Thursday, May 29, 2014

በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነ ጳጳሳቱ አድማና የማኅበረ ቅዱሳን ጣልቃ ገብነት በአቡነ ማትያስ ላይም ቀጥሏል!

ከሊቃነ ጳጳሳቱ ግማሾቹ የራሳቸውን የጉባዔ ላይ የድምጽ ጡንቻ በማፈርጠም ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ከሚመስሏቸው ጋር የመቀናጀት ጠባያቸው ከምንኩስና ጀምሮ የተዋረሳቸው እንጂ ድንገት የተከሰተባቸው ዐመል አይደለም። ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ደግሞ ከዚህ ፈርጣማና  ጠንካራ የቡድን  አቅም መፍጠር ከቻሉት ጋር መለጠፍ የሚፈልጉት አንድም ብቻቸውን መዝለቅ እንደማይችሉ ስለሚያውቁ፤ በሌላ መልኩም ሊመጣ ይችላል ከሚሉት ጥቃት ራሳቸውን ለመከላከል ከመፈለግ ራስን የማዳን ዘዴ የተነሳ ነው። ጥቂቶች ቢሆኑም አንዳንዶቹ ደግሞ ያልሆነ ንትርክና ጭቅጭቅ እንዲነሳ የማይፈልጉ፤ ዝም ብለው በመመልከት ታዛቢ የሚመስሉ በእድሜ የገፉ ሲሆኑ በጣት የሚቆጠሩት ደግሞ ስለቤተክርስቲያን የሚገዳቸው ነገር ግን ድምጻቸው ብዙም የማይሰማላቸው ናቸው።
 የቡድን ኃይል መፍጠር የቻሉት አብዛኛዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት የወጣትነት ዐመል ብዙም ያልራቃቸው፤ በቂ ኃብት ማከማቸት የቻሉ፤ ለተሸከሙት ማዕርግ ሳይሆን ለስምና ለዝና የሚጨነቁ በተለይም ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ንክኪ ያላቸው ናቸው። እነዚህኞቹ ለቤተ ክርስቲያን የሚታይ፤ የሚጨበጥ፤ ለትውልድ የሚተላለፍ ቋሚ ቅርስና ሀብት መፍጠር ያልቻሉ ነገር ግን በምላስ የሰለጠኑ፤ እምቢተኝነትና ቡድንተኝነት እውቀት የሚመስላቸው ናቸው። ቤተክርስቲያን መታመስ የጀመረችው እነዚህኞቹ ቅዱስ ወደተባለው ሲኖዶስ የመቀላቀል እድል ካጋጠማቸው በኋላ ነው። ማኅበረ ቅዱሳንም ከሀገር ቤት እስከ ውጪ ሀገር ድረስ በቤተ ክርስቲያኒቱ መልክና ቁመና ስሩን የሰደደው በእነዚህኞቹ ጀርባ ታዝሎና ተንጠላጥሎ ነው።
የቀድሞውን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እግር ተወርች አስረው አላሰራ ሲሉ የነበሩት እነዚህ ቡድንተኞች ዛሬም አንድ ግንባር ፈጥረው እድሜ ካላስተማራቸው አረጋውኑ መካከል ጥቂቶቹን አሰልፈው ማኅበረ ቅዱሳንን ከጀርባቸው አቁመው ፓትርያርክ ማትያስንም በተመሳሳይ መልኩ አላሰራ፤ አላንቀሳቅስ፤ አላላውስ እያሏቸው ይገኛል። በዚህ መልኩ የት ድረስ መጓዝ እንደሚቻል ለመገመት አይከብድም። ነገር ግን «ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም» እንዲሉ አበው መላ መፈለግ ፓትርያርክ ማለት «ርእሰ አበው» ማለት እንደመሆኑ መጠን የተሰጠውን ሥልጣን ለቡድንተኞች አስረክቦ የተነገረውን የሚቀበል ተላላኪ ማለት ባለመሆኑ ሥልጣኑ ሙሉዕ መሆኑን ማመን የግድ ይሆናል። ስለዚህ በአድመኝነት፤ ለማኅበሩ ወግነው አላሰራ ለሚሉ ምን መደረግ አለበት?  ነገሮች እየጠሩ፤ የችግሩም ገፈት ከላይ ካልተወገደ በስተቀር ተለባብሶ የትም አይደረስም። ቤተ ክርስቲያንም አትድንም፤ ባለማዕርጎቹም በዘመናቸው ንስሐ አይገቡም። ስለዚህ የማያወላዳ እርምጃና ውሳኔ ያለምንም ማቅማማት መውሰድ የግድ ይላል። ጥቂት ነጥቦችን እናንሳ።
1/ ከአድመኞቹ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብዙዎቹ ቃል የገቡበትን መሃላ አፍርሰው የቤተ ክርስቲያኒቱ ተጠሪ ነን ካሉ በኋላ ደመወዝተኛ፤ አበልተኛና የጥቅሟ ተከፋይ ሲያበቁ መንፈሳዊነቱን ክደው፤ ሀብት ንብረት አፍርተው ፤ እንደዓለማውያኑ የሚሊዮን ብር ቤቶችን የገነቡ፤ በባንክ ያከማቹ ስለመሆናቸው መረጃና ማስረጃ የሚቀርብባቸው ስለሆነ በሊቀ ጳጳስነት ማዕርግ የእግዚአብሔርን መንግሥት ብቻ ለማገልገል  ብቃት የሚጎድላቸውና «ለሁለት ጌቶች መገዛት አትችሉም» ያለውን የወንጌል ቃል ያፈረሱ ስለሆነ ከያዙት ማዕርግ ተሰናብተው ወደዓለማዊ ሀብታቸው እንዲሄዱ ሊሸኙ ይገባል።
2/ ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ቃለ መሃላ ከፈጸሙበት «ኩሎ ኀደግነ» ሁሉን ትተን ተከተልንህ ካሉ በኋላ በቀጥታ ያለሰማንያ ጋብቻ በትዳር ወልደው ከብደው የሚኖሩ፤ ገሚሱም በአዲሱ የቤተሰብ ህግ እንደተመለከተው « ትዳር በሚመስል ሁኔታ አብሮ መኖር ራሱ ጋብቻ እንደተፈጸመ ይገመታል» በሚል የህግ መንፈስ መሰረት አግብተው ዓለሙም፤ ሊቀጵጵስናውም ሁሉም ሳይቀርባቸው አጣምረው የያዙ ስለሆነ በእነዚህኞቹ «ጸሊማን አርጋብ»  ላይ በቂ ማስረጃ መቅረብ ስለሚችል በማያወላዳ ውሳኔ ለሌሎች ትምህርት ሊሆን በሚችል መልኩ ለትዳራቸው ታማኝ ሆነው እንዲኖሩ በክብር መሸኘት አለባቸው።
3/ ለዚህ ጥሩ አብነትና ምሳሌ ሊሆን የሚችለው በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከዚህዓለም በሞት የተለዩት የአቡነ ሺኖዳ አስተዳደር ተጠቃሽ ነው። ሊቃነ ጳጳሳት የራሳቸውን ሀብት ማፍራት አይችሉም። መነኮሳት ከመነኮሱበት ገዳም ውጪ ሌላ ገዳም በፍጹም አይቀበላቸውም። ከገዳሙ ከወጣ ምንኩስናውን እንደተወ ይቆጠራል። በሴት የተጠረጠረ መነኩሴ በቀጥታ ተጠርቶ ይጠየቃል እንጂ እንደኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተሸፋፍኖ ያሻውን እንዲፈጽም እድል አይሰጠውም። መረጃና ማስረጃ ከቀረበበት ቀሚሱን ከታች አንስቶ፤ እስከ አንገቱ ድረስ መሃል ለመሃል በመቀስ ቀደው መቋቋሚያ ገንዘብ ሰጥተው ሕዝባዊ እንዲሆን ያሰናብቱታል። ይህ ለሌላው ትምህርት፤ ለቤተ ክርስቲያንም ክብር ይሆናል። ነገር ግን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለው ነገር በዚህ ዘመን አሳፋሪ ሆኗል። ከሊቃነ ጳጳሳቱ ትዳር የመሰረቱ ሞልተዋል። የመነኮሳት ነጋዴ መሆናቸው ሳይታወቅ ሚሊየነር ሆነዋል። ዝሙትና ስርቆት ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደነቀዝ እየበላት ነው። በዚህ መልኩ ከቀጠለች የቤተ ክርስቲያኒቱ ኅልውና አስጊ ነው። እዚህ ላይ ከነጋ ድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ መጽሐፍ ጥቂት ቃል እንዋስ። «እግዚአብሔር መንግሥታችንን፤ ቤተክርስቲያናችንን ለባዕድ አሳልፎ አይሰጣትም እያለ ሕዝባችን በስንፍና ያለሥራ ይኖራል» እውነትም ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር ከጥፋት ተከላከለን፤ ነገር ግን እኛ ለቸርነቱ የተገባውን ሥራ ሠርተን በተግባር አላሳየንም» ብለዋል ነጋድራስ በጽሁፋቸው ከዛሬ ሰማንያ ዓመት በፊት።  ይሁን እንጂ ዛሬም ከስንፍናችን ፈቀቅ አላልንም። እግዚአብሔር ራሱ ይጠብቅ ብለን እኛው ያጠፋናትን ቤተ ክርስቲያን እንደባለእዳ ትተንለታል።
4/ ማኅበረ ቅዱሳን ማነው? የማነው? ምንድነው? ብዙ የሚያጠያይቅ ጉዳይ ነው። የጠራና የማያሻማ መልስ ያስፈልገዋል። ተለባብሶ በበግ ለምድ ተሸሽጎ አይዘለቅም። ስለማኅበረ ቅዱሳን ጥብቅና የሚቆም ማንም ቢኖር የማኅበሩ አባል የመሆን መብቱ የተከበረ ነው። ነገር ግን ሊቀጳጳስ ከሆነ በኋላ ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን የሲኖዶስ አባልነት ሥልጣን ይዞ የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን አይችልም። መሆን ከፈለገ ጵጵስናውን ማስረከብ አለበት።  አንድ ሚኒስትር የኢህአዴግ ምክርቤት አባልና የሰማያዊ ፓርቲ አባል በአንድ ጊዜ መሆን አይችልም። አንዱን ይተዋል፤ ወደአንዱ ይጠጋል እንጂ። ይህንን ለማስተካከል የፓትርያርኩ ሥልጣን ምሉዕ ነው። እነዚህ በሁለት ልብ ሲኖዶሱን የሚያውኩ ጳጳሳት በህግ አግባብ ካልተወገዱ የሲኖዶስ ሕውከት ማብቂያ አይኖረውም። ስለማኅበረ ቅዱሳን የሚከራከር ሊቀጳጳስ ከሲኖዶስ አባልነቱ ወደታች ወርዶ የተራ ማኅበር ደጋፊ ከሆነ ማዕርጉን ተገፎ  በማኅበር አባልነቱ እንዲቀጥል ከሲኖዶስ ሊባረር ይገባዋል።
5/ ፓትርያርክ ማትያስ ቆምጨጭ ያለና እርምት የሚሰጥ እርምጃ ከመውሰድ ውጪ በእንደዚህ ዓይነት የአድማና የቡድን ጭቅጭቅ እየተሰላቹ የትም አይደርሱም። ሊቀጳጳስ የሚባለው ማዕርግ ሊከበር የሚችለው ራሱ ማዕርጉን የተሸከው ሰው አክብሮ፤ የሚያስከብር ሥራ ሲሰራበት ብቻ ነው። ሹመትማ ይሁዳም ከሐዋርያት አንዱ ነበር። ነገር ግን ጥፋት እንጂ ልማት አልሰራበትምና ሐዋርያ መባሉ ቀርቶ «ሰያጤ እግዚኡ» ከመባል አልዳነም። ስለዚህም ቤተ ክርስቲያንን ከመሸጥ የማይመለሱ እነዚህ አድመኞች ሊቃነ ጳጳሳት ሻጮች ቢባሉ ምንም አያስነውርም። ስም መጥቀስ አያስፈልግም እንጂ እነማን ማናቸው? ምን አደረጉ? ምንሰሩ? በደንብ ይታወቃል።
6/ ቤተ ክርስቲያንን ከውድቀት ለማዳን፤ ማዕርጋት ዋጋና ክብር እንዲኖራቸው ለማድረግ ሲባል ያልተፈለገ ነገር ግን አስገዳጅ እርምጃ እስከመውሰድ የሚዘልቅ ክስተት መፈጠሩ አይቀርም።  ፓትርያርክ ከሆኑ በኋላ ከሚቆጠቁጠው የመንፈሳዊ ኅሊና ቁጭትና ከታሪክ ወቀሳ ለመዳን መስራት የሚገባውን ሁሉ ካልሰሩበት ማዕርጉን ተሸክሞ መቀመጥ በቤተክርስቲያን ውድቀት ላይ መተባበር በመሆኑ ሹመቱን አስረክቦ የራስን ነጻነት ማወጅ የተሻለ ነው።
በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነጳጳሳቱ አድማና የማኅበሩ ሴራ በአቡነ ማትያስም ላይ የሚቀጥለው  እስከመቼ ነው?
 አቡነ ማትያስ አርፈው የማኅበሩ አባል ሊቀ ጳጳስ ሌላ ፓትርያርክ እስኪሆን ድረስ ይህ ውጊያ አያቆምም።

Thursday, May 22, 2014

ግዝት(ውግዘት)…ኑፋቄ….መናፍቅነት…ግዝት-ዘበከንቱ… እና ወፈ-ገዝት መሆን!


 ( በአማን ነጸረ )
1. ግዝት(ውግዘት)፡ ማለት አንድ ምዕመን(አማኝ) በአፉ ክርስቲያን ነኝ ቢልም በተግባር ከሃይማኖት ወጥቶ ከበጎ ምግባር አድጦ(ተዛንፎ) ሲገኝ ከማኅበረ ምዕመናን እንዲለይ በስልጣነ-ክህነት የሚፈጸም መንፈሳዊ ቅጣት ነው፡፡
2. የውግዘት ዓላማ፡(ሀ)ቤ/ክ እንዳትረክስ፣(ለ)ኑፋቄው ወደ ሌሎች እንዳይዛመት፣(ሐ)ተወጋዡ በንስሐ እንዲመለስ እድል ለመስጠት ነው፡፡
3. የውግዘት ቅድመ-ሁኔታዎች፡(ሀ)ተጠርጣሪው ከሃይማኖት እና/ወይም ከበጎ ምግባር መውጣቱን ማረጋገጥ፣(ለ)ከጥፋቱ/ከክህደቱ እንዲመለስ ደጋግሞ መገሰጽና መምከር፣(ሐ)ተመክሮ ካልተመለሰ በስልጣነ-ክህነት አውግዞ መለየት፣(4)ውግዘቱ እንደጥሰቱ ዓይነት ከማዕረግ ዝቅ ማድረግ ወይም ስመ-ክርስትናን ነጥቆ መለየት ሊሆን ይችላል፡፡ከዚህ በኋላ ድርጊቱ-ኑፋቄ ተወጋዡም-መናፍቅ ይባላሉ፡፡በነገራችን ላይ ምንፍቅና የሚል ቃል በየመጻህፍቱ አላየንም፡፡በግእዙ ኑፋቄ ነው የሚባለው፡፡በአማርኛ መናፍቅነት፡፡
4. ግዝት-ዘበከንቱ እና ወፈ-ገዝት መሆን፡ ከላይ ያሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ያላሟላ ግዝት ግዝት-ዘበከንቱ ሲባል ገዛቹም ወፈ-ገዝት ይባላል፡፡ነገር ግን ተጠርጣሪው በግልጽ የተወገዘ ሃይማኖትንና ምግባርን ሲያራምድ ያገኘነው እንደሆነ መናፍቅ ብንለው ፍርድ የለብንም፡፡
5. ከንቱ እና ከንቱ አንድ ወገን ብለን ስለመርገም ዘበከንቱም እንናገር፡ ሀቅ ላይ ያልተመሰረተና የሚረገመውን ሰው ህሊና የመውቀስ አቅም የሌለው ከንቱ እርግማን በመጽሐፈ ምሳሌ 26 ቁ 2 እንደተገለጸው….እንደሚተላለፍ ድንቢጥ፣ወዲያና ወዲህም እንደሚበር ጨረባ እንዲሁም ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም፡፡ፍትሐ ነገስቱም በአንቀጽ 11 እንዲህ አይነቱን ረጋሚ “ወኩሎ ዘይረግም ይረግም ነፍሶ” ይለዋል::
ምንጭ፡ (1) መርሐጽድቅ ባህለ ሃይማኖት በ1988 ዓ.ም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የታተመ ገጽ 157 እስከ 161 ፣ (2)የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ-237፣ (3) ጥቅሶች፡ ማቴ 18 ቁ 15-18፣2ተሰ 3ቁ14፣ቲቶ 3 ቁ 11፣1ጢሞ 1ቁ 19፣2ጢሞ 2 ቁ 17፣1ቆሮ 5 ቁ 5፣2ቆሮ 2 ቁ 6
መነሻ፡ በ40 ቀን ያገኘነውን ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ባልተሰጠ ስልጣነ-ክህነት ሊነጥቁ የሚሞክሩ ወፈ-ገዝት ወንድሞቻችን!!

Sunday, May 18, 2014

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል የጉባዔ ተግዳሮት እንደሚገጥማቸው ይጠበቃል!





የዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ከመቼውም ጊዜ የተሻለ ምስጢራዊነቱን የጠበቀ እንዲሆን ተሞክሯል። ይህ ማለት ግን ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰወረ የአጀንዳ፤ የውይይት ሂደትና የውሳኔ እልባት ነበረ ማለት አይደለም። ምስጢራዊነቱ  የቤት ልጅ ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ለአብዛኛዎቻችን እንዲጠበቅ ያስፈለገበት ዋና ምክንያት በቅዱስ ፓትርያርኩ በተሰጠ የቅድመ ጉባዔ መመሪያ ቢሆንም በአንጻሩ ማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱም ምስጢራዊነቱ ቢጠበቅ የኅልውና ጉዳይ የባቄላ ወፍጮ እንዳይሆን ከመፈለግ የተነሳ እንደሆነ ውስጥ አዋቂ ምንጮች ግምታቸውን ያስቀምጣሉ። ምክንያቱም የዘንድሮው የጉባዔ ሂደት የማኅበሩን የሁለት ዐሥርተ ዓመታት ጉዞ ወሳኝ በሆነ መልኩ የሚመለከት ጉዳይ ከመኖሩ የተነሳ ምስጢራዊነቱ እንዲጠበቅ አስፈልጓልም በማለት ያክላሉ።
ቅዱስ ፓትርያርኩን ከገጠሟቸው ተግዳሮቶች አንዱ «ማኅበረ ቅዱሳን በምን ሕግና መንገድ ሊተዳደር ይገባዋል» በሚለው አንገብጋቢ ጉዳይ ላይና አዳዲስ ሊሾሙ በሚችሉ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ላይ የተያዘው የሁለት ወገን ሰልፍ ምክንያት እንደሆነ ይነገራል።
አንዱ ሰልፍ  በቅዱስ ፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል የሚነሳው ሃሳብ የማኅበሩ እንቅስቃሴ ከሰላምና ከፍቅር ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ የምትታወክበትና ያልተፈለገ እሰጥ አገባ ውስጥ የምትዘፈቅበት ምክንያት ስለበዛ እንደማኅበር መቆየት አለበት የሚያሰኝ አመክንዮ ባይኖርም እንኳን እንዲኖር ካስፈለገ አቅሙንና ደረጃውን አውቆ፤ እንቅስቃሴው ከአቅሙ ጋር ተገናዝቦ በተወሰነ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ ኅልው እንዲሆን የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣለት ጥብቅ ፍላጎት ያላቸው መሆኑ ነው።
ሁለተኛው ሰልፍ ደግሞ የማኅበሩ አባላት በሆኑ ሊቃነ ጳጳሳትና ማኅበሩ ራሱ በስለላ መዋቅሩ በኩል በሚያካሂደው የሩጫ ዘመቻ የተነሳ ያለው ሰልፍ ሲሆን ይህም ሲከናወን የቆየውን ስልት ማስቀጠል የሚያችል ልዩ መብት በራሱ ሰዎች በኩል አርቅቆ ለማስጸደቅ መቻል ነው። ይኼውም ማኅበሩ እስካሁን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር በተመሳሳይ የዘመቻ ስልት አፈንግጦ የወጣበትና በሥራ አስኪያጁ ስር እንዲቆይና የራሱን ኅልውና ለማቆየት አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣ የተሰጠውን የቆይታ ጊዜ ባለመጠቀሙ በዚህ ጉባዔ ላይ በሚፈልገው የጊዜ መግዢያ መንገድ የመቋጨት ዓላማ እንዳለው ከውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን ለማወቅ ተችሏል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ጉዳይ የአዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሲሆን ማኅበሩና ታዛዥ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት በሁለት መንገድ እየተሰናሰለ ለማስኬድ እየተሞከረ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ። ይኼውም በእነሱ ምርጫና አጽዳቂነት ተመልምለው ለሲኖዶስ መቅረብ የሚገባቸውን የመለየት ስራ ያከናወኑ ሲሆን በፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል ሊቀርቡ የሚችሉ ነገር ግን ለማኅበሩ ኅልውና ስጋት ሊሆኑ እንደሚችሉ ቅድመ ግንዛቤ የተያዘባቸውን አስቀድሞ ውድቅ የማድረግ ስልት መያዙም ሌላኛው እቅድ ስለመሆኑም ይነገራል። በተለይም እንደአባ ሠረቀ ብርሃን ወልደሳሙኤልና መሰል ተቃናቃኞች በምንም ዓይነት መንገድ ቢሆን ከእጩዎች ዝርዝር ውስጥ መግባት እንደሌለባቸው በማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል በጥቁር መዝገብ ውስጥ የሰፈሩ ናቸው። በሌላ መልኩም ንቡረ እድ አባ ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ በሥራ ችሎታና ሙስናን በመዋጋት ጠንካራ ስለመሆናቸው ጥያቄ ባያስነሳም በማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ የማያጎበድዱ፤ ለሹመት ደጅ የማይጠኑና እጅ መንሻ  የማያቀርቡ በመሆናቸው ለእጩነት ችላ ከተባሉት መካከል ናቸው።  
በፓትርያርኩ በኩል ሊቀርቡ የሚችሉና ማኅበረ ቅዱሳን ዓይናቸውን ማየት የማይፈልጋቸው እጩዎችን ላለመቀበል በደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በኩል በሁለተኛነት የተያዘው ዘዴ  ደግሞ «እኛ ምን ሠርተን ነው፤ የአዳዲስ እጩዎች ምርጫ ለማጽደቅ እንዲህ የሚያጣድፈን ምክንያት የለም!»  የሚል ሲሆን ጊዜውን በማዘግየትና የምርጫውን በር በመዝጋት ያልፈለጓቸውን ሰዎችን ለማስቀረት እንደስልት መያዙ ነው።
በሌላ መልኩም ከፓትርያርኩ ስር የማይጠፉ ለዓመታት የጵጵስና ስካር እያንገዳገደ ያቆያቸው አንዳንድ መነኮሳት ሰርገው ለመግባት የሚያደርጉት ሩጫ ሳይጠቀስ መታለፍ የሌለበት ሆኖ ተገኝቷል። ለዚህ ማዕርግ ብቁ ስለመሆናቸው የምዕመናንና ምዕመናት ምስክርነት የሌላቸው እንዲሁም ያለደረጃቸው ካቴድራል የተሰጣቸው ጠልፎ በላዎችና ተሸክመው የመጡትን ዶላር መመንዘር የማይሰለቻቸው ደግሞ ጺማቸውን እየላጉ ጳጳስ ለመሆን ማስፈሰፋቸው ትኩረት የሚያሻው ነገር ነው።  ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በአንድ በኩል ሠርተው ማሰራት የሚችሉትን ወደእጩነት እንዳይቀርቡ በር በመዝጋት ላይ ሲተጉ በሌላ በኩል ደግሞ በጓሮ በር መግባት የሚፈልጉ እንደቅድስት ሥላሴው ጎረምሳ አስተዳዳሪና መሰል የሹመት ስካር የሚያንገዳግዳቸው የችሎታ ባዶዎች አሰፍስፈው መገኘታቸው ጉዳዩን አስቸጋሪም፤ አሳዛኝም፤ አሳፋሪም ያደርገዋል።

ስለዚህ ፓትርያርኩ ተግዳሮት ገጥሟቸዋል ስንል በእነዚህ ውስብስብ እንቅስቃሴዎች የተነሳ ሲሆን መወሰድ የሚገባው ርምጃም ትኩረት የሚያሻው፤ ካለፈ በኋላ የማይቆጭ መሆን ስለሚገባው አበክረን ማሳሰብ እንወዳለን።

አጭር ነገር ግን የትኩረት አቅጣጫን የሚለውጡ ግንዛቤዎች፤

1/ ማኅበሩ እንደፈለገና እንዳሻው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚናኝ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ማኅበሩ ማኅበር እንጂ የቅዱስ ሲኖዶስ ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤት ወይም የቤተ ክህነቱ የመምሪያ አካል አይደለም። ሲኖዶስ ስለአንድ ማኅበር ከዓመት ዓመት በአጀንዳ የሚነጋገርበት ምክንያት የለም። ስለዚህ፤
  ሀ/ ቢቻል ራሱን ችሎ ሥልጣን ባለው አካል ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ እንደማኅበር በሀገሪቱ ሕግ እንዲንቀሳቀስ  በነጻ መተው አለበት እንጂ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶለት በራሱ እጅ እየተለበለበ መቀጠል የለበትም።  «ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ» ያቃተው ለምንድነው? ስለዚህ በዚህ ጉባዔ ፓትርያርኩ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እልባት እንዲያገኝ ማድረግ አለባቸው። በቀጠሮ የነፍስ መግዢያ ጊዜ የሚጠይቁ አፍራሾችን መዋጋት አለባቸው።
 ለ/ ማኅበሩ በኛው ስር ሆኖ ቢሰራ ውጤታማ መሆን ይችላል የሚል ግምት ካለ ( ከታየው ተሞክሮ የተነሳ የተሳሳተ ግምት እንደሆነ ቢታወቅም) የማኅበሩን ያለፈ ታሪክ ገምግሞ ወደፊት ምን ሊሰራ ይችላል በሚል ግንዛቤ ስር ሰፊ ጥናት ተወስዶ በተገደበና በተወሰነ የመተዳደሪያ ደንብ  ተቀርጾ አቅሙን ለክቶ በመስጠት የማያዳግም መቋቻ ሊደረግበት ይገባል።
2/ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫ በተመለከተ፤ ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት የራሳቸውን የሲኖዶስ አባላት ቁጥር ከፍ የማድረግና የትኛውንም ውሳኔ በአብላጫ ድምጽ ሙሉ በሙሉ የመቆጣጠር ፖለቲካዊ ስልት ለማስፈጸም የፈለጓቸውን በጥቆማ የማቅረብ ሲሆን በዚሁ ተቃራኒ ደጋፊ ያልሆኑና ለኅልውናቸው ስጋት እንደሆኑ የሚታሰቡትን እጩዎች ደግሞ በልዩ ልዩ መንገድ የመከላከል ሁኔታ አለ። ስለዚህ ይህንን ማጤን አስፈላጊ ነው እንላለን።
3/  በሌላ መልኩም የማኅበሩንና የደጋፊዎቹን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ብቻ ሳይሆን በእጩ ምርጫው ዝርዝር ውስጥ ያልተፈለጉ ሰዎች እንዳይገቡ ማድረግ በፓትርያርኩ በኩል እጅግ ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ ነው። ስነ ምግባራቸው፤ እውቀታቸው፤ ችሎታቸው፤ የአስተዳደር ብቃታቸው፤ ተሞክሮአቸውና መንፈሳዊ ብስለታቸው ሳይታይ በብልጣብልጥ ዘዴና በገንዘብ አቀባባዮች የተጋነነ መረጃ የተነሳ ኤጲስ ቆጶስነትን ለማሸከም መሞከር ነገ ለሿሚው ኀፍረት፤ ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሸክምና ውርደትን ሊያስከትል ስለሚችል የሹመት ስካር ያጠቃቸውን የጥቅምትና የግንቦት ተስፈኞች መከላከል ትኩረት ያሻዋል።

በመጨረሻም ቅዱስ ፓትርያርኩ በማኅበሩ ዙሪያ እየያዙ የመጡት ግንዛቤና ስጋት የመሆኑን ደረጃ የመገንዘብ አቋም የሚደገፍና የሚበረታታ ነው። ቤተ ክርስቲያኒቱ ከማኅበሩ ያለኪሳራ አንዳች አላተረፈችም፤ አታተርፍምም። ማኅበሩ ግን ያለቤተክርስቲያኒቱ ከባህር የወጣ ዓሳ ነው። ስለዚህ የፓትርያርኩ ስልጣን አንድን ማኅበር ጥግ ለማስያዝ የሚያንስ አይደለም። በቤተክርስቲያኒቱ ከፍተኛው የስልጣን እርከን ላይ የተቀመጠ ፓትርያርክ ከሀገሪቱ ሕግ ጋር ተቀናጅቶ የሚያስቸግረውንና ለአስተዳደር እንቅፋት የሆነውን ክፍል በህግ አደብ ለማስያዝ የማንም ጳጳስ የጩኸት እርዳታ አስፈላጊው አይደለም።  
ያለበለዚያ በማኅበሩ ተግዳሮት እየቆሰሉ እስከሞት መቀጠል አለያም አሜን ብሎ እጅ በመስጠት ታማኝ ሆኖ የማገልገል ምርጫ ብቻ ነው ከፊት ለፊት ያለው። አቡነ ጳውሎስን እያታለለ እስከኅልፈታቸው የተዋጋቸው ማኅበር ዛሬም ውጊያውን አላቋረጠም። ግን እስከመቼ?