Wednesday, December 19, 2012

በእጃቸው ካደጉ ልጆቻቸው አንዱ ነኝ

    ለደጀ ብርሃን
    “ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉ፤ገንዘብን የሚወዱ ትምክህተኞች፤ትዕቢተኞች፤ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፤ የማያመሰግኑ፤ ቅድስና የሌላቸው፤ፍቅር የሌላቸው፤ዕርቅን የማይሰሙ ሃሜተኞች፤ ራሳቸውን የማይገዙ፤ጨካኞች መልካም የሆነውን የማይወዱ ከዳተኞች፤ ችኩሎች፤ በትዕቢት የተነፉ.....ይሆናሉ።”
(2ኛ ጢሞ. ምዕ. 3 ቁጥ.1-5)
Ø ለደጀ ብርሃን ማህበራዊ ድረ ገጽ ብሎገሮች /አምደኞች፤
በዚሁ ብሎጋችሁ የታላቁን ገዳምና መንፈሳዊ ማሰልጠኛ ዝዋይ ገዳም፤ እንዲሁም የመናኙን አባት ብጹዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ስም አንስታችሁ የጻፋችሁትን አሳዛኝና ህሊናዊ ሚዛን አልባ መረጃ ተመልክተናል።
እናንተ ማስተዋልን በተቀማ፤ የህሊና ፍርድ ለመስጠትም ማገናዘብ ባልቻለ ጭፍን ሀሳብና ክፉ ልብ፤ እንዲሁም የሚዲያን ባለሙያ ስነ ምግባር ባልጠበቀ ማንነት የጻፋችሁትን ይህንን የአንድ በስርቆትና የስነ ምግባር ጉድለት የተከሰሰና በህግ የተፈረደበት(እናንተው ራሳችሁ በጽሁፋችሁ እንደገለጻችሁት ማለት ነው)ግለ ሰብ ወሬ አይተን ዝም ብንል የእውነት አምላክ እውነቱን በሚያውቀው ህሊናችን ላይ ይፈርድብናልና የሚሰማ ልብና የሚያስተውል አእምሮ ቢኖራችሁም ባይኖራችሁም እውነቱን ልንነግራችሁ ግድ ነው።
ከሁሉ አስቀድመን ከላይ በመግቢያው የተጠቀሰውን የቅዱስ ጳውሎስን ህያው ቃል አንባቢ ሁሉ እንዲያስተውለው እንመክራለን። ምክንያቱም የተነሳንበትን ርዕሰ ጉዳይ የተመለከተ ሁሉ ምን አይነት ዘመን ላይ እንደ ደረስን ይገነዘብ ዘንድ ነው።
ይህ ዘመን የሀሰት አባት ዲያብሎስ በአንድም በሌላም መንገድ ውጊያውን ያጠነከረበት፤ በሀሰተኛ መረጃዎችም የዓማኙን ሁሉ ልብ ለስህተት ይማርክ ዘንድና በእውነተኛይቱ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንና መንፈሳውያን መሪዎችዋ ላይ በክፋት ያዘምት ዘንድ አበክሮ የሚሰራበት ክፉ ወቅት ነው። በእርግጥም ይህን የክፋትና የዓመጽ ዘመን መጨረሻ ምንነት አስቀድሞ በመንፈስ ቅዱስ ያየው ታላቁ ሀዋርያ በዚሁ የስህተት ዘመን የሚነሱትን የሀሰት መልዕክተኞች ማንነት ሲገልጽ፦
“አእምሮአቸው የጠፋባቸው፤ ስለ እውነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው እውነትን ይቃወማሉ” ካለ በኋላ የክፋት አሰራራቸው የትም እንደማይደርስ ሲያረጋግጥ ደግሞ፦
“ዳሩ ግን የእነዚህ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ሆነ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም” ይላል። (2ኛ ጢሞ. ምዕ. 3 ቁ. 8—10)።
ስለሆነም የእውነት አምላክ ሁላችንንም ከስህተት ይጠብቀን ዘንድ እየጸለይን እንቀጥላለን።
ለመሆኑ እንዲህ በክፋት የዘመታችሁበት ታላቅ ገዳም ታሪክ እውነታና እንዲህ በክፉ ስም የኮነናችኋቸው ብጹዕ አባት ማንነት ምን ይሆን?
ይህ በክፋት ወሬ ስሙን ልታጎድፉት የምትጥሩት የቤተ ክርስቲያኒቱ ተስፋና አለኝታ የሆነው ታላቅ ገዳምና የካህናት ማሰልጠኛ ዝዋይ ገዳም በቀደሙትና የቤተ ክርስቲያን ብርሃን በነበሩት የህያው ታሪክ ባለቤትና ጻድቅ አባት አባ ጎርጎርዮስ የሸዋ ሊቀ ጳጳስ መንፈሳዊ ራዕይ የተመሰረተና ከእርሳቸው ዘመን ጀምሮ እስካሁን ድረስ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አለኝታ የሆኑና በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ቤተ ክርስቲያኒቱን በቅንነት የሚያገለግሉ ደቀመዛሙርትን በመንፈሳዊ ህይወትና በመልካም ስነ ምግባር አንጾ ከማፍራቱ በላይ አሁን ቤተ ክርስቲያኒቱን በጵጵስና ማዕረግ በአባትነት የሚመሩ ብዙ ብጹአን አባቶችን ያስገኘ፤ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያን የነገ ተስፋ የሚሆኑ እጓለማውታ ህጻናት በቃለ እግዚአብሄር ተኮትኩተውና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍቅር ታንጸው የሚያድጉበት መንፈሳዊ የበረከት ስፍራ እንጂ በእናንተ አፍ እንደተባለው የጥፋትና የርኩሰት ቦታ አይደለም።


ስማቸው በእናንተ ዘንድ በበጎ ያልተነሳው እኚህ ገዳማዊና እውነተኛ መናኝ አባትን ማንነትስ ታውቁ ይሆን?
እኚህን ገዳማዊ መነኮስ አባት (የቀድሞውን አባ ተጠምቀ) ለዚሁ ገዳም ባለ አደራ አባትነት የመረጧቸውና በገዳሙ ሁለንተናዊ አገልግሎት ኃላፊነት ላይ የሾሟቸው በመንፈስ ቅዱስ ምሪታቸው የሚታወቁትና እግዚአብሄር ከሰጣቸው ጸጋ የተነሳ የሰውን ማንነት እንዲሁ በማየት አስቀድመው ይረዱ የነበሩት አቡነ ጎርጎርዮስ የሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሲሆኑ፤ እሳቸውም በዚያን ጊዜ በገዳማዊ ህይወትና በእውነተኛ የምናኔ ጽናት፤ እንዲሁም በንጽሃ ምንኩስና እና በአገልግሎት ትጋት ለብዙ መነኮሳት በምሳሌነት የሚያነሱላቸው እኚሁን ባህታዊ መነኮስ (የቀድሞ አባ ተጠምቀ) የአሁኑን አቡነ ጎርጎርዮስ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ነበር።
አሁንም ቢሆን ሁሉም የሚያውቀውና የሚመሰክረው የእኚህ አባት ፍጹም ገዳማዊ ህይወትና ጸሎተኝነት ለብዙዎች አርአያና ምሳሌ ሆኖ ብዙዎችን ለምነና ከመማረኩ የተነሳ በእሳቸው እጅ ማዕረገ ምንኩስናን ተቀብለውና ከበረከታቸው ተካፍለው ለጵጵስና ማዕረግ የበቁ አባቶች ብዛት የእሳቸውን መንፈሳዊ ማንነት የሚያሳየን ህያው ምስክር መሆኑን የሚረዳው አስተዋይ ህሊና ያለው ሰው ብቻ ነው።
ምክንያቱም እውነት የሆነው የእግዚአብሄር ቃል እንደሚያስረዳን እንዲህ ያሉ መንፈሳዊ በረከቶች ሊገኙ የሚችሉት እግዚአብሄር አብሮት ከሆነ የእግዚአብሄር ሰው ብቻ ነውና።
“እግዚአብሄርን የሚፈራ ፈቃዱንም የሚያደርግ ቢኖርያንን እግዚአብሄር ይሰማዋል እንጂ ኃጢአተኛውን እንዳይሰማ እናውቃለን”። (ዮሐ. ምዕ. 9ቁ.31)
ከዚህም ሌላ እኚህ መናኝ አባት ብጹዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ወደ ዝዋይ ገዳም በፈቃደ እግዚአብሄር ከመጠራታቸው አስቀድሞ በተባህትዎ ከኖሩበት የትህርምትና የቅድስና ስፍራ ከሆነው፤ እህልም ከማይቀመስበት ቅዱስ ስፍራ የጻድቁ ወላዴ አእላፍ አቡነ ሳሙኤል ገዳም ዋልድባ ህይወታቸው ልምድ የተነሳ አሁን እንኳን የሚቀርብላቸውን ምግብ በአግባቡ የማይመገቡ ተሃራሚ መሆናቸን አብረዋቸው የኖሩ ልጆቻቸው ብቻ ሳይሆኑ የሚያውቋቸው ምዕመናን ሁሉ የሚመሰክሩላቸው እውነታ ነው።
ታድያ እኒህን አባት እንዲህ ባለ ክፉ ስም ማንሳት በሚያውቃቸው ሁሉ ዘንድ ትዝብት ላይ የሚጥል ከመሆኑ ሌላ በእውነተኛው አምላክ ዘንድስ አያስፈርድባችሁምን?
በእርግጥ ይህ የድፍረት ቃላችሁ አትኩሮ ላስተዋለው የዘመኑን ፍጻሜና የእናንተንም የጥፋት መልእክተኝነት የሚመሰክር እውነት ከመሆኑም በላይ ፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ምን ያህል በጥፋት እየዘመታችሁ እንደሆነ በግልጽ የሚያስረዳን ሀቅ ነው።
ምክንያቱም እጅግ ብዙ የሆኑ አሳዳጊ የሌላቸው እጓለማውታ ህጻናትን ሰብስቦ በመንፈሳዊ ትምህርትና በመልካም ስብእና አንጾ በማሳደግ ለቤተ ክርስቲያን የነገ ተረካቢ እያፈራ ያለውን ይህን ታላቅ ገዳም እንዲህ ባለ ክፉ ስም መወንጀል ቤተ ክርስቲያኒቱን የነገ ተረካቢና ተተኪ ለማሳጣት የሚደረግ ቀጥተኛ የሆነ ጸረ ቤተ ክርስቲያን ዘመቻ እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም።
የንጹሃን አባቶቻችንም ክቡር ስም እንዲህ ባለ ከንቱ ውንጀላ ይጎድፋል ብላችሁ አስባችሁ ከሆነ የሚገርም ሞኝነት ነው።
ለማንኛውም አምላከ አበው ልዑል እግዚአብሄር እውነተኛውን ፍርድ ይስጣችሁ።
(በብጹዕነታቸው በረከት በእጃቸው ካደጉልጆቻቸው አንዱ ነኝ)።