Wednesday, September 6, 2017

«አማለደ» ያለው አማለደ ለማለት ሳይሆን . . . » ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ሦስተኛውና የመጨረሻው ክፍል )





Kesis Melaku Terefe

መነሻው እንደጰላድዮስ በጥያቄ፥ እንደንስጥሮስ በክርክር ቢሆንም፥ ለተነሡት ጥያቄዎችና ክርክሮች መልስ እንዲሆን ቅዱሳን አባቶቻችን ጽፈውልን የተዉልን ጦማሮችና ድርሳናት ፥ ዛሬ በጨለማ እንዳንዳክር መንገድ ጠቋሚዎች ሆነው፥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በሚገባ እንድንመረምርባቸው ረድተውናል። ዛሬም በስሕተት ጎዳና ካሉት ጋር የምናደርገውን ክርክር የምንመራው ፥ እነዚህ አባቶቻችን የቀደዱልንን ፈር በመከተል ነው። ምስክራችን ቅዱሳን ሐዋርያት፥ ሐዋርያውያን አበው፥ የኋላ ሊቃውንት እና ሲኖዶሶቻቸው ነው። ከሳሾቻችን ክርክሩን ለማሸነፍ እየሞከሩ ያሉት፥ በቃላት ስንጠቃና በብልጣ ብልጥነት ነው። ቢታጣ ቢታጣ፥ የግእዙንም ሆነ የአማርኛውን ሰዋስው ተጠያቂ የሆኑትንና በዚህም የኢትዮጵያውያን ሁሉ ባለውለታ የሆኑትን አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌንና ደስታ ተክለ ወልድን ለአማርኛ ቃል ክርክር ምስክር ስላደረግናቸው፥ የቦሩ ሜዳውን ክርክር ወደኛ ለማምጣት እየሞከሩት ነው። ትንሽ ቆይተው ደግሞ ኪዳነ ወልድ የተረጎሙት ሕዝቅኤል ይቃጠልልን ብለው ቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ አቧራ እንደሚያስነሱ እንጠብቃለን። ለነገሩ ይህን የሚያውቁት አይመስለንም። አለቃ ግን  አፉ ያልተገራ ጨዋ እንዲህ ሲሰድባቸው ቢሰሙ ኖሮ በአጭሬ ግጥማቸው ያቀምሱት ነበር። ግን ምን ያደርጋል!
እኛ ግን የተዋህዶ ማኅተም እየተባለ የሚጠራው፥ የእስንድርያው ፓትርያርክ ቅዱስ ቄርሎስ፥ « ከመ አሐዱ ክርስቶስ» የተሰኘውን ተዋህዶን ያመሠጠረበትን ድንቅና ታላቁን ድርሰቱን ሲጀምር፥ « ለትምህርተ ቅዱሳት መጻሕፍት አልቦ ዘይጸግቦን ግሙራ ወኢመኑሂ፤ የቅዱሳት መጻሕፍትን ትምህርት ማንም ማን አይሰለችም።» በማለት እንደተናገረው ያለ መሰልቸት፥ ከአበው የተማርነውን እንጽፋለን እንናገራለን። የእግዚአብሔር ቃልን ከመናገር ቸል አንልም አንሰለችም። ይኸው ሃይማኖቱ የቀና ( ኦርቶዶክሳዊ) አባት፥ « ሲሲተ ልብ ቃላቲሁ ለእግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ቃል የልቡና ምግብ ነው» እንዳለው፥ በዚህም ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሕይወታቸውን እንደሚመግቡ ተስፋ እናደርጋለን።
ወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥ ባለፈው በክፍል ሁለት ጽሑፋችን አራት ዋና ዋና ነገሮችን አንሥተናል፥ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናትነት ፍጹም ሰው በመሆኑ እንደሆነ፤ ሊቀ ካህናትነቱ በሹመት እንደሆነ፥ ሊቀ ካህንነቱ ለማስታረቅ እንደሆነ፥ በመጨረሻም ሊቀ ካህናትነቱ እንደ መልከ ጼዴቅ እንደሆነ ተመልክተናል። በዚህ ክፍል ሦስት ጽሑፋችን ደግሞ የአውጣኪን የስህተት ጎዳና በመከተል፥ የክርስቶስን የሊቀ ካህናትነቱን የማስታረቅ አገልግሎት የካድክባቸውን ነጥቦች በማንሳት፥ አንድ በአንድ መልስ እንሰጣለን።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ «ከዚህም አያይዞ፡-“እርሱም በሥጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚ ችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤”ብሎአል። የቅዱስ ጳውሎስ የትርጓሜ መጽሐፍ፡-ይኸንን ገጸ ንባብ ሲያብራራው፡-“ወእመ ሀሎ በመዋ ዕለ ሥጋሁ፥ ጸሎተ ወስኢለ አብአ፥ በዐቢይ ገዓር ወአንብዕ።ይኸውም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነትን ሥራ በሠራበት ወራት (ከቤተል ሔም እስከ ቀራንዮ ባደረገው የማዳን ጉዞ) ጸሎ ትን፡-እንደ ላም፥ምልጃን(ልመናን)፡-እንደ በግ አድ ርጎ፥በፍጹም ሐዘንና በብዙ ዕንባ አቀረበ ፤”ብሎአል።ምክንያቱም፡-የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ለል መና እና ለምልጃ የሚያቀርቡት የበግ እና የላም መሥዋዕት ነበር።በመሆኑም፡-በንባቡ ጸሎትና ምልጃ የተባለው፡-“አማለደ፤” ለማለት ሳይሆን፥እንደ ላምና እንደ በግ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን እንደሆነ ማስተ ዋል ይገባል » ብለህ ነበር።
ይህ ጽሑፍህ  ከእግዚአብሔር ቃልና ከአባቶች ትርጓሜ ጋር ሙግት የያዘ ነው። አንደኛ፥ ጸሎት እና ምልጃ ተብሎ የተጻፈውን  ጸሎትና ምልጃ ብላችሁ አታንብቡ ትለናለህ። የእግዚአብሔርን ቃል ታጣምም ዘንድ እንዴት ደፈርህ። በዚህ አላበቃህም።  ሁለተኛ፥ አባቶች « ጸሎትን እንደ ላም ምልጃን እንደ በግ አድርጎ አቀረበ» ብለው የተረጎሙት፥ ጸሎትና ምልጃ ለማለት አይደለም  በማለት ምልጃና ጸሎት ተብሎ የቀረበው ሥጋው ነው በማለት ነበር ያስቀመጠው። ይህ ሁሉ ግን ፥ ክርስቶስ በሊቀ ካህንነቱ አልማለደም አልጸለየም ለማለት ነው።  ያንተን ትርጓሜ የማንቀበልበትን በዝርዝር እናስረዳ፤
፩ኛ. ንባቡ የሚለው « ጸሎትንና ምልጃን» አቀረበ ነው።
« እርሱም ሥጋ ለብሶ በዚህ ዓለም በነበረበት ጊዜ፥ በታላቅ ጩኸትና እንባ ከሞት ሊያድነው ወደሚችለው ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤ ጽድቁንም ሰማው» ነው የሚለው። በዚህ ንባብ ውስጥ ጌታ በመዋዕለ ሥጋዌው ያደረጋቸው ነገሮች በግልጥ ተቀምጠዋል። ጩኸት ( ገዓር) እና እንባ (አንብእ) ጸሎት እና ምልጃ ተነግረዋል።  ምንም እንኳ ሙሉ በሙሉ ወልድ በሥጋው ወራት ወደ አባቱ እንደጸለየ ብትክድም፥ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባብ ይህን በግልጥ ያስቀምጣሉ።

ስለ ጸሎቱ ለምሳሌ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ጌታ በጌቴሴማኒ ሲጸልይ የነበረውን ሁኔታ ሲገልጥ እንዲህ ይላል። የሚያበረታታው የእግዚአብሔር መልአክም ከሰማይ ታየው። ፈራ መላልሶም ጸለየ ላቡም በምድር ላይ እንደሚወርድ እንደ ደም ነጠብጣብ ሆነ» ይላል፤ ሉቃስ ፳፫፥፵፬። እዚህ ላይ ከመጸለይ ባሻገር፥ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ « ፈራ» ብሎ ሲናገር እናያለን። ቀሲስ ደጀኔ ባንተ አተረጓጎም ከሄድን « ፈራ ሲል ፈራ ማለት አይደለም» ብለን የፈጠራ ትርጉም መስጠት እንችል ነበር። ግን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲህ በማድረግ አናጣምም። ፈራ ሲል ፈራ ነው። አማለደ ሲል አማለደ ነው። ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ? የእግዚአብሔር ልጅ እንዴት ፈራ ይባላል፥ አባቶች በሚገባ መልሰውታል። « በሰው ልማድ ፈራ፤» አሉ፤ ትርጓሜ ወንጌልን ተመልከት። ማለትም በእውነት ፍጹም ሰው ስለሆነ ማናቸውም ሰው እንደሚፈራው ነው የፈራው። ከኃጢአት በቀር እንደኛ የሆነ ሰው ነውና። ነገር ግን ከዚያ በላይ ታላቅ የሆነ መልእክት አለ። ለምን ፈራ? እኛን ሆኖ፥ ስለ እኛ ብሎ ስለሆነ የወደቀውና የተነሣው፥ የፈራውም የእኛን ፍርሃት ነው። በእውነት እኛን ሆኖ የእኛን ፍርሃት ፈራ። « ሶበሰ ኢፈርሃ እምኢሰሰለ ፍሃት እምኔነ፤ ባይፈራ ኖሮ ( የምትሃት ቢሆን ኖሮ፥ ወይም በእውነት ሳይፈራ ለትምህርት ብቻ ያሳየው ቴያትር ቢሆን ኖሮ) ፍርሃት ከእኛ ባልተወገደ ነበር።»  የጸለየውም መላልሶ ነው። አባቶች እንዳስቀመጡት፥ « ወጸርሐ ኀበ አቡሁ ከመ ትምጽኦ ረድኤቱ፤ ረድኤቱ ትመጣለት ዘንድ ወደ አባቱ ጮኸ፤» እንዴት ይህ ሊሆን ቻለ ቢባል በለበሰው ሥጋ።
ይህ የአባቶች ትርጓሜ፥ ከነባቤ መለኮት ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ትምህርት ጋር አብሮ የሚሄድ ነው። አቡልናርዮስ ጌታ ነፍስን አልነሣም ብሎ የኑፋቄ ትምህርቱን ይዞ ሲነሣ ቅዱስ ጎርጎርዮስ የሰጠው መልስ «What has not been assumed has not been healed; it is what is united to his divinity that is saved. ያልነሣውን አልፈወሰውም፤ ከመለኮትነቱ ጋር የተዋሃደውን ያንን  ነው የዳነው» ነበር ያለው። ይህ የነባቤ መለኮት ጎርጎርዮስ አባባል የሚያስረግጥልን፥ ጌታ የኛን ባሕርይ የተዋሃደው ሊያድነን ነው።
ያዳነን የተዋሃደውን ባሕርይ ነው። ከኃጢአት በቀር፥ የሚዝል፥ የሚደክም የሚፈራ፥ የሚራብ የእኛን ባሕርይ ነው የተዋሃደው። በእውነት የሰውን ባሕርይ ገንዘብ አድርጎአልና።
ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ይህን የቅዱስ ሉቃስን ንባብ ሲተረጉመው እንዲህ አለ። « እርሱ እንደፈራ በተናገረ ጊዜ ጌታ የተዋሐደውን የሰውን ባሕርይ አስረዳ፤ እውነተኛ ሰው እንደሆነም አስረዳ። በዚህም ጌታ የተዋሐደው ኃጢአት የሌለበትን የሥጋን ሥራ ሰው መሆኑንም አስረዳ፤ ፍርሃት ከመለኮት ባሕርይ አይደለም። ወዙ እንደ ደም ነጠብጣብ በዝቶ እስኪወርድ ድረስ አለ፤ ደም መስሎ መውረድም የሥጋ ገንዘብ ነውና። የሚያጽናናው የእግዚአብሔር መልአክም ከወደ ሰማይ መጣ አለ።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ም. ፶፮. ክፍል ፫ ቍ. ፵፪- ፵፫
፪ኛ. የአባቶች ትርጓሜም ትኩረት የሚያደርገው  « ጸሎትንና ምልጃን» ነው።  
ይህን እንደገና አባቶች በትርጓሜያቸው እንዴት እንዳስቀመጡት እንመለከት፦  « ሰው ኾኖ የስውነት ሥራ በሠራበት ወራት፤ጸሎትን እንደላም ስኢልን እንደበግ አድርጎ አቀረበ።በፍጹም ኀዘን በብዙ ዕንባ አቀረበ። የልቡና ነውና፥ ግዳጅ ይፈጽማልና፥ አንድ ጊዜ ነውና በታላቅ ጩኸት ( ኀዘን) እና በእንባ አለ። ከሞት ሊያድነው ወደሚቻለው ወደ አብ አቀረበ። የምእመናንን ድኅነት ለራሱ አድርጎ፥አንድም ምእመናንን ከሞት ሊያድንለት ወደሚቻለው ወደ አብ አቀረበ። ቁርጥ ልመናውንም ሰማው። የባሕርይ ልጅ ሲሆን፥ ታዞ መከራ ስለተቀበለ፥ መታዘዝን አመለከተ ( ዐወቀ)። ትንቢተ ነቢያትን፥ ዘመንን፥ ቀጠሮን፥ አሥሩ ቃላትን፥ ሕማማተ መስቀልን ፈጽሞ፥ ለሚያምኑበት ኹሉ ሕይወትን የሚያድል ኾነ። የዘላለም ሕይወት ሆነ»
በግዴለሽነት የአባቶችን ትርጓሜ « ለማቃናት » የጮሌነት አካሄድ ብትሄድም፥ ትርጓሜው አይሰድህም። « « ጸሎትን እንደላም ስኢልን እንደ በግ አድርጎ አቀረበ» ሲል ላምና በግ ስለተጠቀሰ « ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን የሚያመለክት ነው» ያልከው መሥዋዕት ያለ ምልጃና ያለጸሎት እንደማይቀርብ ባለማስተዋልህ ነው። ያው የአባቶች ትርጓሜ ትኩረቱ ምን ላይ እንደሆነ፥ በጥንቃቄ ትረዳው ነበር። ለምሳሌ « በፍጹም ኀዘን በብዙ ዕንባ አቀረበ» የሚለውን ሲተረጉሙ የሚያሳየው ይህን እውነት ነው። እነርሱ ያሉት « የልቡና ነውና፥» ማለት የመታየት፥ የምትሃት አይደለም፤ « ግዳጅ ይፈጽማል » ማለት የቤዛነት ሥርየተ ኃጢአትን የሚያሰጥ ነው ል  « አንድ ጊዜ ነው» አንድ ጊዜ ለዘላለም የከናወነው ነው የሚል ነው። ይህ ብቻ አይደለም ። « ወሰምዖ ጽድቆ፥ ጽድቁ ተሰማለት» የሚለውን « ቁርጥ ልመናውንም ሰማው» ብለው ነበር የተረጐሙት። ንባቡ ልመናው ስለመሰማቱ ፥ ስለመታዘዙ ነው የሚናገረው። እንህ   « ቁርጥ ልመናውን ሰማው ማለት፥ ቁርጥ ልመናውን ሰማው ለማለት አይደለም» ካላልክ በስተቀር፥ የቀረበffው ቁርጥ ልመና ነው፤ የቀረበው ምልጃ ነው።

፫ኛ. ዓለም የታረቀው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበው ጸሎትና ምልጃ ነው።
ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ የጸለየው ጸሎት የምልጃ ጸሎት ነው። ይህን በተለይ ዮሐንስ 17 በግልጥ ያሳየናል። በዚያ ጸሎት ውስጥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ለነበሩት ደቀመዛሙርቱ ብቻ ሳይሆን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ ነበር የጸለየው። በመስቀል ላይ የነበረው ጩኸቱም በመስቀል ላይ የቀረበ የምልጃ ጩኸት ነው። ይህን ከእኔ ይልቅ አለቃ አያሌው ውበት ባለው አገላለጥ አስቀምጠውታል። አስተውል አለቃ እንዴት አድርገው ይህን የቤዛነት ሥራ እንደገለጡት በጥንቃቄ ተከታተለው።
አለቃ አያሌው እንዲህ ይላሉ፦ « በዕለተ ስቅለት በካህኑ ፋንታ ሆኖ « እኔ ስለ እነዚህ እለምናለሁ፤ ስለ ዓለም አልለምንም፤ ስለሰጠኸኝ እንጂ፡ የአንተ ናቸውና የእኔም የሆነ ሁሉ ያንተ ነው። የአንተውም የእኔ ነው። እኔም ስለእነርሱ ከብሬአለሁ፤ ከዚህም በኋላ በዓለም አይደለሁም። . . . ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑትም ደግሞ እንጂ ስለእነዚህ ብቻ አልለምንም» ብሏል። ( ዮሐ ፲፯፥፱-፳) ስለጠቅላላ ምእመንን ባቀረበው ጸሎትም በመስቀል ላይ ሳለ አባት ሆይ የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» « አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ» ብሎ በመናገር፥ « ራሴን ስለበጎቼ አሳልፌ እሰጣለሁ እሺ በጄ ብዬ መጣሁ ብሎ የተናገረው ቃል ሲፈጸም « አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ እሰጣለሁ ብሎ ነፍሱን ከሥጋው በመለየቱ፥ ከአሮን ክህነት በላቀና በረቀቀ የክህነት ሥርዓት ካህን፥ አስታራቂ መታረቂያ መሥዋዕት ሆኖ በፈጸመው በሞቱ የሰውና የእግዚአብሔር እርቅ ከፍጻሜ ደረሰ። ከአብ፥ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም ይቅር ባይ፥ ታራቂ፥ መስዋዕት ተቀባይ ፥ ሕይወትን አዳይ ዋጋ ከፋይ በመሆኑ በኃጢአት ምክንያት ተቋርጦ የነበረው የሰውና የእግዚአብሔር አንድነት በተዘምዶውና ( ሰው በመሆኑንና) በቤዛነቱ ታደሰ። » ( ምልጃ እርቅና ሰላም፤ ገጽ ፳፩- ፳፪) ይህ የአለቃ አገላለጥ ሰፊ ትንታኔ የሚያስፈልገው ብቻ ሳይሆን፥ በዝምታ ( በጽሞና) ልናሰላስለው የሚገባን ድንቅ የመዳናችን ምሥጢር ነው።
ቤተ ክርስቲያን ስቅለቱን በየዓመቱ ስታከብር፥ የስቅለቱን ንባብ ካህኑ ካነበበ በኋላ ባለው የወንጌል መርገፍ ላይ « ጊዜ ተሰዓቱ ሰዓት ገዓረ ኢየሱስ በቃሉ ወወጽአት መንፈሱ ሶቤሃ፤ በዘጠኝ ሰዓት ኢየሱስ በታላቅ ድምጽ ጮኸ፤ ያን ጊዜም ነፍሱም ወጣች» ብሎ አሰምቶ በዜማ ይናገራል። ይህም ከማር ፲፭፥፴፯ ላይ ያለው ነው። ይህ ጩኸት የህመም ጩኸት ነው። ይህ ጩኸት የተራ እሩቅ ብእሲ ( ተራ ሰው) ጩኸት ስላይደለ ግን አባቶች እንደሚሉት፥ « ግዳጅ የሚፈጽም» ለቤዛነት የሆነ፥ ኃጢአትን የሚያስተሠርይ ለዘላለም የሆነ ጩኸት ነው።
፬ኛ. የሰውነቱንና የአምላክነቱን ሥራዎች እንዴት እንደምንናገር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የሰጠን ምክር
እዚህ ላይ፥ ቀሲስ ደጀኔ ትልቁ ስህተትህ መለኮት ገንዘብ ያደረጋቸውን የትስብእትን ሥራ በሚገባ ለይተህ ለመዘርዘር አለመቻልህ ብቻ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ የትስብእቱን ሥራ መካድህ እንደሆነ ደጋግሜ ተናግሬአለሁ ። ይህም አውጣኪን ወደ ስህተት የወሰደ መንገድ ዛሬም አንተን ወደ ከባድ ስህተት እየወሰደህ ነው።
በሰውነቱ የሠራቸውን ሥራዎች፥ በአምላክነቱ የሠራቸውን ሥራዎች እንዴት መናገር እንችላለን? እዚህ ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዕብ ፭፥፭ንና የመሳሰሉትን ኃይለ ቃላት በእንዴት ያለ መንገድ መተርጎም እንዳለብን የሰጠውን ምክር፥ ማለትም የቅዱስ ጳውሎስን አካሄድ በጥንቃቄ ያብራራበትን ብትይዝ ኖሮ ወደ ብዙ ስህተት አትገባም ነበር። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ አጻጻፍ ሲናገር እንዲህ ይላል ፦ « የጳውሎስ ልማድ አንድም ትምህርቱ እንዲህ ነው። የጌታን ልዕልናውን አንድም የአምላክነቱን ነገር ልናገር ባለ ጊዜ፥ (ይመጽእ ለኰንኖ ዓለመ) በዓለም ላይ ለመፍረድ ይመጣል አለ። ትህትናውን አንድም የሰውነቱን ነገር ልናገር ባለ ጊዜ ፥ (አብአ ጸሎተ ወስኢለ) ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤(ወሰምዖ ጽድቆ) ቁርጥ ልመናው ተሰማለት፤ ( ወሰመዮ ሊቀ ካህናት) ሊቀ ካህናት አድርጎ ሾመው፥ ( ወፈጺሞ ኮነ ዐሣዬ ሕይወት) ሁሉን ከፈጸመ በኋላ ሕይወትን የሚያድል፥ የዘላለም ሕይወት ሆነ አለ።»  ይህን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን የአተረጓጎም ስልት ብትይዝ ለወደፊቱም ከብዙ ስህተት ትድናለህ።


፭ኛ. አማለደ . . . ይማልዳል ስንል ምን ማለታችን ነው?
ስለ ክርስቶስ ምልጃ ስንነጋር ብዙ ጊዜ ከቅዱሳን ጸሎትና ልመና ጋር ስለሚያያዝ ልዩነቱን በግልጥ ለማስቀመጥ የሚከተሉትን ነጥቦች ማስቀመጥ አለብን። የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት የምንጠቅሰው የቅዱሳንን ጸሎትና በረከት ለመካድ ከሆነ እንግዲያውስ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት ፈጽሞ አልተረዳንም። እንዲሁ፥ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት የምንክደው የቅዱሳንን ክብር ያጎላን መስሎን ከሆነ ከባድ የሆነ ስህተት ውስጥ ወድቀናል። ሁለቱ ፈጽሞ የተለያዩ ናቸውና ። የሚከተሉትን ነጥቦች በጥንቃቄ ተመልከት።
አንደኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ፥ ክርስቶስ የእኛ ሊቀ ካህናት በመሆኑ የሚያከናውነው ነው። በሌላ አነጋገር ማላጅነቱ የትስብእቱ ( የሰውነቱ) ሥራ ነው።  እርሱ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል መካከለኛ ነው።መካከለኛነቱም ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑ ነው። የቅዱሳን ጸሎት፥ ከቅዱሳን ጋር ካለን ሕብረት ( communion of saints) የሚመነጭ ነው። በሰማያት ያለችው ድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን እና በምድር ያለችው አንድ ናትና። አባቶቻችን « እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ» እንዳሉ።
ሁለተኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ በደም የሆነ ነው። ማለትም ክርስቶስ ጸሎቱንና ምልጃውን ያቀረበው ራሱን መሥዋእት አድርጎ በማቅረብ ነው። ዓለምን ለማዳን የፈሰሰ ደም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። የእሩቅ ብእሲ ( የሰው ብቻ ደም) ዓለምን ስለማያድን፥ የፈሰሰው ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ የሆነ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። ከአቤል ጀምሮ እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ድረስ የፈሰሰው ደም አለምን አልጠቀመም። ዓለምን ያስታረቀው የምልጃ ደም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። ሰማዕታት ደማቸውን ቢያፈሱ ለምስክርነት ነው። « ሰማዕታት ከዓዉ ደሞሙ በእንቲአሁ፤ ሰማዕታት ስለእርሱ [ ምስክርነት] ደማቸውን አፈሰሱ» እንደተባለ። የእርሱ ግን የመሥዋዕትነት ነው። የመታረቂያ ነው።
ሦስተኛ ፥ የክርስቶስ ምልጃ ለቤዛነት ነው። ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የታረቀበትና የሚታረቅበት ነው። ዛሬም በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት ነው። ቤዛ ማለት «ለውጥ፥ ምትክ» ማለት ነው። በእኛ ፈንታ ገብቶ የእኛን ጩኸት የጮኸልን ክርስቶስ ነው። የቅዱሳን ምልጃ ግን ወደ ክርስቶስ የሚደረግ ልመና ነው። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ እንደተናገሩት « The intercessions of the saints for us are merely praying for us; ቅዱሳን ስለ እኛ የሚማልዱት ስለ እኛ የሚጸልዩት ነው። they are of the pleading type, which is completely different to Christ’s atoning mediation» ይህ የቅዱሳን ጸሎት የልመና ዓይነት ሲሆን፥ ለኃጢአት ሥርየት ከሆነው የክርስቶስ መካከለኛነት ፈጽሞ የተለየ ነው» ይሉናል።
አራተኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ እምቢ ያልተባለ አዎን አሜን የሆነ ነው። ክርስቶስ ያማረ ሽቱ አድርጎ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ በማቅረቡ አባቱ በደስታ ተቀብሎታል። ከስሞች ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ተቀብሎአል።
አምስተኛ የክርስቶስ ምልጃ አንድ ጊዜ ለዘላለም የሆነ ነው። በዕለተ አርብ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ባከናወነው እርቅ፥ ለዘላለም መታረቂያ ሆኖልናል። ዛሬ እንደገና ክርክር፥ ዛሬ እንደገና መውደቅና መነሣት አያስፈልገውም። መሥዋዕቱ ሞቶ የቀረ አይደለም። ሊቀ ካህናቱ ሞት የገደበው አይደለም። የታረደው በግ ዛሬም ሕያው ስለሆነ፥ ሊቀ ካህናቱም ለዘላለም በሕይወት ስለሚኖር፥ ወደ እርሱ የሚመጡትን ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው።
አለቃ አያሌው የተናገሩትን እዚህ ላይ እንደገና መድገሙ መልካም ነው። « እኔ ስለ እነሱ እለምናለሁ» ያለው ቃሉ ጊዜ የሚወስነው ሳይሆን እስከ አለም ፍጻሜ የሚሠራ ነው። ይህንንም « እኔ የምለምንህ ስለ እነዚህ ብቻ አይደለም። በቃላቸው ስለሚያምኑብኝም ጭምር ነው እንጂ ያለው ቃሉ ያጸናዋል። ዓለምን ሲፈጥር የተናገረው ቃሉ እስከ ዛሬ በመሥራት ላይ እንዳለ፥ እስከ ዓለም ፍጻሜ ሲሰራ እንደሚኖር፥ ይህም « እኔ ስለ እነሱ እለምናለሁ» ያለው ቃሉ እስከ ዓለም ፍጻሜ ሲሰራ ይኖራል። እንግዲህ ቅዱስ ጳውሎስ « እርሱ ቢያጸድቅ የሚኮንን ማነው? ሞቶ የተነሣው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በአብ ቀኝ ተቀምጦአል። ስለ እኛ ይከራከራል» ይላል። ( ሮሜ 8፥34) እንዲሁም « እነዚያን ብዙዎቹን ካህናት ሞት ይሽራቸዋልና ( ያልፋሉና) ለዘለዓለም አይኖሩም። እኔ ሕያው ነኝ ያለ እሱ ግን ለዘለዓለም ይኖራል። ክህነቱም አይሻርም። ፈጽሞ ሕያው ነውና ያስታርቃቸውማልና። በሱ አስታራቂነትም ወደ እግዚአብሔር ለሚቀርቡት ሁሉ ፍጹም ድኅነትን ሊሰጣቸው ይችላል። እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባናል። እውነተኛ የዋህ ከኃጢአት ሁሉ የራቀ፥ ንጹሕ ከሰማየ ሰማያት የመጠቀ» ያለ ስለዚህ ነው። እስከ ዓለም ፍጻሜ በመሥዋዕትነት በሚቀርብባት በቤተ ክርስቲያን ሲሠራ የሚኖር የማያቋርጥ ኃይል ነውና። ዕብ 7፥23_26) እንግዲህ ጌታ « አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ህልቀተ ዓለም፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ» ( ማቴ 28፥20) ሲል በተናገረው ቃል መሠረት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን በምታስተምርበት መልእክቱን በምታስተላልፍበት ጊዜና ሥፍራ ሁሉ የሚረዳት፥ በልዩ ልዩ አደባባይም የሚከራከርላት መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ በጻፈው መእክቱ « ይትዋቀስ በእንቲአነ» ስለ እኛ ይከራከራል ብሎ እንደጻፈ፥ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር አምላኪየ ናሁ ወልድከ መሥዋዕት ዘያሰምረከ ወበዝንቱ አናህሲ ሊተ ኵሎ ኃጢአትየ» እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ አንተን ደስ የሚያሰኝህ መሥዋዕት ልጅህ እነሆ፤ በዚህም ኃጢአቴን አስተስርይልኝ» እያለች መሥዋዕቷን በምታቀርብበት ጊዜ ሁሉ « ወአንሰ በእንቲአሆሙ እስዕል» ያለው ቃሉ ስለሚረዳቸው ለዘለዓለም ሕያው ነውና ይማልድላቸዋል» ብሎ ጻፈ።»
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « ጌታችን አምላካችን መድኃኒ ታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡-በመዋዕለ ሥጋዌው(በተዋህዶ ሰው በሆነበት ዘመን) ለአብነት(ምሳሌ ሊሆነን) ያደረገውንና ለድኅነታችን ብሎ የፈጸመውን መለ የት ያስፈልጋል። ብዙዎች እነዚህ ሁለት ነገሮች እየተደባለቁባቸው ነው፥“ዛሬም ያማልዳል፤” የሚሉት።ጌታችን አምላካ ችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡-እከብር አይል ክቡር፥እጸ ድቅ አይል ጻድቅ ሲሆን፡-የጾመው፥የጸ ለየው፥የሰገደው፥ለእኛ፡-አብነት(ለበጎ ነገር ሁሉ አርአ ያና ምሳሌ) ሊሆነን ነው። ለምሳሌ፡-አልዓዛርን ከማ ስነሣቱ በፊት ወደ አብ ከጸለየ በኋላ፡-“ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ፤”ብሎአል። ከዚያ በፊት የኢያኢሮስን ልጅ፡-ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንዲት በሆነች ሥልጣኑ አስነሥቶአል። ጥምቀታችንን በጥምቀቱ ቀድሶ የሰጠን፥ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንድንጠመቅም ያዘዘን፥ሕገ ወንጌልን የሠራልን፥ኅብስቱ ተለውጦ ሥጋ መለኮት፣ደሙም ተለውጦ ደመ መለኮት የሚሆ ንበትን ሥርዓተ ቍርባን ሠርቶ ያሳየን ፥ምሥጢሩንም በመስቀል ላይ የፈጸመልን ለድኅነታ ችን ነው።» ብለሃል
ይህ ያስቀመጥከው ቃል በቤተ ክርስቲያናችን ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ ትምህርት ነው። የምትጽፋቸውን ጽሑፎች ስመለከት ሁለት አደገኛ የሆኑ ሐሰተኛ የመከራከሪያ መንገዶችን ትጠቀማለህ። የመጀመሪያው የማከፈለውን የማይለያየውን መለያየት ( false dichotomy) ነው። ሁለተኛው ደግሞ ፥ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያላሉትን እንዳሉ አድርጎ በማቅረብ ( false premise) ፥ በዚያ ላይ የቅዱሳት መጻሕፍትን ማስረጃ ማቅረብ ነው።

በመጀመሪያ ደረጃ ጌታ ከጽንስ እስከ እርገት ያደረጋቸው ነገሮች በሙሉ ለቤዛነት ለደኅንነታችን ያደረጋቸው ሥራዎች ናቸው።  እነዚህ የቤዛነት ሥራዎች  ደግሞ አብነትም ሆነውናል።  ለምሳሌ ጾሙን፥ ጸሎቱን ስግደቱን ለአብነት እንደሆነ ተናግረህ፥ በመስቀሉ የተከናወነው ግን ለድኅነታችን እንደሆነ ተናግረሃል። ይህ ፍጹም ክህደት ነው። በመስቀሉ ላይ የተከናወነው ለደኅንነታችንም ለአብነታችንም መሆኑን ሲገልጥልህ፥ ቅዱስ ጴጥሮስ « የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና። እርሱም ኃጢአት አላደረገም፥ ተንኰልም በአፉ አልተገኘበትም፤ ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤» ብሎአል። ፩ ጴጥ ም. ፪፥፳፩
ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነው፥ « የጾመው የጸለየው የሰገደው ለእኛ አብነት ነው» በማለት በጾሙና በጸሎቱ ውስጥ ያለውን  የቤዛነቱን ሥራ ሙሉ በሙሉ ወደጎን ማድረግህ ነው። ቅዱሳት መጻሕፍትም የአበው ትርጓሜዎችም የጸለየው ወደ አብ መሆኑን ተናግረዋል። በመስቀል ላይ « የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ የጸለየው ለአብነት ለምሳሌ ብቻ ነውን? ይህን ከቶ ከየት አመጣኸው? በጾሙ ቢያስተምረንም፥ በዚያው በጾሙ ደግሞ ዲያብሎስን ድል ነስቶልናል። ጾሙ የምሳሌ ብቻ አይደለም። የቤዛነትም ነው።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያከናወነው ሥራው ብቻ ሳይሆን፥ ቃሉም ትምህርቱም ሥራውም የቤዛነት እንደሆነ፥ ይህም እስከ አለም ፍጻሜ እንደሚሠራ፥ አለቃ አያሌው ሲናገሩ፥ « እኔ በምድር ላይ ልሠራው የሰጠኸን ሥራ ፈጽሜ አከበርኩህ አሁንም አንተ አባት ሆይ ዓለም ሳይፈጠር ከአንተ ጋር በነበረኝ ክብር ግለጠኝ» በማለት ጌታችን ወደዚህ ዓለም ከመምጣቱ አስቀድሞ ወደነበረበት ካረገ በኋላ ምእመናን ኃይሉን፥ ጌትነቱን፥ ምልዓቱን፥ ስፋቱን፥ ርቀቱን፥ ጥንታዊና ዘለዓለማዊነቱን ለማወቅ ችለዋል። ተአምራት ብቻውን አይረዳም፤ ኃይል ካልተሰጠው በቀር። ከሙሴ ጀምሮ ብዙ ነቢያት ተአምራት ሲያደርጉ ኖረው አልፈዋል። ሥራቸውም ታሪክ ሆኖአል። ሠርተዋል፥ ሠርተው ነበር በማለትም ተወስኖአል። የጌታ ሥራ ግን ቃሉም ሥራውም ለዘላለም እንዲሆን እስከ ዓለም ፍጻሜም እንዲሠራ የተነገረና የተደረገ በመሆኑ በመዋዕለ ስብከቱ ብቻ ታይቶ የቀረ፥ ተሰምቶ ያለፈ አይደለም።»  ካሉ በኋላ « ከዕለተ ጽንስ እስከ ዕለተ ዕርገት የፈጸመው የቤዛነት ሥራ በየጊዜው የተነሡ ምዕመናን ወደ እግዚአብሔር ሊያቀርባቸው  ፍጹም ድኅነት ሊሠጣቸው ይችላል።»
መደመደሚያ፤ ምልጃ ለምን አስቸጋሪ ሆነ?
ባለፉት ሦስት ተከታታይ ጽሑፎች ቀሲስ ደጀኔ የገባበትን ስህተቶች ለማሳየት ሞክሬአለሁ። በዚህም ውስጥ እግዚአብሔር ወልድ በሰውነቱ ያከናወናቸው ሥራዎች ለድኅነታችን ወሳኝ የሆኑ ሥራዎች ስለሆኑ ስለእነዚህ ነገሮች ስንናገር በግዴለሽነት ልንናገር እንደማይገባ አመልክቼአለሁ። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ እንደተናገሩት እኛ ክርስቶስን « አንድ ባሕርይ » ስንል የሚያስረዳው ፍጹም የሆነ ተዋህዶን ነው እንጂ የአምላክነትና የሰውነት መቀያየጥና መደባለቅ አይደለም። አምላክነቱ ወደ ሰውነቱ አልተለወጠም፤ ሰውነቱም ወደ አምላክነቱ አልተቀየረም። በኦርቶዶክሳውያኑ እና በአውጣኪ መካከል የነበረው ትልቅ ልዩነት ይህ ነው። አውጣኪ የቄርሎስ ጠበቃ እንደሆነ አድርጎ ራሱን ቢያስቀምጥም፥ ለቄርሎስ « አንድ ባሕርይ» ማለትና ለአውጣኪ አንድ ባሕርይ ማለት የተለያየ ነበር። ለቄርሎስ አንድ ባሕርይ ማለት ክርስቶስ በፍጹም ተዋህዶ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው እንደሆነ ነው። በዚህም ተዋህዶ ያለመቀላቀል እና ያለመደባለቅ የቃልና የትስብእት መገናዘብ ስላለ፥ መከፈልና መለየት የለም። ለአውጣኪ ግን እንዲህ « አንድ ባሕርይ ሲል ትስብእትንና መለኮትን አንድ ላይ አጣፍቶ ነው። በመሆኑም ለእርሱ የሰውነቱን ነገር ለመናገር ቋንቋ የለውም።




ይህን ባለፉት ሦስት ክፍሎች በተነተንነውና መልስ በሰጠንበት የቀሲስ ደጀኔ ጽሑፎች ውስጥ በግልጥ አይተነዋል። ኢየሱስ ክርስቶስ በላ፥ ጠጣ፥ ማለደ፥ ጸለየ ለቀሲስ ደጀኔ ስድብ ነው። ምክንያቱም እንዴት አምላክ በላ ይባላል። እንዴት አምላክ ጸለየ ይባላል። እውነቱን ነው። የረሳው ግን ያ አምላክ የእኛን ባሕርይ ገንዘብ አድርጎአል። በመሆኑም በልቷል፥ ማልዷል፥ ጸልዮአል። አንቀላፍቷል። ሞቶአል። በሰውነቱ።
በአሁኑ ወቅት ጥቂቶች ያይደሉ፥ ራሳቸውን ሰባኪና ሊቅ ያደረጉ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን መድረክ ላይ ሆነው የሚናገሩትና ትምህርት ብለው የሚያቀርቡት ነገር፥ አንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን የማታውቀው ትርኪ ምርኪ ሲሆን ፥ አንዳንዱ ደግሞ የለየለት ፍጹም ክህደት ነው።
ለምሳሌ በቅርቡ አንዱ በአውደ ምሕረት ላይ ቆሞ በሥነ ሥርዓት የሰበከው እንዲህ ይላል። « ተአምረ ማርያም ከሌለ፥ ማርያም የለችም፥ ማርያም ከሌለች፥ ክርስቶስ የለም፥ ክርስቶስ ከሌለ ሥላሴ የለም፤ ሥላሴ ከሌለ እግዚአብሔር የለም።» ይላል። ይህ የኑፋቄ ሁሉ ኑፋቄ ነው። ይህ ሰባኪ እንዲህ ብሎ የሰበከው፥ ነገር አሳምራለሁ፥ የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት የማይቀበሉ ሰዎችን እቃወምበታለሁ ብሎ ነው።  ነገር ግን ያስተማረው ሀልዎተ እግዚአብሔርን ገደል የከተተ ትምህርት ነው።
ታዲያ ብዙዎቹ ወደዚህ ዓይነት ክህደት ውስጥ የሚገቡት ትምህርታቸውን ቤተ ክርስቲያኒቱ ባስቀመጠችው ቀዋሚ ትምህርት ላይ ስለማይመሠርቱና  ፕሮቴስታንቶችን ወይም ሌሎች የእምነት ድርጅቶችን በማየት እምነታቸውን ለመቅረጽ ስለሚሞክሩ ነው።
ለምሳሌ አንዳንድ ፕሮቴስታንቶች የቅዱሳንን ጸሎትና ምልጃ በመካድ የሚጠቅሱት ሮሜ 8፥34ን፥ ዮሐ 2፥1ን ነው። እነዚህ ንባቦች ክርስቶስ ለእኛ አስታራቂያችን፥ ተከራካሪያችን ጠበቃችን እንደሆነ የሚገልጡ ንባቦች ናቸው። ታዲያ ጥቂት ያይደሉ የኛዎቹ መልስ ሰጪዎች የሚያደርጉትና እያደረጉ ያሉት፥ አንደኛ ሙሉ በሙሉ የክርስቶስን ማስታረቅ፥ምልጃውን፥ ጠበቃነቱን መካድ፥ ከዚያ አልፎ ደግሞ እነዚህን ምንባቦች ለመቀየር ወይም ለማደብዘዝ መሞከር ነው። ይህ በእግዚአብሔር ቃል ላይ የሚሠነዘር ወንጀል ነው።
ማድረግ ያለብን ምን ነበር ? ማድረግ ያለብን ፥ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት፥ የክርስቶስን መካከለኛነት መካድ ሳይሆን በክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት እና በቅዱሳን ጸሎት መካከል ያለውን ልዩነት ማሳየት ነው፤   የክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት መዳናችን የተመሠረተበት ታላቅ ምሥጢር ነው። በግዴለሽነት ወደጎን የምናደርገው አይደለም። ለድርድርም የሚቀርብ አይደለም።

የክርስቶስ የማስታረቅ ሥራ ከፍጡራን የልመና ጸሎት ፍጹም የተለየ ነውና። ከዚህ በፊት በሌሎች ጽሑፎቻችን ላይ የጠቀስነው ቢሆንም ሊቀ ሊቃውንት አባ መልአኩ ታከለ የተናገሩትን እንደገና እንጥቀስ ፥ « ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅም፥ ጳውሎስን አራቂ ዘውእቱ አምሳሊሁ ለክርስቶስ፤ በክርስቶስ አምሳል አስታራቂ ( አማላጅ) ነው ብሏል የክርስቶስ አራቂነት በሞቱ ሲሆን የጳውሎስ ግን በጸሎቱና በትምህርቱ። ስያሜው በመገናኘቱ ምንም አያስደንቅም ተግባሩ የተለያየ ነውና ከዚህ የተነሳ ትምህርቱን መመለክቱ ተገቢ ነው። ይህን ለመረዳት የቤተክርስቲያንን ትምህርት ማወቅ ያስፈልጋል።» ብፁዕ አቡነ ሽኖዳ ያሉት ይህን ነው።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳም ለፕሮቴስታንቶች በሰጡት መልስ የቅዱሳንን ምልጃ እና የክርስቶስን ምልጃ ለይተው በሁለቱ መካከል ያለውን ልዩነት ሲያብራሩ በመጥቀስ ጽሑፋችንን እንደምድም። በነገራችን ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ ከክርስቶስ ምልጃና መካከለኛነት ጋር አዛምደው የጠቀሱአቸውን ንባቦች በጥንቃቄ ተመልከቱ እና የዘመናችን አውጣኪዎች እንዴት እንደሚክዷቸውና ለመቀየር እንደሚሞክሩ አስተውሉ። ከ
The mediation of the Lord Jesus Christ is an atonement, which means that He mediates for the forgiveness of our sins, being the Atoner who paid our debts on our behalf. His mediation means that He says to the Father: “Do not count their transgressions because I have carried their iniquity” (Is.53: 6). Thus He stands as a Mediator between God and men; or rather, He is the only Mediator between God and men; He fulfilled God’s Divine Justice and granted people the forgiveness of sins, by dying for them.
የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ፥ ለኃጢአት ሥርየት ( atonement) ነው። ይህም ማለት፥ ስለ እኛ ዕዳችንን የከፈለ ማስተስረያ በመሆን፥ ለኃጢአታችን ይቅርታ መማለዱ ነው። የእርሱ ምልጃ ማለት፥ ለአባቱ « አባት ሆይ በደላቸውን አትቁጠርባቸው፤ ምክንያቱም በደላቸውን እኔ ተሸክሜአለሁ» ማለቱ ነው። ( ኢሳ ፶፫፥፮) በመሆኑም፥ እርሱ በሰዎች እና በእግዚአብሔር መካከል መካከለኛ ሆኖ ቆሞአል። ወይም በሰዎችና በእግዚአብሔር መካከል ብቸኛው መካከለኛ ነው። እርሱ ስለ ሕዝቡ በመሞት፥ የእግዚአብሔርን ፍትሕ ያረካና ለሕዝቡ የኃጢአት ሥርየትን የሰጠ ነው። This is what St. John the Apostle mea
nt when he said: “And if anyone sins, we have an Advocate with the Father, Jesus Christ the righteous. And He Himself is the propitiation for our sins, and not for ours only but also for the whole world”(1John.2: 1,2). Here, the atoning mediation is very clear. It is a mediation for the sinner: “If anyone sins”, and this sinner needs atonement. The only One who offered this atonement was Jesus Christ the righteous. Hence He can mediate for us through His blood which was shed for us.
ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ «ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።እርሱም የኃጢአታችን ማስተስሪያ ነው፥ ለኃጢአታችንም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኃጢአት እንጂ።»  በማለት የተናገረው ይህን ነው ፩ ዮሐ ፪፥፩፡፪። በዚህ፥ የማስተሥረያ መካከለኛነቱ ግልጥ ነው። መካከለኛነቱ ለኃጢአተኛ ነው። « ማንም ኃጢአት ቢያደርግ»፤ ይህ  ኃጢአተኛ የኃጢአት ሥርየት ያስፈልገዋል። ይህን የኃጢአት ማስተስሪያ ማቅረብ የሚችል ጻድቅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። በመሆኑም እርሱ ስለ እኛ ባፈሰሰው በደሙ በኩል ይማልድልን ዘንድ ይችላል።

The same meaning is given in the words of St. Paul the Apostle about the Lord Jesus Christ being the only Mediator between God and men. He says: “For there is one God and one Mediator between God and men, the Man Christ Jesus, who gave Himself a ransom for all” (1Tim.2: 5,6). The Lord Jesus Christ mediates for us as the Redeemer who sacrificed Himself and paid the price of our sins. This type of mediation is utterly unquestionable. It is attributed to Christ only, whereas the intercessions of the saints has no connection with atonement or redemption. It is intercessions for us to the Lord Jesus Christ Himself.
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ብቸኛው መካከለኛ ስለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውም ተመሳሳይ ትርጕም አለው። «አንድ እግዚአብሔር አለና፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ፥» ፩ ጢሞ ፪፥፭፡፮። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛ የሚሆንልን፥ ራሱን መስዋዕት ያደረገና የኃጢአታችን ዋጋ የከፈለልን ቤዛ ሆኖልን ነው። እንዲህ ዓይነቱ መካከለኛነት ጥያቄ ውስጥ የማይገባ ነው። የሚሰጠውም ለክርስቶስ ብቻ ነው። የቅዱሳን ምልጃ በአንጻሩ፥ ከቤዛነት ( redemption) እና ከኃጢአት ማስተስሪያ ( atonement) ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። የቅዱሳን ምልጃ ስለ እኛ ወደ ራሱ ወደ ጌታ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የመለመን ነገር ነው።» በማለት አብራርተው ተናግረዋል።
እኛም በዚሁ ለቀሲስ ደጀኔ የሰጠነውን መልስ እንደመድማለን። ይህን እንድንጽፍና ስለ እምነታችን እንድንመሰክር አቅምና ጉልበት የሆነን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይክበር ይመስገን።





Saturday, August 12, 2017

ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)


« አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን » ??? ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)

ወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥ በክፍል አንድ ጽሑፌ ላይ፥በመካከላችን ስላለው ልዩነትና፥ ምሥጢረ ተዋህዶን ምን ያህል በተሳሳተ መንገድ እንደተረዳኸው ለማስረዳት ሞክሬአለሁ። በተለይም ቄርሎስን በትክክል ባለመረዳትህ፥ መገናዘብን እንደመቀላቀል እንደቆጠርከው፥ የቃልን ገንዘብ ዘርዝረህ የሥጋን ገንዘብ ግን ሙሉ በሙሉ መካድህን አመልክቼህ ነበር። ለዚህም ራሱን ቄርሎስን ምስክር አድርጌ አቅርቤአለሁ። በዚህ በክፍል ሁለት ጽሑፌ እንደተለመደው ያንተን ጽሑፍ በማስቀደም የእኔን መልስ ደግሞ በሥፍራው አስቀምጣለሁ። ስለ ብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ስለጻፍከው፥ እንዴት በክርስቶስ እንደተፈጸመ አባቶች የሚተረጉሙትን እንዳለ ስላስቀመጥክ፥ከአንዳንድ አንተ ከጨመርካቸው ጥቃቅን ነገሮች በቀር እኔም ስለምስማማበት ለቦታና ለጊዜ ስንል በማለፍ በቀጥታ፥የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ስለሆነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ተናገርከው ታላቅ ስህተት እንመጣለን። ይኸውም በእብራውያን መልእክት ላይ « አብ ሾመው» የሚለውን አንተ ደግሞ በራስህ  « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» ብለህ መጽሐፍ ቅዱስን ተጋፍተህ ፥ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጣረስ ቃል አስቀምጠሃል።  የዛሬው ክፍል ሁለት ጽሑፌ ይህች አደገኛ ሐረግ « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» የሚለው ላይ ያተኮረ ነው። ይህን ከራስህ ጽሑፍ እንመልከተው።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ለራሱ ክብርን የሚወስድ የለም። (እግዚአብሔር እንደ አሮን ከመረጠው በቀር ማንም ተነሥቶ ሥልጣነ ክህነትን ለራሱ ገንዘብ ማድረግ የሚቻለው የለም)።”ብሎአል። =ከዚህም አያይዞ፡-“እንዲሁ ክርስቶስም ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ ራሱን ያከበረ(የሾመ) አይ ደለም፤ ነገር ግን፡-“አንተ ልጄ ነህ፥እኔም ዛሬ ወለድሁህ፥ያለው እርሱ ነው፤ዳግመኛም፡-እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘላለም ካህን አንተ ነህ፥ይላል፤”ብሎአል።መዝ፡፪፥፯፤፻፱፥፬፣ማቴ፡ ፫፥ ፲፯፤፲፯፥፭።ይህም፡-“አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለሃል።
ነገረ መለኮት በተለይም ምሥጢረ ሥጋዌ፥ በመላ ምት ወይም በግምት የሚነገር ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ቃልና የአበውን ምስክርነት በመያዝ በጥንቃቄ የሚነገር ነው። አሁን ግን በአንተ በቀሲስ ደጀኔ ጽሑፍ ላይ የምመለከተው ድፍረት ነው። ጥንቃቄ የጎደለው ታላቅ ድፍረት ነው። ለየዋህና የቤተ ክርስቲያኒቱን ነገረ መለኮት ለማያውቅ ሰው፥የተደረደረው ጥቅስ የእውነት ማረጋገጫ ሊመስል ይችላል። ከጥቅሱ በስተጀርባ ያለውን ታላቅ ስህተት ግን አያስተውልም። በዚህ በዛሬው ጽሑፌ፥ ምን ያህል የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀዋሚ ትምህርት እንደናድከው የማመለክትህ በአንዲቱ ሐረግ ብቻ ነው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» የምትለውን አባባልህን በጥንቃቄ ተመልከተው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን»? አብ ካልሾመው ታዲያ ማን ሾመው? መጽሐፍ ቅዱሱ « ራሱን የሾመ አይደለም» እያለ የተናገረው ስለምንድነው? ቃሉ እንዲህ በግልጥ እየነገረህ፥ ከቅዱስ ቃሉ ጋር ጦርነት ውስጥ መግባት ለምን አስፈለገ? ይህን እውነት ለመቀበል የከበደህ የምሥጢረ ሥጋዌን ነገር በተለይም የሥጋን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ከአምላክነቱ ቆርጠህ ስለ ጣልክ፥ ወይም ለመለኮት ከተዋሃደው ከትስብእቱ የተነሣ ሊነገርለት የሚገባውን እንዳለ ለመቀበል አለመፈለግህ ነው።
አንተ ጥቅሱን እና የአበውን ትርጓሜዎች ወደ ጎን በማድረግ፥ ሁለት አሳቦችን አቅርበሃል፤ የመጀመሪያው « አብ ሾመው ማለት አይደለም» የሚል ነው። ሁለተኛው ደግሞ፥ « ሾመው» የሚለው ቃል ፥ « ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው» የሚል ነው። ይህን ያስባለህ በተደጋጋሚ የወደቅህበት የአውጣኪ ስህተት ነው። ይህ ባለአዋቂነት የመጣ አሳብ፥ እርሱ በአምላክነቱ ከአብ ጋር እኩል ሆኖ ሳለ እንዴት ይሾማል የሚል ነው። አውጣኪ ያልኩህ የእኛን ሥጋ መልበሱን ፈጽሞ መካድህ፥ መዋቲ ( ሟች) ሥጋ መልበሱን፥ በዚህም« ሕቀ አህጸጽኮ እመላእክቲከ» ከመላእክት ጥቂት አሳነስከው መባሉን መርሳትህ፥ ፍጹም ሰው መሆኑን መዘንጋትህ ነው። ይህን ከአውጣኪ የመነጨውን ስህተት ሙሉ በሙሉ ለመደምሰስና በሥጋው አብ ሾመው ተብሎ ሊነገር እንደሚገባ ለማስረዳት፥ ራስህ መነሻህ ያደረከውን የዕብራውያን ንባብና አሳብ ከአባቶች ትርጓሜና ትምህርት አንጻር መተንተን አለብን፤
አንተ የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭-፯ን አባቶች በትርጓሜ ጳውሎስእንዴት እንደተረጐሙት እንመለክተው፤መጀመሪያ ገጸ ንባቡን እንዳለ አስቀምጣለሁ ከዚያም የአባቶችን ትርጓሜ አስቀምጣለሁ፤ ገጸ ንባቡ እንዲህ ይላል፦ «እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም ነገር ግን፦ አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ ያለው እርሱ ነው፤እንደዚህም በሌላ ስፍራ ደግሞ፦ አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ይላል። እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ »
የአባቶች ትርጓሜ ደግሞ እንዲህ ይላል፦
« እንደዚህም ኹሉ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት ይባል ዘንድ ራሱን የሾመ አይደለም። አንተ ልጄ እኔ ዛሬ ወለድኩህ ያለው እሱ፥ ዳግመኛ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ፤ አንድም አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ።»
አባቶች በግልጥ ያስቀመጡት ይህን ነው። ምንም ሌላ ሐታታ የማያስፈልገው ግልጥና ጥርት ያለ ነው። ንባቡን እናቃናው ብለው ለማጥፋት አልደፈሩም። ያሉት « « ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ነው ያሉት። አመክንዮ ዘሐዋርያትም ይህን ሲያረግጥ « ወዐረቀ ትዝምደ ሰብእ ምስለ እግዚአብሔር ሊቀ ካህናቲሁ ለአብ። የአብ ሊቀ ካህናት የሚሆን እርሱ ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀን » ይላል። የአብ ሊቀ ካህናት ብሎታል። በአብ ፊት የሚቆምልን የሚታይልን ሊቀ ካህናት ማለት ነው። ከዚህ የተነሣ ስለ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ስናምንም ሆነ ስናስተምር የሚከተሉትን ሦስት ነገሮች አስረግጠን መናገር አለብን።

፩ኛ. ሊቀ ካህናት የሚለው ስያሜ ለክርስቶስ የተሰጠው ሰው በመሆኑ ነው።

ሊቀ ካህናት የሚለው የሥጋዌ ስሙ ነው፤ ደግሞም የሹመት ስም ነው። የባሕርይ አምላክ ለሆነ ለእርሱ ሹመትን መቀበል ተዋርዶ አይሆንም ወይ? አዎ በሚገባ። ነገር ግን በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት መወሰንን የተቀበለ፥ በየጥቂቱ ያደገ፥ ከእናቱ ጡት ወተትን በመለመን ያለቀሰ፥ በሥጋው ከአባቱ ሹመትን ተቀበለ መባሉ የከበደን ከቶ ለምን ይሆን? ከጽንስ እበየማነ አብ እስከሚቀጥበት እስከ እርገቱ የሠራው የቤዛነት ሥራ ( ማለትም በእኛ ተገብቶ፥ በእኛ ፈንታ ሆኖ መሆኑን) መሆኑን መናገር ያሳፈረን ለምን ይሆን?
ሃይማኖተ አበው እንዲህ ይላል፦ « ፩ዱ ለሊሁ ወረደ ወተሠገወ እምህላዌነ ወኮነነ ሊቀ ካህናት ወአዕረገ በእንቲአነ ሥጋሁ መሥዋዕተ ለአቡሁ ወአብጽሐነ ሎቱ በዘቦቱ ሐመ፤ እርሱ አንዱ ወደዚህ ዓለም ወርዶ ባሕርያችንን ባሕርይ አድርጎ ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) ሆነን፤ ስለ እኛም ሥጋውን መሥዋዕት አድርጎ ወደ አባቱ አቀረበ እንጂ፤ በታመመበት በሥጋው ለርሱ ገንዘብ ለመሆን አበቃን » (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፮) ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በግልጥ እንደተናገረው፥ ሊቀ ካህናት ተብሎ የተነገረለት፥ ወደዚህ ዓለም በወረደ ጊዜ ነው።  ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እንዲህ ይላል። « በሰው ባሕርይ ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ፥ ስለ እኛም ራሱን ቍርባን መሥዋዕት አድርጎ ለአባቱ ያቀርብ ዘንድ ወልድ ዋሕድ ሰው ሆነ።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ም. ፶፮. ክፍል ፬ ቍ. ፱፤

እዚህ ላይ አንድ ጥልቅ እውነትን እንዳስስ፤ ለመሆኑ ሥግው ቃል ሊቀ ካህናት ለመሆን ለምን አስፈለገው? ይህን ድንቅ ምሥጢር ለመረዳት ሰፊ ሐተታ የሚያስፈልገው ቢሆንም ከተነሣንበት ዓላማ አንጻር፥ ካህን ሆኖ ፍጥረት ወደ አምላኩ ለማቅረብ የተፈጠረው አዳም፥ በኃጢአት በመውደቁ ምክንያት፥ ሁለተኛው አዳም ክርስቶስ፥ በእርሱ በኩል፥ ሰው ብቻ ሳይሆን ፍጥረት ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ይገባ ዘንድ ነው። ቅዱስ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሲገልጥ እንዲህ ይላል። «በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤ በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።» ( ኤፌ ፩፥፱-፲) በሰማይና በምድር ያለው እንዴት በክርስቶስ እንደሚጠቀለል፥ የሐዋርያት ተከታያቸው የሆነው ሄኔሬዎስ በመጻሕፍቱ የገለጠውን በሰፊው ወደ ፊት እናየዋለን። ለአሁን ግን ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ በጸለየው ጸሎት ላይ አስደናቂ የተዋሕዶን ምሥጢር እንዴት እንደገለጠው እንመልከተው። « የሰውን ባሕርይ እስኪዋሐድ ፥ ዘመዳቸውም ሆኖ ሰውን ሁሉ ወደ እርሱ እስኪያቀርብ ድረስ፥ ሰው ፊትህን አይቶ ሕያው መሆን አይቻለውም ነበርና። ሰዎች መለኮትን ያዩት ዘንድ የበቁ እስኪሆኑ ድረስ በሰው ባሕርይ ተገለጠ። በሥጋ ዘመዳችን ሆኖ ባየነው ጊዜ በአብ ቸርነት የወልድን ጌትነት እናመሰግነዋለንና» ሃይማኖተ አበው ዘጎርጎርዮስ ዘአርማንያ ም. ፲፭. ክፍል ፪. ቍ ፲-፩ አሁንም እኛን ተዛምዶ ወደ እርሱ ያቀረበን ሊቀ ካህናችን ይክበር ይመስገን።
እዚህ ላይ ቀደም ሲል የተናገርኩትን እንደገና አስረግጬ ለመናገር፥ ሐዋርያ፥ ክርስቶስ፥ ሊቀ ካህናት፥ ሰው፥ የሚሉት ስሞቹ በሥጋው ያገኛቸው ስሞች ናቸው። ለምሳሌ ይኸው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል። « አብ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም ስለ ላከው፥ ሐዋርያ አለው፤ ስለ አመንበት በጎ ሥራ ለመሥራት የምንቀና፥ ደግ ወገን አድርጎ ገንዘብ አድርጎናልና፥ ለእኛ ማልዶልናልና ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) አለው» ይለናል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፮

፪ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው በአባቱ ነው።

ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ግልጥ አድርጎታል። አንተው የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭ን አባቶች«ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ብለው ተርጉመውታል። የአባቶችን ትርጓሜ «ልታቃና » ካልሞከርክ በቀር መልሱ ግልጥ ነው። በሌላ ሥፍራም ሐዋርያው « ሕጉ ድካም ያላቸውን ሰዎች ሊቀ ካህናት አድርጎ ይሾማልና፤ ከሕግ በኋላ የመጣ የመሐላው ቃል ግን ለዘላም ፍጹም የሆነውን ልጅ ይሾማል» ይላል። ( ዕብ ፯፥፳፰)  አባቶች ይህን ንባብ ሲተረጉሙ ሰፊ ግንዛቤን የምናገኝበትን ሐተታ ስለሚሰጡበት እዚህ ላይ መመልከቱ መልካም ነው። እንዲህ ይላሉ፦ « ኦሪትሰ ሰብአ ትሰይም ሊቀ ካህናት መዋቴ፤ ኦሪትስ የሚሞት ሰውን ሊቀ ካህናት አድርጋ ትሾማለች። የቀድሞው ሊቀ ካህናት ዕለት ዕለት መሥዋዕት ማቅረቡ፥ የዛሬው ዕለት ዕለት አልማቅረቡ እንደምን ነው ትሉኝ እንደሆነ ኦሪት መዋቲ ( ሟች) ሰውን ሊቀ ካህናት ትሾም ነበረና፥ ደካማ ሰውን ትሾም ነበረና፥ የቀደመው ሊቀ ካህናት አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ሥርየት ድኅነት ማሰጠት የማይቻለው ስለሆነ ነው። ወቃለ መሐላሁሰ ዘመጽአ እምድኅረ ኦሪት ሤመ ለነ ወልደ ፍጹመ ዘለዓለም። ከኦሪት በኋላ በመሐላ የተሠራ ሕገ ወንጌል ግን ሕያው ወልድን፥ ኃያል ወልድን ሹሞልናልና። የዛሬ አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ስርየት ድኅነት መስጠት የሚቻለው ስለሆነ ነው።»
ሃይማኖተ አበው ደግሞ ግልጥ አድርጎ ምንም ማፈናፈኛ ሳይሰጥ አያስቀምጠዋል፤እንዲህ ይላል፦« ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት በአደረገው በአብ ዘንድ የታመነ እውነተኛ ነው አለ። ለወገኖቹ በጎ ማገልገልን እንዲያገለግል ይጐዱም ዘንድ ቸል እንደማይላቸው እኛ እንድናውቅ መናገሩ ነው። ሊቀ ካህናት አደረገው ( ገብሮ) ያለውንም ሐዋርያ ሊቀ ካህናት አድርጎ እንደ ሾመው መናገሩ ነው። በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት ተናገረ እንጂ፥ ሥጋ ፍጡር ነውና።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፯-፳፰
ቀሲስ ደጀኔ እልህ ሃይማኖት ካልሆነብህ በቀር፥ ያነሣኻቸውን ሁለት ነገሮች ይህን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጥቅስ ይንድብሃል። የመጀመሪያው « አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን » የሚለው አሳብህን፥ ሊቀ ካህናት አደረገው ማለት ሊቀካህናት አድርጎ ሾመው ማለት እንደሆነ ይነግርብሃል ። ሁለተኛ « የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለህ ከራስህ አንቅተህ ያስቀመጥከውን ትርጓሜህን፥ በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት  እንጂ» ይልብሃል።
አሁንም ደጋግሜ በፍቅር የምነግርህ፥ ወደዚህ ታላቅ ክህደት ያገባህ፥ የትስብእትን ገንዘቦች በሙሉ መካድህ ነው። ሾመው ለማለት ያስቸገረህ አዋረድኩት ብለህ ነው። ነገር ግን ዓለም የዳነበት የድኅነት ምሥጢር ይህ ተዋርዶቱ ነው። አንተ ግን በካራ ቆረጥከው፥ ከፈልከው። ተዋህዶን አፋለስከው። ሾመው የተባለው በአምላክነቱ ሳይሆን በሰውነቱ ነው። የፈጠረውን ሥጋ በመልበሱ፥ የፈጠረውን ሥጋ በመዋሃዱ ነው።

፫ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው ለማስታረቅ ነው።

ቀደም ሲል ባየነው በዕብ ፭፥፭ ላይ፥ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመበትን ሲተረጉሙ አባቶቻችን በገጸ ንባቡ ላይ በመመርኮዝ የተሾመበትን ምክንያት በሚገባ ግልጥ አድርገው አሳይተውናል። እንዲህ ይላሉ፦ « አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ አለ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ። » አባቶች ያሉትን አስተውል። ክህነቱ የታወቀው፥ በአስታራቂነቱ፥ ጸሎትንና ስኢልን ( ምልጃን) በማቅረቡ ነው።
የሊቀ ካህናት ዋና ሥራ ምንድነው ስንል፥ ማስታረቅ፥ መማለድ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደነገረን «. . . ኃጢአታችንን ለማስተስረይ፥ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም [ሐዋርያው]ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ፥ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም ነገር ያስተምረን ዘንድይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው?» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፫-፲፬

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዚህ ሥፍራ አራት መሠረታዊ ነጥቦችን ያነሣል። አንደኛ፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት የሆነን ኃጢአታችንን ለማስተስረይና ከአብ ጋር ለማስታረቅ ነው። በሁለተኛ ደረጃ፥ ሊቀ ካህናት የሆነልን እርሱ በሁሉ የሚያዝንልንና የሚራራልን፥ የእኛን ድካም የሚያውቅ በነገር ሁሉ እኛን የመሰለ ነው። ሦስተኛ፥ የሥጋዌው ዋና ተልዕኮ የማስታረቅ አገልግሎት ነው። ሌላ ምክንያት የለውም። አራተኛ፥ ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ( ይህን የማስታረቅ አገልግሎት ማለትም የክርስቶስን  ምልጃ፥ ከክርስቶስ መካከለኛነት አንጻር በክፍል ሦስት ጽሑፋችን  በሰፊው እንዳስሰዋለን።)

፬ኛ. ሊቀ ካህንነቱ ለዘላለም ነው።

በብዙው ክርክራችን ውስጥ የዘነጋነው አንድ ታላቅ ጥያቄ አለ። ይኸውም ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ሊቀ ካህናት ነው ወይስ አይደለም ? የሚል ነው። ቅዱሳት መጻሕፍትም ሆኑ የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት የሚመልሱልን በአዎንታ ነው። የመልክአ ኢየሱስ ደራሲ ይህን እውነታ ሲናገር እንዲህ ይላል፦
« እምሥራቀ ፀሐይ እስከነ ዐረብ ይትአኰት ስሙ ለእግዚአብሔር አምላክነ፤ ኪያከ ወልዶ ዘፈነወ ለነ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ፤ አስተጋብአነ ኀበ ትረፍቅ መካነ፤ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንሕነ።
« አንተን ልጁን የላከልን፥ የአምላካችን የእግዚአብሔር  ስሙ ከመ ጸሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያ ይክበር ይመስገንና ሊቀ ካህናችንን የምትሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ በመላው ዓለም የተበተን እኛን ( ቤተ ክርስቲያንን) አንተ ባለህበት በዚያ ሰብስበን» በዕለተ አርብ ባቀረበው መሥዋዕት፥ በዚያ በብርቱ ጩኸትና ዕንባ ባቀረበው ጸሎትና ምልጃ፥ ዛሬም ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ መቅረቢያችን ነው ።
ሞት እንደሚያግደው እንደ አሮን ልጆች ክህነት ሳይሆን፥  ክህነቱ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ክህነት ለዘላለም ነው የተባለው ለዚህ ነው። በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ይፍታህ ይህድግ በማለት በወንጌል የተገኘውን ከኃጢአት ነጻ የመሆን አዋጅ ( ሥርየተ ኃጢአትን ስታውጅ) « ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የካህናት አለቃ ( ሊቀ ካህናት) ይቅር ባይ» ብላ ሊቀ ካህንነቱን በመናገር ነው።
ሐዋርያውም በግልጥ «እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ » ብሎአልና ሊቀ ካህናችን አሁንም በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የምመጡትን ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው። ዕብ ፯፥፳፫-፳፮
እንግዲህ እስከ አሁን የተማርነውን የዕብ ፭፥፭-፯ን በካታኪዝም ( በጥያቄና መልስ) ብናስቀምጠው ብናቀርበው ይህ ነው። « ሊቀ ካህናት አድርጎ የሾመው ማን ነው? አባቱ እግዚአብሔር አብ። እንዴት ሾመው ተባለ፤ ሥጋን በመልበሱ ምክንያት። ሊቀ ካህናት የሆነው ለምንድነው? ሊያስታርቀን። የሚያስታርቀን ከማን ጋር ነው? በአምላክነቱ ከራሱ ጋር እንዲሁም ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር፤ እንዴት አድርጎ አስታረቀን? በራሱ መሥዋዕትነት ጸሎትና ምልጃን በማቅረብ ነው። ሊቀ ካህንነቱ እስከመቼ ነው? ሊቀ ካህንነቱ እንደ መልከጼዴቅ ባለ ሹመት ለዘላለም ነው። እርሱ ለዘላለም ህያው ሆኖ ይኖራልና፤ በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ፈጽሞ ያድናቸዋል።

መደምደሚያ

እንግዲህ ከላይ በዝርዝር ያሳየሁህ፥ በግዴለሽነት፥ « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» ብለህ ያስቀመጥከው የስህተት ቃል፥ ምሥጢረ ሥጋዌን እንዴት እንደሚያፈልስ ነው። ሁለቱን ግብራት አንዱን በመሰረዝ ወይም በመቀላቀል ወይም መክፈልና በመነጠል የሚደረግ ትንተና አደገኛ በሆነ የስህተት ገደል ውስጥ ይጥላል። ከዚህ ስህተት ራስን ለመጠበቅ ኦርቶዶክሳውያኑ አባቶች የጌታን የማዳን ሥራ የገለጡበትን መንገድ መከተል ያሻል። የጎርጎርዮስ ዘኑሲስን ምክር ልብ በል። « ሁለቱ ግብራት ለርሱ አንድ እንደሆኑ አየህን? ሰው የሆነ አምላክ እርሱ ነው። አንድ ነው ሁለት አይደለም። ፈጣሪ መለኮቱን ፍጡር ወደ መሆን አልለወጠውም። ፍጡር ሥጋውንም ፈጣሪ ወደ መሆን አልለወጠውም። መችም መች አንድ ብቻ ነው። ሁለት አይደለም። የተገዢ ባሕርይን የተዋሐደ በእርሱ ትህትና እኛ እንከብር ዘንድ የተዋረደ እርሱ ነው። ሕማማችንን የታገሠ፥ ደዌያችንን የተሸከመ፥ በደላችንን የተቀበለ፥ ስለ እኛ ራሱን የማያልፍ የማይለወጥ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ የማይሻር የማይለወጥ ካህን እርሱ ነው። የሚሠዋ በግ እርሱ ነው። የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው። ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው።»  ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ም. ፴፮ ክፍል ፬ ቍ. ፳፬-፳፭  ትስብእትንና መለኮትን በተዋህዶ መግለጥ ማለት ይህ ነው። ያለመቀላቀል፥ ያለመክፈል፥ ያለመለወጥ፥ ያለመለየት፤ ተዋህዶ በተአቅቦ ማለት ምሥጢሩ ይህ ነው። ይህን ከተረዳኸው፥ አብ ሾመው፥ ወደ አብ ጸለየ ማለደ የሚል ስታገኝ አይከብድህም፤ ከሁሉም በላይ  እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን የእኛን ባህርይ ገንዘብ ባደረገ በእርሱ አታፍርም።  የአብ ሊቀ ካህናት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ፥  አስደናቂ የሆነውን ሰው የመሆኑን ምሥጢር፥ አሁንም አብዝቶ ይግለጥልን። አሜን።

ማሳሰቢያ፦ በሚቀጥለው በክፍል ሦስት ደግሞ « ይማልዳል ለማለት ሳይሆን » በማለት የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የጻፍከውን ስህተት፥ ቅዱሳት መጻሕፍትንና የአበውን መጻሕፍት በመጥቀስ እናርመዋለን። በዚያ ውስጥም መካከለኛነት፥ ምልጃ፥ አስታራቂነት ስለሚሉት ቃላት መጽሐፍ ቅዱስና የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ያስተማሩትን በሚገባ እናየዋለን።



Monday, July 24, 2017

ግልጥ የወጣ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል አንድ)



ከቀሲስ መላኩ ተረፈ


ለወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥በዕብ ፭፥፯ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል መሠረት አድርገህ ( የብፁዕ አባታችንና የእኔን ፎቶ አስደግፈህ) የጻፍከውን ተመለከትኩት፤ በአንድ በኵል፥ ከተራ አሉባልታና ክስ ወጥተን፥በክርክርም ቢሆን፥  ስለ ክርስቶስ እንድንነጋገር ያደረገንን አምላክ ሳመሰግን፥ በሌላ በኩል አንተና አንተን ተከትለው በቲፎዞ የሚነጉዱት ስለገባችሁበት ከባድ አደጋ ሳስብ አዝናለሁ። ይህ የልጅ ጨዋታ አይደለም። አሁን እያደረጋችሁ ያላችሁት፥ ቤተ ክርስቲያንን ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር የሚያለያይ፥ አባቶቻችን በስንት ተጋድሎ ያቆዩትን የተዋህዶ ምሥጢር የሚያፋልስ ነው። በመሆኑም የሚቀጥለው ጽሑፌ በአንድ በኩል በጥንቃቄ የአባቶችን ትርጓሜና የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት እንድታጠናው ለማሳሰብ ሲሆን፥ በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የተጋረጠውን አደጋ ለማሳሰብ ነው። ምንም እንኳ እኔን መናፍቅ ብትለኝም፥ አንዳንዱን የአተረጓጎምህን መንገድ ስመለከት መናፍቅ ለማለት ይከብደኛል። ከምርምርና ከዕውቀት ሳይሆን፥ከአላዋቂነት የመጣ ስህተት ነውና የማየው።  በመሆኑም በመጀመሪያ ጽሑፍህን በትምህርተ ጥቅስ ጎላ ብሎ እንዲቀመጥ በማድረግ፥ ለእያንዳንዱ መልስ ለመስጠት  እሞክራለሁ። በአንቀጽ የተከፋፈለ ባይሆንም ለመልስ እንዲረዳኝ ከፋፍየዋለሁ፤ አላስፈላጊ የሆነና አለቦታው የገባውን ንባብ ግን ከጊዜና ከቦታ አንጻር አልፌዋለሁ፤
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ ፦  “ እርሱም በሥጋ ወራት . . . ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤”ዕብ፡፭፥፯። =ይኸንን ኃይለ ቃል የተናገረው፡-ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ነው።ይህ ሐዋርያ መልእክ ቶቹን ሁሉ የጻፈው በጸጋ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ነው።ይኸንንም፡-የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ፡-“እን ዲህም የተወደደው ወንድማችን ጳውሎስ ደግሞ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ጻፈላችሁ፥በመልእክ ቱም ሁሉ ደግሞ እንደ ነገረ ስለዚህ ነገር ተናገረ።በእነዚያ ዘንድ ለማስተዋል የሚያስቸግር ነገር አለ፥ያል ተማሩትና የማይጸኑትም ሰዎች ሌሎችን መጻሕፍት እንደሚያጣምሙ እነዚህን ደግሞ ለገዛ ጥፋታ ቸው ያጣምማሉ።”በማለት ገልጦታል።፪ኛ፡ጴጥ፡፲፭። =ቅዱስ ጴጥሮስ እንደመሰከረው፥መናፍቃኑ፡-አጥፍቶ ጠፊ የሆኑት፥በአብዛኛው፡-የሐዋርያውን መልእክታት በመጠቃቀስ ነው።ይኸውም የንባቡን ትርጓሜና ምሥጢር ካለማስተዋልና መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ሌሎች ልበ ወለድ መጻሕፍት ከመመልከት ነው።» ብለሃል።
ግሩም ነው! ስድቡን ቀነስ ብታደርገውም፥ ዛሬም ያችው የተለመደችው መናፍቃን የምትለውን ቃል ፎቶአችንን አስቀምጠህ ተጠቅመሃል።  ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረው ቃል በእውነትም ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረውን የምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነገር ባለማስተዋል የሚያጣምሙትን የገሠጸበት ቢሆንም፥ ዛሬም መጻሕፍትን ለሚያጣምሙት የሚጠቀስ ቃል መሆኑ እሙን ነው። በአንድ በኩል የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ ንባብ ጥሬ ዘሩን ሳይቀር ለመለወጥ የደፈርህ፥ እንዲህ ተብሎ ሊጻፍ አይገባም ያልክ አንተ ነህ፤ በሌላ በኩል የአባቶችን ትርጓሜ እንኳ ሳይቀር፥ ያለምንም ሐፍረት ያጣመምክ አንተ ስለሆንክ « ለገዛ ጥፋታቸው ያጣምማሉ» የተባለው የሚቀጸለው ለአንተ ነው። ትርጓሜ ጳውሎሱን ሳይቀር እንዴት እንዳጣመምከው በግልጥ በማስረጃ አመጣዋለሁ። ወደ እኔ ጽሑፍ ከሄድክ፥ በማስረጃነት ያቀርብኩልህ ትርጓሜ ወንጌልን፥ ሃይማኖተ አበውን፥ የጥንትና የዘመናችን አባቶችን እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስን ነው። ጳውሎሱን አንተም እኔም የምንጠቅሰው ኃይለ ቃሉ ያለበት ስለሆነ ነው። ዛሬም ከእነዚሁ ንጹሐን ምንጮች ነው የምጠቅስልህ፤  መናፍቃኑ ላልከው ግን እኔም እንደ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ እልሃለሁ፤  «ነገር ግን ይህን እመሰክርልሃለሁ፤ በሕጉ ያለውን በነቢያትም የተጻፉትን ሁሉ አምኜ የአባቶቼን አምላክ እነርሱ ኑፋቄብለው እንደሚጠሩት መንገድ አመልካለሁ፤» ሐዋ ፳፬፥፲፬
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « ለመሆኑ፡-ሐዋርያው መልእክት ትርጓሜ ምንድነው? -“ነገርን ከሥሩ፥ውኃን ከጥሩ፤”እንዲል፡-መልእክቱን ለመረዳት በመጀመሪያ የነገሩን ሥረ መሠረት እንመለከታለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡-ዕብራውያን ምዕራፍ አምስትን የጀመረው፥ በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩት ሊቃነ ካህናት፡-ለአዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት፡-ለኢየሱስ ክርስቶስ የነበራቸ ውን ምሳሌነት በማብራራት ነው። በምሳሌውና በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነትም የፈጣሪና የፍጡር ነው፥እነርሱ ፍጡራን ፥እርሱ ግን ፈጣሪ ነው፤እነርሱን የሾማቸው እርሱ ነው፥እርሱ ግን ሿሚ የለበትም፤ ሹመት የባሕርይ ገንዘቡ ነው።» ብለሃል።
ይህ ሙሉ የእብራውያንን የሊቀ ካህንነት ትምህርት የገለጠ አይደለም። ለምሳሌ ስለ አዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት ስትናገር፥ በምሳሌናው በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነት የፈጣሪና የፍጡር ነው ብለሃል፤ መልካም ነው።  ይህ እንዳለ ሆኖ ግን፥ ነገርን ከሥሩ እንዳልከው የዕብራውያን መልእክት በዋናነት የሚያሳየን አንተ ልትናገረው ያልደፈርከውን ነገር ነው። ይኸውም፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በእውነት ሰው የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ በእኛ ፈንታ የቆመ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ፥ የጮኸ፥ የደከመ፥ የለመነ፥ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበና አሁን በእውነተኛይቱ ድንኳን ያለ አስታራቂያችን ሊቀ ካህናት መሆኑን ነው። ይህን በዕብራውያን መልእክት  ውስጥ በሙሉ እናየዋለን።

አንደኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የቆመ ሊቀ ካህናት ነው። « እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ።» ( ዕብ ፬፥፲፬ ) አባቶቻችን ይህን ሲተረጉሙ « ብንመለስ ማን ያስታርቀናል እንዳይሉት፥ ብነ ሊቀ ካህናት አለ፤ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ደግ አስታራቂ ኢየሱስ ክርስቶስ አለን።»  

ሁለተኛ፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን የሆነ ነው። «ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።» ዕብ ፬፥፲፬።  ሊቀ ካህናትም ያሰኘው ይኸው ፍጹም ሰው መሆኑ ነው። « ከግብራችን ሲያወጣው « ዘእንበለ ኃጢአት ባሕቲታ ከኃጢአት በቀር » አለ። ከባሕሪያችን ሲያገባው « ምኩር በኩሉ በአምሳሊነ እንደ እኛ የተፈተነ» አለ» ይለናል፥ ትርጓሜ ጳውሎስ።    ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በነገር ሁሉ እኛን መምሰሉ እንዴት እንደሆነ ሲናገር፥ « እንደ እኛ ፍጹም ሰው ሆኖ መወለዱ፥ ከኃጢአት ብቻ በቀር፥ እንደ እኛ ለሥጋ የሚስማማውን፥ ሁሉ መሥራቱ ነው እንጂ፤ይኸውም በፈቃዱ ያደረገው መፀነስ፥ መወለድ፥ መብላት፥ መጠጣት፥ መተኛት፥ መድከም፥ መታመም መሞት ነው።» ይላል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪


ሦስተኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ የሆነ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ ስለሆነ፥  የተቤዣቸውንና ያዳናቸውን « ወንድሞቼ ሊል ያላፈረ፥ « በኵረ አኃው» ነው።  «ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና። የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸውና፤ስለዚህም ምክንያት፦ ስምህን ለወንድሞቼ እነግራቸዋለሁ በማኅበርም መካከል በዜማ አመሰግንሃለሁ፤ ደግሞም፦ እኔ በእርሱ እታመናለሁ፤ ደግሞም፦ እነሆኝ እኔን እግዚአብሔር የሰጠኝንም ልጆች ሲል ወንድሞች ብሎ ሊጠራቸው አያፍርም።» ዕብ ፪፥፲-፲፫  ። አስተውል፥ በሥጋዌው ከእኛ ጋር በመዛመዱ፥ « የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸው» ተባለ፤ትርጓሜ ጳውሎስ ይህን ሲያብራራው፥ « እነሱን ያከበረ እሱና የከበሩ እነሱ ካንድ ከእግዚአብሔር ካንድ ከአብርሃም ተገኝተዋልና» ይለዋል።

አራተኛ፥ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ መታዘዝ ለእኛም መታዘዝን ያስተማረንና እንደ ሊቀ ካህንነቱ ወደ አባቱ በብርቱ ጩኸትና እንባ ጸሎትንና ምልጃ ያቀረበ ነው።   « እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው።» ( ዕብ ፭፥፰-፲)፤ ይህን ገጸ ንባቡን ሆነ የአበውን ትርጓሜ እንዴት እንዳጣመምከው በቦታው እናየዋለን።

አምስተኛ፥ ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ በኩል ወደ አብ የሚቀርቡትን ፈጽሞ የሚያድን ሕያውና ዘላለማዊ ሊቀ ካህን ነው።   «እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤» (ዕብ ፯፥፳፬-፳፮)፤

ስድስተኛ፥ ዛሬ ይህ ሊቀ ካህናችን በሰማያዊት ድንኳን በእጅ ባልተሠራችው፥ስለ እኛ የሚታይልን ነው። «በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፥ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት።»( ዕብ ፰፥፩-፪) የእኛ አባቶች « ሊቀ ካህናት ዘይቀውም ሎሙ ለቅዱሳን፥ በደብተራ ስምዕ እንተ እግዚአብሔር ተከላ፤» ብለው ያመሠጠሩት ይህን ንባብ ነው።
ሰባተኛ፥ ሊቀ ካህናችን ወደዚህች ሰማያዊት ድንኳን የገባው፥ የገዛ ደሙን ይዞ ነው፤ ። «ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ፥ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን፥ የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም. . .  ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።» ዕብ ፱፥፲፩- ፲፪፡፳፬
ስምንተኛ፥ ሊቀ ካህናችን እርሱ ወደ ገባበት ድንኳን ለመግባት የምንችልበትን ተስፋ ሰጥቶናል፤ ይህችም ተስፋ የነፍሳችን መልሕቅ « እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘለዓለም ሊቀ ካህናት ሆኖ ሐዋርያችን ኢየሱስ ከእኛ በፊት ወደ ገባባት መጋረጃም ውስጥ የምታስገባ ናት።» (ዕብ ፮፥፳፤)

ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ በንባብ፡-“ተሾመ፥ተቀባ፤”የሚል ቢገኝም ምሥጢረ ተዋህዶን ለማመ ልከት(በተዋህዶ አምላክ ሰው፥ሰውም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ፥ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ መክበሩን ለማስረዳት) ስለሆነ በትርጓሜ ይቃናል።ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲ ያን፡-ወልደ አብ፥ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ፡-በተዋህዶ ከበረ የሚሉት ለዚህ ነው። ምክንያቱም ቅዱስ ቄርሎስ እንደተናገረው፡-በተዋህዶ የመለኮት ገንዘብ ለሥጋ፥የሥጋም ገን ዘብ ለመለኮት ሆኖአል። » ብለሃል።
ቄርሎስን በሚገባ ሳይገነዘብ ገደል የገባውን አውጣኪን ሆነሃል የምልህ እዚህ ላይ ነው። የጻፍከውን ጽሑፍ እንደገና መለስ ብለህ ቃኘው፥ እናም  « በተዋህዶ የሥጋ ገንዘብ» ምንድነው? ሁሉንም ክደኸዋል። ቄርሎስ በድርሳኑ ደጋግሞ እንደገለጠው፥ አንድ ባሕርይ ሲል፥ የቃልና የሥጋን መገናዘብ ሲናገር፥ የክርስቶስን ፍጹም ሰውነት ክዶ አይደለም። የመለኮት ገንዘብ፥ የእግዚአብሔር ልጅ መሆን ፥ አምላክነት፥ ሕይወት መስጠቱ ፥ ማዳኑና  እነዚህን የመሣሠሉት ሁሉ የሥጋም ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። የሥጋ ገንዘብ የሆኑት ደግሞ፥ የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ መፍራት፥ መራብ፥ መጠማት፥መጸለይ መማለድ፥ ወደ አብ መጸለይ፥ መሞት እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉት ወይም እንደ አባቶች አነጋገር፥ በጥንት በበአት፥ በልደት፥ በሕማምና በሞት እኛን የሆነባቸው የሥጋ ሥራዎች ሁሉ የመለኮት ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። አንተ ግን የአምላክነቱን ገንዘቦች ስታምን የሥጋን ገንዘቦች ግን ፈጽሞ ክደኸዋል። እኛ በሥጋው ይህን አደረገ ስንል ለመለኮት ሰጥተን ነው። በአምላክነቱ ይህን አደረገ ስንል ለሥጋ ሰጥተን ነው። ሳናፋልስ፥ ሳንከፍል፥ ሳንቀላቅልና ሳንለውጥ አንዱን በተዋህዶ የከበረውን አምላክ እንዲህ እንመሰክራለን።   ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ ማለት፥ ተለወጠ፥ተቀላቀለ አያሰኝምና። ትርጓሜህ በሙሉ ተዋህዶን የሚያፋልስ እንጂ ተዋህዶን የሚጠብቅ አይደለም። ላንተ መገናዘብ ማለት የትስብእትን ነገር እንዳለ መካድ ሆኖብሃል። ይህ አደገኛ ነው።   በትርጓሜ እያቃናህ ሳይሆን እያጣመምከው ነውና።
አሁን ከሊቃውንቱ ስለምጠቅስልህ በእርጋታ አስተውል፤ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት  በሃይማኖተ አበው ም. ፷፩ ክፍል ፫ እና ፬ ላይ እንዲህ ይላል። «  አስተርአየ በሥጋ እንዘ ኢያስተርኢ በሕላዌ መለኮት፤ በባሕርየ መለኮቱ የማይታይ ሲሆን፥ በሥጋ ታየ . . . በመለኮት ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞትን ገንዘብ አደረገ፤ በመለኮት መወሰን ሳይኖርበት በሥጋ ተወሰነ፤የማይመረመር ሰማያዊ እርሱ ሥጋን ተዋህዶ በምድር ተገለጠ።» ካለ በኋላ አንተ ደጋግመህ የካድከውን እርሱ እንዴት እንደሚገልጠው ተመልከት እንዲህ ይላል። «የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ የሠላሳ ዐመት ጎልማሳ መሆን፥ የመለኮት ሥራ አይደለም። ይህም ምንም ስለ እርሱ ቢነገር፥ የመለኮት ገንዘብ አይደለም። ሰው ስለሆነ እንጂ »
 

ይህ የተዋህዶ ምሥጢር ወደ ጥልቅ አምልኮ የሚጋብዝ ነው። ከንቱ ከሆነ የቃላት ስንጠቃና ክርክር ወጥተን፥ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን ነገር እንድናሰላስል የሚያደርግ ነው። ይህ የአእምሮ ጅምናስቲክ አይደለም። የአምልኮ ውበት ነው። እናም ጎርጎርዮስ በ፷፩ኛ ምዕራፉ በክፍል ፭ ላይ እንዲህ ይላል፤ « ቀዳማዊ ዘሀሎ እምቀዲሙ እንበለ ጥንት ኮነ ይእዜ ዘቦቱ ጥንት። ጥንት ሳይኖረው በቅድምና የነበረ ቀዳማዊ እርሱ ዛሬ ጥንት ያለው ሆነ። ዘኢተገብረ አስተርአየ ይእዜ በለቢሰ ሥጋ ዘተገብረ፤ ያልተፈጠረ እርሱ የተፈጠረ ሥጋን ተዋሕዶ ዛሬ ታየ። በከመ ጽሑፍ ዘይብል አእምሩ ዘንተ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት እምነትነ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚእነ ምዕመን በኀበ ዘገብሮ። ሊቀ ካህናት ሐዋርያ ባደረገው በአብ ዘንድ የታመነ የምናምንበት አስታራቂያችን መምህራችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዕውቁ ተብሎ እንደተጻፈ።  ዘኢያገምሮ መካን አግመረቶ ድንግል በከርሣ። ሰማይ ምድር የማይወስነውን ድንግል በማኅፀኗ ወሰነችው። ባዕል ዘይሁብ ብዕለ ለነዳያን። ብዕል ለሌላቸው ብዕልን የሚሰጥ እርሱ፤  ኮነ ነዳየ በእንተ ሥርዓተ ትስብእት። ሰው ስለ ሆነ ድሀ ተባለ። ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ። በርሱ ድሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ። ነሣዕኩ አርአያሁ ወኢአቀብክዋ እርሱን መም ሰሉን በተፈጥሮ ገንዘብ አደረግሁ፤ ጠብቄም አላስቀረሁትም። ወውእቱሰ ነሥአ ሥጋየ ከመ ያድኅነኒ፥ ሊተ ዘገብረኒ በአርአያሁ ወበአምሳሊሁ። እርሱ ግን በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረኝ እኔን ያድነኝ ዘንድ ሥጋዬን ተዋሐደ። ወረሰዮ ሥጋየ ዘእንበለ ሞት። ሥጋዬንም ሞት የሌለበት አደረገው። . . . ቀዳሚሰ ወሀበነ አርአያሁ ክብርተ። ቀድሞ ክብርን የምታስከትል እርሱን መምሰልን ሰጠን። ወዳግመ ነሥአ ሥጋነ ኅሥርተ። ዳግመኛ ግን ኃሣርን የምታስከትል ሥጋችንን ተዋሐደ። ወዝንቱ ግብር ልዑል። ይህ ሥራ ረቂቅ ነው።»
 በተዋህዶ የከበረው እርሱ ፥ « እከብር የማይል ክቡር፥ እጸድቅ የማይል ጻድቅ ሲሆን»፥ እኔን እና አንተን ያድን ዘንድ በሥጋው ተዋረደ፥ ደሀ ሆነ፥ ወደቀ፥ ጮኸ፥ ማለደ፥ ተሰቃየ፥ ቃተተ፥ አምላኪየ አምላኪየ አለ። በሥጋው።  « ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ።» በእርሱ ደሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ።
ይህን ያህል ስለ ትስብእቱ ሥራ መጨነቃችን ከቶ ለምንድነው? ምክንያቱም የደኅንነታችን ነገር ላይነጣጠል ከእርሱ ጋር ስለ ተያያዘ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር እንዲህ አለ፤ « ሰው የሆነም ዘመድ ሊሆነን ብቻ አይደለም። ፈጽሞ ይቅር አለን እንጂ፤ ኃጢአታችንን ለማስተስረይ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም  ነገር ያስተምረን ዘንድ ይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው? ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ያቀረበው መሥዋዕትስ ምንድነው መሥዋዕት ለመሆን የነሣው ሥጋው ብቻ ነው እንጂ»   ይላል።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ ባለፈው እንደ ጠቀስነው፡-ለአማርኛው ጥንት ግዕዝ በመሆኑ፥አማርኛውን ከግዕዙ ጋር እያ ገናዘብን እያንዳንዱን ቃል በዝርዝር እንመለከታለን። (አንዳዶች ይኼ የጠፋኝ ለማስመሰል፥ የመጀመሪያው የግሪኩ ነው ይላሉ።እነዚህ ሰዎች ግሪከኛውን በቅጡ ይወቁት አይወቁት አላ ውቅም።ምናልባት የእግዜር ሰላምታ ያህል ጥቂት ሞክረው ይሆናል።ነገር ግን ግዕዙም፥መጻ ሕፍቱም፥ሊቃውንቱም ከእኛ ጋር መሆናቸውን ማስተዋል ይገባል።ከዚህም ጋር ወደ ሌላ የሚኬደው ሲቸግር ብቻ መሆኑን መዘንጋት አይገባም።እኔ እያልኩ ያለሁት፡-ጥንት ቅዱሳት መጻሕፍት የተተረጎሙት ከባዕድ ቋንቋ ወደ ግዕዝ ነው፥ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ አማርኛ ተተርጉመዋል።ስለዚህ በቅድሚያ ማየት ያለብን የአማርኛው ቅጂና ግዕዙ መስማማታቸውን ነው።) » ብለሃል።
እዚህ ላይ ለአንተም ሆነ ለሌሎች ግልጥ የምናደርገው፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም፥ የግእዙ ትርጉም በዓለም ካሉት ትርጉሞች ሁሉ  ቀደምት ከሆኑትና ዛሬም ለምስክርነት የሚፈለግ ትርጉም ነው፤የትርጉሙ ጥንቃቄ፥ ከግሪኩ ጋር ያለው ቅርበት፥  በብዙ ደከመው ለእኛ ያስተላለፉት አባቶች፥ ለቅዱሳት መጻሕፍት ምን ያህል ክብር እንዳላቸው የሚያስረዳ የመንፈሳዊነታቸው ሕያው ምስክር ነው። ። በረከታቸው በእኛ ላይ ይደርብንና ፥ እነርሱ ለእኛ ያስተላለፉትን፥ ዛሬ እናንተ ልታፈልሱት መሞከራችሁ ነው እንድንጮህ ያደረገን።
ባለፈው ጽሑፍህ ስለ ሮሜ ፰፥፴፬ ያስቀመጥከው ከግእዙም ከአማርኛውም የሌለ ነው። ግእዙ ለምሳሌ የሚለው « ወይትዋቀስ በእንቲአነ» ነው። በየትኛው ሰዋስው ነው፥ ወይትዋቀስ በእንቲአነ « ስለ እኛ ይፈርዳል» የሚያሰኘው? በምስጢር ትለኝ ይሆናል። አንተ እኮ እየቀየርክ ያለኸው ገጸ ንባቡን ነው።  የአባቶች ትርጓሜ እንዳትል « ስለ እኛ ይከራከራል» ነው የሚለው እንጂ ስለ እኛ ይፈርዳል አይልም።  በነገራችን ላይ ግእዙና ግሪኩ አንድ ዓይነት አሳብ የያዙ ናቸው። « « ይትዋቀስ ይከራከራል» የሚለውና በግሪኩ “ ἐντυγχάνει  entynchanei “ ይማልዳል ተብሎ የተተርጎመው)  በምስጢር ብቻ ሳይሆን በቀጥታ ትርጉም ይገናኛሉ።  መማለድ ማለት ስለ አንድ ሰው ፈንታ ሆኖ ቆሞ መከራከር ማለት ነውና ። አንዳቸው በአንዳቸው ትርጉም ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ይፈርዳል ግን በገጸ ንባቡ በፍጹም የማይገናኝ፥ ከአባቶች መጻሕፍትም ምስክር የማይቀብርለት ነው።  ወደ ግሪኩ የሄድነው አንተ እንደምትለው ግእዙን ንቀን ሳይሆን አሁን ክርክራችን « ይትዋቀስን»  እንዴት እንተርጉመው ስለሆነ ነው።  የአባቶችን ትርጓሜ፥ የቅዱስ ዮሐንስን ትርጓሜ፥ ሃይማኖተ አበውን ወደ ጎን ስላደረጋችሁ፥ ቅዱስ መጽሐፍ ነውና ከመጀመሪያው እንዴት ተጻፈ ማለት የግድ ያስፈልጋል። ቅዱሳት መጻሕፍትን ስለመተርጎም ስናስብ ልንከተለው የሚገባንን አካሄድ  ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ መጽሐፍ ቅዱስን ባስተረጎሙበት ወቅት በጻፉት መቅድም ላይ በሚገባ ገልጠውልናል። እንዲህ ይላሉ፥ « የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጕም ከመሠረታዊ ቋንቋው ከዕብራይስጥና ከፅርዕ ጋር እየተያየ ሊታረም እንደሚገባው ስለ ተመለከትን፥ በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት ለዚህ ሥራ ተገቢ የሆኑትን ሊቃውንት መረጥን።»   ይላሉ።  እኛም ስንለው የነበረውን ይህን የንጉሠ ነገሥቱን አካሄድ ነው።
የ፪ሺ ዓመቱም መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ፥ ተርጓሚዎቹ በግልጥ ያስቀመጡት ሐቅ አለ። ይኸውም ከትርጓሜው ይልቅ ፖለቲካው ማለትም የእናንተ ተጽእኖ አስገድዶአቸው መሆኑን ለመግለጥ፥ « በግሪኩ ይማልዳል ይላል» ብለዋል። በተጨማሪ ማለት የነበረባቸው፥« ግእዙም እንዲህ አይልም ተገደን ነው እንጂ»  ነበር። ተርጓሚዎቹ የሚያመልጡበትን መንገድ ቢያስቀምጡም፥ ጥቂት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችን ለማስደሰት፥ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ አንገት የሚያስደፋ ሥራ ነው ነው የተሠራው። ( ይቀጥላል።)

ከቀሲስ መላኩ ተረፈ) ከቀሲስ መላኩ