Wednesday, July 23, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)
የመጨረሻ ክፍል

የተአምረ  ማርያም  ጸሐፊዎች  ሰዎችን  በማስፈራራትና  በማስደንገጥ የማይመረምሩትና  ከገዢው  ቃል  ጋር  የማያስተያዩት  ሃይማኖት  ግዞተኛ አድርገው  ለማኖር  የፈጠሩት  ፈጠራ  ከተፈጥሮና  ከስነ  ፍጥረትም ከአእምሮም  ጋር  የሚጋጭ  ነው።  እነዚህ  ናሙና  ከስነ  ፍጥረት  ሕግ  ጋር የሚጋጩ ያፈነገጡ ታሪኮች ናቸው።

ጥቂት ተጨማሪ ናሙና ግጭቶች

መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚናገረው  መደመጥና  መከበር  እንዳለበት  ሁሉ  ዝም ባለበት  ጉዳይ  ሁሉ  ዝምታውም  መከበር  አለበት  እንጂ  በራሳችን  ምናብ የተፈተሉ  ነገሮችን  እየፈጠርን  ያላለውን  ማስባል  የለብንም።  የኢየሱስ የልጅነቱ  ዘመናት  ታሪኮች  በወንጌላት  ውስጥ  አልተጻፉም።  ያልተጻፉት አስፈላጊ  ስላልሆኑ  ነው።  ቢሆኑ  ኖሮ፥  እኔ  ደግሞ  ስለ  ተማርኸው  ቃል እርግጡን  እንድታውቅ  በጥንቃቄ  ሁሉን  ከመጀመሪያው  ተከትዬ በየተራው  ልጽፍልህ  መልካም  ሆኖ  ታየኝ    ያለውና  ከወንጌላቱ  ሁሉ በዝርዝር የዘገበው ሉቃስ ይህን አይጽፍም ኖሮአል?

   ስሟስ? የማርያምን  የስሟን ትርጉም በመቅድሙ  ላይ  “መንግሥተ  ሰማይ መርታ  የምታገባ”  ማለት  ነው  ሲል  ይተረጉማል።  በሌሎችም  ቦታዎች፥ ለምሳሌ፥  ምዕ.  12፥  74፥  98  ወዘተ፥  በዕብራይስጥ  ማሪሃም  የተባለች እያለ ተመሳሳይ ስምና ትርጉም ያቀርባል። እንዴት ፈጥረው ቢተረጉሙት ነው  ባለ  አራት  ፊደል  ስም  ይህ  ሁሉ  ቃል  ያለበት  ትርጉም  የሚሰጠው?
መምራት፥  ማስገባት፥  እና  መንግሥተ  ሰማያት  የሚባሉት  ቃላት  ማርያም ወይም  ሚርያም  በሚባለው  ስም  ውስጥ  ከቶም  የሉም።  በመጀመሪያ በዕብራይስጥ  ማሪሃም  አትባልም፤  ሚርያም  ናት።  ማርያም  በምንም ቋንቋ፥  በዐረብኛም  እንኳ  ማሪሃም  አልተባለችም።  ደግሞም  የስሟ ትርጉም  የተለያዩ  አገባብ  ትርጉሞችም  እንኳ  ተጨምረው  ዓመጽ፥ እንቢተኝነት፥ መራራ፥ መራራ ባሕር ማለት ነው እንጂ መንግሥተ ሰማይ መርታ  የምታገባ  ማለት  አይደለም።  ይህ  አልዋጥ  ካለንም  በግድ እንዋጠው፤ ዕብራይስጥ ብለን ከጠቀስን ትርጉሙ ይኸው ነው። በተአምር  21  ኢየሱስና  ማርያም  ለሐዋርያት  ተገልጠው  ጌታ  ለሐዋርያት በእርሱና  በእናቱ  ስም  በ4ቱ  ማዕዘናት  አብያተ  ክርስቲያናት  ይሠሩ  ብሎ አዘዘ።  በስሟ  ቤተ  ክርስቲያን  ማነጽ  ቀርቶ  ሐዋርያት  ስሟን  ጠርተው ሰብከው  ያውቃሉ?  በምዕ. 7  ደግሞ  ዕርገቷን  በ4ቱ  ማዕዘን  እንዲያውጁ አዘዛቸው  ይላል።  ሐዋርያት  እንዲህ  ተብለው  ይህን  አለመጻፋቸው ይደንቃል!  የታዘዙትን  ቤተ  ክርስቲያን  አለመሥራታቸውም  ዕርገቷን
አለማወጃቸውም  ያስጠይቃቸዋል።  አንዱን  ቤተ  ክርስቲያን  ጴጥሮስ እዚያው  ማነጹ  ተጽፎአል።  በአዲስ  ኪዳንና  በመጀመሪያዎቹ  የቤተ ክርስቲያን  ታሪክ  ዘመናት  ውስጥ  ክርስቲያኖች  ምእመናንን ሲያንጹ እንጂ ሕንጻ  ሲሠሩ  አይታወቅም።  ያመልኩ  የነበረውም  በምኩራቦችና  በቤት ውስጥ  እንጂ  ሕንጻስ  አላነጹም።  ማርያም  ለመጨረሻ  ጊዜ  በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ  የተጠቀችውም  ይኖሩበት  በነበረው  በተባለው  ሰገነት ውስጥ  ከጌታ  ሐዋርያት፥  ከደቀ  መዛሙርትና  ከወንድሞቹ  ጋር  በጸሎት ስትተጋ  ነው  የታየችው  እንጂ  ሰዎች  ወደ  እርሷና  ወደ  ስዕሏ  ሲጸልዩ አትታይም፤  ሐዋ. 1፥14  እነዚህ ሁሉ  ከሴቶችና  ከኢየሱስ  እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር ይላልና።

     ይኼ ሁሉ  የተደረተባት  ድሪቶ  ማርያምን  እንደሚያሳዝናት  የታወቀ  ነው። በእውነቱ  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ደራሲዎቹ  በመልካቸው እንደምሳሌያቸው  የፈጠሯት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ከቶም አይደለችም።  እምነታችንንም  ራስና  ፈጻሚውን  ኢየሱስን  ተመልክተን ከተባለለት  ከኢየሱስ  ሰዎች  ዓይናቸውን  እንዲያነሡ፥  እንዲያውም ከቶውኑ  እንዳያዩት ተብሎ  የተፈጠረችና ማርያም  ተብላ  የተሰየመች  ሴት ናት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ዛሬም  ብትጠየቅ  ያኔ  እንዳለችው፥ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ የምትል ናት።
በተአምር  4  ላይ  ማርያምን  ለመገነዝ  ሲሄዱ  ታውፋንያ  የተባለ  አይሁድ አልጋዋን  ስለያዘ  እጁ  በመልአክ  ተቆርጦ  አልጋው  ላይ  ቀረ።  ይህ  ሰው ሐዋርያትን  ይቅርታ  ጠየቀ፤  ክርስቶስንም  ይቅር  እንዲለው  ለመነ። ሐዋርያት  ግን  ወደ  እመቤታችን  ለምን  አሉት።  ማርያም  ቀድሞውኑ ከሞት  ተነሥታ  ነበርና  ለመናት።  ማርያምም  ጴጥሮስን  እንዲቀጥልለት ነገረችው። ጴጥሮስም በክርስቶስ ስምና በማርያም ስም እጁን መለሰለት። ይህ  ጴጥሮስ  ሐዋርያው  ጴጥሮስ  ከሆነ  መቸም  ይደንቃል።  ይህ  ጴጥሮስ በሐዋ.  3፥6  ብርና  ወርቅ  የለኝም፤  ይህን  ያለኝን  ግን  እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው ያለውና በኋላ በዚህ ስም ላይ ሌላ የለጠፈበት ነው? ይህ ጴጥሮስ በሐዋ. 4፥12 መዳንም በሌላ  በማንም  የለም፤  እንድንበት  ዘንድ  የሚገባን  ለሰዎች  የተሰጠ  ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና  ያለው ነው? እንዴት ያለ ቁልጭ  ያለ ግጭት ነው?  ይህ  የተከሰተው  ከሐዋ. 3  እና  4  በኋላ  ነው  ቢባል  ጴጥሮስ  ብዙ ቆይቶ  በጻፈው  በመልእክቱ  ምነው  የማርያምን  ስም  እንዲያው  አንዴ እንኳ  ያላስገባው?  ይህ  በኢየሱስና  በማርያም  ስም  ብሎ  እንደተናገረ የተጻፈለት  ጴጥሮስ  በመልእክቱ  ውስጥ  በ1ጴጥ. 4፥14  ስለ  ክርስቶስ  ስም ብትነቀፉ የክብር መንፈስ የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ላይ ያርፋልና ብፁዓን  ናችሁ  ያለውና  የክርስቶስን  ስም  ብቻ  ያጎላውና  የእርሱን  ብቻ ማንነት  አጉልቶ  የገለጠው  ነው?  ነው  ቢባል  እንኳ  የቱን  እንቀበል?  መጽሐፍ ቅዱስን ወይስ መጽሐፍ ቅዱስን የሚጻረረውን ሌላ መጽሐፍ? በተአምር  3  ማርያምን  ለመቅበር  ሲሄዱ  ሐዋርያት  ሁሉ  ጥለዋት  ተበተኑ ከዮሐንስ  በቀር  ይላል።  ልክ  ጌታ  ሲያዝ  እርቃኑን  በነጠላ  ከሸፈነው ዮሐንስ  በቀር  ሁሉ  እንደሸሹ  ይህንንም  የጻፈው  ይህ  ደቀ  መዝሙር መሆኑ  እንደተጻፈ  እዚህም  የፍልሰቱን  መጽሐፍ  የጻፈ  እርሱ  መሆኑ
ተጽፎአል።  የዚህ  ምዕራፍ  ግጭት  ከምዕ.  6  ጋር  ነው።  በተአምር  3  ጥለዋት  ተበተኑ  ሲል  በተአምር  6  ፈጽሞ እንዳልጣሏት፣  ግን  ገንዘው፥ ታቅፈው፥  ተሸክመው  እጅ  ነስተው  በጌቴሴማኒ  ቀበሯት  እንጂ አልጣሏትም ይላል። የቱ ነው ትክክል? ምዕ. 3 ወይስ 6? ለነገሩ የተለያዩ ሰዎች  ያዋጡት  መጽሐፍ  ስለሆነ  እንዲህ  እርስ  በርሱ  ቢጋጭ አያስገርምም።
በምዕ. 10  ኢየሱስ  በዋሻ  ውስጥ  መወለዱና  በጨርቅ  መጠቅለሉ  ሳይሆን የበለስ ቅጠል መልበሱ፥ በምዕ. 11 ደግሞ በጨርቅ መጠቅለሉ ተጽፎአል። በመንገድ  መካከል  ተወለደም  ይላል።  ይህ  የራስ  ከራስ  ግጭት  ነው።
መልአክ  ሄዶ  ለሰብዓ  ሰገል  እንደነገራቸው፥  ሰብዓ  ሰገል  ደግሞ  ሽቱም አምጥተውለት  እንደነበር  ተጽፎአል።  እነዚህ  ሁሉ  የተጻፈ  ታሪክን የሚያፋልሱ ናቸው።

    ከንጉሥ  ልጇ  ደም  በፈሰሰ  ደሟ  እኛን  ንጹሐን  አድርጋ  . . .  ይላል  ምዕ. 12፥54።  የማን  ደም  ነው  የፈሰሰ?  የማን  ደም  ነው  ያዳነ?  የማርያም  ደም ያዳነ በሆነማ  ኖሮ  ክርስቶስ ምነው  በመስቀል መዋሉ? ቃሉ በኤፌ. 2፥13  የሚለው አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ  በክርስቶስ  ደም  ቀርባችኋል  ነው  እንጂ  ከልጇ  በፈሰሰው በማርያም ደም  ቀርባችኋል  አይልም።  ጳውሎስ  ኤፌሶንን  ሲጽፍ ማርያም ሞታ  ወይም  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  አርጋ  ስለነበረ  ጳውሎስ ይህንን  ማወቅ  ነበረበት።  ቆላ.  1፥19  በመስቀሉ  ደም  ሰላም  ማድረጉን ይናገራል፤  ሌላ  ደም  አይናገርም።  ዕብ.  9  በሙሉው  ይህንን  ደም ይናገራል  እንጂ  የማርያም  ደም  አይልም።  1ጴጥ. 1  የተዋጀንበትን  ክቡር ደም የክርስቶስ ደም ይለዋል እንጂ የማርያም አይለውም።
በምዕ.  7  በፍልሰቷ  ቀን  (ለነገሩ  ቀኖቹ  ሁሉ  በኛ  አቆጣጠር  ነው የተጻፉትና  በግብጽ  ወይም  በአይሁድ  ቆጠራ  ተጽፈው  መመንዘራቸው አልተነገረም)  በነሐሴ  16  ተዝካሯን  ለዘከረ  ኃጢአቱ  እንደሚሰረይ  ጌታ እንደሰጠ  ይናገራል።  በጣም  ትልቅ  ግጭት!  ኃጢአት  የሚደመሰሰው በነሐሴ  16  ተዝካር  ማድረግ  ከሆነ  መጽሐፍ  ቅዱስ  ከሚለው  ጋር  ፈጽሞ ይጣላል።  በክርስቶስ  በማመን  በጸጋ  ድኖ  በመስቀል  ላይ  በፈሰሰ  ደሙ የኃጢአት  ማግኘት  ወይስ  ደግሶ  አብልቶ  መዳን?  ወይስ  ከሁለቱ  ደስ ያለንን መርጠን መውሰድ?
በተአምር  32  ስለ  አንዲት  ዘማዊት  ይናገራል።  እንደ  ሙሴ  ሕግ እንድትወገር  እንደተፈረደ  ይናገራል  ደግሞም  ቤተ  መቅደስ  ውስጥ  ገብታ ይላልና  ደግሞም  በአዲስ  ኪዳን  ኃጢአተኛን  በድንጋይ  መውገር  የለምና ይህ  የብሉይ  ኪዳን  ዘመን  ይመስላል።  እንዳይባል  ደግሞ  ዘማዊቷ የማርያምን  ስዕል  አግኝታ  ለመነች  ይላል።  መልእክቱ  ወደ  ስዕል  ለምኖ መፍትሔ  ማግኘት  ቢሆንም  በመቅደስ  ውስጥ  የማርያም  ስዕል  ሊኖር አይችልም።  የቤተ  ክርስቲያን  መቅደስ  ነው  ከተባለ  ደግሞ  በቤተ ክርስቲያን  ወይም  በክርስትና  ዘመን  ኃጢአተኛን  መውገር  ከየት  የመጣ ፍርድ ነው? እርስ በራሱ የተማታ ታሪክ ነው።
ሰይጣን  መንፈስ  ነው  እንጂ  ስጋዊ  አካል  አይደለም።  በምዕራፍ  34  ሰይጣንን ማርያም በጥፊ አጩላው ልቡናውን ሲስት ይታያል። በምዕራፍ 51  ደግሞ  የመነኮሳትን  ምድጃ  ስላፈረሰ  አንድ  ሰይጣን  ተጽፎአል። መነኮሳቱ  ወደ  ማርያም  ጮኹና  ለ12  ዓመታት  ባሪያ  ሆኖ እንዲያገለግላቸው  ምድጃቸውን  ያፈረሰውን  ያንኑ ሰይጣን ሸለመቻቸው።
እነዚህ  መነኮሳት  ሰይጣንን  ተቃወሙት  የሚለውን  ቃል  አይታዘዙም ማለት  ነው።  ወይም  ቃሉን  ጨርሶውኑ  አያውቁም  ማለት  ነው።  ሳያውቁ ግን  መነኩሴዎች  ናቸው።  ማዕድ  ቤት  አስገብተው  እየፈጨ፥  እያቦካ፥ እየጋገረ ዓሳ ነባሪ እያጠመደ ከመርከብ ጋር እየተሸከመ አምጥቶ መርከቡ ውስጥ  የነበሩትን  ሰዎች  የሚያስመነኩስ  ይህ  አገልግሎት  ከማዕድ  ቤት ሥራ ያለፈ ነው!
    በምዕራፍ  37  ማርያም  ቴክላ  ወደተባለች  ሴት  ሄዳ  ስታስተዛዝናት፥ ልጇን  30 ዓመት በሆነው  ጊዜ  ከእርሷ ቀምተው  በእንጨት  ላይ ሰቅለው እንደ  ገደሉት  ነገረቻት። ጌታ ከማርያም  ተቀምቶ  ተገደለ  ወይስ ቀድሞም ሊሞት  ነው  የመጣው?  ደግሞስ  በ30  ዓመቱ  ነው  የተገደለው?  ሉቃ.  3፥23  በሠላሳ  ዓመቱ  አገልግሎቱን  መጀመሩን  ነው  የጻፈው።  ሳያገለግል ነው የተሰቀለው ማለት ነው? ተአምረ ማርያም ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ገድሎች ጋርም ይጋጫል፤  ይጣላል።  አንድ  ብቻ  ምሳሌ  ለመውሰድ፥  በገድለ  ተክለ ሃይማኖት  በመግቢያው  ምዕራፍ  ቁ.  40-46  እና  80-81  “.  .  .  አባቴ የሚለው  ግን  ዝክሩን  የሚዘክር  ስሙን  የሚጠራ  ከሱ  ጋራ  የዘላለም ሕይወት  ያገኛል  ዝክሩን  ያልዘከረ  ቃሉን  ያልጠበቀ  ከርስቱ  ከመንግሥተ ሰማያት  የተለየ  ይሆናል  የሞቱ  ሰዎችን  ነፍስ  ሁሉ  ክርስቲያን  የሚባሉ ጻድቅም  ኃጥእም  ቢሆን  የሞቱትን  ከክቡር  አባታችን  ከተክለ  ሃይማኖት ዘንድ  ሳያደርሱ  አይወስዳቸውምና  . . .  ለሥጋችሁ  መጠበቂያ  ለነፍሳችሁ መዳኛ  ነውና፤  ኃጢአታችሁን  የሚያነጻ  .  .  .”  ይላል።  እዚህ  ተክለ ሃይማኖት  የመንግሥተ  ሰማያት  መንገድ፥  የነፍስ  መዳኛና  የኃጢአት ስርየት  ሆኖ  ተገልጦአል። 16
   ማርያም  ወደ  መንግሥተ  ሰማይ  መርታ የምታስገባ  ተብላለች  ተክለ ሃይማኖትም በሩ  ከሆነ  የመዳን መንገዱ ብዙ ነው ማለት ነዋ! የማርያም ዝክር ነው መዳኛው ወይስ የተክለ ሃይማኖት?
በምዕ.  98  ስለ  ይሁዳ  እግረ  መንገድም  ቢሆን  የተነገረው  ጌታን  ሽጦ እናቱን  አግብቶ  አባቱን  መግደሉ  ተጽፎአል።  ቅደም  ተከተሉ  እንደዚያ ከሆነ  እናቱን  አግብቶ  አባቱን  የገደለው  ጌታን  ከሸጠ  በኋላ  ነው  ማለት ነው።  በትክክል  የሞተው  መቼ  እንደሆነ  ባይታወቅም  ተጸጽቶ  ወዲያው ሄዶ  ነው  ታንቆ  የሞተውና  (ማቴ.  27፥1-10)  ጋብቻውም  ግድያውም በሰዓቶች  ውስጥ  ምናልባት  በደቂቃዎች  መሆን  አለበት።  ያለዚያ  እናቱን አግብቶ  አባቱን  የገደለውንና  የአይሁድ  ሕግ ዝም  ያለውን  ሰው  ነው  ጌታ ከሐዋርያቱ ክልል ያስገባው።
     በምዕ. 121  ኢየሱስን  በ8  ዓመቱ  በጎች  እንዲጠብቅ  ላከችው  ይልና  ወደ ደብረ ዘይት መጥቶ በጎቹን አሰማራ ይላል። ለማያውቅ ሰው ልክ  እሰፈር ዳርቻ  በጎቹን  ወስዶ  የመሰገ  ይመስላል።  የሚኖሩት  ናዝሬት  በጎች የሚጠብቀው  ደግሞ  ደብረ  ዘይት  መሆኑን  እንደገና  እናስተውል።  ደብረ ዘይት እኮ ከናዝሬት የ105 ኪሎ ሜትር ሩቅ አገር ነው። በኛ አገር ከአዲስ አበባ  ናዝሬት  ማለት  ነው።  መልክዓ  ምድሩን  ለማያውቁና  ለማይጠይቁ ወይም  የተባለውን  ሁሉ  እውነት  ነው  ብለው  ለሚቀበሉ  አድማጮች የተጻፈ  በመሆኑ  ደራሲዎቹ  ይህን  እና  ይህን  የመሰሉትን  ግጭቶች ለመመርመር ሙከራ አላደረጉም።
በምዕ.  120  ኢየሱስን  በ5  ዓመቱ  የሚያስተምረው  አስተማሪ፥  “ይህ የመበለት  ልጅ”  ይለዋል።  ማርያም  መበለት  ሆነችሳ!  ዮሴፍ  ሞተ  ይሆን?
መቼም  የኢየሱስ  አስተማሪ  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  ዮሴፍ “ጠባቂዋ”  መሆኑን  አያውቅም።  በምዕ. 121  ደግሞ  በ8  ዓመቱ  አሳዳጊው ዮሴፍ  ተጠቅሶአል።  በወንጌሉ  ውስጥ  ደግሞ  በ12  ዓመቱም  በሕይወት መኖሩ  ተዘግቦአል።  በተአምረ  ማርያም  ዮሴፍ  የማርያም  እጮኛ  እንኳ ሆኖ  አልቀረበም።
ሲደመደም፥  ተአምረ  ማርያም  ለሥጋዊ  አኗኗርና  ለኃጢአተኛ  ተፈጥሮ የሚስማማ  መጽሐፍ  ነው።  መጽሐፍ  ቅዱሳዊ  የቅድስና  አመላለስ፥ ክርስቶስን  መምሰል፥  ዋጋ  መክፈል፥  ለእውነት  መሰደድ  በውስጡ የሉበትም።  ክርስቶስን  አዳኝ  አድርጎ  መቀበልና  የሕይወት  ጌታ  አድርጎ እርሱን  መከተል  የሉበትም።  በምንም  ኃጢአት  ውስጥ  ተኑሮ  ለስዕል አቤት  ከተባለ፥  ዝክር  ከተዘከረ፥  በማርያም  ስም  አንዳች  ከተደረገ መንግሥተ  ሰማያት  የመግባት  ተስፋ  አለ።  ስለዚህ  እንደፈለጉ  ኖሮ ማርያምን  ጠርቶ  መናገርና  እርሷ  ደግሞ  ለልጇ  ተናግራ  የሚሹትን  ሁሉ ማድረግ ስለምትችል መልካሙን ገድል መጋደል አይታወቅም። ተአምረ  ማርያምን  ማሔስን  ካላቆሙት  በቀር  መቆም  አይችልም።
ምክንያቱም  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ከራሱ  ከመጽሐፉ  ሌላ  ምዕራፍ፥ ከታሪክና  ከእውነት፥  ከአእምሮና  ከተፈጥሮ፥  በተለይም  ከመጽሐፍ  ቅዱስ ጋር  በምሬት  የሚጣላ  መጽሐፍ  ነው።  በአጭር  ቃል  ተአምረ  ማርያም ጠላት ከዘራቸው ብዙ እንክርዳዶች አንዱ ነው።
ጌታ ከአርያም ይባርካችሁ።
ዘላለም መንግሥቱ  © 2012 (፪ሺህ፬) ዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት
1 ሰውና እግዚአብሔር በኃጢአት ምክንያት ተለያዩ
3. ሰው በራሱ ጥረት ወደ እግዚአብሔር መድረስ አይችልም።
በመጣጥፉ ውስጥ የተጠቀሱ መጻሕፍት፤
በአባቶቻችን  አፈርን፥  ባዩ  ታደሰ  እርዳቸው  (መምህር)፥
[ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም] አዲስ አበባ፥ ፪ሺህ፫ ዓ. ም.።
ይነጋል፥  ጽጌ  ስጦታው  (ዲያቆን)፥  አፍሪካ  ማተሚያ፥  አዲስ
አበባ፥ Ŧ ŹƃƂƋ ዓመተ ምሕረት።
ገድለ  አቡነ  እስጢፋኖስ  ዘጉንዳጉንዶ፥ 1997   ዓ.  ም.  አሳታሚ፥
መምህር ወማኅበር ዘጉንዳጉንዶ ደብረ ገሪዛን።
ለእውነት እንቁም፥ ስሜ ታደሰ፥ SIM Publishing፥ አዲስ አበባ፥
፪ሺህ ፬ ዓ. ም.።
ገድለ ተክለ ሃይማኖት፥ [አሳታሚና ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም]
አዲስ አበባ፥ 1989 ዓ. ም. ።
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በአስተዋጽዖ፥ መሠረት ስብሐት
ለአብ፥  አሳታሚ  ፍኖተ  ሕይወት  ማኅበረ  መነኮሳት፥  የኅትመት
ዘመን አይታወቅም፥ አዲስ አበባ።
ገድለ  ክርስቶስ  ሠምራ፥  ትንሣኤ  ዘጉባኤ  ማተሚያ  ቤት፥  አዲስ
አበባ፥  1992ዓ. ም. ።
Schaff, Philip,  History of the Christian Church,  Nicene
and Post Nicene Christianity,  T & T Clark, Edinburgh,
1884.
Tamrat, Tadesse,  Church  and State in Ethiopia  1270-1527, Oxford University Press, London, 1972.