Wednesday, January 9, 2013

እውነቱ የቱ ነው? (ከዚህ በፊት የቀረበ)

መነሻ ሃሳብ «ገመና 81» መጽሐፍ

  ሀተታ

በኦርቶዶክሳውያን  ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከታች ጀምሮ እስከላይኛው እርከን ድረስ ያለው ሰው ስህተት ይኖርብናል ወይም ልንሳሳት እንችላለን ብሎ የሚያስብ ማግኘት አዳጋች ነው። በክርስቶስ ደም የተመሰረተችው ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗን በመቀበል እንዳለ መሪውና ተመሪው ራሱንም በዚያው ዓይን እያየ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በሚል ከለላ ስር ራሱን በማስጠለል፤ ስህተትን አምኖ ለመቀበል አይፈልግም። የስህተት አስተምህሮ አለ፤ በእግዚአብሔር ቃል ሲመረመር አደጋው የከፋ ነው፤ የክፉ መንፈስ አሰራር ወደማወቅ እንዳንደርስ ቃሉን በክሏል ሲባል የሚሰጠው ምላሽ፤ 2000 ሺህ ዘመን የኖረችን ቤተክርስቲያን ዛሬ የተነሱ አፍቃሬ ተሐድሶ መናፍቃን ሊያርሟትና ሊበርዟት ይፈልጋሉ በማለት ታፔላ መለጠፍ ይቀናቸዋል። የስም ታፔላ መለጠፍ ብቻ ሳይሆን ሽልማት የሚያሰጥ ቢሆን ኖሮ የተመረጡና ለመስማት የሚዘገንኑ ስድቦችና ዛቻዎች ይዥጎደጎዳሉ።
በእርግጥ የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗ አያጠራጥርም። ምክንያቱም የመሠረታት በዓለቱ ላይ በፈሰሰው ደሙ ነውና። ይህ እውነት ቢሆንም በክርስቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ አባል ሆነው የሚኖሩት የአዳም ልጆች መሆናቸውንም በመዘንጋት የቤተክርስቲያኗን መንፈስና ባህርይ እንዳለ ወደሰዋዊ ማንነት በመውሰድ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በማለት ከስህተት አልባነት የቤተክርስቲያን ማንነት ጋር ራስን መቁጠር ትኩረት የሚያሻው መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል። በእርግጥም የተጠራነው ፍጽምት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹማን እንድንሆን ነው። ነገር ግን ሰው ከተፈጠረበት ማንነት የተነሳ በፍጽምቷ ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹም ሆኖ መኖር የሚችል ማንነት የለውም።
ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሊሆኑን የሚችሉት የገላትያ ሰዎች ማንነት ነው። የገላትያ ሰዎች በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ወደ ሕይወት መንገድ የተመለሱ ሕዝቦች ነበሩ። ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተጨምረው የቆዩ ሆነው ሳለ ሰብአዊ ማንነታቸው አሸንፎአቸው ወደስህተት መንገድ በመግባታቸው በሐዋርያው ጳውሎስ እጅግ የተወቀሱ ሕዝቦች ሆነዋል።
«የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነውገላ 31
ክርስቶስ ኢየሱስ በፊታቸው የተሰቀለ ሆኖ በእምነት ይታያቸው የነበሩት ሕዝቦች ከዚያ የቅድስና ማንነት ወርደውና እውነትን በመተው፤ የጠላት አዚም የወረደባቸው  ሕዝቦች እስከመሆን መድረሳቸውን ሲናገር እናያለን። ሥራቸውን ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የጀመሩ ሆነው ሳለ ቁልቁል ተመልሰው የሥጋን ሃሳብና እውቀት ወደማመን መመለሳቸው በእርግጥም አሳዛኝ የሰው ልጆች ማንነት ማሳያዎች እንደሆኑ የሚያስገነዝበን  ነገር ነው።
«እንዲህን የማታስተውሉ ናችሁ? በመንፈስ ጀምራችሁ አሁን በሥጋ ትፈጽማላችሁንገላ 33 ይላል።
እንግዲህ ክርስቲያኖች ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እምነታቸውን ሊጀምሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ይህንን ፍጽምና ወደአለማወቅ መመለስም ሊታይባቸው ይችላል። ምን ጊዜም ቢሆን የስህተት መንፈስ አገልግሎቱ፤ የእውነቱን መንፈስ ከሰው ልቡና ላይ በመውሰድ ወደስህተት መንገድ መምራት ስለሆነ በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ ሰዎች ውስጥ የስህተት አስተምህሮ እንደሚገባ እናረጋግጣለን።
ብዙዎች የአብያተ ክርስቲያናት አባላት በክርስቶስ ፍቅር ላይ ጸንተው ከመቆም ይልቅ ወደ ምድራውያንና ሰማያውያን ፍጥረቶች ፍቅራቸውን ስለለወጡ የሕይወት መንገድን ስተው መገኘታቸው እውነት ነው።
ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ልጁን ወደ ተሰሎንቄ የላከበት ዋናው ምክንያትም ተሰሎንቄዎች  ከእምነት ጽናታቸው ወደኋላ እንዳይመለሱ በመንፈስ ያበረታታቸው ዘንድ ነበር። ምክንያቱም ፈታኝ የምንጊዜም አዚሙን የሚያፈሰው  የአማኞችን ልቡና በማደንዘዝ ወደ አልሆነ አቅጣጫ መመለስ  ሥራው ስለሆነ ከዚህ ፈታኝ ይጠበቁ ዘንድ እንደላከላቸው ቅዱሱ ወንጌል ይነግረናል።
«ስለዚህ እኔ ደግሞ ወደ ፊት እታገሥ ዘንድ ባልተቻለኝ ጊዜ። ፈታኝ ምናልባት ፈትኖአቸዋል ድካማችንም ከንቱ ሆኖአል ብዬ እምነታችሁን ለማወቅ ላክሁ» 1 ተሰ 35

Monday, January 7, 2013

«በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም» ፩ኛ ቆሮ ፭፤፰


ጨለማ አስቸጋሪ ነገር ነው። የሰው ልጆች የሌሊቱን ጨለማ ማሸነፍ ባይችሉ ማየት የተከለከለ የዓይናቸውን ብርሃን ለማገዝ የተለያዩ የብርሃን ምንጮችን ሰርተዋል። እንደዚያም ሆኖ የሰው ልጆች የብርሃን ምንጮች  ጨለማን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠር አይችሉም። ይልቁንም በእንከንና በችግር የተሞሉ በመሆናቸው በሌሊቱ ጨለማ ውስጥ አንዳንዴ በጨለማው ሊሸነፉ ይችላሉ። እንኳን የሰው ልጆች የብርሃን ስሪቶች ይቅርና የሰማይ አምላክ የፈጠራት የፀሐይ ብርሃን እንኳን ዓለሙን ሙሉ በአንድ ጊዜ እንድትሸፍን ተደርጋ አልተስራችም። ከዚህም የተነሳ በክልል ያልተወሰነ፤ ብቃቱ ምሉዕ የሆነና በጨለማ መተካት የማይችል ብርሃን እስከዛሬ ዓለማችን አልተሰራላትም።   ስለዚህ ለዓይናችን የሚታየው የብርሃን ምንጭ ውሱንነት የዚህን ያህል ግልጽ ከሆነ በሰዎች ውስጣዊ ሕይወት ውስጥ ያለውን የማንነት ብርሃን ከጨለማ ማውጣት የሚችል ማነው?  

 ይህንን የሕይወት ጨለማ፤ በብርሃን መሙላት የሚቻለው ከሰው ልጆች መካከል አንድም ቅዱስና ጻድቅ የሆነ፤ ከሰማያት መላእክት መካከል  ማንም የለም።  ይህንን የሰው ልጆች ሕይወት በጨለማ ውስጥ ከመኖር ወደብርሃን መቀየር የግድ ያስፈለገው ጉድለቱን መሙላት የሚችል ባለመኖሩ ነበር። እሱም ጨለማ የማያሸንፈው፤ ብርሃኑን ለተቀበሉ ሁሉ በውስጣቸው ዘላለማዊ ብርሃን ማኖር የሚችል፤ የብርሃናት ሁሉ ጌታ ለመሆን  የተገባው  መገኘት ነበረበት። በጨለማ የሚሄድን ሕዝብ ወደብርሃን እንዲመጣና በሞት ጥላ ስር የወደቁ ሁሉ ዘላለማዊ ሕይወትን እንዲያገኙ፤ ነፍስና ሥጋን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር ሌላ ማን ይችላል? ፍጹም የሆነ መታመኛ እርሱ ብቻ ነውና! ዳዊት በዝማሬው « እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው» እንዳለው መዝ ፳፯፤፩ ይህንን የሕይወት ጨለማ በብርሃን መግለጥ የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነበር።

የሰው ልጆች ብርሃን የጨለማ  ዓለምን በሙላት መግለጥ የማይችል ከመሆኑም በላይ የነፍስን ጨለማ ደግሞ በብርሃን መሙላት ይችላል ተብሎ ስለማይታሰብ፤  መታመኛ ብርሃን የሆነው እግዚአብሔር፤ ከዘላለማዊ ብርሃኑ የወጣ ብርሃን፤ ከአምላክነቱ የወጣ አምላክ፤ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፤ ጨለማን በመግለጥ ብርሃንን  የሚሰጥ፤ በሞት ጥላ ስር ላሉ ሕይወትን የሚያድል፤ አንድያ ብርሃን ልጁን ለጨለማው ዓለም ላከ። ይህም ብርሃን ወደዓለም መጣ።
«በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ»  ዮሐ ፲፤፵፮ በማለት እውነተኛው ብርሃን እንደተናገረው።
ይህ ብርሃን ወደዓለም የመጣው ጨለማውን ዓለም በማይጠፋ ብርሃን ሊሞላ ነው። በሞት ጥላ ስር ላሉትም ሕይወትን ሊሰጥም ጭምር ነው።«በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው» ኢሳ 9፤2 እንዳለው።  የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ለዓለሙ ሁሉ ሆነ።
«ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል» ኢሳ ፱፤፮

Saturday, January 5, 2013

ምንኩስናና ጋብቻ!

በንጽህናና በድንግልና እየኖሩ የክርስቶስን የማዳን ሥራ ዘወትር እያሰቡ መኖር የእውነተኛ ክርስቲያን አንዱ ገጽታ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስም ይህንን ሲገልጸው  «ነገር ግን ያለ አሳብ ልትኖሩ እወዳለሁ። ያላገባው ጌታን እንዴት ደስ እንዲያሰኘው የጌታን ነገር ያስባልና» በማለት ሳያገቡ የክርስቶስን  መከራ ሞት እያሰቡና የሕይወታቸው መመሪያ አድርገው ለሚኖሩ ትልቅ ሥፍራ ሰጥቷቸው ይገኛል። (1ኛ ቆሮ 7፤32)

ይህ ማለት ግን ያገቡ ሰዎች ክርስቶስን ማገልገል አይችሉም  ማለት አይደለም። እንዲያውም  የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲሉ በትግልና በትልቅ ፈተና ስር ራሳቸውን ጥለው ሥጋቸውን በመጨቆን የሚያሰቃዩትን ሰዎች በድንግልና ያለመቀጠል ብቃታቸውን እንዲህ ሲል ከፈተናቸው እንዲላቀቁ በጌታ መንፈስ ይመክራቸዋል።
«ነገር ግን በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ» 1ኛ ቆሮ 7፤ 9
ክርስቲያን መኖር የሚገባው በተሰጠው ጸጋ እንጂ የሌለውንና ያልተጠራበትን ጸጋ በጥረቱ ለማግኘት በመፈለግ ባለመሆኑ አንዳንዶች በድንግልና እንኖራለን ብለው ሲያበቁ አዳማዊ ማንነታቸው ከሔዋን ጋር የሚያጣምር ሲሆንባቸውና ከቁጥጥር ውጪ በሆነ ምኞት ስር ሲጥላቸው የሥጋ ብልቶቻቸውን በቢላዋ ጎምደው እስከመጣል ይደርሳሉ። ይሁን እንጂ የሥጋ ብልታቸው መቆረጡ የልብ ምኞታቸውም ቆርጦ ሊያስቀረው የማይችል ስለሆነ ዘወትር እንደተቅበዘብዙ ይናራሉ።
«ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፥ አንዱ እንደዚህ ሁለተኛውም እንደዚያ»  1ኛ ቆሮ 7፤7

ሐዋርያው እንዳለው በድንግልና የጌታን ነገር ብቻ እያሰቡ መኖር የተሻለ መሆኑ አይካድም።  ይህ ጸጋ ለሁሉም የሚሰጥ ባለመሆኑ አንዳንዶች ጸጋቸውን ሳያውቁ ሰዎች በደነገጉት የድንግልና ሕግ ሥር ወድቀው የራሳቸውን የጽድቅ መንገድ ለማቆም እየታገሉና  እየተቃጠሉ መኖራቸው እርግጥ ነው። የሥጋ ብልቶቻቸውን ከመቁረጥ አንስቶ አስገድዶ እስከመድፈር ፤ እንስቶችን አባብሎ ከመዳራትና የስርቆሽ ዝሙት እስከመፈጸም መድረሳቸው  የሰውኛ ጥረት ውጤት ነው። አንዳንዶቹ የሥጋው ፈተና የመጨረሻው ጣሪያ ላይ ሲደርስባቸው ለክፉ መንፈስ ተጋልጠው ግብረ ሰዶም እስከመፈጸም ይደርሳሉ።
«የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም» ሮሜ 10፤3
 የተባለው  የእግዚአብሔርን ጽድቅ  ሳያውቁ ለመጽደቅና የራሳቸውን ጽድቅ ለማቆም  ሲታገሉ ከጽድቁ ሥራ ወጥተው የቀሩትን ይህ ቃለ እግዚአብሔር ተፈጽሞባቸዋል ማለት ይቻላል።

ከዓለማውያን ሰዎች ባልተሻለ መልኩ አባ እገሌ እገሊትን ደፍረው ተያዙ፤ አቡነ እገሌ ልጅ ወለዱ፤ እነአባ እገሌም  ግብረ ሰዶም ፈጸሙ እየተባለ ለሰሚ የሚቀፍ ዜና የሚሰማው እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲታገሉ ቆይተው የጭናቸው እሳት እየፈጀ መቆሚያና መቀመጫ ስለሚያሳጣቸው ነው። በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ በሰው ሚስት ላይ የተያዙ፤ አስገድደው የደፈሩ፤ አልፎ ተርፎም ግብረ ሰዶም ፈጽመው የተገኙ የብዙ አባዎች ጉዳይ አሳሳቢነት ለሲኖዶስ ጉባዔ መወያያ  ሆኖ  መቅረቡ አይዘነጋም።
ይህ እንግዲህ የምናውቃቸውንና የምንሰማቸውን አስጸያፊ ተግባራት ሳይጨምር መሆኑ ነው። ይህን ማንሳት በሥጋ ድካም መነኮሳት የሰሩትን ኃጢአት ለማውራት ሳይሆን የጋብቻን ክቡርነት የሚናገረውን የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የራሳቸውን ሕግ ለማቆም በመታገል መካከል በሚፈጠረው ሽንፈት የተነሳ ኢ-ሞራላዊ፤ ኢ- ምግባራዊና ጸረ ሃይማኖታዊ አድራጎት እየተስፋፋ በመገኘቱ ምክንያት እንደሆነ መታወቅ አለበት። የማይቻለውን ለመቻል ሲታገሉ ሽንፈታቸው መረን የለሽ ወደመሆን አድርሷቸው  የመገኘታቸው ነገር ግልጽ ወጥቶ በመነጋገር  አንድ  እልባት ላይ መድረስ ካልተቻለ ድርጊቱ ማቆሚያ የሌለው ሆኖ ይቀጥላል። ይህም በተጎጂው ላይ፤ በእምነቱ ተከታይ ውስጥ እና በማኅበረሰቡ ውስጥ አሉታዊ አስተሳሰብ እንዲኖር የማድረጉ ነገር ማብቂያ የለውም።

Friday, January 4, 2013

«የሦስት ልጆች አባት የሆነው አምላክ፤ የኢሬቻ በዓል»



12, 000 ሺህ ዓመት በፊት የኩሾች ፈርዖን፤ የሰማይና ጸሐይ   «አስራ» የተባለው አምላክ ሦስት ልጆችን ወለደ።  የመጀመሪያ ወንድ ልጁ «ሴቴ»፤ ሁለተኛው ልጁ ደግሞ «ኦራ» ሲባል የመጨረሻ ሴት ልጁ ደግሞ «አቴቴ» ወይም አድባር የምትባል ነበረች። ከጸሐይና ከሰማይ አምላክ «አስራ»  ልጆች መካከል ሴቴ የተባለው የመጀመሪያ ልጁ ታናሽ ወንድሙን ኦራን በድንጋይ ገደለው። በወንድሟ ሞት እጅግ ያዘነችው «አቴቴ»  ዐባይ ወንዝ ዳርቻ ባረፈው በሟች በወንድሟ መቃብር ላይ «ኦዳ» የተባለውን ዛፍ ለመታሰቢያነት ተከለች።
አቴቴ (አድባር) በመቀጠልም ያደረገችው ነገር በገዳይና በሟች ወንድሞቿ ቤተሰቦች መካከል በቀልና ጥላቻ እንዳይኖር ወደሰማይና ጸሐይ አምላክ አባቷ  ወደ አስራ በማመልከቷ የሰላም ምልክት እንዲሆን ከሰማያት ዝናብ ዘንቦ የተከለችውን «ኦዳ» የተባለውን በማለምለም ሰላም እንዲሰፍን አድርጎላታል።

ሟች ኦራም በኦዳ ዛፍ ልምላሜ የተነሳ በጸሐይና በሰማይ አምላክ አባቱ ሥልጣን ምክንያት ከሞት የተነሳና ያረገ ሲሆን ይኸው በኦዳ ዛፍ ስር ሟች ኦራን በማስታወስ የሚደረገው የሰላምና የምህረት አከባበር ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ ቀጥሏል። በቀደምት ኑቢያውያን የሚደረገው አከባበር  በጥንታውያን የአክሱም ስርወ መንግሥትም ዘመን የኦራ መታሰቢያን የሚያመለክት ቋሚ ድንጋዮችን በመትከል ሲታሰብ ኖሯል።

Wednesday, January 2, 2013

አቡነ አብርሃም ቃለ ዐዋዲን ጥሰው ሕገ ወጥ ሥራ እንዲሠራ ትዕዛዝ አስተላለፉ!

 በአዲስ አበቤው ካህን ዘንድ «የጉድ ሙዳይ» የሚል ስመ ተጸውዖ አላቸው። በየሄዱበት የራሳቸውንና የማቅን ስርወ መንግሥት ማደራጀት ተቀዳሚ ተግባራቸው ነው። ከአሜሪካ ተነስተው ሐረር ከወረዱ አንስቶ እንደ በቆሎ የሚጠብሱት የሐረር ምእመናንና ካህናት ፍዳውን እያየ ነው። ከብዙ ወሰን አልባና ጠያቂ የለሽ እርምጃዎቻቸው መካከል በ /www.deselaam-dejeselaam.blogspot.com/ ያገኘነውን  መረጃ፤ አካፍለናችሗል።። መልካም ንባብ!

በሐረር መድኃኔዓለም ደብር አስተዳዳሪ ላይ ሥልጣነ ክህነት እስከመያዝ የሚያደርስ እርምጃ እንደሚወስዱ አስጠነቀቁ
የዘረኝነት መንፈስ የተጠናወታቸው አቡነ አብርሃም ከጉርሱም ያመጡትን ጎጃሜ የቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ነፃነትን የሐረር መድኃኔዓለም ስብከተ ወንጌል ኃላፊ ሆኖ እንዲመደብ አስገዳጅ ትዕዛዘ አስተላለፉ፡፡ ሊቀጳጳሱ ይህንን ትዕዛዝ ከማስተላለፋቸው በፊት በዓመታዊው የቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ላይ ለመገኘት ወደ ቁልቢ የሄዱ ሲሆን ወደ ሐረር እስከሚመለሱ አላደርስ ብሏቸው ካሉበት ሆነው የመድኃኔ ዓለም አስተዳዳሪውንና የሰበካ ጉባዔው ምክትል ሰብሳቢውን ጠርተው ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል፡፡
ለማስጠንቀቂያው የተጠቀሰው ዋና ምክንያት የደብሩ ሰበካ ጉባዔ በውስጥ ካሉት ካህናት መካከል በማስታወቂያ አወዳድሮ መመደቡ ሲሆን፣ ደብሩ ይህንን ሽሮ የሥራ መደቡን ለጉርሱሙ የራጉኤል ደብር አለቃ ክፍት አድርጎ ለምን አልተቀበላቸውም የሚል ነው፡፡ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤቱ የደብሩን ስብከተ ወንጌል ኃላፊ ቀሲስ ፋሲል አጥናፉን በዕድገት ወደ ራሱ ጽ/ቤት ስብከተ ወንጌል ክፍል ሲወስድ በተፈጠረው ክፍት መደብ ላይ የደብሩ ሰበካ ጉባዔ አወዳድሮ መቅጠሩ በአቡነ አብርሃም ዘንድ እንደ ጥፋትና ድፍረት ተቆጥሯል፡፡
ቃለ ዐዋዲው የደብሩ ሰበካ ጉባዔ ከካህናት መካከል አወዳድሮ በደብሩ ስብከተ ወንጌል ኃላፊነት የሥራ መደብ ላይ የመመደብ ሙሉ ሥልጣን ያለው ሲሆን የተመደቡት ካህንም ሙሉ መስፈርቱን አሟልተው ዕድገቱን እስካገኙ ድረስ አቡነ አብርሃም በሥራ አስኪያጃቸው በኩል ይህንኑ ተቀብለው ማፅደቅ ነበረባቸው፡፡ ይሁን እንጂ፣ እርሳቸው ይህንን በጉልበት ሽረው "የጉርሱሙን አስተዳዳሪ ተቀበሉ"! ብለው ትዕዛዝ ሲያስተላልፉ በየትኛው ማስታወቂያ አወዳድረው እንደቀጠሩ ሲጠየቁ "ዕወቅ እንጂ፣ አትመራመር" በሚል አምባገነናዊ አስተሳሰብ ያሻኝን አደርጋለሁ በሚል ስሜት ቀጭን ትዕዛዝ በማስተላለፍ ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የጉርሱሙ የደብር አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ነፃነት ወደ ሐረር መድኃኔዓለም ደብር ስብከተ ወንጌል ኃላፊነት መደብ ተዛውረው ሲመጡ የሽረት(የዝቅታ) ያህል ነው፡፡ "አቡነ አብርሃም ለሰውዬው ካዘኑላቸው ለምን እዚያው ሀገረ ስብከት ጽ/ቤቱ ውስጥ ቦታ አልፈለጉላቸውም"? ብለው ብዙዎች ይጠይቃሉ፡፡ ነገር ግን አቡነ አብርሃምም ሆኑ አስተደሳዳሪው ያንን መደብ ለመያዝ የቋመጡበት ምክንያት በይፋ ባይታወቅም፣ ቤተክርስቲያንን በጎጃሜዎች ለመሙላት እና እግረ መንገድም አድባራትንና ገዳማትን በ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባላት ለማስያዝ  ነው ሲሉ ብዙዎች አስተያየት ይሰጣሉ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሁለት ቢላዋ!


በየድረ ገጹ የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ መደረግ የለበትም እያለ የሚያላዝነው ማኅበረ ቅዱሳን በከፍተኛ አመራሩ በኩል የፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴ አባል ነው። በሌላ መልኩ ከአመራሮቹ አንዱ  ለቪኦኤ በሰጠው የግሉ መግለጫ እርቅ ይቅደም በማለቱ ከሥልጣኑ አባረውታል። ማቅ በሁለት ቢላዋ እየበላ ይህንን የዋህ ህዝብ ያታልላል። ከአስመራጩ አንዱ የሆነው የማቅ አመራር ምነው ድምጹ አይሰማ? ይህንን ደብዳቤ ተመልከቱ!!


Tuesday, January 1, 2013

ሁሉም ፓትርያርኮች የመንግሥት ጥገኞች ነበሩ!

ቤተክርስቲያኒቱ  ከምሥረታዋ ጀምሮ  የነገሥታቱ እጅ ተለይቷት አያውቅም። የሲሶ መንግሥትነት ድርሻዋም ከዚሁ ይመነጫል። የረጅሙን ዘመን የእንዴትነቱን ታሪከ ለጊዜው እንተወውና ስለፓትርያርኮቹ እውነታ ግን ጥቂት እንበል።

አጭር ምልከታ፡

1/ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ /አቡነ ባስልስዮስ/
ትውልድ መንደራቸው ከሸዋ መርሐ ቤቴ የሆኑት ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ /መምህር ገ/ጊዮርጊስ/ እየተባሉ በመናገሻ ማርያም፣ በኢየሩሳሌምና በኋላም በእጨጌነት የደብረ ሊባኖስ ሹም ሆነው ሲያገለግሉ ቆይተው በጣሊያን ወረራ ወቅት እስከ ማይጨው ድረስ ንጉሠ ነገሥቱን ተከትለው በመሄድ ውጊያውን አብረው ተካፍለዋል። በኋላም የጣሊያን ኃይል እየገፋ  ሲመጣ ከንጉሡ ጋር አፈግፍገው ንጉሡ ወደ ለንደን ሲሸሹ እጨጌው ደግሞ ወደ ኢየሩሳሌም ኮብልለዋል። ጣሊያንም ሀገሪቱን ከተቆጣጠረ በኋላ በጎቻቸውን በትነው በምንደኝነታቸው የተነሳ ወደ ሀገራቸው በፈረጠጡት በግብጻዊው ሊቀ ጳጳስ አባ ቄርሎስ ምትክ ከመጀመሪያዎቹ ኢትዮጵያውያን ጳጳሳት መካከል መጀመሪያ አባ አብርሃምን፣ እሳቸው ሲሞቱ ደግሞ  አባ ዮሐንስን የኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ አድርጎ ጣሊያን ሲሾም ሹመቱን አሜን ብለው በየተራ ተቀብለው ነበር። እንደነ አቡነ ጴጥሮስ የመሳሰሉት ጳጳሳት ለጣሊያን ወራሪ ኃይል ሕዝቡም፣ መሬቱም እንዳይገዙ ሲገዝቱና እስከ ሰማእትነት ሲደርሱ ሌሎቹ ጳጳሳት ደግሞ የጣሊያንን ሹመት እሰየው ብለው መቀበላቸው አይዘነጋም።
ከአምስቱ ዓመት የሕዝቡ መከራ በኋላ ጣሊያን ሲባረር የንጉሠ ነገሥቱን መመለስ ተከትለው እጨጌ ገ/ጊዮርጊስም ተመልሰው ወደ ሀገራቸው ገብተዋል።  ከዚያም በ1940 በግብጻዊው ፓትርያርክ አባ ዮሳብ እጅ ሊቀ ጳጳስ፡ እንደገናም ሌሎች ቀደምት ጳጳሳት እያሉ አጼ ኃ/ሥላሴ በተገኙበት ሥነ ሥርዓት በፓትርያርክ ቄርሎስ እጅ ካይሮ ላይ በሚገኘው ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ፓትርያርከ ዘኢትዮጵያ ተብለው መሾማቸውን የቤተክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል።
ምንም እንኳን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለ1600 ዓመታት በፈጠራ ሕግ በግብጾች የምንዳ አስተዳደር እጅ መቆየትዋን እንዲያበቃ ንጉሠ ነገሥት ኃ/ሥላሴ ከፍተኛ ሚና ቢጫወቱም የፈለጉትን ሰው ወደ  ቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ  የሥልጣን እርከን ማምጣት መቻላቸውን ማስተባበል የማይቻል እውነት ነው። ኢትዮጵያውያን ጳጳሳትም ለጣሊያን ፋሺዝም ሳይቀር የስልጣን ሹመት ፈቃደኛነታቸውን በማሳየት አፍቃሬ ሲመታቸው እስከየት ድረስ እንደሆነ ማሳየታቸውንም  የሚዘነጋ አይደለም።
የሀገሪቱ ሕዝብ በገባር ሥርዓት ውስጥ በጭሰኝነት መከራ እየተጠበሰና ርስት አልባ ሆኖ  እየተሰቃየ  ሳለ በነገሥታቱ የተሾሙት የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች ግልጽ ወገንተኝነታቸው ከነገሥታቱ ጋር  ነበር። ለምሳሌ ያህልም እንደ ደብረ ሊባኖስ ያሉ ትላልቅ ገዳማት  በርስትነት በተቆጣጠሩት ኩዳድ መሬት ላይ የገባሩ ሥርዓት አንዱ አካል በመሆን በክርስቲያን ሕዝባቸው ላይ ጭሰኝነትን መትከላቸው አይዘነጋም። ነገሥታቱ ሲያጠፉ የምትገስጽና የምትመክር ቤተ ክርስቲያን በአመራርዋ እስካሁን አልነበረችም። ይህ እውነት ቢዘገንነንም እውነት ነው። በሐብታምና በደሃ፡ በጨዋ ዘርና በባሪያ፣ በአሳዳሪና በገባር መካከል ያለውን የወንጌል እውነት ማንንም ሳትፈራና ሳታፍር ማስተማር ሳትችል ነጻነቷን ለነገሥታቱ አስረክባ መቆየትዋም አሌ የማንለው ሐቅ ነው። ከነገደ ዛግዌ ወገን ላይ በስመ ኢ- ሰሎሞናዊ ሽፋን ንግሥናን ከመቀማት አንስቶ  አይሁዳዊቷ  ሀገር እስራኤል ነጻነቷን ስታውጅ አናውቅሽም ያሏት፣ ነገር ግን  በስመ ነገደ ይሁዳ  ኢትዮጵያን ለሚገዙ ነገሥታት ታማኝ ሆና ቤተ ክርስቲያኒቷ  መቆየትዋም ለዛሬ የአስተዳደር ድክመትና የሌሎች ወገኖች ደጋፍ  መታጣት አንዱ ምክንያት መሆኑ ይታወቃል። ይህንኑ ተከትሎ የመጡ መሪዎች ሁሉ ለመጠቀሚያነት እጃቸውን ለማስገባት መቻላቸውም  እርግጥ ነው።
2/  ሊቀ ሥልጣናት መልእከቱ/ አቡነ ቴዎፍሎስ

በዚህ የዘመናት ጉዞ አንዱ ክፍል ሆነው በንጉሡ ድጋፍ ፕትርክናውን የጨበጡት አቡነ ባስልዮስም በዚሁ ታሪክ ውስጥ አልፈው በእንደራሴነት ዘልቀው ፓትርያርክ የሆኑት አቡነ ቴዎፍሎስም ከንጉሠ ነገሥቱ ዘንድ ትልቅ ድጋፍ እንደነበራቸው አይካድም። አንዳንድ ጳጳሳት የሳቸውን ፓትርያርክ  መሆን አጥብቀው ከመቃወም አልፈው ደርግ  እርምጃ ሲወስድባቸው እንኳን ድጋፍ እስከመስጠት መድረሳቸው በተደገፈ መረጃ ጭምር የሚነገር እውነት ነው። አቡነ ቴዎፍሎስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ለልማትና ለመንፈሳዊ መነቃቃት መፈጠር ጉልህ ሚና እንዳላቸው ባይካድም ለንጉሡ ሥርዓት ቅርበት እንዳላቸውም  አይዘነጋም።  በአጼ ኃ/ሥላሴ ድርጊት ያቄሙ ጳጳሳት ከአዲሱ ሃይማኖት የለሽ መንግሥት ጋር ወግነው አቡነ ቴዎፍሎስ  እንዲታሰሩ መስማማታቸው ሳያንስ ፓትርያርኩ በእስር  እያሉ ሌላ ፓትርያርክ ለመሾም ራሳቸውን ለማጨት የፈለጉ ነበሩ።  ብልጡ ደርግ ግን አቋም የለሾች መሆናቸውን አይቶ ከወላይታ አንድ ደብር የተገኙትን ባሕታዊ አባ መልዓኩን ለፓትርያርክነት አቅርቦ ጳጳሳት ሳሉ ተራ መነኩሴው በአንድ ጊዜ አቡነ ተ/ሃይማኖት አሰኝቶ ለፓትርያርክነት ለማብቃት ችሏል። ብዙዎቹ ጳጳሳት በሹመቱ ቅሬታ ቢኖራቸውም አይምሬው ደርግ እንደሚሰለቅጣቸው ስላወቁ ባይወዱም ምርጫውን በመንፈ ቅዱስ  እንደተደረገ ቆጥረው ለመቀበል መገደዳቸው ይታወቃል። በምርጫው ላይ የደርግ ጣልቃ ገብነት እንደነበረ  ቢታወቅም  ከአምስቱም የፓትርያርኮች ዘመን በተሻለ  የአቡነ ተ/ሃይማኖትን ፓትርያርክነት ሕዝቡ ከልቡ ተቀብሎት እስከ ዛሬም በታሪካዊነቱ ያወሳዋል። ደርግም ሳያውቀው ከሥልጣን ጥመኞቹ ጳጳሳት እጅ መንጭቆ ለአንድ ባህታዊ አሳልፎ በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱን ጠቅሟታል። ሌላው ቢቀር አቡነ ተ/ሃይማኖት ጸሎተኛ ባህታዊና መፍቀሬ ነዋይ እንዳልነበሩ  ይመሰከርላቸዋል። ከአለባበስ ጀምሮ እስከ አመጋገባቸው ብርቱ ሰው ነበሩ። ያም ሆነ ይህ በሹመታቸው ላይ የደርግ ፈቃደኝት እንደነበር አይካድም።

3/ አራተኛው ፓትርያርክና ለሁለት ሲኖዶሶች መፈጠር ምክንያት እንደሆኑ የሚነገርላቸው የአባ ገ/ሊባኖስ /አቡነ  መርቆሬዎስ/ ወደ ፓትርያርክነት መምጣትም የደርግ እጅ እንደነበረበት ከጥርጣሬ በላይ በማስረጃ የሚናገሩ የወቅቱን አመራረጥ የተሳተፉት የሚናገሩት ነው። በተለይም የደርግ ማእከላዊ ኮሚቴ አባልና የጎንደር ክ/ሀገር አስተዳዳሪ፣ በኋላም የክ/ሀገሩ የኢሰፓ 1ኛ ጸሐፊ የሆነው የጓድ መልአኩ ወሳኝ ድርሻ እንደነበረበት በሕይወት ያሉ ሰዎች ዘወትር የሚያነሱት ታሪክ ነው። በተለይም አባ መርቆሬዎስ የጎንደር ሊቀ ጳጳስ ሳሉ ዲቁናና ቅስና ለመቀበል ወደ እርሳቸው ዘንድ ይመጡ ለነበሩት በመቶዎች ለሚቆጠሩ ካህናት የሚያቀርቡት ቃለ ቡራኬ “ይህ ሁሉ ወጣት ጠመንጃ ቢሸከም” ይሉ እንደነበር በሥፍራው የነበሩ ካህናትና መነኮሳት እማኞች ዛሬም ያስታውሱታል። ከኢህአዴግ መንግሥት ጥርስ ውስጥም የከተታቸው በአንድ ወቅት ለደርግ መንግሥት የጦርነት ድጋፍ የሚሆን ገንዘብ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም በመስጠታቸውና ይህም በሚዲያ በመነገሩ እንደሆነ  ይገመታል። ከደርግ  ጋር ከምርጫ  እስከ ሃሳብ ድጋፍ ድረስ የተሰናሰሉ እንደነበር ቢያቅረንም በእውነቱነቱ መጋት የግድ ይሆናል።  በአባ መርቆሬዎስ ፓትርያርክነት ዘመን ቤተ ክህነቱ የጥቂት ወገኖቻቸውና ደጋፊዎቻቸው መፈንጫ እንደነበር ጊዜው ቢረዝምም እንዴት እንረሳለን የሚሉ ዛሬም አሉ። የእነ ሊቀማእምራን አበባው ይግዛውን አስተዳደር የሚያስታውሱ  ከደርግ ጋር እስከቆንስላነት የነበራቸው ትስስር በመዘንጋት ተበዳዮች ነበርን ባዮች፣ የእነሱ የግፍ አገዛዝ ይመለስልን ብለን እንዴት በተስፋ እንጠብቃለን? በማለት ጥያቄ ያነሳሉ። ምንም ይሁን ምንም የፓትርያርክ መርቆሬዎስ ቤተ ክህነት ከደርግ ጋር ቁርኝት እንደነበረው መካድ አይቻልም። ይህንን ቁርኝት ተከትሎ በደርግ ተበደልኩ የሚል ወገን የፓትርያርኩን በሥልጣን ላይ መመለስ ባይቀበል አያስገርምም። ያስደንቅ የነበረው ቤተ ክህነቱ በየጊዜው ከሚመጣ  የሀገሪቱ ባለሥልጣ ጋር ሳይለጠፍ ራሱን ችሎ ቢገኝ ነበር።

4/ የአባ ገ/መድኅን/ አባ ጳውሎስ/ ዘመነ ፕትርክና

ይህ ዘመን በብዙ እንከን የተሞላና በፖለቲካ ንፋስ የታመሰ ዘመን ነበር። በአንጻሩም አብያተ ክርስቲያናት በልማት ራሳቸውን ያሳደጉበትና አብዛኛው ካህናት የተሻለ የደመወዝ ተከፋይ መሆን የቻሉበትም ዘመን ነው። ያም ሆኖ ኢህአዴግና አባ ጳውሎስ እስከ ኅልፈታቸው ሳይከዳዱ በመደጋገፍ ጊዜያቸውን የፈጸሙበት ዘመን እንደነበርም  መዘንጋት አይቻልም። አቡነ  መርቆሬዎስን ከማባረር ጀምሮ  አቡነ ጳውሎስን እስከ ማስመረጥና ድጋፉ ሳይቋርጥ እስከመጨረሻው ድረስ ወዳጅነታቸው ሳይረግብ  መቀጠሉን መካድም ግልጹን እውነታ ወደ ውሸትነት አይለውጠውም። አቡነ ቴዎፍሎስ ሲታሰሩ እንደተስማሙት ሁሉ አቡነ መርቆሬዎስ ሲባረሩ በተመሳሳይ መልኩ የሊቃነ ጳጳቱ ብርቱ ድጋፍ ከኢህአዴጉ መራሽ መንግሥት ጋር ነበረ። በአቡነ መርቆሬዎስ ሥልጣንና አስተዳደር ቅሬታ የነበራቸው ጳጳሳትና ሠራተኞች በምትካቸው ሌላ ለመምረጥ ሲቻኮሉም ታይተዋል። ግማሹ እኔ እሾማለሁ በሚል ሂሳብ ሲሆን ገሚሱ ደግሞ  ማንም ይሾም ማንም፣ አባ መርቆሬዎስ ወርደው ብቻ ያሳየኝ ከሚል ጥላቻ የተነሳ ነበር። ስማቸውን መጥቀስ የማንፈልጋቸው ሰዎች አቡነ መርቆሬዎስ ወርደው ለማየት የቱን ያህል ፍላጎት እንደነበራቸው በወቅቱ ከማውረድ ጀምሮ  ለአዲስ ሰው ምርጫ ያደርጉት የነበረው ሩጫ አይረሳንም።
የአባ ጳውሎስ ዘመነ ፕትርክና በአንጻራዊ ሰላምና ልማት  /የመንበረ ፓትርያርክ አዳዲስ ህንጻዎችን ልብ ይሏል/ የታየበት ዘመን ቢሆንም በአስተዳደር  ብልሹነትና  በገንዘብ ምዝበራ ረገድ ከየትኛውም ዘመን በተለየ  እጅግ የከፋ ነበር። በአባ ጳውሎስ ዘመን የጵጵስና ማእርግ የምርጫ ሥነ ምግባር ውጥንቅጡ የወጣበትና ለጵጵስናም የነበረ ክብር የወረደበት ዘመን መሆኑም አይዘነጋም።  መጋቤ ምስጢር ወ/ ሩፋኤል በአንድ ጽሁፉ እንዳለው እንደ ስምዖን ቀሬናዊ ከመንገድ እየተጎተቱ የተጫኑበትና “ብንድራቸው ይሻላል” የተባሉ ሁሉ ሥልጣን ላይ የወጡበት አሳዛኝ ዘመንም እንደነበር ይታወሳል። የእውነት ወንጌል ከመቼውም ጊዜ በላይ ዋጋ ያጣበት፡ ሥጋውያን ማኅበራት ነፍስ የዘሩበት ቢሆንም ብዙዎች የተጋረደውን እውነት ገልጠው ለማየት ይቻሉበትም ዘመን ሆኖ  አልፏል።