Tuesday, May 14, 2013

ኢህ አዴግ ምን ይጠብቃል?


ምድራውያን መንግሥታት በተወሰነ ጊዜ ውስጥ  ይመጣሉ፤ ይሄዳሉ፤ እስከምጽአት ቀን ሕዝቦች ግን በሀገራቸው ቋሚ ዘላቂ ትውልዶች ሆነው ይቀጥላሉ። ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ ውስጥ ከቅርብ ጊዜ በኋላ ሕዝቡን የሚያቃቅር፤ እርስ በእርሱ የሚያፋጅ፤ ጎሳ ዘርና ብሔር የሚለያይ፤ ሃይማኖታዊ ብጥብጥን የሚቀሰቅሱ ሁኔታዎች እየታዩ መሆናቸው ሀገራችንን ወዴት እየወሰዳት ነው ከሚያሰኝበት ደረጃ ላይ ደርሷል። የብሔሮች እኩልነትና የሃይማኖቶች ነጻነት ተከብሮባታል በተባለባት ኢትዮጵያ ውስጥ አሳዛኝ ሂደቶች እየታዩ ነው። በጭፍን ጥላቻ የትግራይን ብሔር የሚጠሉ እንዳሉ አማራውን ሁሉ እንደጨቋኝ የሚመለከቱ ሰዎችም የጥላቻ ዘር እየዘሩ መገኘታቸው ወደፊት ምን ዓይነት ሁኔታ ይፈጠር ይሆን ቢያሰኘን አግባብነት አለው ብለን እናስባለን። በሩዋንዳና በቡሩንዲ፤ በሴራሊዮንና በላይቤሪያ፤ በኮንጎና ኮትዲቯር የተከሰተው ፍጅት አሁን በሀገራችን ውስጥ እየታየ እንዳለው የብሔርና የጎሳ ጥላቻዎች ቀስ በቀስ እያደጉ የፈጠሩት ክስተት እንጂ ድንገት የደረሰ አይደለም። ስለዚህ ማዕከላዊ የኢትዮጵያ መንግሥት ዝም ብሎ የሚያየው እስከመቼ ነው? የሶማሌ ክልል ፕሬዚዳንት ሆኖ የፌዴራሉ መንግሥት አካል የሆነው ግለሰብ በአማራና በትግራይ፤ በአሮሞና በሌሎች ብሔሮች መካከል የዘር ፍጅት እንዲከሰት ለጎሳ መሪዎች ማብራሪያና መግለጫ መስጠቱን እንዴት በዝምታ ይመለከተዋል? አማሮችንና ኦሮሞዎችን ጥሉ፤ ትግሬዎችን ውደዱ ማለት ምን ማለት ነው? በአንድ ቀን ከስልጣን አስወርዶ በሕግ ቁጥጥር ስር የሚያስውለውን ይህንን ቅስቀሳ መንግሥት ዝም ማለቱ በቅስቀሳው ፈቃደኝነቱን አያሳይም?  ቃላት እየተተረጎመ ጋዜጠኞች ሕዝብን ለዐመጽ በማነሳሳት ወንጀል እስከእድሜ ልክ ሲፈረድባቸው ይህ የክልል ፕሬዚዳንት ሆኖ ዘር ከዘር ሊያፋጅ ትምህርትና ስልጠና ሲሰጥ ዝም የሚባለው ለምንድነው? ኢሳት የተባለው በውጭ ሀገር የሚገኘው ቴሌቪዥን ጣቢያ መረጃዎችን አግኝቶ ባያወጣው ኖሮ ውስጥ ውስጡን ይህ ቅሰቀሳና ዘመቻ  እንደማይኖር ምን ማረጋገጫ ይኖረናል? ኢሳትን ውሸታምና የቅጥረኛ ቴሌቪዥን ጣቢያ እያሉ ከማጣጣል ይልቅ የተባሉትን መረጃዎች አጣርቶ የሕዝቡን የጥያቄ ወይም የጥርጣሬ መንፈስ ማስተካከል አይሻልም? በበኩላችን የሀገራችን የሕዝቦች አንድነትና እኩልነት፤ ሰላምና ነጻነት የተከበረባት ኢትዮጵያ እንድትኖር ካለን ጽኑ ፍላጎት የተነሳ የሶማሌ ክልል ፕሬዚዳንት ኦሮሞና አማራ እርስ በእርስ የሚፋጁ ጠላቶች ናቸው፤ ትግሬዎች ግን ወዳጆች ናቸው ያሉበትን፤ የቅርብ ሠራተኛቸውና የሶማሌ ክልል ተወላጅ የሆነው ወጣት ለኢሳት የተረጎመውን ይህንን ቪዲዮ እንዳለ ለማቅረብ ወደናል። «አሁን ምን ያደርጋል ድስትን ጥዶ ማልቀስ፤ አስቀድሞ ነበር መጥኖ መደቆስ»እንዲሉ መንግሥት የእርምት እርምጃውን አስቀድሞ እንዲወስድ ጥያቄያችንን በዚሁ አጋጣሚ ለማቅረብ እንወዳለን።


Sunday, May 12, 2013

አዲስ ሃይማኖት አልመሰረትንም

(አዲስ አድማስ)!
 ከቤተክርስቲያን ጋር ፀብ የለንም፤ ለአመፃ አልመጣንም” (“የማህበረ ዘደቂቅ ኤሊያስ” መሪዎች)
“በማህራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም. ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ የጥንቷን ሃይማኖት እያስተካከልን ነው -ቅዱስ ኤልያስ በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው”
ነብዩ ኤልያስ ለፍርድ ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየታየ ነው ከሚለው እምነታቸው ጋር በተያያዘ ድንጋይ ተወርውሮባቸው በተፈጠረ ሁካታ ለሰባት ቀናት ታስረው የነበሩት አባ ዮሴፍ ብርሃነ፣ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን፣ መምህር ወልደመስቀል ፍቅረማሪያም እንዲሁም ፕሮፌሰር ይስማማው አለሙ፤ ሃይማኖታችን ተዋህዶ ነው፤ ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ ነው ይላሉ፡፡ “ማህበረ ዘደቂቀ ኤልያስ” በሚል ስያሜ ራሳቸውን የሚጠሩት የማህበሩ መሪዎች፤ አዲስ ሃይማኖት እንዳልፈጠሩ ሲያስረዱ፣ የጥንቷን እውነተኛ ሃይማኖት ወደ ትክክለኛ ቦታዋ እንድትመለስ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ ይህን የምንሰራው ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ እንጂ እኛ በመሰለን መንገድ አይደለም የሚሉት የማህበሩ መሪዎች፤ በማህበሩ ውስጥ ኤልያስ ነኝ የሚል ሰው የለም ብለዋል፡፡
ከማህበሩ መሪዎች መካከል አንዱ የሆኑት አባ ዮሴፍ ብርሃነ “ኤልያስ ወደ ምድር መጥቷል” በሚለው እምነታቸው ዙሪያ ተጠይቀው፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ አለምን ለመፋረድ ከገነት ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው ብለዋል፡፡ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፡፡ እኛ ኤልያስ አልመጣም ስላልን አይቀርም ያሉት አባ ዮሴፍ፤ ኤልያስ እንደሚመጣ በመፅሃፍ ቅዱስ በግልፅ የተነገረ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የሚመጣበት ጊዜም ስለተጠቀሰ ጊዜውን አስልቶ ማወቅ ይቻላል ብለዋል፡፡ ከአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ተቃውሞ እንደተሰነዘረባቸው ያመኑት አባ ዮሴፍ፤ እስካሁን ጉዳዩ በሲኖዶስ ቀርቦ እንዳልተወገዘና ሲኖዶሱ ጉዳዩን ቢመረምረው እንደሚወዱ ገልፀዋል። ማህበሩን ከተቀላቀለች አንድ አመት ከ7ወር እንደሆናት የገለፀችው አርቲስት ጀማነሽ፤ አንዳንድ ሰዎች ጀማነሽ የመሠረተችው አዲስ ሃይማኖት መጥቷል በሚል ህብረተሰቡን እያደናገሩ ነው ካለች በኋላ፣ እኔ የመሠረትኩት አዲስ ሃይማኖት የለም ብላለች፡፡ “ተዋህዶ” የሚለው ስም ከጥንት የኖረ የሃይማኖታችን መገለጫ እንጂ እኔ የፈጠርኩት አይደለም ያለችው አርቲስቷ፤ “እውነትን እየተናገረ በሚኖር ሰው ላይ ክፉ ስም እየለጠፉ ለማሳደድና እውነትን ለመደበቅ ከመሞከር እውነቱን መመርመር ይሻላል” ብላለች፡፡
ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ መሆኑን የሚያምኑት የማህበሩ መሪዎች፤ የጥንቷ እውነተኛ ሃይማኖት መገለጫዋ ተዋህዶ የሚለው ስያሜ ነው ብለዋል፡፡ “ኤልያስ መጥቷል ትላላችሁ፤ ኤልያስ በማህበራችሁ ውስጥ አለ ወይ?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ “ኤልያስ መጥቷል አልመጣም የሚለው መልዕክት ሊያከራክር ቢችልም፣ እስካሁን በማህበራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም” ብላለች፡፡ መ/ር ወልደመስቀልም በበኩላቸው፤ በበረሃ ያሉ፤ በፆምና በፀሎት የተጉ አባቶቻችን ኤልያስ ተገልጦላቸዋል፣ ዳሷቸዋል፣ አነጋግሯቸዋል” ብለዋል፡፡ በፖሊስ የታሰሩበትን ምክንያት ተጠይቀው ሲመልሱ፣ በሚያዝያ 16 ቀን የኪዳነምህረትን ዝክር ለመዘከር 4 ኪሎ ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን አካባቢ ወደ ምትገኝ የማህበሩ መሰብሰቢያ ቤት ፀበል ፃዲቅ ይዘው በሚሄዱ አባላት ላይ አንዳንድ የሠፈሩ ወጣቶች ድንጋይ በመወርወራቸው በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በወጣቶቹ ድርጊት አንዲት ታዳጊ መፈንከቷን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በእለቱ በከሣሽነት ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሄደው የከሳሽነት ፎርም ሞልተው ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ፣ በጣቢያው አዛዥ ውሳኔ የከሳሽነት ቃላቸው ተቀይሮ በተከሳሽነት ቃላቸውን እንዲሰጡ መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡
ከከሳሽነት ወደተከሳሽነት እንዲቀየሩ የተደረገው ቀደም ሲል የአካባቢው ሰው ለፖሊስ ጣቢያው ተደጋጋሚ አቤቱታ በማቅረቡ መሆኑን መምህር ወልደመስቀል ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ መርሃ ግብሮችን ሲያከናውን ድምጽ ይረብሸናል የሚሉ አቤቱታዎች እንደቀረቡብን ተረድተናል፣ ነገር ግን በፍርድ ቤት ሲቀርቡ በደፈናው ሁከት ፈጠራችሁ የሚል ክስ ነው የተመሰረተብን ብለዋል የማህበሩ መሪዎች፡፡ በመጀመሪያ የፍርድ ቤት ውሎ የዋስ መብታቸውን ቢጠይቁም፤ መርማሪው የአካባቢው ህብረተሰብ ቦታውን ለቀው እንዲወጡ የሚል አቤቱታ እያቀረበ ስለሆነ ጉዳዩ እስኪጣራ የዋስ መብታቸውን እቃወማለሁ በማለቱ ለ7 ቀናት በእስር መቆየታቸውን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በመጨረሻ ግን ስትፈለጉ ትቀርባላችሁ ተብለው እያንዳንዳቸው በ500 ብር ዋስ እንደተለቀቁ ተናግረዋል፡፡

Friday, May 10, 2013

«ጠንቋዩ ግርማ ወንድሙ በእስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ሲያደርግ ከነበረው የጥንቆላ ሥራው ታገደ»



ግርማ ወንድሙ የተባለው አጥማቂ ነኝ ባይ ግለሰብ ከሚያዚያ 28/2005 ዓ/ም ጀምሮ ከአጥማቂነት ሥራው መታገዱንና ሰው ማንጋጋቱን እንዲያቆም የታዘዘ መሆኑን አያይዞ ባወጣው የእግድ ደብዳቤ ላይ ዝርዝር ምክንያቱን ተጠቅሶ ተጽፎለታል።
እንደሚታወቀው ጠንቅ ዋይ ግርማ ወንድሙ  በመንግሥት ባልተመዘገበና ከአነስተኛና ጥቃቅን የሥራ መስኮች ውስጥ አንዱ ባልሆነው ልዩ የሥራ ፈጠራ ላይ ተሰማርቶ ጥንቆላውን በሱዳንና በሺናሻ ዕጽ እየታገዘ ጤናማውን ሁሉ እያሳበደና እያስጮኸ ሲያጭበረብር መቆየቱ ይታወቃል። ቤተ ክህነት ይህንን ማጭበርበሩን በጸጋ መንፈስ ቅዱስ የሚያደርግ ያህል ቆጥራ ዝምታን በመመምረጧ ልጆቼ ናቸው የምትላቸው ተከታዮቿን ገንዘባቸውን እየመዘበረ፤ አእምሮአቸውን እያቃወሰ፤ የተረጋጋና ሰላማዊ ኑሮ እንዳይኖሩ ብኩን እያደረገ፤ ለሰይጣን ግዛት እያመቻቸ ሲሸኛቸው እስካሁን ዝም ከማለቷ ባሻገር አቡነ እስጢፋኖስን የመሳሰሉ ጳጳሳት ደግሞ ለግርማ ወንድሙ ጥንቆላ እውቅና በመስጠት ይባስ ብለው ሀገረ ስብከታቸው ድረስ ወስደው ሕዝቡን እያሳበደ ገንዘብ እንዲሰበስብላቸው እስከማድረግ መድረሳቸውን አይተን አፍረናል።
ግርማ ወንድሙ የሥራ ፈጠራውን ተደናቂ የሚያደርገው በቤተክርስቲያን ከለላ ስሟን እየጠራና ግቢዋን ተተግኖ መሆኑ እንጂ በግብር ከታምራት ገለታ የሚለይ አይደለም። ከዚያ ባሻገር በስመ አጥማቂና ባህታዊ በቤተ ክርስቲያን ተጠግተው ሕዝብ በማስጮህ ገንዘብ የመሰብሰቢያ ስልት እንጂ ግርማ ወንድሙ መንፈስ ቅዱስ ስላደረበት አይደለም። ቅዱሳን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ሙት ሲያስነሱም ሆነ ድውይ ሲፈውሱ ውሃ ውስጥ በመዝፈቅ ወይም በመቁጠሪያ በመደብደብ ሳይሆን ስመ እግዚአብሔርን በመጥራት ብቻ ነው።
«ጴጥሮስ ግን። ብርና ወርቅ የለኝም፤ ይህን ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው።በቀኝ እጁም ይዞ አስነሣው፤ በዚያን ጊዜም እግሩና ቍርጭምጭምቱ ጸና» የሐዋ 3፤6-7
መንፈስ ቅዱስ ባደረባቸው አባቶች እንኳን ቃል ተናግረው ይቅርና ጥላቸው ሲያርፍባቸው ሙታን ይነሱ፤ ድውያን ይፈወሱ ነበር። ጠንቅ ዋዩ ግርማ ወንድሙ ግን በእጁ ላይ የሚያንጠለጥላትን መቁጠሪያ ካልያዘ ማዳን ሳይሆን ማሳበድ የማይችል አስማተኛ ነው። የቅርብ ወዳጁ የሆነ አንድ ሰው መረጃ እንዳካፈለን ግርማ ወንድሙ ገንዘብን የአምላኩ ያህል እንደሚወድና እስካሁንም ባግበሰበሰው ብር እንዳልረካ ነገር ግን ወደአሜሪካ መሄድ የሚችልበትን መንገድ ወይም ከሰዎች ጋር እንዲያገናኘው ብዙ ጊዜ እንደጠየቀው የገለጸልን ሲሆን ይህንን ለገንዘብ ያለውን ፍቅር በመመልከት ቀድሞ በሱ ላይ የነበረውን የማጥመቅ ችሎታ እንደተጠራጠረው ተናግሯል። አሜሪካ የመሄዱ ጉዳይ ለጊዜው ባይሳካለትም ሰሞኑን ወደእስራኤል በአበሾች ላይ  እብደት በማስፋፋት ገንዘብ ለመሰብሰብ ማቅናቱ ይነገራል። የግርማን ከሀገር መውጣት ተከትሎ የእስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በሌለበት የእግድ ደብዳቤ ጽፈውበታል። ቀጣዩ ጉዞው ምናልባትም አሜሪካ ይሆንና የሚበቃውን ዘርፎ የሚመኘውን ያህል ካገኘ አንዷን ቆንጆ አግብቶ ባለትልቅ ኢንቨስትመንት ባለቤት የመሆን ሕልሙን ያሳካል ማለት ነው። የሰው ሃሳብ እንደዚያ ቢሆንም የእግዚአብሔር የተለየ ስለሆነ ግርማ ወንድሙ ሥጋዊ ሩጫህን በጥንቆላ ከምትጨርስ ንስሐ በመግባት ራስህን አድን ምክራችን ነው።
 የእግዱን ደብዳቤ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ