጣት ስለሚያትተው ትንቢት የተሰራጨ አንድ ጽሑፍ ነበር ጽሑፉንም የተለያዩ ታዋቂ ሰዎች አስተያየታቸውን አስፍረውበት ነበር ከአስተያየቶቹ መካከልም አይ ይህ ትንቢት እኮ ድሮ ገና ድሮ ከእየሱስ ክርስቶስ ልደት በፊት በ572 ቅ.ል.ክ አካባቢ በናቡከነፃር ጊዜ ተፈፅሟል ያሉም ነበሩ፡፡ በዚህ አሁንም ድረስ እያነጋገረ ባለ ፅሑፍ ተነስተን እስኪ በደንብ ትንቢቱን በጥሞና እንየው፡፡
በደንብ መታየት ያለበት ነገር የግብፅ የቅርብ ጊዜ እርስ በእርስ መባላት በየአደባባዩ ጐራ ለይቶ መወራወር ከቱኒዚያ በተነሳው የጐዳና ላይ ግጭት ቀጥሎ የአለምን ትኩረት የሳበ ነበር፡፡ የግብፃዊያኑ አመፅ ዋናው አላማም ለ30 አመት ግብፅን አንቀጥቅጦ የገዛውን የሆስኒ ሙባረክን መንግስት መገልበጥ ነበር፡፡ በአሜሪካ መንግስትና በአንዳንድ የምዕራቡ ሐገራት ባለስልጣናት ግፊትም ሆስኒ ሙባረክ ስልጣናቸውን በፌቡራሪ 12 ቀን መልቀቂያ ጠይቀው ለግብፅ ጦር ሰራዊት አስረከቡ፡፡ ከዛ ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁኗ ደቂቃ ድረስ በግብፅ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የስልጣን ሽኩቻና ብጥብጥ ተፋፍሟል ዋናው ግፊትም ያለው ግብፅ በሐይማኖት መሪዎች የምትመራ ጠንካራና እስላማዊ ሐገር ሆና እንድትቀጥል ለማድረግ የሚደረግ ጥረት ነው፡፡
ተራማጅ እስላም በሚል መፈክር ስርም ከጀርባ ሁኖ ማርሹን በመቀያየር የሚገኘው “ሙስሊሞቹ ወንድማማቾች” (Muslim brotherhood) የሚባለው ድርጅት እንደሆነ የአደባባይ ሐቅ ነው፡፡ ቀስ በቀስም በጥበብ ቁልፍ የስልጣን ቦታዎችን እየያዘ ገና እየወጣ የሚገኝ ፓርቲ ነው ዋናው አላማውም ግብፅን ጠንካራ የሙስሊሞች ሐገር እንድትሆን ማስቻል ነው፡፡ በቅርቡ የሚታየው ሁኔታ እንደሚያመለክተውም የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ በግብፅ ጦር ውስጥ ያሉ ቁልፍ ሰዎችን እያዳከመና ወደ ፓርቲው እየቀላቀለ ስልጣኑን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ቀን ከሌት እየሰራ ይገኛል፡፡
ባጭሩ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚገልፁት በጣም የጦፈ የስልጣን መያዝ ፉክክር እንደሚደረግና የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ እንደሚያሸንፍና ተራማጅ እስላም ስልጣን ላይ እንደሚሆን ይገልፃሉ፡፡
ሙባረክ ስልጣኑን ባስረከቡ ማግስት ነው እንግዲህ እስራኤላውያን ነቃ ብለው የግብፅን ሁኔታ በጥሞና ማዳመጥ የጀመሩት የስለላ ኤክስፐርቶቻቸውንም ያሰማሩት፡፡ ምክንያቱም እ.ኤ.አ ማርች 31,1979 ጀምሮ ከ30 አመታት በላይ ያስቆጠረ የሰላም ስምምነት ከሙባረክ ጋር እስራኤል አድርጋ ነበር ሙባረክ ሲወድቅም ስምምነቱ ተቋረጠ፡፡ ባለፉት 30 አመታት ምንም እንኳ ግብፅ በጨቋኙ የሆስኒ ሙባረክ አገዛዝ ስር ብትሆንም እንኳ ግብፅ ለእስራኤል ደቡባዊ ድንበር መጋጋት የሆስኒ ሙባረክ ወታደሮች ከፍተኛ ጥበቃ ያደረጉ ነበርና ነው፡፡ ነገር ግን አሁን ያ አስተማማኝ ጥበቃ የለም ስለዚህ እስራኤል ሆየ ነቃ! ብላ ነገሩን መከታተል ጀመረች፡፡
ይህ የእስራኤል ስጋትም ሳይውል ሳያድር እውን መሆኑ ተረጋገጠ ሁለቱ በተባበሩት መንግስታት አሸባሪ ተብለው የተፈረጁትና እስራኤልን ከምድረ ገፅ ለማጥፋት ሙሉ ጊዜአቸውን ሰውተው የሚንቀሳቀሱት የአሸባሪ ቡድኖቹ የሐማስና የፋታህ መሪዎች ሳይውል ሳያድር ግብፅ ካይሮ ላይ በሚያዚያ 26 ተገናኙና ጦራቸውን አንድ በማድረግ እስራኤልን ለመዋጋት ተፈራረሙ፡፡
የአሸባሪ ቡድኑ ፋታህ ኘሬዝዳንት ሞሐመድ አባስም ንግግራቸውን አሰሙ፡፡
“እኛ ፍልስጤማውያን ከዛሬ ጀምሮ ያንን ጥቁር የልዩነት ዘመናችንን አጠናቀናል! ሐማስ የፍልስጤም ሕዝብ አባልና አካል መሆኑን አውጀናል፡፡ እንግዲህ እስራኤል ከሰፈራ ኘሮግራም ወይም ከሰላም አንዱን መምረጥ አለባት!” ሲሉ ተኮፈሱ፡፡
አሁን በእርግጠኝነት ለመናገር ከዚህ በኋላ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል የሚደረግ የሰላም ስምምነት ሊኖር አይችልም፡፡ ቀዩ መስመር ይሉሐል ይሄኔ ነው! ፍልስጤም የምትባል ሐገርን ለማቋቋምና እውቅናን ለመስጠት ፋታህ እና ሐማስ መሞከራቸው አይቀሬ ነው ከዚች ቀን ደቂቃና ሰከንድ ጀምሮም ነበር እስላሞቹ ወንድማማቾችና እስራኤል አይጥና ድመት የሆኑት፡፡
እንግዲህ ቅድም የገለፅኩት የግብፃዊያን ትንቢት በትንቢተ ሕዝቅኤል ላይ ቁልጭ ብሎ ተቀምጧል ያልኩት ከፅሑፉ ተነስቸ ነው፡፡ ምክንያቱም ሕዝቅኤል በግልፅ ግብፆች የሚቀጡት ከእስራኤል ጋር አልተባበርም በማለታቸው ነው ይላል፡፡ “ግብፅ ለወደፊቱ አይቀጡ ቅጣት ነው የሚደርስባት ፍርዱም የቆሻሻ መጣያ ቦታ እስክትመስል በግብፅ ይታያል እያለ ቃል በቃል የሚከተሉትን የመፅሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ያትታል፡፡

 ሕዝቅኤል 29 (6:12)
በግብፅም የሚኖሩ ሁሉ ለእስራኤል ቤት የሸንበቆ በትር ሆነዋልና እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ያውቃሉ”
“በእጅ በያዙህ ጊዜ ተሰበርህ ጫንቃቸውንም ሁሉ አቆሰልህ በተደገፈብህ ጊዜ ተሰበርህ ወገባቸውንም ሁሉ አንቀጠቀጥህ”
“ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል እነሆ ሰይፍ አመጣብሃለሁ ሰውንና እንስሳንም ከአንተ ዘንድ አጠፋለሁ፡፡”
“የግብፅ ምድር ባድማና ውድማ ትሆናለች እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ አንተ ወንዙ የእኔ ነው የሰራሁትም እኔ ነኝ ብለሀልና”
“ስለዚህ እነሆ በአንተና በወንዞችህ ላይ ነኝ የግብፅንም ምድር ከሚግዶል ጀምሮ እስከ ሴዌኔና እስከ ኢትዮጵያ ዳርቻ ድረስ ውድማና ባድማ አደርጋታለሁ፡፡”
“የሰው እግር አያልፍበትም የእንስሳም ኮቴ አያልፍባትም እስከ 40 አመትም ድረስ ማንም አይኖርባትም፡፡”
“ባድማም በሆኑ ምድሮች መካከል የግብፅን ምድር ባድማ አደርጋታለሁ ባፈረሱትም ከተሞች መካከል ከተሞችዋ 40 አመት ፈርሰው ይቀመጣሉ ግብፃውያንንም ወደ አህዛብ እበትናቸዋለሁ በአገሮችም እዘራቸዋለሁ፡፡”

 በአሁኑ ሰአት ያለምንም ጥርጥር ግብፅ እስራኤልን ለማጥፋት ለብዙ አመታት ቀን ከሌሊት ሲማስኑ ከኖሩ ሙስሊም አሸባሪዎች ጋር ህብረት ፈጥራለች፡፡
ይህ የአሸባሪነት ትብብርም በቅርቡ እንደ ሰደድ እሳት መቀጣጠሉና ብዙ አሸባሪዎችን በህብረት አሰባስቦ እስላማዊ ወንድማማቾችን አሁን ጊዜው ደርሷል እስራኤል ትወረር ማስባሉ የማይቀር ሐቅ ነው፡፡
ብዙ ሰዎች ከላይ የጠቀስኩትን የሕዝቅኤል 29 ትንቢት ገና ወደፊት አለም ስትጠፋ የሚፈፀም ትንቢት ነው እንጅ አሁን ጊዜው ገና ነው እያሉ ይቃወማሉ፡፡
አንዳንዶቹ ደግሞ ትንቢቱ እኮ ድሮ ገና ድሮ በባሊሎናዊያን ጊዜ ተፈፅሟል ይላሉ፡፡ ነገር ግን አብዛኞቹ ልብ ያላሉት ነገር ቢኖር የሕዝቅኤል ትንቢት ስለፍፃሜው ሲተነብይ እሚያወራው ሴዌኔ ስለሚባል ቦታ የሚደርስበትን የወደፊት መከራ ነው የሚዘረዝረው፡፡ በዛ ላይ ደግሞ ከላይ የዘረዘርኩት የመፅሐፍ ቅዱስ ቃል እንደሚያትተው ግብፅ በታሪኳ መቸም ቢሆን ለ40 አመታት ያህል ሰው የሌለባት ምድረ በዳ ሆና አታውቅም ይህም ትንቢቱ ገና ወደፊት ለመሆኑ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡
ለብዙ አመታት ስናምንበት የኖርነው የሕዝቅኤል ትንቢት በተፈጥሮው ቅኔያዊ ይዘቱ ያይላል፡፡ ይህንን ለማለት ያስቻለኝ ምክንያትም ሕዝቅኤል ትንቢቱን ሲፅፈው በዛ ጊዜ “የሴዌኔ ማማ” የሚባል ነገር ወይም ቦታ የለም አልነበረም እንደውም እ.ኤ.አ እስከ 1967 ጊዜ ድስ ይህ ቦታ አልተሰራም በ1967 ግን ይህ ቦታ በሚደንቅ ሁኔታ ታላቁ የአስዋን ግድብ ሆኖ ብቅ አለ፡፡ በግብፅ ደቡባዊ በኩል አባይን ተከትሎ ተገነባ፡፡ “ሴዌኔ” የሚለው ስም የመጣው ሲቭኔ ከሚለው የሒብሩ ቃል ሲሆን ትርጓሜውም “መግቢያ” ወይም “ቁልፍ” ማለት ሲሆን ይህም ስም የጥንት ግብፃውያንን መግቢያ ያመላክታል፡፡ ከደቡባዊ ግብፅ ወይም ከኢትዮጵያ ተነስቶ አንድ ሰው ወደ ግብፅ ሲገባ የሚያየውን መግቢያ ወይም ቁልፍ በግልፅ ያትታልና፡፡
በጣም ብዙና የተለያዩ ታሪካዊ መረጃዎችን ብናገላብጥ የመፅሐፍ ቅዱስ ሴዌኔ በእርግጥም አስዋን ግድብ ነው ይላሉ፡፡ ከነዚህ መረጃዎች መካከል አንዱ በ1966 እ.ኤ.አ በኬል እና ዳልሽ የተፃፈው የብሉይ ኪዳን ጥናትና አስተያየት የሚለው መፅሐፍ ይገኝበታል፡፡ ግንኙነቱንም ሲያጠናክረው በግሪኮች “ሴዌኔ ብሩዳሽ” እንደፃፈው “ሴርቱዋጅንት” ወይም የመጨረሻዋ የግብፅ ደቡባዊ ከተማ ከኩሽ ማለትም ኢትዮጵያ አቅጣጫና ጐን ናት ይላል፡፡ አሁንም ድረስ ከአባይ ምስራቃዊ ቦታዎች አካባቢ የሚታዩ ኢትዮጵያዊ የሆኑ አንዳንድ የጥንት ስልጣኔ መገለጫዎች በግብፅ ደቡባዊ አዋሳኝ ከተማ ሴርቱዋጅንት አካባቢ ይገኛሉ፡፡
የሚገርመው ነገር ኬል እና ደልሽ በ1866 የብሉይ ኪዳን ጥናትና አስተያየት ሲፅፉ አስዋን ላይ ምንም አይነት ማማ አልነበረም ሕዝቅኤል ትንቢቱን በ570 ቅ.ክ.ል በፊት ሲፅፈውም ምንም አይነት ማማ አልነበረም፡፡ እውነታው ግን ታላቁ የአስዋን ሐይድሮ ኤሌክትሪክ ግድብ በግብፃውያንና በራሻውያን ተሰርቶ በ1967 እ.ኤ.አ እስከሚጠናቀቅበት ቀንና ደቂቃ ጊዜ ምንም አይነት ማማ በአስዋን ላይ አልነበረም፡፡
አሁን ግን ይህ ግድብ ሲጠናቀቅ በአካባቢው ያለው ብቸኛ ማማና ወደ ላይ የተራራ ያህል ገዝፎ የሚታየው የአስዋን ግድብ እራሱ ነው፡፡ ለዛም ነው ይህ “ሴዌኔ” እየተባለ በትንቢት ሲገለፅ የነበረው ቦታ በአሁኑ ሰአት አስዋን እየተባለ የሚጠራው ቦታ መሆኑን አጋግጠናል የሚሉት፡፡ ግብፃውያኑ የራሽውያንን ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ግድባቸውን በተሳካ ሁኔታ ሙሉ በሙሉ ሲያጠናቅቁም ተኮፈሱና እስከ ዛሬ ድረስ የሚመፃደቁበትን አባባላቸውን ለልጅ ልጅ እንዲወረስ እያደረጉ እንደ ምሳሌያዊ አነጋገር ይጠቀሙበታል፡፡

“ወንዙ የእራሴ ነው የሰራሁትም እኔ ነኝ” ግብፃውያን

 ሕዝቅኤል 29 (2-5)
“የሰው ልጅ ሆይ ፊትህን በግብፅ ንጉስ በፈርኦን ላይ አድርግ በእርሱና በግብፅ ሁሉ ላይም ትንቢት ተናገር፡፡”
“እንዲህም በል - ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላላ በወንዞች መካከል የምትተኛና ወንዙ የእኔ ነው ለራሴም ሰርቸዋለሁ የምትል ታላቅ አዞ የግብፅ ፈርኦን ሆይ እነሆ በአንተ ላይ ነኝ፡፡”
“በመንጋጋህ መቃጥን አገባብሃለሁ የወንዞችህንም አሶች ወደ ቅርፊትህ አጣብቃለሁ ከወንዞችህም መካከል አወጣሀለሁ የወንዞችህም አሶች ሁሉ ወደ ቅርፊትህ ይጣበቃሉ፡፡
“አንተና የወንዞችህን አሶች ሁሉ ወደ ምድረ በዳ እጥላለሁ በምድርም ፊት ላይ ትወድቃለህ እንጅ አትከማችም አትሰበሰብም መብልም አድርጌ ለምድር አራዊትና ለሰማይ ወፎች ሰጥቼሃለሁ፡፡”
ትንቢቱ ዝም ብሎ በመጀመያ ሲታይ የሚመስለው ለግብፅ ንጉስ ፈርኦን ፓሮህ የተፃፈ ይመስላል ቀስ እያላችሁ በደንብ መፈተሽ ስትጀምሩ ግን ትንቢቱ የተፃፈው “በባህር ላይ ስለሚኖረው” ታላቅ አዞ መሆኑን ታውቃላችሁ፡፡
ቀጥሎም አንተና የወንዞችህ ወይም የአባይ አሳዎች ሁሉ ወደ ምድረ በዳ እጥላለሁ ለምድር አራዊትና ለሰማይ ወፎችም መብል አደርግሃለሁ እያለ ያትታል፡፡
አባይ በየአመቱ እየተንደረደረ በከፍተኛ ሙላት ነበር ወደ ግብፅ የሚገባው ነገር ግን ግድቡ ከተሰራ በኋላ ሰጥ ለጥ ብሎ ነው ግብፅ ውስጥ የሚጓዘው በትንቢቱ እንደተገለፀው አባይን እንደገና በከፍተኛ ሙላት እያስጋለቡ በግብፅ ውስጥ ለማስጓዝ ብቸኛው መንገድ አንድ እና አንድ ብቻ ነው ግድቡን ማፍረስ፡፡
ሌላው አስደናቂ ነገር ይህ ታላቅ ግድብ የተገነባው በጣም በትልልቅ ብረቶችና ኮንክሪቶች ተጠፍጥፎ ከመሆኑ የነሳ የዘርፉ ባለሙያዎች የአስዋን ግድብ በምንም አይነት ቦምብ ቢመታ ሊፈርስ አይችልም፡፡ ከኒውክሌር ቦምብ በቀር ማለታቸው ትንቢቱን ገና ያልተፈፀመ ስለመሆኑ ያረጋግጣል፡፡ ኒውክሌር ቦምብ የአሁን ቴክኖሎጂ ነውና፡፡

 እስራኤላዊያን ጠበብቶች ምን አሉ?

በ2002 የእስራኤል የፓርላማ አባል የነበረ አቪጐር ሊበርማን የተባለ ሰው ነው ለመጀመሪያ ጊዜ ይህች በየጊዜው ለእስራኤል ችግር መነሻ እየሆነች ላስቸገረችው ግብፅ የምትባል ሐር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የሚሆን መፍትሄ አግኝቻለሁ ብሎ ንግግሩን ያሰማው፡፡
“እስራኤል በቀላሉ ግብፅን በአንድ ኒውክሌር ቦምብ ድምጥማጧን ማጥፋት ትችላለች አለ” ልብርማን ስለ ግድቡ በደንብ ነበር ያጠናው ያሰማራቸው ረዳቶችም አስዋን ግድብ በጣም ትልቅና ግዙፍ ከመሆኑ የነሳ በተራ ቦምብ እንደማይፈርስ ተረድቶ ነበርና ኒኩሌየር ቦምብ ብቸኛ አማራጭ መሆኑን ተንትኖ አስረዳ፡፡
ሌላኛው የፓርላማ አባል ይጋል አሎን ቀጠለና ይህንን ጥሩ ዜና የምስራች ለእስራኤላዊያን በአደባባይ አበሰረ፡፡ እነዚህ ሁለት ጀግኖች አብዛኞቹ እስራኤላዊያን የሚያውቁትን ነገር ግን በውስጣቸው አምቀው የያዙትን እውነት በአደባባይ ያበሰሩ ጀግኖች አደረጋቸው፡፡ ሊበርማን ከእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እስከ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴርነት ድረስ፣ ይጋል ደግሞ ለሰባት አመታት በሚኒስቴርነት ሐገራቸውን አገልግለዋል፡፡
ሊበርማንና ይጋል እስከ አሁኗ ደቂቃ ድረስ ግብፃውያን አንገታቸውን ደፍተው እድሜልካቸውን መፍትሄ የማያገኙለትን የቤት ስራ ሰጥተዋቸዋል፡፡
እነኚህ ሁለት እስራኤላዊያን ሲናገሩም የእስራኤል የማንነት ጥያቄ በግብፃውያን ወረራ የሚስተጓጐል ከሆነ ጨዋታው የሚሆነው እንደዛ በምትመፃደቁበት ግድባችሁ ላይ ይሆናል በማለት አስረገጡ፡፡
“በኑክሊር ቦምብ አስዋንን እናፈርሰዋለን፡፡ በውሃውም በሰዓታት ሰምጣችሁ ታልቃላችሁ አርፋችሁ ቁጭ በሉ፡፡ “ይኸው እነሱም አርፈው እስከ ዛሬ ቁጭ ብለዋል፡፡

 የሚከተሉት የማጠቃለያ የመፅሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች በመጨረሻው ቀን ላይ ያተኩራሉ ልብ ብላችሁም አስተውሉ የሴዌኔ ማማም ተጠቅሷል፡፡

 (ሕዝቅኤል 30 1፡6)
“የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ የሰው ልጅ ሆይ ትንቢት ተናገር እንዲህም በል”
“ጌታ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል” ዋይ በሉ ለቀኑ ወዮ ቀኑ ቅርብ ነው የእግዚአብሔር ቀን ቅርብ ነው የደመና ቀን የአህዛብ ጊዜ ይሆናል፡፡
“ሰይፍ በግብፅ ላይ ይመጣል ሁከትም በኢትዮጵያ ይሆናል የተገደሉትም በግብፅ ውስጥ ይወድቃሉ ብዛትዋንም ይወስዳሉ መሰረቷም ይፈርሳል፡፡”
“ኢትዮጵያና ፋጥ ሎድም የደባለቀም ሕዝብ ሁሉ ኩብም ቃል ኪዳንም የገባችው ምድር ልጆች ከእነሱ ጋር በሰይፍ ይወድቃሉ፡፡”
“እግዚአብሄር እንዲህ ይላል ግብፅን የሚደግፉ ይወድቃሉ የሐይሏም ትእቢት ይወርዳል ከሚግዶል ጀምሮ እስከ ሴዌኔ ድረስ በእርስዋ ውስጥ በሰይፍ ይወድቃሉ ይላል ጌታ እግዚአብሄር፡፡”

ለዚህም ነው ግብፅ ለመኖሪያ የማትመች የተንኮለኞችና የእግዚአብሔር ቃል ተቃዋሚዎች ሐገር በመሆኗ ለ40 አመት ያህል ማንም የማይኖርባት ምድረ በዳ አደርጋታለሁ ያለው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል በሕዝቅኤል 38 ላይ እስራኤልን ተባብረው ከሚያጠቋት የጐግ ሐይሎች ጋር ግብፅ ያልተጠቀሰችውም እኮ ስለማትኖር ነው እንጂ ብትኖርማ የመጀመያ ቋሚ ተሰላፊ ነበር እኮ የምትሆነው፡፡
በራዲዮአክቲቭ ንጥረ ነገር በተበከለ ውሃ የተጥለቀለችን አንድ ሐገር ለማፅዳት የሚፈጀውን ሐይልና ገንዘብ አስቡትና ምን ያህል አስቸጋሪ ነው ብላችሁ እራሳችሁን ጠይቁ፡፡ ወይም ከመጨረሻው ቀን በኋላ በእግዚአብሄርና በተከታዮቹ የሚፀዳው ቦታ ግብፅ ይሆነ ይሆናል፡፡ ማን ያውቃል? እባካችሁ ኢትዮጵያዊያን ጀግኖችም በዚህ ጉዳይ ላይ አንድ ነገር በሉ “ግብፅ ሆይ አርፈሽ ቁጭ በይ! በእሳት አትጫወች! ግድባችንን እንዳንሰራ ወንድ የሆነ ያስቆመናል! አለዛ በደህና ጊዜ የሰራሽውን የአስዋን ግድብ መጥፊያሽ ይሆናል! አሁን ያለው ኢትዮጵያዊ ትውልድ ከምታስቢው በላይ ነቃ ያለ ነው እንኳን ለወደፊቱ ድሮ ለሄደብን አፈርም ካሳ መጠየቁ አይቀርም” እኔስ እችን ፅፌ ትንሽ ንዴቴ ተንፈስ አለልኝ! እናንተስ?

 የምወዳትን ኢትዮጵያ እግዚአብሔር ይባርካት፡፡

                              አመሰግናለሁ፡፡

                       አማኑኤል ዊንታ

                   ባህር ዳር ሰኔ 2005