Wednesday, November 9, 2011

ክብር ለሚገባው ክብር ስጡ!



ሮሜ 13፣7 «ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ፤ ግብር ለሚገባው ግብርን፥ ቀረጥ ለሚገባው ቀረጥን፥ መፈራት ለሚገባው መፈራትን፥ ክብር ለሚገባው ክብርን ስጡ»

ክብር ለአንድ ነገር ዋጋ መስጠትን ይመለክታል። ዋጋው ደግሞ በዓይነት፣በገንዘብ፣በጉልበትና
በሃሳብ ወይም በመንፈስ ሊገለጥ ይችላል። የሰው ልጅ በሕይወቱ ዘመን ይህንን ዋጋ ሲከፍል ኖሯል፤ ይኖራልም። ሰው ለፈጣሪውና ለሚያመልከው፤ ለሚበልጠው፤ ለሚወደው፤ ለሚፈራው፤ ለሚመራው ክብርን ይሰጣል። ምናልባት የሚሰጥበት መንገድና የሚሰጥበት ምክንያት ይለያይ እንደሆነ እንጂ ክብርን ስለመስጠት ሃሳብ ጥያቄን የሚያስነሳ ጉዳይ እንዳልሆነ እንስማማለን።

ሰው ፈጣሪው ስላደረገለትና ስለሚያደርግለት ነገር ሁሉ ክብርንና ምሥጋናን ይሰጣል። ክብርን የሚሰጠው ስለተደረገለት ብቻ ሳይሆን ፈጣሪ በመሆኑ ክብር ስለሚገባውም ጭምር ነው።

ነቢዩ ሙሴና ሕዝቡ እግዚአብሔር ከጠላት እንዳዳናቸው ደስታቸውን በዝማሬ ገልጠው ክብር ሰጥተውታል።

«በዚያም ጊዜ ሙሴና የእስራኤል ልጆች ይህንን መዝሙር ለእግዚአብሔር ዘመሩ፥ እንዲህም ብለው ተናገሩ። በክብር ከፍ ከፍ ብሎአልና ለእግዚአብሔር እዘምራለሁ ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ጣለ» ዘጸ ፲፭፣፩

ክብሩ ከፍ ከፍ ያለ፣ ኃይልና ሥልጣን በእጁ የሚገኝ፣ ማድረግ የሚፈልገውን ከማድረግ የሚከለክለው ለሌለ ምስጋና ይገባዋል ሲሉ ተገቢውን ክብር ሲሰጡ እናያለን። ስለተደረገላቸው ብቻ ሳይሆን ክብሩ ፍጹማዊ በመሆኑ ለመለኰታዊነቱ ተገቢ ክብር እንደሆነም ሌላ ሥፍራም እንደዚሁ ምሥጋና ሲሰጡ እናገኛቸዋለን።

«በተራራው ራስ ላይ በእስራኤል ልጆች ፊት የእግዚአብሔር ክብር መታየት እንደሚያቃጥል እሳት ነበረ» ዘጸ ፳፬፣፲፯

ክብሩ ታላቅና ሰው ሊቀርበው የማይችል መለኮታዊ እሳት ስለሆነ ክብርና ምስጋና የተገባው ነበረ። የእግዚአብሔር ክብር በቦታና በሥፍራ አይወሰንም፣ መለኮታዊ አገዛዙ ሁሉን የመላ ስለሆነም ጭምር ክብር ይገባዋል። ሁሉን በሙላት መሸፈን የሚችል ያለእሱ ማንም የለምና።

Sunday, November 6, 2011

እኔ በእግዚአብሔር የምታወቅበት ማንነት!


በዚህ ምድር ሳለን እውቀታችን ያች ትንሿ ጭንቅላታችን በሚመጥናት መልኩ የያዘችውን ያህል ብቻ ታውቃለች። ከዚያ በላይ ልሁን ብትልም መስፋት ከምትችለው በላይ አትወጣም። ዓለም ባላት እውቀት የምታውቀው ማወቅ የቻለችውን ያህል ብቻ ነው። የሰው አእምሮ ከምታውቀው በላይ ለመሆን ብትሞክር የእውቀት መቋጠሪያዋ ይበጠስና የያዘችው ማፍሰስ ሲጀምር ሰው ለመባል ያበቃትን ማንነት ትስትና አጠቃላይ እኛነታችንን ወደ ሌላ ምዕራፍ ታሸጋግራለች። ወደ እብደት ወይም ወደ እንስሳት ጠባይዓት ማለት ነው።
አንደኛው የዓለም ጦርነትም ይሁን ሁለተኛው የዓለም ጦርነት መነሻቸው ሰው ካለው እውቀት በላይ ለማምጣት በተመኘ እውቀት የተከሰተ ነው። ምናልባትም ሶስተኛው የዓለም ጦርነት ሊመጣ የሚችለውና የከፋ የሚያደርገውም የሰው እውቀት ከማወቅ ጣሪያ በላይ ለመውጣት በሚያደርገው ጥረት ወዳለማወቅ ተሻግሮ የሚጎትተው እብደትና የእንስሳነት ጠባይ መገለጫ ሊሆን ይችላል።
ይህንንም ጥንታውያን አበው«እጅግም ስለት፤ ይቀዳል አፎት»ይላሉ። መጽሐፍ ቅዱስም የእግዚአብሔር ቁጣ እንዲርቅና የተመዘዘው ሰይፍ እንዲመለስ ሲያመለክት እንዲህ ሲል ይነግረናል። «አንተ የእግዚአብሔር ሰይፍ ሆይ፥ ዝም የማትለው እስከ መቼ ነው? ወደ ሰገባህ ግባ ጸጥ ብለህም ዕረፍ » ኤር 47፤6
በምድራችን ላይ የሚታየው የጦርነት፤ የእልቂት፤የእርስ በእርስ መበላላት፤ የበሽታና የረሃብ ክስተቶች ሁሉ የሰው እውቀት ያመጣው ጣጣ እንጂ የፈጣሪ ፈቃድ አይደለም። ምክንያቱም የያዝነው የዘመኑ እውቀት ስለቱ ለመኖርያ የተሰጠውን አፎት ዓለምን እየቀደደ በመገኘቱ ሰው ሰውኛነቱን ወደመካድ እብደትና እንስሳነት እውቀት እየተሸጋገረ በመገኘቱ የተነሳ ነው። እንዲሁም ይህ ሰይፍ ወደሰገባው (አፎቱ) የማይመለሰው የሰው ልጅ ያለው እውቀት እግዚአብሔር እሱን (የሰው ልጅን) እንዴት እንደሚያውቀው ለማወቅ ከመፈለግ ውጪ ስለሆነ ነው። በአጭር አገላለጽ ሰው ስለእግዚአብሔር ያለው እውቀት እሱ ማወቅ የሚችለውንና ለማወቅ የሚፈልገውን ያህል ሲሆን በአንጻሩ እግዚአብሔር ሰውን እንዴት እያወቀው እንደሆነ ለማወቅ አልቻለም ማለት ነው።

Thursday, November 3, 2011

እርግማንና ረጋሚዎች!



ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በኦሪቱ በኋላም በወንጌል የበራላትንና ከእግዚአብሔርም የተሰጣት ከአፍሪካ እስከ በመካከለኛው ምስራቅ ገናና ታሪክ እስከ የመንም ድረስ የነበራትን የግዛት እንዲሁም የጸጋ፤የበረከት፤ መሬቷ ወርቅ፤ ወንዞቿ ወይን፤ ደኖቿ ኤደን፤ ሕዝቦቿ ታታሪ ሆነው የኖሩበትን ዘመን የቀየረውና የገለበጠው ምንኩስና የሚባለው የሰነፎችና «የአጸድቃለሁ፤ እኔም በስራዬ እጸድቃለሁ» የሚለው ማኅበር ከተንሰራፋ በኋላና ወንጌልን አሽቀንጥሮ ቤተመቅደሱን የሞላው ገድል የሚሉት የእግዚአብሔርን ክብር በመጋረድ ቅዱሳን ለተባሉት ክብርና መንቀጥቀጥን እንዲሰጥ የሚያስገድደው መጽሐፍ ቦታውን ከያዘና ተአምር የሚባል የዘርዓ ያዕቆብ የግዝት መጽሐፍ ብዙ ደም አፋስሶ፤ አፍንጫና ጆሮ አስቆርጦ፤ በሕይወት ሳሉ ከጉድጓድ አስቀብሮ የደም መሬት ኢትዮጵያ ላይ ከነገሰ በኋላ ነው። በኦርቶዶክስ ቤ/ክ መጽሐፍ ቅዱስን በደንብ ማንበብ የተጀመረው የፕሮቴስታንት እምነት መጽሐፍ ቅዱስን ይዞ ስለሚሰብክ እሱን ለመቋቋም ተብሎ እንጂ ከእቃ ግምጃ ቤት ወጥቶ አያውቅም። በትግራይ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ መጽሐፍ ቅዱስን ይዞ የታየ ጴንጤ ወይም ካቶሊክ ያሰኝ እንደነበር አይዘነጋም። ድርሳነ ሚካኤልን ወይም የሆነ ተአምርን ከተሸከመ እሱ የወንጌል ሰው ሳይሆን ኦርቶዶክሳዊ እንደሆነ ይቆጠራል።
ሌላው ቀርቶ« ኦርቶዶክሳዊ ሆኖ «ኢየሱስ ጌታ ነው»ብሎ መናገር እንደጴንጤ ያስቆጥራል። ማር 12፤29...ጌታ አምላካችን አንድ ጌታ ነው» የሚለውን መመስከር ወንጀል ሆኖ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሌለው 78 ሰው ቅርጥፍ አድርጎ በላ የሚባለውን የተረት ታሪክ መናገር እንደክርስቲያን የሚያስቆጥረው በምን ስሌት ነው?