Sunday, November 30, 2014

በምድር ላይ በክፉው መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ አሰተኛ ክርስቶሶች (ክፍል 4 )

ላዝሎ ቶት(1938-2012) 

በትውልዱ ሀንጋሪ፤ በዜግነት አውስትራሊያዊ የሆነ ሰው ነው። በትውልድ ሀገሩ በጂኦሎጂ ትምህርት ዲፕሎማ የነበረው ቢሆንም የእንግሊዝኛ ቋንቋው ደካማ ስለነበርና የሙያ ክህሎቱም ተቀባይነት ባለማግኘቱ አውስትራሊያ እንደገባ ሀንጋሪ በተማረው ሙያ መስራት አልቻለም። በኋላም በአንድ ሳሙና ፋብሪካ በቀን ሰራተኝነት ተቀጥሮ ጥቂት ከቆየ በኋላ በ1971 ዓ/ም ወደኢጣሊያ አቅንቷል።  ጣልያን እንደደረሰም እኔ «ኢየሱስ» ነኝ እያለ ለመስበክ ቢሞክርም ጣሊያንኛ ባለመቻሉ ስብከቱን ያዳመጠው አልነበረም። ከሮማው ካቶሊክ ፖፕ ጳውሎስ 6ኛ ለመገናኘትና የራሱን ማንነት ሊገልጽላቸው እንደሚፈልግ ደብዳቤ ጽፎላቸው ደብዳቤው ከፖፑ ሳይደርስ መንገድ ላይ ቢቀርበትም በሌላ መንገድ ለመገናኘት ያልተሳካ ሙከራም አድርጓል። ይሁን እንጂ በዚህ ሁሉ ተስፋ ያልቆረጠው «ቶት» የመጨረሻ ሙከራውን ለማድረግ በ33ኛው ዓመት ዕድሜው ግንቦት 21 ቀን 1972 ዓ/ም ጂኦሎጂስቶች በተለይ የሚጠቀሙበትን ትንሽ መዶሻ ከፍ አድርጎ በመያዝና በአደባባይ እየጮኸ «እኔ ኢየሱስ ነኝ፤ ሞቼም ነበር፤ ሕያው ነኝ» እያለ ይረብሽ ጀመር። ከዚያም ወደ ቫቲካን ሲቲ በመግባት በሚካኤል አንጄሎ የተሰራውን ቅርጽ ማለትም ኢየሱስ ከመስቀል ላይ ወርዶ በእናቱ በማርያም እቅፍ ላይ ሆኖ ከአንገቱ ዘንበል ብሎ የሚታየውን ምስል በያዘው መዶሻ መደብደብ ጀመረ። በድብደባውም የማርያምን ምስል ቀኝ ክንድ፤ የአንድ ዓይን ክፍሏንና አፍንጫዋን ሰብሮ ጥሏል።


 በቦታው ከነበሩ ጎብኚዎች አንዱ የሆነው ቦብ ካሲሊ የተባለ ሰው ቶት ላይ ተጠምጥሞ በመያዝ ሊያስጥለው ችሏል። ቶት በቁጥጥር ስር ውሎ ህክምና ሲደረግለት የአእምሮ በሽተኛ መሆኑ በመረጋገጡ ከጣሊያን ወደአውስትራሊያ በአስቸኳይ እንዲባረር ተደርጓል። አውስትራሊያም እንደደረሰ በተመሳሳይ ድርጊት ላይ በመገኘቱ ከህሙማን ክብካቤ ማዕከል እንዲገባ ተደርጎ ህይወቱ እስካለፈችበት 2012 ዓ/ም ድረስ በዚያው ሲረዳ ቆይቷል።

===============================================================================

ዌይን ቤንት ወይም ማይክል ትራቬሰር (ከ1941- እስካሁን በሕይወት ያለ)

 በ1941 ዓ/ም የተወለደ ሲሆን  በአይዳሆ ሴንትፖይንት ከተማ በምትገኝ «ጌታ የኛ ቅድስና ቤተ ክርስቲያን» መሪ የነበረ ሰው ነው። ቤንት የዚህች ቤተክርስቲያን መሪ ከመሆኑ በፊት «በሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን» ፓስተር ሆኖ ያገለግል ነበር። በ1987 ዓ/ም ቤተ ክርስቲያኒቱን በይፋ ለቆ ሲወጣ «ሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን የታላቂቱ ጋለሞታ ሴት ልጅ ናት» ብሎ በአደባባይ ተናግሮ ነበር። ይህንን ለማለት ያበቃውን ምክንያት ግን በወቅቱ አልተናገረም።  ከዚያም ወደ አይዳሆ በማምራት ጥቂት ጊዜ በአባልነት ከቆየ በኋላ በ2000 ዓ/ም «ጌታ የኛ ቅድስና» በተባለችውና አነስተኛ ቁጥር በያዘችው ቤተ ክርስቲያን መሪ  ለመሆን ቻለ። በዚያው ዓመት «እግዚአብሔር፤ አንተ ኢየሱስ ነህ ብሎ ተገልጾ ነገረኝ» በማለት ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት አወጀ። ጥቂት ቆይቶም ከሰባት ደናግላን ጋራ ለወሲብ እንድትተኛ የሚል ትዕዛዝ ስለመጣልኝ ደናግል ልጆቻችሁን እንድትሰጡኝ በማለት ጥያቄውን አቀረበ። ገሚሶቹ የቡድኑ አባላት ሃሳቡን ውድቅ ያደረጉበት ቢሆንም በግላጭ ሴት ልጁን አሳልፎ የሰጠው ማን እንደሆነ ሳይታወቅ በምስጢር ከደናግላን ጋር ወሲብ መፈጸሙ በኋላ ላይ በፖሊስ በተደረገበት ምርመራ ሊረጋገጥ ችሏል። ቻናል 4 የተባለው የዩኬ ቴሌቪዥን ጣቢያ በ2007 ዓ/ም ከዌይን ቤንት ጋር ባደረገው ቃል ምልልስ ስለደናግላኑ ወሲብና ከእግዚአብሔር ስለሚመጣለት ትዕዛዛት ተከታታይ ፕሮግራም አስተላልፎ ነበር።(ከቪዲዮዎቹ አንዱን ለማየት እዚህ ይጫኑ)
  የዓለምም መጨረሻ ጥቅምት 31/2007 ዓ/ም እንደሚሆንና ተከታዮቹም ለመነጠቅ እንዲዘጋጁ የተናገረ ቢሆንም ቀኑ ሲደርስ እንዳለው የሆነ ነገር ምንም አልነበረም።  ይልቁንም ቤንት ከልጁ ሚስት፤ ከደናግላን ጋር እንዲሁም ለአቅመ ሄዋን ካልደረሱ ታዳጊዎች ጋር ወሲብ በመፈጸም ወንጀል ተከሶ በ2008 ዓ/ም የ18 ዓመታትን እስራት ተከናንቦ ከርቸሌ ወርዷል። ዌይን ቤንት ከርቸሌ ከወረደ በ2014 ዓ/ም ገና 6ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን ቢያንስ በአመክሮ ለመፈታት ከእንግዲህ 3 ዓመት ገደማ በዚያው መቆየት ይጠበቅበታል። 

==============================================================================

አሪፊን ሙሐመድ ( 1943- እስካሁን ያለ)

 አሪፊን ሙሐመድ በ1943 ዓ/ም ከሙስሊም ቤተሰብ በማሌዢያ ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ህውከት እንደደረሰ በ1980ቹ አጋማሽ  በማላያን ቋንቋ «ካራጃአን ላንጊት» ወይም በእንግሊዝኛው «የሰማይ መንግሥት» የተሰኘ ድርጅት አቋቋመ። በአክራሪ ሙስሊሞች በምትታወቀው ማሌዢያ ውስጥ አሪፊን ሙሐመድ «እኔ አልመሲህ ዒሳ፤ ቡድሃ፤ ሙሐመድ ሺቫ ነኝ» እያለ በመስበክ ተከታዮችን ለማፍራት ጊዜ አልፈጀበትም። በዚህ አድራጎቱ ብርቱ ተቃውሞ ገጠመው። በተደጋጋሚ ሲታሰር፤ ሲፈታ ቆይቶ መንግሥታዊ ስርዓቱን በዓመጽ ለመገልበጥ በመሞከርና ሃይማኖታዊ ብጥብጥን በመፍጠር ወንጀል ተከሶ ድርጅቱ እንዲዘጋ፤ በአባልነት የተሳተፉትም እንዲታሰሩ ሲወሰን አሪፊን ሙሐመድ ሾልኮ አመለጠ። ከአራቱ ሚስቶቹ ሦስቱና ከተከታዮቹም 58 ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ።

 እያንዳንዳቸውም 3000 የማሌዢያን ገንዘብ እንዲከፍሉና ሁለት ዓመት እንዲታሰሩ ፍርድ ቤት ወሰነባቸው።  የድርጅታቸውም ህንጻና ማንኛውም ንብረት እንዲፈርስ ተደረገ። አሪፊን ሙሐመድ አንዴ ኢየሱስ ነኝ፤ አንዴ ማህዲ ነኝ እያለ ተከታዮቹን ቢያጭበረብርም በማሌዢያ መንግሥት በወንጀል ከሚፈለጉ ሰዎች ቀንደኛው ሲሆን ማሌዢያን ለቆ ከጠፋ በኋላ በታይላንድ ውስጥ ተሸሽጎ እንደሚገኝ ይገመታል።
==================================================================================

ማታዮሺ ሚትሱኣ (1944- እስካሁን በሕይወት ያለ) 

በጃፓን፤ ኦኪናዋ ከተማ በጥር 5/ 1944 ዓ/ም ተወለደ። ከዚያም ለአቅመ ትምህርት እንደደረሰ በመጀመሪያ በተወለደት ቦታ በኋላም በቶኪዮ ቹዋ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ድግሪውን አግኝቷል። በ1997 ዓ/ም «ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚያዊ ኅብረት ፓርቲ» የተባለውን ሃይማኖትንና ፖለቲካን በጥምር የሚያንቀሳቅስ ፓርቲ መሰረተ። እንደሃይማኖት ሥርዓት ዓለም በኔ እንዲገዛ «እኔ ኢየሱስ ነኝ» አለ። እንደፖለቲካ አስተዳደር ደግሞ ዓለም በኔ እንዲመራ «የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ መሆን ያለብኝ እኔ ነኝ አለ»። የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ለመሆን ባለው ከፍተኛ ጉጉት የርሱ ፓርቲ በተደጋጋሚ በምርጫ ቢወዳደርም  እንኳን ከትልቅ ስልጣን ሊደርስ ቀርቶ የመንደር ምርጫም ማሸነፍ ሳይችል ቀርቷል። በምርጫ የተፎካከሩትን ሰዎች ለዚህ ድርጊታችሁ የምሰጣችሁ ምክር «ራሳችሁን አጥፉ»  ያላቸው ሲሆን ስልጣን ብይዝ ደግሞ ሁሉንም ሰብስቤ እሳት ውስጥ እጨምራቸው ነበር እያለ ሲለፍፍ ተሰምቷል።

== ==============================================================



ጆሴ ሉዊስ ደ ጂሰስ ሚራንዳ ( 1946- 2013) 

 ፖርቶሪኮ ውስጥ ፖንሴ በተባለች ከተማ በ1946 ዓ/ም ተወለደ። ወላጆቹ በጣም ድሃ ስለነበሩ የሴቶችን ቦርሳ መመንተፍ የተለማመደው በልጅነት ዕድሜው ነበር። ገና የ14 ዓመት ዕድሜ ሳለም የሔሮይን አደገኛ ተጠቃሚ እስከመሆን ደርሷል።  ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ በፖንሴ ከተማ በነበረችው መጥምቃውያን ቤተ ክርስቲያን ተቀላቀለ። እግዚአብሔር ባደረገልኝ ጥሪና እገዛ ከነበረብኝ ደባል ሱስ ሁሉ ተላቅቄአለሁ አለ።  ጆሴ ሚራንዳ በ1973 ዓ/ም  ሁለት መላዕክት መጥተው በነገሩኝ መሠረት «እኔ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ሆኜ በምድር ላይ መገለጤን ነግረውኛል» ብሎ መለፈፉን «ሀ»ብሎ ጀመረ። በማያሚ፤ ፍሎሪዳ የስደት ኑሮውን የቀጠለው ሚራንዳ የ15 ደቂቃ የሬዲዮ ፕሮግራም በማሰራጨት የሱን ኢየሱስነት ይሰብክ ገባ። በስብከት መርሐ ግብሩ «ሚኒስትሮ ግሬሴንዴ  ኤን ግራሲያ» ወይም « በጸጋው የማደግ አገልግሎት» የተሰኘ ድርጅት ከመሰረተ በኋላ በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች ማስፋፋቱን ቀጠለ። በ35 ስቴቶች በከፈተው ተቋም 287 የሬዲዮ ጣቢያዎችና በእንግሊዝኛና ስፓኒሽ ቋንቋ የሚተላለፍ የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን ስርጭትም እስከማስተላለፍም ደርሷል።
ጆሴ ሚራንዳ አንድ ጊዜ ሐዋርያው ጳውሎስ ነኝ፤ አንድ ጊዜ ደግሞ ኢየሱስ ነኝ እያለ ከቆየ በኋላ በ2006 ዓ/ም ክህደቱን በማጠናከር ከዛሬ ጀምሮ «እኔ የኢየሱስ ተቃዋሚ ነኝ» ሲል አወጀ።  «Anti Christ» ወይም ተቃዋሚው ስለሆንኩኝ መለያ ምልክቴ በራእይ 13 ላይ የተጠቀሰው«666» ቁጥር ነው በማለቱ  ተከታዮቹ ሁሉ በሰውነታቸው ላይ እንዲነቀሱ ትዕዛዝ አስተላለፈ። ተከታዮቹም «666» ቁጥርን በሰውነታቸው ላይ በሰልፍ ተነቀሱት።
የሚራንዳ ወርሃዊ ደመወዝም ልዩ ልዩ ክፍያና አበልን ሳይጨምር 228,000 ዶላር ገደማ ነበር። ሚራንዳ ባደረበት የጉበት ህመም በተወለደ በ67 ዓመቱ በ2013 ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል። ከ2 ሚሊዮን በላይ በሚገመቱ ተከታዮቹም ዘንድ «እንደመልከ ጼዴቅ ለዘለዓለም የሚኖር» ተብሎለታል።
በአንድ ወቅት CNN ካቀረበው የጆሴ 666 ታሪክ የተወሰደ ቪዲዮ ይመልከቱ።





Monday, November 24, 2014

ኡጋንዳዊቷ የቤት ሠራተኛ ሕይወት ለማጥፋት በመሞከር ወንጀል ተከሠሠች!

( ዕድሜአቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ እንዲመለከቱ አይመከርም ) The film is not suitable for viewing by anyone under 18 years of age

ባለፉት ቅርብ ቀናት በኢትዮጵያ ውስጥ ሐና በተባለች ታዳጊ ወጣት ላይ አስነዋሪና እጅግ አሳሳቢ ድርጊት ተፈጽሞ የብዙዎችን ልብ እንደሰበረ ይታወቃል። ማኅበራዊ አኗኗራችን ከመተሳሰብ እያፈነገጠ፤ ሥነ ምግባራዊ አስተሳሰባችን እያደፈ የመሄዱ ምልክት ነው። ዓለም አንድ መንደር እየሆነች ነው ሲባል በመሰልጠኑ ብቻ ሳይሆን በመሰይጠኑም ጭምር በመሆኑ ስግብግብነት፤ ራስ ወዳድነት፤ ብልግናና ዐመፃንም ዓለማዊ መንደርተኝነት እያካፈለው ይገኛል። ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጸመው አስነዋሪ ድርጊት ትኩሳቱ ሳይበርድ አንድ መንደር የሆነችው ዓለም ከወደዑጋንዳ ሌላ ዜና ብቅ አለች። በአንዱ ጫፍ የተፈጸመው ወሬ ወደሌላ ጫፍ ለመድረስ ደቂቃ የማይፈጅባት ዓለማችን ካስተናገደቻቸው ብዙ ዜናዎች መካከል አንዱን አሳዛኝ ድርጊት አሰማችን። ጉዳዩ እንዲህ ነው።

  ድርጊቱ የተፈጸመው በዑጋንዳ፤ ኪዋቱሌ በተሰኘች አነሰተኛ ከተማ ነው። ድርጊቱን የፈጸመችው የ22 ዓመቷ ጆሊ ቱሙሂርዌ የተባለች የቤት ሠራተኛ ስትሆን በተቀጠረችበት ቤት ውስጥ እንድትንከባከብ ከአሰሪዎቿ አደራ የተሰጣትን ሕጻን በዘግናኝ ሁኔታ ስትደበድብ በቤት ውስጥ ስውር ካሜራ የተቀረጸ ቪዲዮ ያሳያል። በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተሠራጨው ይህ ቪዲዮ ብዙዎቹን አሳዝኗል። በጣም የሚረብሸው ይህ ምስል ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ እንደዋለ ዓለም ዐቀፍ ትኩረት ስቧል።  የሕጻኗ ወላጅ አባት የሆነው ኤሪክ ካማንዚ ቪዲዮውን እንደተመለከተ ለኪዋቱሌ  ፖሊስ ጣቢያ በማመልከቱ ፖሊስ ደብዳቢዋን የቤት ሠራተኛ በቁጥጥር ስር አውሎ «በማሰቃየትና ለመግደል ሙከራ በማድረግ» ወንጀል የክስ ፋይል ከፍቶ ለፍርድ ቤት እንዳቀረባት የተገኘው ዜና ያስረዳል።  የቤት ሰራተኛዋ ከተቀጠረች 26 ቀናት ብቻ ያስቆጠረች ቢሆንም የፈጸመችው ድርጊት በተመሳሳይ ሁኔታ የቆየች እንደሚመስል ፖሊስ ግምቱን የሰጠ ሲሆን  ስለሰራተኛዋ ማንነትና የቀደመ ተግባር ምርመራ ለማድረግ የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ለፍርድ ቤቱ በማመልከቱ ለታህሳስ 8/2014 እንዲያቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል። ሕጻኗ በደረሰባት ጭካኔ የተሞላበት ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባት ቢሆንም እስካሁን ህክምና እየተደረገላት በሕይወት እንደምትገኝ ታውቋል።
ሕጻናት የተለየ ክብካቤና ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው ቢሆንም ዓለም በምታስተናግደው የሥነ ልቡና ማኅበራዊ ቀውስ የተነሳ ለጥቃት እየተጋለጡ ይገኛሉ። ፍሪሃ እግዚአብሔር የሌለው ትውልድ ከሥነ ምግባር ውጪ በመሆን ለማኅበራዊ ኑሮ የአስተሳሰብ ቀውስ መጋለጡ አይቀሬ ነው። አሳዛኝና አስነዋሪ ድርጊት የመፈጸሙ ምክንያትም ይህ ነው።  በየቤታችን ለሕጻናት፤ በየአካባቢው ለሴቶችና ለታዳጊ ወጣቶች፤ ለአረጋውያንና ረዳት ለሌላቸው የምናደርገውን ክትትልና ቀና ድጋፍ በማጎልበት «የአባቴ ብሩካን» ተብሎ የተነገረውን የሕይወት ዋጋ ለማግኘት ዛሬውኑ እንነሳ!!

«ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደ ሆነ፥ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ» 1ኛ ጴጥ 2፤2



Friday, November 21, 2014

ፍሪማሰንሪ /freemasonry/ ምንድነው?




ከዚህ በፊት በአንድ ጽሁፍ «ስለኤርያ 51» አጭር ምስጢራዊ ጽሁፍ ማስነበባችን ይታወሳል። አሜሪካና ዲሞክራሲ፤ ሥልጣኔና አሜሪካ መሳ ለመሳ ናቸው። እንደዚሁ ሁሉ ሌላው ዓለም ይቅርና የሀገሪቱ ዜጋ የማያውቃቸው ብዙ ምሥጢሮችም ያሉባት ሀገር ናት። ላይ ላዩን በዲሞክራሲው ዕድገት ጫፍ ረግጫለሁ በማለቷና በሥልጣኔውም መጥቄአለሁ እያለች ከመለፈፏ ጀርባ ብዙ ጉድ እንዳዘለች ብዙው ሰው አያውቅም፤ ቢያውቅም ትኩረት አይሰጠውም።  በነገረ መለኮት የበሰሉና የትንቢቱ ፍጻሜ ሰዓት መድረሱን በደንብ ያጠኑ ምሁራን ግን አሜሪካንን «ታላቂቱ ባቢሎን» ይሏታል። ምክንያቱም በአደባባይ ከሚታወቅላት የዲሞክራሲውና የሥልጣኔው እርከን ባሻገር የተሸከመችው ጉድ የት የለሌ ነውና። ሁሉም ነገር ከብረት በጠነከረ ምስጢርና ከምስጢሩ አጠባበቅ ጋር ሕይወት በሚያስከፍል ዋጋ፤ የረቀቀ መዋቅር በተዘረጋበት ሥርዓት የምትመራ ሀገር በመሆኗ እያወቁ ወይም ሳያውቁ ታደነዝዛለች።  በህጋዊ ደረጃ ከ«Church of Satan” አንስቶ እስከመጨረሻው ክሂዶተ እግዚአብሔር  «Atheism” ድረስ በነጻ የሚንቀሳቀሱባትና ለዓለሙ ሁሉ ማዕከል ሆና የምታገለግለዋ አሜሪካ ጾታን በመቀየር እንዲሁም የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻንም በመፍቀድ መሪ በመሆን ታገለግላለች።

      ሌላው ቀርቶ በየዓመቱ የሚከበረውን የሀለዊን /Halloween/ በዓል ጥቅምት/31 ቀን ከጫፍ ጫፍ በማክበር አሜሪካንን የሚቀድማት የለም። ለነገሩ «ሀለዊን» የሞቱ ቅዱሳንን ለማሰብ በሚል ይጀመር እንጂ ድርጊቱ የሙት መንፈስ የሆነውን ሰይጣንን ለማሰብ የተሰራ ለመሆኑ የድርጊቱ ክንዋኔ ያስረዳል። የሚያስፈራ ምስልና ቅርጽ፤ ጥርሱ ያገጠጠ፤ ዓይኑ ያፈጠጠ፤ አጽሙ  የተቆጠረ ማስጠሎ ነገር ለብሶ ወይም አጥልቆ  ሰውን በማስደንገጥና በማስፈራራት ቅዱሳንን ማክበር ነው ቢባል እንዴት ሊሆን ይችላል? ለነገሩ ቅዱሳንን ተጠግቶ ይህንን ማድረጉ ራሱን የቻለ ሌላ ምስጢር ስላለው እንጂ ቅዱሳንን ስለሚወክል አይደለም። (የዚህን ምስጢር ፍቺ በዚህ ጽሁፍ ቀጣይ ክፍሎች ለመዳሰስ ይሞከራል) አሜሪካ ለመጨረሻው ዘመን የተዘጋጀችና ለጥፋት ነጋሪት የምትጎስም ሀገር በመሆንዋ ነገሩ ሁሉ እየተበላሸ ሄዷል። ባለፈው ጥቅምት 31/ 2014 ዓ/ም በሚዙሪ፤ ሴንት ሉዊስ ከተማ ዓለም አቀፍ የ«ሀሎዊን» በዓል እንደሚደረግ የተላለፈው የጥሪ ምስል እንደሚያሳየን የጨለማውን ኃይል ካልሆነ በስተቀር ሌላ ማንን ሊሆን ይችላል? እስኪ ምስሉን አይተው ግምትዎን ይስጡ!!
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነን አሜሪካ ከምታስተናግዳቸው እንግዳ ነገሮች አንዱ ክፍል ስለሆነው ስለ«ፍሪማሰንሪ»/freemasonry/ ውቅያኖስ ታሪክ ጥቂቱን በጭልፋ ልናካችላችሁ ፈልገን ነው። ምክንያቱም የአንድ ዓለም አገዛዝ /One World Order/ እንዴት እየሰራ እንዳለ በማወቅ ከሚመጣው የስህተት መንፈስ እንድንጠበቅ አበክረን ለማስገንዘብ ነው። በዚህ ዙሪያ ምሁራኑ በሀገርኛ ቋንቋ ጽፈው በሰፊው እስኪያስነብቡን ድረስ ለጥንቃቄ እንዲበጅ በጥቂቱ እንዲህ አቅርበነዋል። መልካም ንባብ!

ፍሪማሰንሪ ምንድነው?

     «ማሰን» የሚለው ቃል ከላቲኑ / machio/ ከሚለው ቃል የተወረሰ ነው።  ትርጉሙም «ድንጋይ ጠራቢ ፈላጭ ወይም ግንበኛ  ማለት ነው።  ቃሉም ከ1155 እ,ኤ,አ ጀምሮ አገልግሎት ላይ ውሏል። freestone-mason ማለት «ነጻ ድንጋይ ጠራቢ፤ ግንበኛ ሰው ማለት ሲሆን ይህም ስያሜ በዚህ ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች «free mason» ፍሪማሰን በሚል አኅጽሮት አገልግሎት ላይ እንደዋለ በ1908 ዓ/ም የታተመው የፍሪማሰን ዜና መዋዕል መጽሐፍ ያስረዳል።  የላቲኑን ውርስ ቃል ተከትሎ “free” እና “mason” ከሚለው የእንግሊዝኛ ጥምር ቃላት የተገኘው ይህ ስያሜ ድንጋይ የመጥረብ፤ የመቁረጥና የመገንባትን ድርጊት ሲያመለክት «ፍሪማሰንሪ» /freemasonry/ ይባላል።  ይህም በነጻ ፈቃድ፤ በራስ ውሳኔ ዓለቱን ጠርቦ የማይነቃነቅና የማይናወጥ መሠረት ያለው ግንብ የመገንባት ዓላማ ነው ማለት ነው።  

«ፍሪማሰን» የተባለው ስያሜ በግንበኝነት ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች በተናጠል ሲጠሩበት የቆየ ቢሆንም ከ14ኛው ክ/ዘመን መጨረሻ ጀምሮ በአውሮፓ የህንጻ ምህንድስና ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች በጥቂት ሰዎች ተደራጅተው ራሳቸውን የመጥራት እንቅስቃሴ ጀምረው ነበር። ይሁን እንጂ የማሰን የተናጠል እንቅስቃሴ ቀደም ሲል እንደነበረ ቢሆንም ድርጅታዊ ሕግና ፒራሚዳዊ የብቃት የእርከን ደረጃ ወጥቶለት የተመሰረተው በ1717 ዓ/ም በለንደን ከተማ ነው።። በ1731 በአሜሪካ ፤ በ1736 በስኮትላንድ መሰረቱን አስፋፋ። ከዚያም በ1725 በአየር ላንድ እንደተጀመረ ይነገራል።  አሜሪካ ውስጥ የተቋቋመው በጣም ደርጅቶና ጎልብቶ ዓለም ዐቀፍ ቅርጽ ለመያዝ በቅቷል። 

      ይህ የፍሪማሰን ማኅበር የአውሮፓን የኢንዱስትሪ አብዮት ተጠግቶ የተመሰረተው የህንጻና የምህንድስና ባለሙያዎችን የያዘው እንቅስቃሴ ቅርጹንና መልኩን ለውጦ በሰው አእምሮና አስተሳሰብ ላይ እንደህንጻ የሚያድግ ግብረገብነትን፤ በጎ አድራጎትንና  መልካም ስብእና ያለው ሕብረተሰብን የመፍጠር ዓላማ ባለው መመሪያ ላይ ራሱን በማቆም ሕግና ደንብ አውጥቶ መሥራት መጀመሩን የተጻፈ ታሪኩ ያስረዳል። 

  ምንም እንኳን የፍሪማሰንሪ ማኅበር በኦፊሴል ከአምልኮና ከፖለቲካ አስተሳሰብ ነጻ ነኝ ቢልም በ1723 እና በ1738 ዓም ተሻሽሎ በወጣው የፍሪማሰንሪ ሕገ መንግሥት ላይ እንደተመለከተው የሁሉም ነገር ንድፍ / architect/ ባለቤት «እግዚአብሔር ነው ስለሚል እንቅስቃሴው ሃይማኖት ለበስ እንደሆነ ፍንጭ ከመስጠቱም በላይ ድርጅቱ የራሱ የሆነ ዶግማና መመሪያ ስላለው የእምነት ድርጅት አይደለሁም የሚለው አባባሉ ተቀባይነት እንዳይኖረው አድርጓል።  ድርጅቱ የአንድ ወጥ የሃይማኖት ተቋም ላለመሆኑ እንደመከራከሪያ የሚያቀርበው ጭብጥ የፍሪማሰንሪ አባል ለመሆን  የየትኛውንም ሃይማኖት ተከታይ ወይም የሃይማኖት መጽሐፍ ተቀባይ ወይም የትኛውንም የፖለቲካ መስመር የያዘ ሰው በአባልነት መቀበል መቻሉን በማስረጃነት ያቀርባል።  ድርጅቱ ይህንን ይበል እንጂ አባል የሚሆን ሰው ቀድሞ የነበረውን እምነቱን ይሁን አመለካከቱን እንዲጥል ሳይገደድ የፍሪማሰንን አስተምህሮና ሕግ በተከታታይ ተምሮ በድርጅቱ የረቀቀ አስተሳሰብ ውስጥ እንዲሰጥም ማድረግ በራሱ ቀድሞ የነበረውን የማስቀየር ዘዴ እንደሆነ በተሞክሮ ያዩት ሰዎች በተግባር ያረጋገጡት ሀቅ ነው።

    እንደፍሪማሰንሪ አባባል የጥበቦች ሁሉ /Architect/ የንድፍ ባለቤት እግዚአብሔር ሲሆን ያገኙትን ጥበብ ወደተግባር የሚለውጡት ደግሞ የፍሪማሰንሪ እውቀት የተሰጣቸው ሰዎች ናቸው ይላሉ። ለምሳሌም የኖኅ መርከብ የተሰራቸው በኖኅ የፍሪማሰን እውቀት ነው። የባቢሎን ግንብ ይሁን የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ያለፍሪማሰን እውቀት ፍጻሜ አያገኝም ነበር ባዮች ናቸው። የግብጽ ፒራሚዶች የፍሪማሰን ጥበብ ውጤት ነው። የኖስቲኮች እውቀት፤ የግሪክ ፍልስፍና፤ የፓይታጎረስ ስሌት፤ የዞሮአስተር ትምህርት፤ የቻይና ጥበብ፤ የአልኬሚስቶች ፈጠራ ሁሉ በፍሪማሰን እውቀት ጎልምሶ ወደተግባር የተለወጠ መሆኑን ያምናሉ። 

   ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ሲመለመል የትኛውንም ሃይማኖት የሚከተል ወይም የትኛውንም የሃይማኖት መጽሐፍ የሚቀበል ሰው መሆኑ ችግር የለውም። እንዲተውም አይጠበቅም። ቁምነገሩ አንድ ጊዜ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ከሆኑ በኋላ ድርጅቱን መልቀቅ እንደማይቻል ወይም በምክንያት ከለቀቁ ደግሞ የቆዩበትን የድርጅቱን ምስጢር ማውጣት የሞት ዋጋ እንደሚያስከፍል አስቀድሞ ቃለመሃላ ይፈጽማል። ፍሪማሰንሪ በስብከትና በድለላ የአባልነት ምልመላ አያደርግም። አብዛኛው የዚህ ድርጅት አባላት ፕሬዚዳንቶች፤ ጠቅላይ ሚኒስትሮች፤ ዶክተሮች፤ ፕሮፌሰሮች፤ ጀነራሎች፤ ዳኞች፤ የሴኔትና የምክር ቤት አባላት፤ ቢሊየነሮች፤ ታዋቂ ሰዎችና ከፍተኛ ነጋዴዎች ናቸው። ከአሜሪካ 44 ፕሬዚዳንቶች ውስጥ 14ቱ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባላት እንደነበሩ በግልጽ ሲታወቅ  ከተቀሩትም ውስጥ በምስጢራዊ አባልነት የነበሩ እንዳሉ ይነገራል።

ፍሪማሰንሪ ካሉት 330 (ሠላሳ ሦስት ድግሪ) ማእርጋት አንዱ በሆነው የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ የተወሰኑ ትምህርቶችን አስቀድሞ ከወሰደ በኋላ ወደድግሪ ትምህርቱ ሲገባ ይህንን መሃላ ይፈጽማል።

« ዛሬ የፍሪማሰንሪ አባል ከሆንኩ በኋላ አባል ለሆንኩበት ድርጅት ካልታመንኩ ወይም ብከዳ ወይም ምስጢር ባወጣ በጎሮሮዬ ላይ ስለት ይረፍ፤ ምሳሴ ከስሩ ተነቅሎ ይጣል፤ አጽሜ አመድ ሆኖ ከውቅያኖስ የጥልቁ አሸዋ ውስጥ የተሰወረ ይሁን» ይላል። ለምን?

የፍሪማሰንሪ ዓርማና ሌሎች ምልክቶች ምንድናቸው? ከኢሉሚናቲ ጋር ያላቸው ግንኙነት ምንድነው? ይህንንና ሌሎች ምስጢሮችን በቀጣይ ክፍል ለማቅረብ እንሞክራለን።