Thursday, December 20, 2012

ጳጳሳቱንም ሆነ መንግሥትን በፓትርያርክ ምርጫ ላይ ስህተት እንዳይፈጽሙ እናሳሰባለን!

አባ ጎርጎርዮስ ፓትርያርክ ለመሆን የጓጓ ይመስላል።
Ø መንግሥትም እሱን የፈለገ ቢመስልም ምርጫው ከምራጭ ላይ የወደቀ ነው!!
Ø አባ ጎርጎርዮስ ምርጫው በእጣ ሳይሆን በካርድ ይሁን ሲል ውሏል። ለምን ይሆን?
Ø የውጭ ዜግነት ያላቸው ጳጳሳት ከጫወታው ውጪ ስለተደረጉ ሸክሙ ቀሎላቸው ይሆን?
ከአሜሪካው ሲኖዶስ ጋር ሲደረግ የቆየውና እርቅ ይሁን የሥልጣን ሼር /አክሲዮን/ መሆኑ ያልታወቀው ጉዳይ ያበቃለት ይመስላል። ይህም የምርጫ ህግና አስመራጭ በመምረጥ የሀገር ቤቱ ሲኖዶስ  ስለምርጫው አይቀሬነት እቅጩን ተናግሯል። ሥልጣን፣ ሥልጣን ከሚል ጩኽት ባሻገር መንፈሳዊ እርቅ ፈጽሞ የማይታይበትን ጉዞ በወጪና በኪሳራ ከማጀብ ይልቅ አዲስ ምርጫ አድርጎ  ሁለቱም ወገን ቁርጣቸውን አውቀው በያዙት ተግባር ላይ ትኩረት እንዲሰጡ ማድረጉ የተሻለ ነው የሚል እምነት አለን። ዋናው ነገር የክርስቶስን ቤተ ክርስቲያን፣ ክርስቶስ እንደሚወደው አድርጎ ከመምራቱ ላይ እንደነበር ያኔም ይሁን ዛሬ ሁላችንም ችግሩን ስለምናውቀው ስለ ሥልጣን ሼር በመጨቃጨቅ ጊዜ ማጥፋት የለብንም። ሁሉም ባለበት የሐዋርያነትን ሥራ ይሥራ!!!
ይልቅስ አፋችንን ከፍተን ውጪ ውጪውን ስናማትር ብልጦች ተሽቀዳድመው ለቀም ሳያደርጉ የሀገር ቤቱን ሹመት ነቅተን መከታተሉ ጠቃሚ ነው።
የምርጫ ህጉ ከጸደቀ በኋላ ምርጫው በእጣ እንዳይሆንና እንደ ቀበሌ ሊቀመንበር ምርጫ በካርድ እንዲሆን ብዙ እንደተከራከረ የሚነገርለት አባ ጎርጎርዮስ፣ የውጭ ዜግነት ያላቸውን በህግ ሽፋን ለምርጫ እንዳይቀርቡ ካስወገደ በኋላ ራሱን ለፓትርያርክነት ማዘጋጀቱን ይነገራል። ላለፉት 20 ዓመታት በምሥራቅ ሸዋ / ስብከት ተቀምጦ ምንም ዓይነት የልማት እንቅስቃሴ ሳያሳይ ይህችን ቀን ሲጠባበቅ የቆየው ጳጳስ፣ ዛሬ ፓትርያርክ ለመሆን ሲሯሯጥ እጅግ ያስገርማል። ከዝዋይ ገዳም የአትክልት ሽያጭ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር እንደሰበሰበ የውስጥ አዋቂ መረጃዎቻችን  ከመጠቆማቸውም  ከዚያም ባሻገር በጆሮ ለመስማት በሚቀፍ ግብር ላይ የሚጠረጠር ሰው ዓይኑን በጨው ታጥቦ ቢቀርብ ቤተክርስቲያን እንዲህ ዓይነቱን ፓትርያርክ አድርጋ ልትሸከም መዘጋጀት አይገባትም። የውስጥ ጉዳችንን ለማን እንነግራለን ብለው እንጂ ይህንን መጥፎ ግብሩን ጳጳሳትም ሳይቀሩ ያውቁታል። መንግሥትም ቢሆን በህዝቡ ዘንድ የጠራ ስምና ግብር የሌለውን እንደዚህ ዓይነቱን ሰው ወደ ሥልጣን እንዲመጣ በማድረግ በራሱ ላይ እሳት ሲያነድ መኖር የለበትም እንላለን።  መንግሥት ለዚህ ሰው ውስጥ ውስጡን ድጋፍ ለማድረግ የወደደው በምን መለኪያ ይሆን?
የውጭ ዜግነት ያላቸው ጳጳሳት በምርጫ የመወዳደር ፋይል በምርጫ ህጉ ተዘግቶ ወደ መዝገብ ቤት ተመልሷል። በዚያ ላይ ምርጫው በእጣ ሆኖ እግዚአብሔር የወደደው ይሁን እንዳንል እነ አባ ጎርጎርዮስ በካርድ ሽፋን ሥልጣን እጃችው ሊያስገቡ እጣ የሚባል ነገር መነሳት የለበትም በማለት መጽሐፍ ቅዱሳዊውን የምርጫ ሥርዓትን ሲቃወሙ ይገኛሉ።

የሐዋ 1 23_ 26
ኢዮስጦስም የሚሉትን በርስያን የተባለውን ዮሴፍንና ማትያስን ሁለቱን አቆሙ። ዕጣም ተጣጣሉላቸው፥ ዕጣውም ለማትያስ ወደቀና ከአሥራ አንዱ ሐዋርያት ጋር ተቈጠረ

አባ ጎርጎርዮስ እጣ እንዳይሆን የፈለገው በመንፈስ ቅዱስ አሠራር ስለማያምን ነው ወይስ በምድራዊ ጥበብ ሥልጣን በእጁ የሚገባበት ዘዴ ተነግሮታል? በእርግጥ አባ ጎርጎርዮስና የመንፈስ ቅዱስ አሠራር አይተዋወቁም። ስለዚህ  ምርጫ በእጣ ሳይሆን በምርጫ ካርድ ነው ማለቱ ብዙም አያስገርምም። ነገር ግን 20 ዓመታት ያህል ከአቡነ ጳውሎስ እግር ስር አድፍጦ ሲጠባበቃት የቆያት ሥልጣን  እንደ ልቡ መሻት በምርጫ ካርድ ለቀም ካደረጋት በእርግጥም የቤተክርስቲያኒቱ መከራና ወጀብ ገና አላበቃም የሚያሰኝ ነው።
ወዳጆቼና ልጆቼ የሚላቸውን እየመረጠ ወደ ውጭ ሀገር ሲልክ እንደቆየ ሀገር ያወቀው፡  ጸሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው። የሱ ፓትርያርክ መሆን ወደ ውጭ የመሄድ እቅድ ላላቸው ወዳጆቹ የእልልታ ዘመን ሆነላቸው ማለት ነው። በአባ ጳውሎስ እጅ እንዳሻው መላክ የቻለ ሰው የሥልጣን ሰይፉ በእጁ ሲገባማ እንዴት አብዝቶ እንዳሻው አይቆርጥ? 
የምሥራቅ ሸዋውን አጤ ጳጳስ ፓትርያርክ ለማድረግ መንግሥት የሚፈልግ ከሆነ ትልቅ ስህተት እየፈጸመ መሆኑን ልንጠቁመው እንወዳለን። የችሎታ፣ የምግባር፣ የአስተዳደርና የእውቀት ችግር ቤቱን የሰራበትን ሰው በመሾም ከኪሳራ በስተቀር ምንም ትርፍ አያገኝበትም። የሚፈለገው ሰው ሚዛናዊ፣ መንፈሳዊና ልማታዊ አባት መሆን አለበት።
 እን እኛ ሃሳብ አባ ጎርጎርዮስ ፓትርያርክ ከሚሆን ይልቅ ቤተ ክርስቲያን ያለ ፓትርያርክ  ብትኖር ይሻላታል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ነገር ለአዲሱ ፓትርያርክ ምርጫ፣ አስመራጭ ኮሚቴ መመረጡ ታውቋል። አስመራጭ ኮሚቴ መዋቀሩ የሚያሳየው ድምዳሜ አቡነ መርቆሬዎስ በፓትርያርክነት ተመልሰው በሥልጣን እንደማይቀመጡ ነው። አራት ነጥብ። በኮሚቴነት የተመረጡት ሰዎች ማንነት በከፊል እንደታወቀው ፣ ከሊቃነ ጳጳሳት አቡነ ጢሞቴዎስ፣ አቡነ ቄርሎስ፣ አቡነ እስጢፋኖስ፣ አቡነ ቀሌምንጦስ  ሲገኙበት ከየመምሪያው ደግሞ ሊቀ ትጉሃን ኀይለ ጊዮርጊስ ዳኜ (ማቅ)፣  ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ሲሆኑ፡  አቶ ባያብል ሙላቱ (ከማቅ) እና አቶ ዓለማየሁ ተስፋዬ ከኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት እንደሚገኙበት ተጠቁሟል።
በካርድ ምርጫ ከሆነ ፓትርያርክ ሆኖ የሚመረጠውን እኛ አስቀድመን ገምተናል!!!!!!!!!!! ማን ይመስላችኋል?