Saturday, August 12, 2017

ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)


« አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን » ??? ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)

ወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥ በክፍል አንድ ጽሑፌ ላይ፥በመካከላችን ስላለው ልዩነትና፥ ምሥጢረ ተዋህዶን ምን ያህል በተሳሳተ መንገድ እንደተረዳኸው ለማስረዳት ሞክሬአለሁ። በተለይም ቄርሎስን በትክክል ባለመረዳትህ፥ መገናዘብን እንደመቀላቀል እንደቆጠርከው፥ የቃልን ገንዘብ ዘርዝረህ የሥጋን ገንዘብ ግን ሙሉ በሙሉ መካድህን አመልክቼህ ነበር። ለዚህም ራሱን ቄርሎስን ምስክር አድርጌ አቅርቤአለሁ። በዚህ በክፍል ሁለት ጽሑፌ እንደተለመደው ያንተን ጽሑፍ በማስቀደም የእኔን መልስ ደግሞ በሥፍራው አስቀምጣለሁ። ስለ ብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ስለጻፍከው፥ እንዴት በክርስቶስ እንደተፈጸመ አባቶች የሚተረጉሙትን እንዳለ ስላስቀመጥክ፥ከአንዳንድ አንተ ከጨመርካቸው ጥቃቅን ነገሮች በቀር እኔም ስለምስማማበት ለቦታና ለጊዜ ስንል በማለፍ በቀጥታ፥የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ስለሆነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ተናገርከው ታላቅ ስህተት እንመጣለን። ይኸውም በእብራውያን መልእክት ላይ « አብ ሾመው» የሚለውን አንተ ደግሞ በራስህ  « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» ብለህ መጽሐፍ ቅዱስን ተጋፍተህ ፥ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጣረስ ቃል አስቀምጠሃል።  የዛሬው ክፍል ሁለት ጽሑፌ ይህች አደገኛ ሐረግ « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» የሚለው ላይ ያተኮረ ነው። ይህን ከራስህ ጽሑፍ እንመልከተው።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ለራሱ ክብርን የሚወስድ የለም። (እግዚአብሔር እንደ አሮን ከመረጠው በቀር ማንም ተነሥቶ ሥልጣነ ክህነትን ለራሱ ገንዘብ ማድረግ የሚቻለው የለም)።”ብሎአል። =ከዚህም አያይዞ፡-“እንዲሁ ክርስቶስም ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ ራሱን ያከበረ(የሾመ) አይ ደለም፤ ነገር ግን፡-“አንተ ልጄ ነህ፥እኔም ዛሬ ወለድሁህ፥ያለው እርሱ ነው፤ዳግመኛም፡-እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘላለም ካህን አንተ ነህ፥ይላል፤”ብሎአል።መዝ፡፪፥፯፤፻፱፥፬፣ማቴ፡ ፫፥ ፲፯፤፲፯፥፭።ይህም፡-“አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለሃል።
ነገረ መለኮት በተለይም ምሥጢረ ሥጋዌ፥ በመላ ምት ወይም በግምት የሚነገር ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ቃልና የአበውን ምስክርነት በመያዝ በጥንቃቄ የሚነገር ነው። አሁን ግን በአንተ በቀሲስ ደጀኔ ጽሑፍ ላይ የምመለከተው ድፍረት ነው። ጥንቃቄ የጎደለው ታላቅ ድፍረት ነው። ለየዋህና የቤተ ክርስቲያኒቱን ነገረ መለኮት ለማያውቅ ሰው፥የተደረደረው ጥቅስ የእውነት ማረጋገጫ ሊመስል ይችላል። ከጥቅሱ በስተጀርባ ያለውን ታላቅ ስህተት ግን አያስተውልም። በዚህ በዛሬው ጽሑፌ፥ ምን ያህል የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀዋሚ ትምህርት እንደናድከው የማመለክትህ በአንዲቱ ሐረግ ብቻ ነው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» የምትለውን አባባልህን በጥንቃቄ ተመልከተው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን»? አብ ካልሾመው ታዲያ ማን ሾመው? መጽሐፍ ቅዱሱ « ራሱን የሾመ አይደለም» እያለ የተናገረው ስለምንድነው? ቃሉ እንዲህ በግልጥ እየነገረህ፥ ከቅዱስ ቃሉ ጋር ጦርነት ውስጥ መግባት ለምን አስፈለገ? ይህን እውነት ለመቀበል የከበደህ የምሥጢረ ሥጋዌን ነገር በተለይም የሥጋን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ከአምላክነቱ ቆርጠህ ስለ ጣልክ፥ ወይም ለመለኮት ከተዋሃደው ከትስብእቱ የተነሣ ሊነገርለት የሚገባውን እንዳለ ለመቀበል አለመፈለግህ ነው።
አንተ ጥቅሱን እና የአበውን ትርጓሜዎች ወደ ጎን በማድረግ፥ ሁለት አሳቦችን አቅርበሃል፤ የመጀመሪያው « አብ ሾመው ማለት አይደለም» የሚል ነው። ሁለተኛው ደግሞ፥ « ሾመው» የሚለው ቃል ፥ « ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው» የሚል ነው። ይህን ያስባለህ በተደጋጋሚ የወደቅህበት የአውጣኪ ስህተት ነው። ይህ ባለአዋቂነት የመጣ አሳብ፥ እርሱ በአምላክነቱ ከአብ ጋር እኩል ሆኖ ሳለ እንዴት ይሾማል የሚል ነው። አውጣኪ ያልኩህ የእኛን ሥጋ መልበሱን ፈጽሞ መካድህ፥ መዋቲ ( ሟች) ሥጋ መልበሱን፥ በዚህም« ሕቀ አህጸጽኮ እመላእክቲከ» ከመላእክት ጥቂት አሳነስከው መባሉን መርሳትህ፥ ፍጹም ሰው መሆኑን መዘንጋትህ ነው። ይህን ከአውጣኪ የመነጨውን ስህተት ሙሉ በሙሉ ለመደምሰስና በሥጋው አብ ሾመው ተብሎ ሊነገር እንደሚገባ ለማስረዳት፥ ራስህ መነሻህ ያደረከውን የዕብራውያን ንባብና አሳብ ከአባቶች ትርጓሜና ትምህርት አንጻር መተንተን አለብን፤
አንተ የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭-፯ን አባቶች በትርጓሜ ጳውሎስእንዴት እንደተረጐሙት እንመለክተው፤መጀመሪያ ገጸ ንባቡን እንዳለ አስቀምጣለሁ ከዚያም የአባቶችን ትርጓሜ አስቀምጣለሁ፤ ገጸ ንባቡ እንዲህ ይላል፦ «እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም ነገር ግን፦ አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ ያለው እርሱ ነው፤እንደዚህም በሌላ ስፍራ ደግሞ፦ አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ይላል። እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ »
የአባቶች ትርጓሜ ደግሞ እንዲህ ይላል፦
« እንደዚህም ኹሉ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት ይባል ዘንድ ራሱን የሾመ አይደለም። አንተ ልጄ እኔ ዛሬ ወለድኩህ ያለው እሱ፥ ዳግመኛ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ፤ አንድም አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ።»
አባቶች በግልጥ ያስቀመጡት ይህን ነው። ምንም ሌላ ሐታታ የማያስፈልገው ግልጥና ጥርት ያለ ነው። ንባቡን እናቃናው ብለው ለማጥፋት አልደፈሩም። ያሉት « « ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ነው ያሉት። አመክንዮ ዘሐዋርያትም ይህን ሲያረግጥ « ወዐረቀ ትዝምደ ሰብእ ምስለ እግዚአብሔር ሊቀ ካህናቲሁ ለአብ። የአብ ሊቀ ካህናት የሚሆን እርሱ ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀን » ይላል። የአብ ሊቀ ካህናት ብሎታል። በአብ ፊት የሚቆምልን የሚታይልን ሊቀ ካህናት ማለት ነው። ከዚህ የተነሣ ስለ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ስናምንም ሆነ ስናስተምር የሚከተሉትን ሦስት ነገሮች አስረግጠን መናገር አለብን።

፩ኛ. ሊቀ ካህናት የሚለው ስያሜ ለክርስቶስ የተሰጠው ሰው በመሆኑ ነው።

ሊቀ ካህናት የሚለው የሥጋዌ ስሙ ነው፤ ደግሞም የሹመት ስም ነው። የባሕርይ አምላክ ለሆነ ለእርሱ ሹመትን መቀበል ተዋርዶ አይሆንም ወይ? አዎ በሚገባ። ነገር ግን በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት መወሰንን የተቀበለ፥ በየጥቂቱ ያደገ፥ ከእናቱ ጡት ወተትን በመለመን ያለቀሰ፥ በሥጋው ከአባቱ ሹመትን ተቀበለ መባሉ የከበደን ከቶ ለምን ይሆን? ከጽንስ እበየማነ አብ እስከሚቀጥበት እስከ እርገቱ የሠራው የቤዛነት ሥራ ( ማለትም በእኛ ተገብቶ፥ በእኛ ፈንታ ሆኖ መሆኑን) መሆኑን መናገር ያሳፈረን ለምን ይሆን?
ሃይማኖተ አበው እንዲህ ይላል፦ « ፩ዱ ለሊሁ ወረደ ወተሠገወ እምህላዌነ ወኮነነ ሊቀ ካህናት ወአዕረገ በእንቲአነ ሥጋሁ መሥዋዕተ ለአቡሁ ወአብጽሐነ ሎቱ በዘቦቱ ሐመ፤ እርሱ አንዱ ወደዚህ ዓለም ወርዶ ባሕርያችንን ባሕርይ አድርጎ ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) ሆነን፤ ስለ እኛም ሥጋውን መሥዋዕት አድርጎ ወደ አባቱ አቀረበ እንጂ፤ በታመመበት በሥጋው ለርሱ ገንዘብ ለመሆን አበቃን » (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፮) ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በግልጥ እንደተናገረው፥ ሊቀ ካህናት ተብሎ የተነገረለት፥ ወደዚህ ዓለም በወረደ ጊዜ ነው።  ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እንዲህ ይላል። « በሰው ባሕርይ ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ፥ ስለ እኛም ራሱን ቍርባን መሥዋዕት አድርጎ ለአባቱ ያቀርብ ዘንድ ወልድ ዋሕድ ሰው ሆነ።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ም. ፶፮. ክፍል ፬ ቍ. ፱፤

እዚህ ላይ አንድ ጥልቅ እውነትን እንዳስስ፤ ለመሆኑ ሥግው ቃል ሊቀ ካህናት ለመሆን ለምን አስፈለገው? ይህን ድንቅ ምሥጢር ለመረዳት ሰፊ ሐተታ የሚያስፈልገው ቢሆንም ከተነሣንበት ዓላማ አንጻር፥ ካህን ሆኖ ፍጥረት ወደ አምላኩ ለማቅረብ የተፈጠረው አዳም፥ በኃጢአት በመውደቁ ምክንያት፥ ሁለተኛው አዳም ክርስቶስ፥ በእርሱ በኩል፥ ሰው ብቻ ሳይሆን ፍጥረት ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ይገባ ዘንድ ነው። ቅዱስ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሲገልጥ እንዲህ ይላል። «በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤ በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።» ( ኤፌ ፩፥፱-፲) በሰማይና በምድር ያለው እንዴት በክርስቶስ እንደሚጠቀለል፥ የሐዋርያት ተከታያቸው የሆነው ሄኔሬዎስ በመጻሕፍቱ የገለጠውን በሰፊው ወደ ፊት እናየዋለን። ለአሁን ግን ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ በጸለየው ጸሎት ላይ አስደናቂ የተዋሕዶን ምሥጢር እንዴት እንደገለጠው እንመልከተው። « የሰውን ባሕርይ እስኪዋሐድ ፥ ዘመዳቸውም ሆኖ ሰውን ሁሉ ወደ እርሱ እስኪያቀርብ ድረስ፥ ሰው ፊትህን አይቶ ሕያው መሆን አይቻለውም ነበርና። ሰዎች መለኮትን ያዩት ዘንድ የበቁ እስኪሆኑ ድረስ በሰው ባሕርይ ተገለጠ። በሥጋ ዘመዳችን ሆኖ ባየነው ጊዜ በአብ ቸርነት የወልድን ጌትነት እናመሰግነዋለንና» ሃይማኖተ አበው ዘጎርጎርዮስ ዘአርማንያ ም. ፲፭. ክፍል ፪. ቍ ፲-፩ አሁንም እኛን ተዛምዶ ወደ እርሱ ያቀረበን ሊቀ ካህናችን ይክበር ይመስገን።
እዚህ ላይ ቀደም ሲል የተናገርኩትን እንደገና አስረግጬ ለመናገር፥ ሐዋርያ፥ ክርስቶስ፥ ሊቀ ካህናት፥ ሰው፥ የሚሉት ስሞቹ በሥጋው ያገኛቸው ስሞች ናቸው። ለምሳሌ ይኸው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል። « አብ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም ስለ ላከው፥ ሐዋርያ አለው፤ ስለ አመንበት በጎ ሥራ ለመሥራት የምንቀና፥ ደግ ወገን አድርጎ ገንዘብ አድርጎናልና፥ ለእኛ ማልዶልናልና ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) አለው» ይለናል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፮

፪ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው በአባቱ ነው።

ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ግልጥ አድርጎታል። አንተው የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭ን አባቶች«ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ብለው ተርጉመውታል። የአባቶችን ትርጓሜ «ልታቃና » ካልሞከርክ በቀር መልሱ ግልጥ ነው። በሌላ ሥፍራም ሐዋርያው « ሕጉ ድካም ያላቸውን ሰዎች ሊቀ ካህናት አድርጎ ይሾማልና፤ ከሕግ በኋላ የመጣ የመሐላው ቃል ግን ለዘላም ፍጹም የሆነውን ልጅ ይሾማል» ይላል። ( ዕብ ፯፥፳፰)  አባቶች ይህን ንባብ ሲተረጉሙ ሰፊ ግንዛቤን የምናገኝበትን ሐተታ ስለሚሰጡበት እዚህ ላይ መመልከቱ መልካም ነው። እንዲህ ይላሉ፦ « ኦሪትሰ ሰብአ ትሰይም ሊቀ ካህናት መዋቴ፤ ኦሪትስ የሚሞት ሰውን ሊቀ ካህናት አድርጋ ትሾማለች። የቀድሞው ሊቀ ካህናት ዕለት ዕለት መሥዋዕት ማቅረቡ፥ የዛሬው ዕለት ዕለት አልማቅረቡ እንደምን ነው ትሉኝ እንደሆነ ኦሪት መዋቲ ( ሟች) ሰውን ሊቀ ካህናት ትሾም ነበረና፥ ደካማ ሰውን ትሾም ነበረና፥ የቀደመው ሊቀ ካህናት አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ሥርየት ድኅነት ማሰጠት የማይቻለው ስለሆነ ነው። ወቃለ መሐላሁሰ ዘመጽአ እምድኅረ ኦሪት ሤመ ለነ ወልደ ፍጹመ ዘለዓለም። ከኦሪት በኋላ በመሐላ የተሠራ ሕገ ወንጌል ግን ሕያው ወልድን፥ ኃያል ወልድን ሹሞልናልና። የዛሬ አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ስርየት ድኅነት መስጠት የሚቻለው ስለሆነ ነው።»
ሃይማኖተ አበው ደግሞ ግልጥ አድርጎ ምንም ማፈናፈኛ ሳይሰጥ አያስቀምጠዋል፤እንዲህ ይላል፦« ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት በአደረገው በአብ ዘንድ የታመነ እውነተኛ ነው አለ። ለወገኖቹ በጎ ማገልገልን እንዲያገለግል ይጐዱም ዘንድ ቸል እንደማይላቸው እኛ እንድናውቅ መናገሩ ነው። ሊቀ ካህናት አደረገው ( ገብሮ) ያለውንም ሐዋርያ ሊቀ ካህናት አድርጎ እንደ ሾመው መናገሩ ነው። በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት ተናገረ እንጂ፥ ሥጋ ፍጡር ነውና።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፯-፳፰
ቀሲስ ደጀኔ እልህ ሃይማኖት ካልሆነብህ በቀር፥ ያነሣኻቸውን ሁለት ነገሮች ይህን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጥቅስ ይንድብሃል። የመጀመሪያው « አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን » የሚለው አሳብህን፥ ሊቀ ካህናት አደረገው ማለት ሊቀካህናት አድርጎ ሾመው ማለት እንደሆነ ይነግርብሃል ። ሁለተኛ « የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለህ ከራስህ አንቅተህ ያስቀመጥከውን ትርጓሜህን፥ በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት  እንጂ» ይልብሃል።
አሁንም ደጋግሜ በፍቅር የምነግርህ፥ ወደዚህ ታላቅ ክህደት ያገባህ፥ የትስብእትን ገንዘቦች በሙሉ መካድህ ነው። ሾመው ለማለት ያስቸገረህ አዋረድኩት ብለህ ነው። ነገር ግን ዓለም የዳነበት የድኅነት ምሥጢር ይህ ተዋርዶቱ ነው። አንተ ግን በካራ ቆረጥከው፥ ከፈልከው። ተዋህዶን አፋለስከው። ሾመው የተባለው በአምላክነቱ ሳይሆን በሰውነቱ ነው። የፈጠረውን ሥጋ በመልበሱ፥ የፈጠረውን ሥጋ በመዋሃዱ ነው።

፫ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው ለማስታረቅ ነው።

ቀደም ሲል ባየነው በዕብ ፭፥፭ ላይ፥ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመበትን ሲተረጉሙ አባቶቻችን በገጸ ንባቡ ላይ በመመርኮዝ የተሾመበትን ምክንያት በሚገባ ግልጥ አድርገው አሳይተውናል። እንዲህ ይላሉ፦ « አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ አለ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ። » አባቶች ያሉትን አስተውል። ክህነቱ የታወቀው፥ በአስታራቂነቱ፥ ጸሎትንና ስኢልን ( ምልጃን) በማቅረቡ ነው።
የሊቀ ካህናት ዋና ሥራ ምንድነው ስንል፥ ማስታረቅ፥ መማለድ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደነገረን «. . . ኃጢአታችንን ለማስተስረይ፥ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም [ሐዋርያው]ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ፥ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም ነገር ያስተምረን ዘንድይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው?» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፫-፲፬

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዚህ ሥፍራ አራት መሠረታዊ ነጥቦችን ያነሣል። አንደኛ፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት የሆነን ኃጢአታችንን ለማስተስረይና ከአብ ጋር ለማስታረቅ ነው። በሁለተኛ ደረጃ፥ ሊቀ ካህናት የሆነልን እርሱ በሁሉ የሚያዝንልንና የሚራራልን፥ የእኛን ድካም የሚያውቅ በነገር ሁሉ እኛን የመሰለ ነው። ሦስተኛ፥ የሥጋዌው ዋና ተልዕኮ የማስታረቅ አገልግሎት ነው። ሌላ ምክንያት የለውም። አራተኛ፥ ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ( ይህን የማስታረቅ አገልግሎት ማለትም የክርስቶስን  ምልጃ፥ ከክርስቶስ መካከለኛነት አንጻር በክፍል ሦስት ጽሑፋችን  በሰፊው እንዳስሰዋለን።)

፬ኛ. ሊቀ ካህንነቱ ለዘላለም ነው።

በብዙው ክርክራችን ውስጥ የዘነጋነው አንድ ታላቅ ጥያቄ አለ። ይኸውም ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ሊቀ ካህናት ነው ወይስ አይደለም ? የሚል ነው። ቅዱሳት መጻሕፍትም ሆኑ የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት የሚመልሱልን በአዎንታ ነው። የመልክአ ኢየሱስ ደራሲ ይህን እውነታ ሲናገር እንዲህ ይላል፦
« እምሥራቀ ፀሐይ እስከነ ዐረብ ይትአኰት ስሙ ለእግዚአብሔር አምላክነ፤ ኪያከ ወልዶ ዘፈነወ ለነ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ፤ አስተጋብአነ ኀበ ትረፍቅ መካነ፤ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንሕነ።
« አንተን ልጁን የላከልን፥ የአምላካችን የእግዚአብሔር  ስሙ ከመ ጸሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያ ይክበር ይመስገንና ሊቀ ካህናችንን የምትሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ በመላው ዓለም የተበተን እኛን ( ቤተ ክርስቲያንን) አንተ ባለህበት በዚያ ሰብስበን» በዕለተ አርብ ባቀረበው መሥዋዕት፥ በዚያ በብርቱ ጩኸትና ዕንባ ባቀረበው ጸሎትና ምልጃ፥ ዛሬም ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ መቅረቢያችን ነው ።
ሞት እንደሚያግደው እንደ አሮን ልጆች ክህነት ሳይሆን፥  ክህነቱ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ክህነት ለዘላለም ነው የተባለው ለዚህ ነው። በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ይፍታህ ይህድግ በማለት በወንጌል የተገኘውን ከኃጢአት ነጻ የመሆን አዋጅ ( ሥርየተ ኃጢአትን ስታውጅ) « ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የካህናት አለቃ ( ሊቀ ካህናት) ይቅር ባይ» ብላ ሊቀ ካህንነቱን በመናገር ነው።
ሐዋርያውም በግልጥ «እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ » ብሎአልና ሊቀ ካህናችን አሁንም በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የምመጡትን ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው። ዕብ ፯፥፳፫-፳፮
እንግዲህ እስከ አሁን የተማርነውን የዕብ ፭፥፭-፯ን በካታኪዝም ( በጥያቄና መልስ) ብናስቀምጠው ብናቀርበው ይህ ነው። « ሊቀ ካህናት አድርጎ የሾመው ማን ነው? አባቱ እግዚአብሔር አብ። እንዴት ሾመው ተባለ፤ ሥጋን በመልበሱ ምክንያት። ሊቀ ካህናት የሆነው ለምንድነው? ሊያስታርቀን። የሚያስታርቀን ከማን ጋር ነው? በአምላክነቱ ከራሱ ጋር እንዲሁም ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር፤ እንዴት አድርጎ አስታረቀን? በራሱ መሥዋዕትነት ጸሎትና ምልጃን በማቅረብ ነው። ሊቀ ካህንነቱ እስከመቼ ነው? ሊቀ ካህንነቱ እንደ መልከጼዴቅ ባለ ሹመት ለዘላለም ነው። እርሱ ለዘላለም ህያው ሆኖ ይኖራልና፤ በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ፈጽሞ ያድናቸዋል።

መደምደሚያ

እንግዲህ ከላይ በዝርዝር ያሳየሁህ፥ በግዴለሽነት፥ « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» ብለህ ያስቀመጥከው የስህተት ቃል፥ ምሥጢረ ሥጋዌን እንዴት እንደሚያፈልስ ነው። ሁለቱን ግብራት አንዱን በመሰረዝ ወይም በመቀላቀል ወይም መክፈልና በመነጠል የሚደረግ ትንተና አደገኛ በሆነ የስህተት ገደል ውስጥ ይጥላል። ከዚህ ስህተት ራስን ለመጠበቅ ኦርቶዶክሳውያኑ አባቶች የጌታን የማዳን ሥራ የገለጡበትን መንገድ መከተል ያሻል። የጎርጎርዮስ ዘኑሲስን ምክር ልብ በል። « ሁለቱ ግብራት ለርሱ አንድ እንደሆኑ አየህን? ሰው የሆነ አምላክ እርሱ ነው። አንድ ነው ሁለት አይደለም። ፈጣሪ መለኮቱን ፍጡር ወደ መሆን አልለወጠውም። ፍጡር ሥጋውንም ፈጣሪ ወደ መሆን አልለወጠውም። መችም መች አንድ ብቻ ነው። ሁለት አይደለም። የተገዢ ባሕርይን የተዋሐደ በእርሱ ትህትና እኛ እንከብር ዘንድ የተዋረደ እርሱ ነው። ሕማማችንን የታገሠ፥ ደዌያችንን የተሸከመ፥ በደላችንን የተቀበለ፥ ስለ እኛ ራሱን የማያልፍ የማይለወጥ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ የማይሻር የማይለወጥ ካህን እርሱ ነው። የሚሠዋ በግ እርሱ ነው። የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው። ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው።»  ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ም. ፴፮ ክፍል ፬ ቍ. ፳፬-፳፭  ትስብእትንና መለኮትን በተዋህዶ መግለጥ ማለት ይህ ነው። ያለመቀላቀል፥ ያለመክፈል፥ ያለመለወጥ፥ ያለመለየት፤ ተዋህዶ በተአቅቦ ማለት ምሥጢሩ ይህ ነው። ይህን ከተረዳኸው፥ አብ ሾመው፥ ወደ አብ ጸለየ ማለደ የሚል ስታገኝ አይከብድህም፤ ከሁሉም በላይ  እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን የእኛን ባህርይ ገንዘብ ባደረገ በእርሱ አታፍርም።  የአብ ሊቀ ካህናት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ፥  አስደናቂ የሆነውን ሰው የመሆኑን ምሥጢር፥ አሁንም አብዝቶ ይግለጥልን። አሜን።

ማሳሰቢያ፦ በሚቀጥለው በክፍል ሦስት ደግሞ « ይማልዳል ለማለት ሳይሆን » በማለት የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የጻፍከውን ስህተት፥ ቅዱሳት መጻሕፍትንና የአበውን መጻሕፍት በመጥቀስ እናርመዋለን። በዚያ ውስጥም መካከለኛነት፥ ምልጃ፥ አስታራቂነት ስለሚሉት ቃላት መጽሐፍ ቅዱስና የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ያስተማሩትን በሚገባ እናየዋለን።



Monday, July 24, 2017

ግልጥ የወጣ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል አንድ)



ከቀሲስ መላኩ ተረፈ


ለወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥በዕብ ፭፥፯ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል መሠረት አድርገህ ( የብፁዕ አባታችንና የእኔን ፎቶ አስደግፈህ) የጻፍከውን ተመለከትኩት፤ በአንድ በኵል፥ ከተራ አሉባልታና ክስ ወጥተን፥በክርክርም ቢሆን፥  ስለ ክርስቶስ እንድንነጋገር ያደረገንን አምላክ ሳመሰግን፥ በሌላ በኩል አንተና አንተን ተከትለው በቲፎዞ የሚነጉዱት ስለገባችሁበት ከባድ አደጋ ሳስብ አዝናለሁ። ይህ የልጅ ጨዋታ አይደለም። አሁን እያደረጋችሁ ያላችሁት፥ ቤተ ክርስቲያንን ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር የሚያለያይ፥ አባቶቻችን በስንት ተጋድሎ ያቆዩትን የተዋህዶ ምሥጢር የሚያፋልስ ነው። በመሆኑም የሚቀጥለው ጽሑፌ በአንድ በኩል በጥንቃቄ የአባቶችን ትርጓሜና የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት እንድታጠናው ለማሳሰብ ሲሆን፥ በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የተጋረጠውን አደጋ ለማሳሰብ ነው። ምንም እንኳ እኔን መናፍቅ ብትለኝም፥ አንዳንዱን የአተረጓጎምህን መንገድ ስመለከት መናፍቅ ለማለት ይከብደኛል። ከምርምርና ከዕውቀት ሳይሆን፥ከአላዋቂነት የመጣ ስህተት ነውና የማየው።  በመሆኑም በመጀመሪያ ጽሑፍህን በትምህርተ ጥቅስ ጎላ ብሎ እንዲቀመጥ በማድረግ፥ ለእያንዳንዱ መልስ ለመስጠት  እሞክራለሁ። በአንቀጽ የተከፋፈለ ባይሆንም ለመልስ እንዲረዳኝ ከፋፍየዋለሁ፤ አላስፈላጊ የሆነና አለቦታው የገባውን ንባብ ግን ከጊዜና ከቦታ አንጻር አልፌዋለሁ፤
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ ፦  “ እርሱም በሥጋ ወራት . . . ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤”ዕብ፡፭፥፯። =ይኸንን ኃይለ ቃል የተናገረው፡-ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ነው።ይህ ሐዋርያ መልእክ ቶቹን ሁሉ የጻፈው በጸጋ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ነው።ይኸንንም፡-የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ፡-“እን ዲህም የተወደደው ወንድማችን ጳውሎስ ደግሞ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ጻፈላችሁ፥በመልእክ ቱም ሁሉ ደግሞ እንደ ነገረ ስለዚህ ነገር ተናገረ።በእነዚያ ዘንድ ለማስተዋል የሚያስቸግር ነገር አለ፥ያል ተማሩትና የማይጸኑትም ሰዎች ሌሎችን መጻሕፍት እንደሚያጣምሙ እነዚህን ደግሞ ለገዛ ጥፋታ ቸው ያጣምማሉ።”በማለት ገልጦታል።፪ኛ፡ጴጥ፡፲፭። =ቅዱስ ጴጥሮስ እንደመሰከረው፥መናፍቃኑ፡-አጥፍቶ ጠፊ የሆኑት፥በአብዛኛው፡-የሐዋርያውን መልእክታት በመጠቃቀስ ነው።ይኸውም የንባቡን ትርጓሜና ምሥጢር ካለማስተዋልና መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ሌሎች ልበ ወለድ መጻሕፍት ከመመልከት ነው።» ብለሃል።
ግሩም ነው! ስድቡን ቀነስ ብታደርገውም፥ ዛሬም ያችው የተለመደችው መናፍቃን የምትለውን ቃል ፎቶአችንን አስቀምጠህ ተጠቅመሃል።  ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረው ቃል በእውነትም ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረውን የምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነገር ባለማስተዋል የሚያጣምሙትን የገሠጸበት ቢሆንም፥ ዛሬም መጻሕፍትን ለሚያጣምሙት የሚጠቀስ ቃል መሆኑ እሙን ነው። በአንድ በኩል የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ ንባብ ጥሬ ዘሩን ሳይቀር ለመለወጥ የደፈርህ፥ እንዲህ ተብሎ ሊጻፍ አይገባም ያልክ አንተ ነህ፤ በሌላ በኩል የአባቶችን ትርጓሜ እንኳ ሳይቀር፥ ያለምንም ሐፍረት ያጣመምክ አንተ ስለሆንክ « ለገዛ ጥፋታቸው ያጣምማሉ» የተባለው የሚቀጸለው ለአንተ ነው። ትርጓሜ ጳውሎሱን ሳይቀር እንዴት እንዳጣመምከው በግልጥ በማስረጃ አመጣዋለሁ። ወደ እኔ ጽሑፍ ከሄድክ፥ በማስረጃነት ያቀርብኩልህ ትርጓሜ ወንጌልን፥ ሃይማኖተ አበውን፥ የጥንትና የዘመናችን አባቶችን እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስን ነው። ጳውሎሱን አንተም እኔም የምንጠቅሰው ኃይለ ቃሉ ያለበት ስለሆነ ነው። ዛሬም ከእነዚሁ ንጹሐን ምንጮች ነው የምጠቅስልህ፤  መናፍቃኑ ላልከው ግን እኔም እንደ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ እልሃለሁ፤  «ነገር ግን ይህን እመሰክርልሃለሁ፤ በሕጉ ያለውን በነቢያትም የተጻፉትን ሁሉ አምኜ የአባቶቼን አምላክ እነርሱ ኑፋቄብለው እንደሚጠሩት መንገድ አመልካለሁ፤» ሐዋ ፳፬፥፲፬
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « ለመሆኑ፡-ሐዋርያው መልእክት ትርጓሜ ምንድነው? -“ነገርን ከሥሩ፥ውኃን ከጥሩ፤”እንዲል፡-መልእክቱን ለመረዳት በመጀመሪያ የነገሩን ሥረ መሠረት እንመለከታለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡-ዕብራውያን ምዕራፍ አምስትን የጀመረው፥ በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩት ሊቃነ ካህናት፡-ለአዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት፡-ለኢየሱስ ክርስቶስ የነበራቸ ውን ምሳሌነት በማብራራት ነው። በምሳሌውና በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነትም የፈጣሪና የፍጡር ነው፥እነርሱ ፍጡራን ፥እርሱ ግን ፈጣሪ ነው፤እነርሱን የሾማቸው እርሱ ነው፥እርሱ ግን ሿሚ የለበትም፤ ሹመት የባሕርይ ገንዘቡ ነው።» ብለሃል።
ይህ ሙሉ የእብራውያንን የሊቀ ካህንነት ትምህርት የገለጠ አይደለም። ለምሳሌ ስለ አዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት ስትናገር፥ በምሳሌናው በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነት የፈጣሪና የፍጡር ነው ብለሃል፤ መልካም ነው።  ይህ እንዳለ ሆኖ ግን፥ ነገርን ከሥሩ እንዳልከው የዕብራውያን መልእክት በዋናነት የሚያሳየን አንተ ልትናገረው ያልደፈርከውን ነገር ነው። ይኸውም፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በእውነት ሰው የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ በእኛ ፈንታ የቆመ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ፥ የጮኸ፥ የደከመ፥ የለመነ፥ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበና አሁን በእውነተኛይቱ ድንኳን ያለ አስታራቂያችን ሊቀ ካህናት መሆኑን ነው። ይህን በዕብራውያን መልእክት  ውስጥ በሙሉ እናየዋለን።

አንደኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የቆመ ሊቀ ካህናት ነው። « እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ።» ( ዕብ ፬፥፲፬ ) አባቶቻችን ይህን ሲተረጉሙ « ብንመለስ ማን ያስታርቀናል እንዳይሉት፥ ብነ ሊቀ ካህናት አለ፤ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ደግ አስታራቂ ኢየሱስ ክርስቶስ አለን።»  

ሁለተኛ፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን የሆነ ነው። «ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።» ዕብ ፬፥፲፬።  ሊቀ ካህናትም ያሰኘው ይኸው ፍጹም ሰው መሆኑ ነው። « ከግብራችን ሲያወጣው « ዘእንበለ ኃጢአት ባሕቲታ ከኃጢአት በቀር » አለ። ከባሕሪያችን ሲያገባው « ምኩር በኩሉ በአምሳሊነ እንደ እኛ የተፈተነ» አለ» ይለናል፥ ትርጓሜ ጳውሎስ።    ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በነገር ሁሉ እኛን መምሰሉ እንዴት እንደሆነ ሲናገር፥ « እንደ እኛ ፍጹም ሰው ሆኖ መወለዱ፥ ከኃጢአት ብቻ በቀር፥ እንደ እኛ ለሥጋ የሚስማማውን፥ ሁሉ መሥራቱ ነው እንጂ፤ይኸውም በፈቃዱ ያደረገው መፀነስ፥ መወለድ፥ መብላት፥ መጠጣት፥ መተኛት፥ መድከም፥ መታመም መሞት ነው።» ይላል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪


ሦስተኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ የሆነ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ ስለሆነ፥  የተቤዣቸውንና ያዳናቸውን « ወንድሞቼ ሊል ያላፈረ፥ « በኵረ አኃው» ነው።  «ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና። የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸውና፤ስለዚህም ምክንያት፦ ስምህን ለወንድሞቼ እነግራቸዋለሁ በማኅበርም መካከል በዜማ አመሰግንሃለሁ፤ ደግሞም፦ እኔ በእርሱ እታመናለሁ፤ ደግሞም፦ እነሆኝ እኔን እግዚአብሔር የሰጠኝንም ልጆች ሲል ወንድሞች ብሎ ሊጠራቸው አያፍርም።» ዕብ ፪፥፲-፲፫  ። አስተውል፥ በሥጋዌው ከእኛ ጋር በመዛመዱ፥ « የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸው» ተባለ፤ትርጓሜ ጳውሎስ ይህን ሲያብራራው፥ « እነሱን ያከበረ እሱና የከበሩ እነሱ ካንድ ከእግዚአብሔር ካንድ ከአብርሃም ተገኝተዋልና» ይለዋል።

አራተኛ፥ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ መታዘዝ ለእኛም መታዘዝን ያስተማረንና እንደ ሊቀ ካህንነቱ ወደ አባቱ በብርቱ ጩኸትና እንባ ጸሎትንና ምልጃ ያቀረበ ነው።   « እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው።» ( ዕብ ፭፥፰-፲)፤ ይህን ገጸ ንባቡን ሆነ የአበውን ትርጓሜ እንዴት እንዳጣመምከው በቦታው እናየዋለን።

አምስተኛ፥ ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ በኩል ወደ አብ የሚቀርቡትን ፈጽሞ የሚያድን ሕያውና ዘላለማዊ ሊቀ ካህን ነው።   «እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤» (ዕብ ፯፥፳፬-፳፮)፤

ስድስተኛ፥ ዛሬ ይህ ሊቀ ካህናችን በሰማያዊት ድንኳን በእጅ ባልተሠራችው፥ስለ እኛ የሚታይልን ነው። «በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፥ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት።»( ዕብ ፰፥፩-፪) የእኛ አባቶች « ሊቀ ካህናት ዘይቀውም ሎሙ ለቅዱሳን፥ በደብተራ ስምዕ እንተ እግዚአብሔር ተከላ፤» ብለው ያመሠጠሩት ይህን ንባብ ነው።
ሰባተኛ፥ ሊቀ ካህናችን ወደዚህች ሰማያዊት ድንኳን የገባው፥ የገዛ ደሙን ይዞ ነው፤ ። «ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ፥ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን፥ የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም. . .  ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።» ዕብ ፱፥፲፩- ፲፪፡፳፬
ስምንተኛ፥ ሊቀ ካህናችን እርሱ ወደ ገባበት ድንኳን ለመግባት የምንችልበትን ተስፋ ሰጥቶናል፤ ይህችም ተስፋ የነፍሳችን መልሕቅ « እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘለዓለም ሊቀ ካህናት ሆኖ ሐዋርያችን ኢየሱስ ከእኛ በፊት ወደ ገባባት መጋረጃም ውስጥ የምታስገባ ናት።» (ዕብ ፮፥፳፤)

ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ በንባብ፡-“ተሾመ፥ተቀባ፤”የሚል ቢገኝም ምሥጢረ ተዋህዶን ለማመ ልከት(በተዋህዶ አምላክ ሰው፥ሰውም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ፥ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ መክበሩን ለማስረዳት) ስለሆነ በትርጓሜ ይቃናል።ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲ ያን፡-ወልደ አብ፥ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ፡-በተዋህዶ ከበረ የሚሉት ለዚህ ነው። ምክንያቱም ቅዱስ ቄርሎስ እንደተናገረው፡-በተዋህዶ የመለኮት ገንዘብ ለሥጋ፥የሥጋም ገን ዘብ ለመለኮት ሆኖአል። » ብለሃል።
ቄርሎስን በሚገባ ሳይገነዘብ ገደል የገባውን አውጣኪን ሆነሃል የምልህ እዚህ ላይ ነው። የጻፍከውን ጽሑፍ እንደገና መለስ ብለህ ቃኘው፥ እናም  « በተዋህዶ የሥጋ ገንዘብ» ምንድነው? ሁሉንም ክደኸዋል። ቄርሎስ በድርሳኑ ደጋግሞ እንደገለጠው፥ አንድ ባሕርይ ሲል፥ የቃልና የሥጋን መገናዘብ ሲናገር፥ የክርስቶስን ፍጹም ሰውነት ክዶ አይደለም። የመለኮት ገንዘብ፥ የእግዚአብሔር ልጅ መሆን ፥ አምላክነት፥ ሕይወት መስጠቱ ፥ ማዳኑና  እነዚህን የመሣሠሉት ሁሉ የሥጋም ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። የሥጋ ገንዘብ የሆኑት ደግሞ፥ የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ መፍራት፥ መራብ፥ መጠማት፥መጸለይ መማለድ፥ ወደ አብ መጸለይ፥ መሞት እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉት ወይም እንደ አባቶች አነጋገር፥ በጥንት በበአት፥ በልደት፥ በሕማምና በሞት እኛን የሆነባቸው የሥጋ ሥራዎች ሁሉ የመለኮት ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። አንተ ግን የአምላክነቱን ገንዘቦች ስታምን የሥጋን ገንዘቦች ግን ፈጽሞ ክደኸዋል። እኛ በሥጋው ይህን አደረገ ስንል ለመለኮት ሰጥተን ነው። በአምላክነቱ ይህን አደረገ ስንል ለሥጋ ሰጥተን ነው። ሳናፋልስ፥ ሳንከፍል፥ ሳንቀላቅልና ሳንለውጥ አንዱን በተዋህዶ የከበረውን አምላክ እንዲህ እንመሰክራለን።   ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ ማለት፥ ተለወጠ፥ተቀላቀለ አያሰኝምና። ትርጓሜህ በሙሉ ተዋህዶን የሚያፋልስ እንጂ ተዋህዶን የሚጠብቅ አይደለም። ላንተ መገናዘብ ማለት የትስብእትን ነገር እንዳለ መካድ ሆኖብሃል። ይህ አደገኛ ነው።   በትርጓሜ እያቃናህ ሳይሆን እያጣመምከው ነውና።
አሁን ከሊቃውንቱ ስለምጠቅስልህ በእርጋታ አስተውል፤ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት  በሃይማኖተ አበው ም. ፷፩ ክፍል ፫ እና ፬ ላይ እንዲህ ይላል። «  አስተርአየ በሥጋ እንዘ ኢያስተርኢ በሕላዌ መለኮት፤ በባሕርየ መለኮቱ የማይታይ ሲሆን፥ በሥጋ ታየ . . . በመለኮት ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞትን ገንዘብ አደረገ፤ በመለኮት መወሰን ሳይኖርበት በሥጋ ተወሰነ፤የማይመረመር ሰማያዊ እርሱ ሥጋን ተዋህዶ በምድር ተገለጠ።» ካለ በኋላ አንተ ደጋግመህ የካድከውን እርሱ እንዴት እንደሚገልጠው ተመልከት እንዲህ ይላል። «የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ የሠላሳ ዐመት ጎልማሳ መሆን፥ የመለኮት ሥራ አይደለም። ይህም ምንም ስለ እርሱ ቢነገር፥ የመለኮት ገንዘብ አይደለም። ሰው ስለሆነ እንጂ »
 

ይህ የተዋህዶ ምሥጢር ወደ ጥልቅ አምልኮ የሚጋብዝ ነው። ከንቱ ከሆነ የቃላት ስንጠቃና ክርክር ወጥተን፥ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን ነገር እንድናሰላስል የሚያደርግ ነው። ይህ የአእምሮ ጅምናስቲክ አይደለም። የአምልኮ ውበት ነው። እናም ጎርጎርዮስ በ፷፩ኛ ምዕራፉ በክፍል ፭ ላይ እንዲህ ይላል፤ « ቀዳማዊ ዘሀሎ እምቀዲሙ እንበለ ጥንት ኮነ ይእዜ ዘቦቱ ጥንት። ጥንት ሳይኖረው በቅድምና የነበረ ቀዳማዊ እርሱ ዛሬ ጥንት ያለው ሆነ። ዘኢተገብረ አስተርአየ ይእዜ በለቢሰ ሥጋ ዘተገብረ፤ ያልተፈጠረ እርሱ የተፈጠረ ሥጋን ተዋሕዶ ዛሬ ታየ። በከመ ጽሑፍ ዘይብል አእምሩ ዘንተ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት እምነትነ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚእነ ምዕመን በኀበ ዘገብሮ። ሊቀ ካህናት ሐዋርያ ባደረገው በአብ ዘንድ የታመነ የምናምንበት አስታራቂያችን መምህራችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዕውቁ ተብሎ እንደተጻፈ።  ዘኢያገምሮ መካን አግመረቶ ድንግል በከርሣ። ሰማይ ምድር የማይወስነውን ድንግል በማኅፀኗ ወሰነችው። ባዕል ዘይሁብ ብዕለ ለነዳያን። ብዕል ለሌላቸው ብዕልን የሚሰጥ እርሱ፤  ኮነ ነዳየ በእንተ ሥርዓተ ትስብእት። ሰው ስለ ሆነ ድሀ ተባለ። ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ። በርሱ ድሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ። ነሣዕኩ አርአያሁ ወኢአቀብክዋ እርሱን መም ሰሉን በተፈጥሮ ገንዘብ አደረግሁ፤ ጠብቄም አላስቀረሁትም። ወውእቱሰ ነሥአ ሥጋየ ከመ ያድኅነኒ፥ ሊተ ዘገብረኒ በአርአያሁ ወበአምሳሊሁ። እርሱ ግን በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረኝ እኔን ያድነኝ ዘንድ ሥጋዬን ተዋሐደ። ወረሰዮ ሥጋየ ዘእንበለ ሞት። ሥጋዬንም ሞት የሌለበት አደረገው። . . . ቀዳሚሰ ወሀበነ አርአያሁ ክብርተ። ቀድሞ ክብርን የምታስከትል እርሱን መምሰልን ሰጠን። ወዳግመ ነሥአ ሥጋነ ኅሥርተ። ዳግመኛ ግን ኃሣርን የምታስከትል ሥጋችንን ተዋሐደ። ወዝንቱ ግብር ልዑል። ይህ ሥራ ረቂቅ ነው።»
 በተዋህዶ የከበረው እርሱ ፥ « እከብር የማይል ክቡር፥ እጸድቅ የማይል ጻድቅ ሲሆን»፥ እኔን እና አንተን ያድን ዘንድ በሥጋው ተዋረደ፥ ደሀ ሆነ፥ ወደቀ፥ ጮኸ፥ ማለደ፥ ተሰቃየ፥ ቃተተ፥ አምላኪየ አምላኪየ አለ። በሥጋው።  « ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ።» በእርሱ ደሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ።
ይህን ያህል ስለ ትስብእቱ ሥራ መጨነቃችን ከቶ ለምንድነው? ምክንያቱም የደኅንነታችን ነገር ላይነጣጠል ከእርሱ ጋር ስለ ተያያዘ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር እንዲህ አለ፤ « ሰው የሆነም ዘመድ ሊሆነን ብቻ አይደለም። ፈጽሞ ይቅር አለን እንጂ፤ ኃጢአታችንን ለማስተስረይ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም  ነገር ያስተምረን ዘንድ ይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው? ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ያቀረበው መሥዋዕትስ ምንድነው መሥዋዕት ለመሆን የነሣው ሥጋው ብቻ ነው እንጂ»   ይላል።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ ባለፈው እንደ ጠቀስነው፡-ለአማርኛው ጥንት ግዕዝ በመሆኑ፥አማርኛውን ከግዕዙ ጋር እያ ገናዘብን እያንዳንዱን ቃል በዝርዝር እንመለከታለን። (አንዳዶች ይኼ የጠፋኝ ለማስመሰል፥ የመጀመሪያው የግሪኩ ነው ይላሉ።እነዚህ ሰዎች ግሪከኛውን በቅጡ ይወቁት አይወቁት አላ ውቅም።ምናልባት የእግዜር ሰላምታ ያህል ጥቂት ሞክረው ይሆናል።ነገር ግን ግዕዙም፥መጻ ሕፍቱም፥ሊቃውንቱም ከእኛ ጋር መሆናቸውን ማስተዋል ይገባል።ከዚህም ጋር ወደ ሌላ የሚኬደው ሲቸግር ብቻ መሆኑን መዘንጋት አይገባም።እኔ እያልኩ ያለሁት፡-ጥንት ቅዱሳት መጻሕፍት የተተረጎሙት ከባዕድ ቋንቋ ወደ ግዕዝ ነው፥ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ አማርኛ ተተርጉመዋል።ስለዚህ በቅድሚያ ማየት ያለብን የአማርኛው ቅጂና ግዕዙ መስማማታቸውን ነው።) » ብለሃል።
እዚህ ላይ ለአንተም ሆነ ለሌሎች ግልጥ የምናደርገው፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም፥ የግእዙ ትርጉም በዓለም ካሉት ትርጉሞች ሁሉ  ቀደምት ከሆኑትና ዛሬም ለምስክርነት የሚፈለግ ትርጉም ነው፤የትርጉሙ ጥንቃቄ፥ ከግሪኩ ጋር ያለው ቅርበት፥  በብዙ ደከመው ለእኛ ያስተላለፉት አባቶች፥ ለቅዱሳት መጻሕፍት ምን ያህል ክብር እንዳላቸው የሚያስረዳ የመንፈሳዊነታቸው ሕያው ምስክር ነው። ። በረከታቸው በእኛ ላይ ይደርብንና ፥ እነርሱ ለእኛ ያስተላለፉትን፥ ዛሬ እናንተ ልታፈልሱት መሞከራችሁ ነው እንድንጮህ ያደረገን።
ባለፈው ጽሑፍህ ስለ ሮሜ ፰፥፴፬ ያስቀመጥከው ከግእዙም ከአማርኛውም የሌለ ነው። ግእዙ ለምሳሌ የሚለው « ወይትዋቀስ በእንቲአነ» ነው። በየትኛው ሰዋስው ነው፥ ወይትዋቀስ በእንቲአነ « ስለ እኛ ይፈርዳል» የሚያሰኘው? በምስጢር ትለኝ ይሆናል። አንተ እኮ እየቀየርክ ያለኸው ገጸ ንባቡን ነው።  የአባቶች ትርጓሜ እንዳትል « ስለ እኛ ይከራከራል» ነው የሚለው እንጂ ስለ እኛ ይፈርዳል አይልም።  በነገራችን ላይ ግእዙና ግሪኩ አንድ ዓይነት አሳብ የያዙ ናቸው። « « ይትዋቀስ ይከራከራል» የሚለውና በግሪኩ “ ἐντυγχάνει  entynchanei “ ይማልዳል ተብሎ የተተርጎመው)  በምስጢር ብቻ ሳይሆን በቀጥታ ትርጉም ይገናኛሉ።  መማለድ ማለት ስለ አንድ ሰው ፈንታ ሆኖ ቆሞ መከራከር ማለት ነውና ። አንዳቸው በአንዳቸው ትርጉም ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ይፈርዳል ግን በገጸ ንባቡ በፍጹም የማይገናኝ፥ ከአባቶች መጻሕፍትም ምስክር የማይቀብርለት ነው።  ወደ ግሪኩ የሄድነው አንተ እንደምትለው ግእዙን ንቀን ሳይሆን አሁን ክርክራችን « ይትዋቀስን»  እንዴት እንተርጉመው ስለሆነ ነው።  የአባቶችን ትርጓሜ፥ የቅዱስ ዮሐንስን ትርጓሜ፥ ሃይማኖተ አበውን ወደ ጎን ስላደረጋችሁ፥ ቅዱስ መጽሐፍ ነውና ከመጀመሪያው እንዴት ተጻፈ ማለት የግድ ያስፈልጋል። ቅዱሳት መጻሕፍትን ስለመተርጎም ስናስብ ልንከተለው የሚገባንን አካሄድ  ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ መጽሐፍ ቅዱስን ባስተረጎሙበት ወቅት በጻፉት መቅድም ላይ በሚገባ ገልጠውልናል። እንዲህ ይላሉ፥ « የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጕም ከመሠረታዊ ቋንቋው ከዕብራይስጥና ከፅርዕ ጋር እየተያየ ሊታረም እንደሚገባው ስለ ተመለከትን፥ በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት ለዚህ ሥራ ተገቢ የሆኑትን ሊቃውንት መረጥን።»   ይላሉ።  እኛም ስንለው የነበረውን ይህን የንጉሠ ነገሥቱን አካሄድ ነው።
የ፪ሺ ዓመቱም መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ፥ ተርጓሚዎቹ በግልጥ ያስቀመጡት ሐቅ አለ። ይኸውም ከትርጓሜው ይልቅ ፖለቲካው ማለትም የእናንተ ተጽእኖ አስገድዶአቸው መሆኑን ለመግለጥ፥ « በግሪኩ ይማልዳል ይላል» ብለዋል። በተጨማሪ ማለት የነበረባቸው፥« ግእዙም እንዲህ አይልም ተገደን ነው እንጂ»  ነበር። ተርጓሚዎቹ የሚያመልጡበትን መንገድ ቢያስቀምጡም፥ ጥቂት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችን ለማስደሰት፥ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ አንገት የሚያስደፋ ሥራ ነው ነው የተሠራው። ( ይቀጥላል።)

ከቀሲስ መላኩ ተረፈ) ከቀሲስ መላኩ

Monday, May 15, 2017

የውግዘት ፖለቲካና የቤተ ክርስቲያናችን እጣ ፋንታ


( ክፍል አንድ ) # በቀሲስ መላኩ
መግቢያ
ባለፉት ሃያዎቹ ዓመታት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ
ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ አይታ የማታውቃቸው ሦስት አበይት
ክስተቶች ታይተውባታል። የመጀመሪያው አንደኛው፥ ከፍተኛ
የሆነ የሕዝብ ፍልሰት ነው። በአዲስ አበባ ያሉት አባቶች
በግልጥ ያስቀመጡት ይፋዊ አኀዙ ሰባት ሚሊየን ይባል
እንጂ፥ ከአስር እስከ አስራ አምስት ሚሊየን የሚሆኑ የቤተ
ክርስቲያኒቱ አባላት ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው ወደ ሌሎች
ቤተ እምነቶችና ተቋሞች ሄደዋል። ሁለተኛው ዓቢይ
ክስተት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሦስት መከፈሏ ነው።
የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ አራተኛው ፓትርያክ ብፁዕ
ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከመንበራቸው ከተሰደዱበት
ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስደት ያለው ቅዱስ
ሲኖዶስ፥ በአገር ቤት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ እና ገለለተኛ
በሚል ተከፍላለች። ሦስተኛው እና ቤተ ክርስቲያኒቱ
በታሪኳ አይታው በማታውቀው መንገድ የተከሰቱ ነገሮች
ቢኖሩ በተለይ አዲስ አበባ ባሉት አባቶች ዘንድ፥ «
ውግዘት» እንደ ታላቅ መሣሪያ መያዙ ነው።
በዚህ በያዝነው በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች ተቀራርበው
አሳባቸውን በሚካፈሉበት ዘመን፥ አብያተ ክርስቲያናት
ያለፈ ውግዘታቸውን በይቅርታና በመግባባት አስተካከለው፥
አንድ በሚያደርጋቸው ነገር ላይ ለመነጋገር እየጣሩ ነው።
በቅርቡ የሮም ፖፕና የእስክንድርያው ፓትርያርክ አንዳቸው
የአንዳቸውን ምእመን ዳግም እንዳያጠምቁ
መፈራረማቸው ይታወቃል። ሆኖም ግን ባለፉት 25
ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ ባሉት አባቶች አማካይነት፥
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በሺዎች የሚቆጠሩ
ምዕመናኖቿን እና አገልጋዮቿን አውግዛለች። ከአንድ
ቢሊየን አባላት በላይ ያላት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን
ባለፉት አንድ መቶ አመታት ያወገዘቻቸውና በአዲስ አበባ
ያሉት አባቶች ያወገዙትን ስንመለከት በቍጥር የእኛው
በልጦ እናገኛለን። በአንድ በኩል የምዕመናኑ በሚሊየኖች
ወደ ሌሎች የእምነት ተቋማት መሄድ በሌላ በኵል ደግሞ
ጳጳሳትን ሳይቀር ምእመናንን ጨምሮ በመቶ ሺዎች
የሚቆጠሩ ምእመናንን ማውገዝ ከየት መጣ ለምንድነው
ይህ ክስተት በእኛ ዘመን የተደጋገመው? ከዚህ ውግዘት
በስተጀርባ ያሉት እነማን ናቸው? ተጠቃሚዎቹስ እነማን
ናቸው የሚለውን ለመመለስ በመጀመሪያ ስለውግዘት
በሚገባ ማወቅ ይኖርብናል።
ሀ. ውግዘት ምንድነው?
ውግዘት ቃሉ፥ ወገዘ ከሚለው ግሥ እንደሚገኝ እና
ፍቺውም መገዘት መለየት መካድ መርገም ማለት እንደሆነ
የሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ
ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ይናገራል። ከዚህ ከቃሉ አንጻር
በምንመለከትበት ጊዜ፥ ቃሉ የሚያመለክተን ከዚህ በፊት
ከአንድ አካል ጋር አንድነት (communion) የነበረውን
እንዲለይ (excommuncate) ማድረግ ነው። ይህን
ግልጥ ለማድረግ ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእንዴት
ያለ መንገድ እንደተቀመጠ በማየት ትርጉሙን
እንመለከታለን።
1.ውግዘት እርግማን ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ሲጽፍላቸው
«ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥
ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥
የተረገመ ይሁን። አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን
ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም
ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን።» ይላቸዋል። ( ገላ ፩፥፰-
፱) ግእዙም « አትሙሰ መልአክ እምሰማይ ለእመ
መሀረክሙ ካልአ እምዘ መሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።
በከመ እቤ ቀዳሚ ወይእዜኒ ካዕበ እብል ለእመቦ
ዘመሀረክሙ እምዘመሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።»
አስተውሉ አማርኛው « የተረገመ ይሁን የሚለውን ግእዙ
የተወገዘ ይሁን ይለዋል። ይህ ውግዘት ወይም እርግማን
ምን ማለት እንደሆነ እንመልከት፥ አዲስ ኪዳን
ለመጀመሪያ ጊዜ የተጻፈበትን የግሪኩን ቃል
በምንመለከትበት ጊዜ፥ የተወገዘ ይሁን አናቴማ ኤስቶ
(ἀνάθεμα ἔστω ) ይለዋል። አናቴማ ቃሉ በብሉይ
ኪዳን « እርም»፥ «ለእሳት የተሰጠ» ማለት ነው። ለምሳሌ
ኢያሱ በኢያሪኮ የተገኘው ሁሉ እርም እንዲሆን ሲያዝ
አካን የተባለው ሰው « እርም ከሆነው ነገር ወሰደ»
ይለናል። ኢያሱ7፥1። እንዲህ ዓይነት ብዙ ጥቅሶች
በብሉይ ኪዳን እናገኛለን። በአዲስ ኪዳንም ይህንኑ ቃል
ሳይስት፥ አናቴማ ( ውግዘት እርግማን) ማለት
በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ በገላያ መልእክቱ ላይ በሐዋርያት
ከተሰበከው የጸጋ ወንጌል የተለየ ወንጌልን የሚሰብክ
በዚህ የእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ እንደሚወድቅ ሲናገር
እናያለን።
2. ውግዘት ለሰይጣን አልፎ መሰጠት ነው።
አሁንም ወደ ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ስንመጣ
በ1ቆሮ5፥5 ላይ «መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን
ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን
እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ሲል እናገኛለን። ቅዱስ ጳውሎስ
በዚህ ስፍራ ሐዋርያዊ ውግዘቱን ያሳረፈበት ሰው፥ በሥነ
ምግባር ውድቀት ውስጥ የተገኘ ማለትም የአባቱን ሚስት
ያገባ ሰው ነው። ሐዋርያው ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች
ሲናገር «ይህን ሥራ የሠራው ከመካከላችሁ ይወገድ። እኔ
ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ
ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን
እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም
አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን
ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን፥ መንፈሱ በጌታ
በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት
ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ይላል።
ይህ የቅዱስ ጳውሎስ ቃል ስለ ውግዘት ሦስት ዋና ዋና
ነገሮችን ያሳየናል። አንደኛ፥ ይህ ነገር በጉባኤ በጥንቃቄ
የሚታይ ነው። ጉባኤው የክርስቶስ ጌትነት የከበረበት
ጉባኤ መሆን አለበት። የሐዋርያው ሥልጣን የከበረበት
መሆን አለበት። « እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» በዚህ ዘመን ያለውን
በውግዘት ዙሪያ የሚከናወነው፥ ተመሳሳይነቱ ከፖለቲካ
አደባባዮች ጋር ነው። አንደኛ ከብሮ የሚታየው ክርስቶስ
ሳይሆን የሰዎች የተንኮለኛነት ችሎታ ነው። ለምሳሌ
ባለፉት ሃያ አምስት አመታት በኢትዮጵያ ያሉት አባቶች
በአመት ሁለት ጊዜ ሲሰበሰቡ፥ ከስብሰባቸው በፊት፥
የተቃውሞ ሰልፍ፥ የክስ ደብዳቤዎች፥ ዘመቻዎች፥
ይካሄድባቸዋል። ወደስብሰባው የሚሄዱ አባቶች
ስብሰባው ከመጀመሩ በፊት ተወጋዡ ማን
እንደሚሆን፥ውሳኔው ምን መሆን እንዳለበት ተነግሮአቸውና
ተጽእኖ ተደርጎባቸው ነው የሚገቡት። ነገሮችን ከምንም
ነገር ነጻ በሆነ መንገድ ለማየት የሚሞክሩ አባቶች፥
በስድብ በስም ማጥፋት ጥላሸት ይቀባባቸዋል። በዚህ
ምክንያት አንዳንዶች ዝምታን ሲመርጡ አንዳንዶች
ለተጽእኖው ያጎበድዳሉ። ቅዱስ ጳውሎስ « ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» ሲል « ብርታታችንና
ጉልበታችን የሚሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ይሆናል» ማለቱ
ነው። እውነት የምትነግሠውና ሐሰት ሥፍራን የምታጣው፥
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይልና በመንፈስ ቅዱስ
መሪነት ስንጓዝ ነውና።
ቅዱስ ጳውሎስ ሌላ ታላቅ ነገር ያነሣል። ይኸውም
ውግዘት ምን ያህል አስፈሪ ነገር እንደሆነ የሚያመለክት
ነው። አንድ ሰው ከእድር ቢለይ፥ ሌላ እድር ውስጥ
ይገባል። ወይም በዘመናዊው ዓለም ሌላ ዘዴ ሊጠቀም
ይችላል። ( ላይፍ ኢንሹራንስ ሊገባ ይችላል።)ፋንታ
( ክፍል አንድ ) # በቀሲስ መላኩ
መግቢያ
ባለፉት ሃያዎቹ ዓመታት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ
ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ አይታ የማታውቃቸው ሦስት አበይት
ክስተቶች ታይተውባታል። የመጀመሪያው አንደኛው፥ ከፍተኛ
የሆነ የሕዝብ ፍልሰት ነው። በአዲስ አበባ ያሉት አባቶች
በግልጥ ያስቀመጡት ይፋዊ አኀዙ ሰባት ሚሊየን ይባል
እንጂ፥ ከአስር እስከ አስራ አምስት ሚሊየን የሚሆኑ የቤተ
ክርስቲያኒቱ አባላት ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው ወደ ሌሎች
ቤተ እምነቶችና ተቋሞች ሄደዋል። ሁለተኛው ዓቢይ
ክስተት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሦስት መከፈሏ ነው።
የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ አራተኛው ፓትርያክ ብፁዕ
ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከመንበራቸው ከተሰደዱበት
ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስደት ያለው ቅዱስ
ሲኖዶስ፥ በአገር ቤት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ እና ገለለተኛ
በሚል ተከፍላለች። ሦስተኛው እና ቤተ ክርስቲያኒቱ
በታሪኳ አይታው በማታውቀው መንገድ የተከሰቱ ነገሮች
ቢኖሩ በተለይ አዲስ አበባ ባሉት አባቶች ዘንድ፥ «
ውግዘት» እንደ ታላቅ መሣሪያ መያዙ ነው።
በዚህ በያዝነው በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች ተቀራርበው
አሳባቸውን በሚካፈሉበት ዘመን፥ አብያተ ክርስቲያናት
ያለፈ ውግዘታቸውን በይቅርታና በመግባባት አስተካከለው፥
አንድ በሚያደርጋቸው ነገር ላይ ለመነጋገር እየጣሩ ነው።
በቅርቡ የሮም ፖፕና የእስክንድርያው ፓትርያርክ አንዳቸው
የአንዳቸውን ምእመን ዳግም እንዳያጠምቁ
መፈራረማቸው ይታወቃል። ሆኖም ግን ባለፉት 25
ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ ባሉት አባቶች አማካይነት፥
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በሺዎች የሚቆጠሩ
ምዕመናኖቿን እና አገልጋዮቿን አውግዛለች። ከአንድ
ቢሊየን አባላት በላይ ያላት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን
ባለፉት አንድ መቶ አመታት ያወገዘቻቸውና በአዲስ አበባ
ያሉት አባቶች ያወገዙትን ስንመለከት በቍጥር የእኛው
በልጦ እናገኛለን። በአንድ በኩል የምዕመናኑ በሚሊየኖች
ወደ ሌሎች የእምነት ተቋማት መሄድ በሌላ በኵል ደግሞ
ጳጳሳትን ሳይቀር ምእመናንን ጨምሮ በመቶ ሺዎች
የሚቆጠሩ ምእመናንን ማውገዝ ከየት መጣ ለምንድነው
ይህ ክስተት በእኛ ዘመን የተደጋገመው? ከዚህ ውግዘት
በስተጀርባ ያሉት እነማን ናቸው? ተጠቃሚዎቹስ እነማን
ናቸው የሚለውን ለመመለስ በመጀመሪያ ስለውግዘት
በሚገባ ማወቅ ይኖርብናል።
ሀ. ውግዘት ምንድነው?
ውግዘት ቃሉ፥ ወገዘ ከሚለው ግሥ እንደሚገኝ እና
ፍቺውም መገዘት መለየት መካድ መርገም ማለት እንደሆነ
የሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ
ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ይናገራል። ከዚህ ከቃሉ አንጻር
በምንመለከትበት ጊዜ፥ ቃሉ የሚያመለክተን ከዚህ በፊት
ከአንድ አካል ጋር አንድነት (communion) የነበረውን
እንዲለይ (excommuncate) ማድረግ ነው። ይህን
ግልጥ ለማድረግ ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእንዴት
ያለ መንገድ እንደተቀመጠ በማየት ትርጉሙን
እንመለከታለን።
1.ውግዘት እርግማን ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ሲጽፍላቸው
«ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥
ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥
የተረገመ ይሁን። አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን
ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም
ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን።» ይላቸዋል። ( ገላ ፩፥፰-
፱) ግእዙም « አትሙሰ መልአክ እምሰማይ ለእመ
መሀረክሙ ካልአ እምዘ መሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።
በከመ እቤ ቀዳሚ ወይእዜኒ ካዕበ እብል ለእመቦ
ዘመሀረክሙ እምዘመሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።»
አስተውሉ አማርኛው « የተረገመ ይሁን የሚለውን ግእዙ
የተወገዘ ይሁን ይለዋል። ይህ ውግዘት ወይም እርግማን
ምን ማለት እንደሆነ እንመልከት፥ አዲስ ኪዳን
ለመጀመሪያ ጊዜ የተጻፈበትን የግሪኩን ቃል
በምንመለከትበት ጊዜ፥ የተወገዘ ይሁን አናቴማ ኤስቶ
(ἀνάθεμα ἔστω ) ይለዋል። አናቴማ ቃሉ በብሉይ
ኪዳን « እርም»፥ «ለእሳት የተሰጠ» ማለት ነው። ለምሳሌ
ኢያሱ በኢያሪኮ የተገኘው ሁሉ እርም እንዲሆን ሲያዝ
አካን የተባለው ሰው « እርም ከሆነው ነገር ወሰደ»
ይለናል። ኢያሱ7፥1። እንዲህ ዓይነት ብዙ ጥቅሶች
በብሉይ ኪዳን እናገኛለን። በአዲስ ኪዳንም ይህንኑ ቃል
ሳይስት፥ አናቴማ ( ውግዘት እርግማን) ማለት
በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ በገላያ መልእክቱ ላይ በሐዋርያት
ከተሰበከው የጸጋ ወንጌል የተለየ ወንጌልን የሚሰብክ
በዚህ የእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ እንደሚወድቅ ሲናገር
እናያለን።
2. ውግዘት ለሰይጣን አልፎ መሰጠት ነው።
አሁንም ወደ ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ስንመጣ
በ1ቆሮ5፥5 ላይ «መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን
ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን
እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ሲል እናገኛለን። ቅዱስ ጳውሎስ
በዚህ ስፍራ ሐዋርያዊ ውግዘቱን ያሳረፈበት ሰው፥ በሥነ
ምግባር ውድቀት ውስጥ የተገኘ ማለትም የአባቱን ሚስት
ያገባ ሰው ነው። ሐዋርያው ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች
ሲናገር «ይህን ሥራ የሠራው ከመካከላችሁ ይወገድ። እኔ
ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ
ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን
እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም
አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን
ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን፥ መንፈሱ በጌታ
በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት
ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ይላል።
ይህ የቅዱስ ጳውሎስ ቃል ስለ ውግዘት ሦስት ዋና ዋና
ነገሮችን ያሳየናል። አንደኛ፥ ይህ ነገር በጉባኤ በጥንቃቄ
የሚታይ ነው። ጉባኤው የክርስቶስ ጌትነት የከበረበት
ጉባኤ መሆን አለበት። የሐዋርያው ሥልጣን የከበረበት
መሆን አለበት። « እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» በዚህ ዘመን ያለውን
በውግዘት ዙሪያ የሚከናወነው፥ ተመሳሳይነቱ ከፖለቲካ
አደባባዮች ጋር ነው። አንደኛ ከብሮ የሚታየው ክርስቶስ
ሳይሆን የሰዎች የተንኮለኛነት ችሎታ ነው። ለምሳሌ
ባለፉት ሃያ አምስት አመታት በኢትዮጵያ ያሉት አባቶች
በአመት ሁለት ጊዜ ሲሰበሰቡ፥ ከስብሰባቸው በፊት፥
የተቃውሞ ሰልፍ፥ የክስ ደብዳቤዎች፥ ዘመቻዎች፥
ይካሄድባቸዋል። ወደስብሰባው የሚሄዱ አባቶች
ስብሰባው ከመጀመሩ በፊት ተወጋዡ ማን
እንደሚሆን፥ውሳኔው ምን መሆን እንዳለበት ተነግሮአቸውና
ተጽእኖ ተደርጎባቸው ነው የሚገቡት። ነገሮችን ከምንም
ነገር ነጻ በሆነ መንገድ ለማየት የሚሞክሩ አባቶች፥
በስድብ በስም ማጥፋት ጥላሸት ይቀባባቸዋል። በዚህ
ምክንያት አንዳንዶች ዝምታን ሲመርጡ አንዳንዶች
ለተጽእኖው ያጎበድዳሉ። ቅዱስ ጳውሎስ « ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» ሲል « ብርታታችንና
ጉልበታችን የሚሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ይሆናል» ማለቱ
ነው። እውነት የምትነግሠውና ሐሰት ሥፍራን የምታጣው፥
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይልና በመንፈስ ቅዱስ
መሪነት ስንጓዝ ነውና።
ቅዱስ ጳውሎስ ሌላ ታላቅ ነገር ያነሣል። ይኸውም
ውግዘት ምን ያህል አስፈሪ ነገር እንደሆነ የሚያመለክት
ነው። አንድ ሰው ከእድር ቢለይ፥ ሌላ እድር ውስጥ
ይገባል። ወይም በዘመናዊው ዓለም ሌላ ዘዴ ሊጠቀም
ይችላል። ( ላይፍ ኢንሹራንስ ሊገባ ይችላል።)