Wednesday, April 12, 2017

«አሮጌውን እርሾ አስወግዱ፤ ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና»

Saturday, April 



(በድጋሚ የቀረበ)

ዕብራውያን     פֶּסַח «ፔሳኽ» ይሉታል። ፋሲካ ማለት ነው።  በወርኀ ኒሳን በዐሥራ ዐምስተኛው ቀን ይከበራል። ሥርዓቱ የሚጀመረው በዐሥራ አራተኛው ቀን ዋዜማ ሲሆን በፋሲካው ሳምንት እርሾ የገባበት ምንም ዓይነት ምግብ መመገብ ክልክል ነው።ዕለቱን ተቦክቶ ወዲያው የሚጋገር እንጂ የኮመጠጠ ወይም የቦካና የዋለ፤ያደረ መመገብ በሕጉ እንደተቀመጠው ከእስራኤል አንድነት ያስወግዳል። ከማንኛውም እርድ ላይ ጥሬ መብላት ወይም ከበሉትም አስተርፎ ማሳደር አይፈቀድም። ለመስዋዕት የሚቀርበው የበግ ወይም የፍየል መስዋዕትም እድሜው ከአንድ ዓመት ያልበለጠ ጤናማና የተመረጠ መሆን ይገባዋል። በዐሥራ ዐራተኛው ቀን ምሽት መስዋዕቱ ይታረዳል።ሥጋውን ደግሞ ሌሊት  ከመራራ ቅጠል ጋር ቀላልቅለው ይበሉታል። 
ደሙን ደግሞ  የበሩን ሁለት ረድፍ «መቃንና ጉበኑን» ይቀቡታል።  ሁለቱን ቋሚ መቃንና የላይኛውን ጉበን ሲቀቡት ይህንን ቅርጽ ይይዛል።


ይህ ቅርጽ የዕብራውያን ስምንተኛውን ፊደል «ኼ» የተባለውን ይወክላል። (እንደአማርኛው በጉሮሮ ሳይሆን በላንቃ የሚነበብ ነው) «ኼ» ማለት በዕብራውያን ትርጉም «ሕይወት» ማለት ነው። ዕብራውያንም በፊደላቸው በ«ኼ» ቅርጽ በሚቀቡት ደም የተነሳ ወደፈርዖናውያን ሠፈር የሚያልፈው ሞት አይነካቸውም። ምክንያቱም ሕይወት የሚል ማኅተም በራቸው ጉበንና መቃን ላይ ታትሟልና። ፋሲካ ማለት ይህ ነው። በደሙ ምልክት የተከለሉ በሕይወት ለመቆየት ዋስትና የያዙ ሲሆን ይህንን ማኅተም ያላገኙና ምን እየሆነ እንዳለ የማያውቁ ደግሞ  በሞት የሚወሰዱበት  የፍርድ ምልክት ነው። ደሙ የሞትና የሕይወት መለያ ምልክት ሆኖ አገልግሏል።
ይህ ሥርዓት እስራኤላውያንን ከባርነት፤ ከጠላት አገዛዝና ከመገደል የታደገ የዋስትና መንገድ ነበር። እንደዚሁ ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካ ሕዝብና አሕዛብን ከሰይጣን ባርነትና ከዘላለም ሞት የታደገ በመሆኑ ሐዋርያው ጳውሎስ «እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ። ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና» 1ኛ ቆሮ 5፤7 በማለት የሚነግረን።  አሮጌውን እርሾ ካላስወገድን ፋሲካችን የሆነውን ክርስቶስ መቀበል አይቻልም። የክርስቶስን ፋሲካ እካፈላለሁ በማለት የበዓሉን አከባበር ማድመቅ፤ እንኳን አደረሰህ/አደረሰሽ መባባል ልምድ እንጂ የመለወጥ ምልክት አይደለም። የክፋት እርሾ የተባሉትን ሐዋርያው ጳውሎስ በቆሮንቶስ መልእክቱ ሲነግረን እንዲህ ይለናል። «ሴሰኛ፤ ገንዘብን የሚመኝ፤ ወይም ጣዖትን የሚያመልክ፤ ወይም ተሳዳቢ ወይም ሰካር ወይም ነጣቂ» ከመሆን መታቀብ ብቻ ሳይሆን ከሆኑትም ጋር አብሮ ባለመብላት ጭምር በመከልከል ከአሮጌው እርሾ ሆምጣጣነት መራቅ እንዲገባን ያስፈልጋል። (1ኛ ቆሮ 5፤11) የእስራኤል ዘሥጋ ፋሲካ መጻጻና የቦካ ይከለክል እንደነበረው ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካም እንዲሁ ይከለክላል። በኃጢአትና በዐመጻ የቦካ የውስጣችንን ሆምጣጣ እርሾ ካላስወገድን በስተቀር በፋሲካው የሚገኘውን ሕይወት በፍጹም  አናገኝም።  የቀደመው ፋሲካ እርሾ ያለውን ነገር ከቤቱ ያላጠፋ «ከእስራኤል ጉባዔ ተለይቶ ይጥፋ» የሚል ሕግ ነበረው።  ምድራዊው ፋሲካ ይህንን ያህል ከከበረ ሰማያዊውማ እንደምን የበለጠ አይከብር? ፋሲካን መናገርና ፋሲካን አውቆ መኖር የተለያዩ ነገሮች ናቸው። ስለፋሲካ ብዙ ማስተማርና መናገር ይቻል ይሆናል። ስለፋሲካ የመልካም ጊዜ መግለጫና ስጦታም መለዋወጥ ይቻል ይሆናል። ፋሲካን ማክበር ማለት 2 ወራት በጾም አሳልፎ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታልህ/ፈታልሽ» ተብሎ ልጓም አልቦ የመሆኛ ሰዓት ደረሰ በማለት የሰላምታ መሰጣጣት ፕሮግራም አይደለም። ጾሙ ሲፈታ እንደፈለገን ልንበላ፤ ልንጠጣ፤ ልንናገር የልጓም አጥራችን ተከፈተ ማለት ከሆነ በአሮጌው እርሾ ብቻ ሳይሆን ከሰው የልማድ ስርዓት ጋር እንኖራለን ማለት ነው። የክርስቶስ ፋሲካ ግን በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ አይገኝም። ፋሲካ በስግደትና በወይራ ቅጠል በመጠብጠብ የሚገኝም ጸጋ አይደለም።  ፋሲካ የአንድ ወቅት ራስን ማስገዛትና በጽኑ እሳቤና ጭንቅ ማለፍ ውስጥ የሚመጣም አይደለም።
ፋሲካ በልባችን መቃንና ጉበን ላይ የደሙን ምልክት በመያዝ ዕብራውያን ከሞት እንዳመለጡበት የ «ኼ» ምልክት ማኅተም በመያዝ ብቻ ነው የምንድነው። ያን ጊዜ ብቻ ነው ሞት በራችን ላይ ያለውን የአዲስ ኪዳኑን «ፔሳኽ» አይቶ የሚያልፈው። ይህንን የደም ማኅተም ለመያዝም ከክፋት፤ ከሀሰት፤ ከግፍና ከዐመጻ እርሾ መለየት የግድ ነው። ከዝሙት፤ ከስርቆት፤ ከጉቦ፤ ከምኞትና ከኃጢአት ሁሉ እርሾ ሳንለይ ውስጣችን የሞላውን መጻጻ ተሸክመን የፋሲካ ሕይወት የለም። እስራኤላውያን መዳን የቻሉት የፋሲካቸውን የበግ ደም ምልክት በመያዛቸው ብቻ ነው።  እኛም የአዲስ ኪዳኑ የእግዚአብሔር በግ የክርስቶስን ደም ምልክት ካልያዝን በማንም በሌላ ምልክት ወይም ጻድቅ ዋስትና ልንድን አንችልም። ሁሉም ይህንን የደም ምልክት የመያዝ ግዴታ ስላለበት ማንም ለማንም ዋስትና ሊሆን እንደማይችል ጳውሎስም «ልዩነት የለም፤ ሁሉም የመዳን ጸጋ ያስፈልገዋል» አለን። 

«እርሱም፥ ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው፤ ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ» ሮሜ 3፤22-24
እንግዲህ  ከፋሲካው ተስፋ የምናደርግ ሁላችን እስኪ ራሳችንን እንመርምር። እንደመጽሐፍ ሊያነበን በሚቻለው ከፋሲካችን ክርስቶስ ፊት እስኪ ራሳችንን እናንብበው። በእውነት እነዚህ እርሾዎች በውስጣችን ከሌሉ ከ2000 ዓመት በፊት ለሕይወት የፈሰሰውን ደም ይዘናል ማለት ነው። ያኔም ሞት በኛ ላይ ምንም ሥልጣን እንደሌለው አረጋግጠናል። እስራኤላውያን የበራቸውን ጉበንና መቃን በቀቡ ጊዜ ሞት እንደማይነካቸው እርግጠኞች እንደነበሩ ሁሉ እኛም የበለጠውንና የተሻለውን የሕይወት ደም በእምነት ስለያዝን ለዘላለማዊ ሕይወት እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ከዚያ ባሻገር በየዓመቱ በሚመጣ በዓል የሚገኝ የደም ምልክት የለም። በጥብጠባና በስግደትም የሚገኝ የሕይወት ዋስትና እንዳለ ካሰብን የፋሲካውን ምስጢር በልምድ ሽፋን ስተነዋል ማለት ነው። የተደረገልንን ማሰብ አንድ ነገር ሆኖ ሰው ግን ዓይኑን በዚያ በዓል ላይ ተክሎ የዓመቱ ኃጢአት ወይም ሸክም እንደሚወድቅ ማሰብ ስህተት ነው። ዓመቱን ሙሉ ከክፋትና ከግፍ እርሾ በመላቀቅ፤ ለአንድም ሰከንድ የማይለይ ምልክት ልባችን ጉበንና መቃን ላይ ደሙን በእምነት ይዘን መገኘት የግድ ይሆንብናል። ያኔ ነው ፋሲካችን ታርዷል የምንለው። ያኔም ነው ሁልጊዜ በሕይወት መንገድ ላይ እንዳለን የምናውቀው። መንፈሳዊ ሕይወት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሰምርልን ዕለት፤ ዕለት መታደስ መታደስ ይገባዋል።
«ስለዚህም አንታክትም፥ ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል» 2ኛ ቆሮ 4፤16 ንስሐ እንግባና እንታደስ።
ፋሲካችን የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ ያደረገልንን ውለታ እያሰብን ውስጣችንን መፈተሽ የግድ ነው። በአምናው እኛነታችንና በዘንድሮው እኛነታችን መካከል የሕይወት ለውጥ ከሌለን ሞት በመጣ ጊዜ ምንም የመዳን ምልክት እንደሌላቸው ፈርዖናውያንን ወደዘላለማዊ ሞት መሄዳችን እውነት ነው። በወይራ በመጠብጠብ 30 እና 40 ለመስገድ ከመሽቀዳደም ይልቅ፤ ከሞት የማምለጫ የፋሲካው ዓርማ ክርስቶስን ከኃጢአት በጸዳ ማንነታችን ውስጥ ዘወትር ይዘነው እንኑር። ዝሙት፤ ውሸት፤ስርቆት፤ ሃሜት፤ ነቀፋ፤ ምኞትና ገንዘብን መውደድ ሁሉ ሳንተው ፋሲካን ማክበር አይቻልም። ከቦታ ቦታ በመዞርም ፋሲካ አይገኝም። ፋሲካ በልባችን ላይ አንዴ የተሰራው የክርስቶስ የእምነታችን ከተማ ነው። በዚያ ላይ የማይጠፋ ብርሃን አለ። ክርስቶስ ባለበት በዚያ የልባችን ከተማ ውስጥ ማስተዋል፤ ደግነት፤ በጎነትና ቅንነት አለ። ከዚያ መልካም ከተማ የሚወጣው ሃሳባችን የተራቡትን ያበላል፤ የታረዙትን ያለብሳል፤ የታመሙትን ይጠይቃል። ኑሮአችን፤ አነጋገራችንና አካሄዳችን በልክ ነው። ዕለት ዕለት በምንኖረው ሕይወት እንጂ በዓመት አንድ ቀን በሚከበር ፋሲካ ክርስቶስን መምሰል አይቻልም። ሞት የደሙ ምልክት የሌለባቸውን እስራኤላውያንን ሁሉ ይገድል ነበርና። እኛም በሰማይ የተሰጠንን ተስፋ እስክናገኝ ድረስ ሞት ከተጠበቀልን ተስፋችን እንዳያስቀረን ፋሲካችን ክርስቶስን ዕለት ዕለት በልባችን ይዘን እንኖራለን። ያኔም በክርስቶስ ያለ ተስፋችን ምሉዕ ስለሆነ ስለመዳናችን አንጠራጠርም። አብርሃም ልጅ ሳይኖረው «ዘርህ ዓለሙን ይሞላል» ሲባል በእምነቱ ተስፋውን ተቀበለ። በክርስቶስ ትንሣዔ ያመንን እኛ ደግሞ እንደምንድን ካመን የተሰጠን የመዳን ተስፋ በሰማይ እውነት ሆኖ ይጠብቀናል።  ምክንያቱም የመዳናችን የእምነት ተስፋ ክርስቶስን በልባችን ዕለት ዕለት ይዘን እንዞራለንና!!

Monday, April 3, 2017

ከእንግዲህ የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ አትበሉኝ!


አይደለሁምና፤ አዎን አይደለሁም።
የፕሮቴስታንትም ኃይማኖት ተከታይ አትበሉኝ።
አይደለሁምና።
የሆነ ጊዜ መናፍቅ ትሉኝ እንደነበረም አስታውሳለሁ።
ለምን አላችሁኝ ብዬ አልከፋም!
ታላቁ የእምነት ሞዴላችን ቆራጡ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም በአንድ ጠርጠሉስ በሚባል አእምሮ በደነዘዘው አይሁድ "መናፍቅ!" ተብሏልና።(የሐዋ.ሥራ 24:5)
ግድ የለም።
የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ በመሆን መንግሥተ ሰማይ አይገባም።
ክርስቶስም ይህንን ቃል አልገባልንም፣ የአባቱን ፈቃድ የሚፈጽሙትን ነው እንጂ..።
ጌታ ጌታ ስላልክ፥ በሃሌ ሉያ ስላንጋጋህ፥ በፉጨት በእልልታ ስለቀወጥክ፥ ባይብል በእጅህ ስላልተለየ፥ኢየሱስ ኢየሱስ ስላልክ፣ በየማምለኪያ አዳራሽ ስለተገኘህ፥ በአዲስ ቋንቋ ስለተናገርክ፤ ፐ! አንተ የእግዚአብሔር ሰው ስላሉክ፣በሱፍ በከረባት በየአደባባዩ ስለተገለጥክ፥ ከባህር ማዶ ጀምሮ የአገልግሎትህ ኮሜንት "ተባረክ" ስለጎረፈልህ...በቃ ....እንዲያ በማለት ሰማይ የገባክ አይምሰልህ።
ይሄም ዋስትና አይደለም።
አርብ እሮብ ስለጾምክ፥ ይሄም ሳያንስህ ወራትን ሳምንታትን በመላምት ስያሜ እያቆላመጥክ ክርስትና አይሉት ግብዝና በመጾምህ የተመጻደቅክ ቢመስልህ፣በባዶ እግርህ ስለተጓዝክ፣ግሽን፤ ኩክ የለሽን ስለተሳለምክ፥ ደብረ ዳሞን ስለወጣክ፣ ስዕለትህን በሩቅ ሀገር ንግስ ስላደረስክ፣ ሰባት አመትኮ በአንድ እግሩ ቆሞ ፐ! ብለህ ተከታይህ ነኝ ስላልክ አይደለም፥ዳገት ቁልቁለቱን ወጥተህ ስለወረድክ አይምሰልህ።
በቀን 5 ጊዜ ስለሰገድክ፣ ጥፍርህን ስለሞረድክ፣አፍንጫህን አሻሽተህ ሼይጢያንን እያሳደድኩ ነው ብትልና፣ዘካ ስላወጣክ፥ ጁምአ ስለሰገድክ አይደለም መንግሥተ ሰማይ በዚህ አይገኝም።
በዉል ማንነቱን ባታውቅም የአንድ አምላክ ተከታይ ነኝ ስላልክ፣ ይህ ሁሉ የመንግሥተ ሰማይ ዋስትና ሊሆን አይችልም።
አመቱን እያሰላህ በጨረቃ ተመርተህ ወሩን ሙሉ ስለጾምክ፣ ሱሪህን ስላሳጠርክ፣ ቆቡን ስለደፋህ፣ አንቺም ከጥፍር እስከራስ ስለተከናነብሽ፤ በቀዳደa አጮልቀሽ ስላየሽ መንግሥተ ሰማይ መግባት እንዲያ እንዳይመስልሽ። ይህ ሀሉ እንኳን የምትወርሽበት ለመውረስ በሚደረገው ጉዞ አንድ እርምጃ እንኳን አይሸፍንም።

አይሁድ ነሽ ሙስሊም፣ቡዲዝም ነሽ ሂንዱዝም ኦርቶዶክስ ነሽ ጴንጤ ይህ ሁሉ የመደራጃ እድር ነው።

እኔ ግን የክርስትና የኃይማኖቱ ተከታይ አትበሉኝ እያልኩኝ አንድ ነገር የምለው አለኝ፣
ማንም ምንም ብትሆን ማንነትህና ምንነትህ ለኔ ምንምምም ነው።
ነገር ግን እውነት መንገድና ህይወት እነሰ ነኝ ያለውን፤ በእኔ በቀር ወደአብ የሚደርስ ማንም የለም ያለውን፣በእኔ የሚያምን ለዘላለም ይኖራል ያለውን፣በመካከላችን ያለውን የጥል ግድግዳውን በደሙ አፍርሶ የመጣበትን አላማ ጨርሶ ተፈጸመ በማለት ወደሰማይ ያረገውን፡መጥቼም እወስዳችኃለሁ፣ከእኔም ጋር ለዘላለም ትኖራላችሁ በማለት የማናችሁም አምላክ ያልገባላችሁን ታላቅ የማይታጠፍ የተስፋ ቃል የገባልንን ፥ ስለአንተና ስለእኔ ብሎ ወደምድር በመምጣት ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር ያልቆጠረውን፤ የአብ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን ያላመነ ፤ በእርሱም በቃሉ ያልኖረ፤ በወንጌሉም ያላመነ፤ እርሱ በደሙ በመሠረተው በመሠረቱ ያልቆመ፣ጌታና መዲኅን፣የነፍሱም ዋስትና አድርጎ ያልተቀበለ ሁሉ ምንም ዋስትና የለውም። ። ። ።

ምንም የህይወት ዋስትና የለውም። ።

ይህን ስታሟላ ብቻ ነው የመንግሥተ ሰማይን የመውረስ ዋስትና የሚኖርህ።
እኔም የክርስትና አምነት ተከታይ ሳልሆን የክርስትና እምነት የመሥራቹ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ነኝ።
ስለዚህ ከዚህ በኋላ ኢትዮ ቴሌኮምም ቢሆን ክርስቲያናዊ ለሆኑ በዓላት መልካም ምኞታቸውን ሲገልጹ "የክርስትና እምነት ተከታዮች" ከማለት ይልቅ "የክርስቶስ ኢየሱስ ተከታዮች"ቢሉን ደስ ይለናል።

አዎን የክርስቶስ ኢየሱስ ተከታይ ነኝ።
የእግዚአብሔር የመንግሥቱ ሰባኪ፣
የትንሣኤው መስካሪ፣
የክርስቶስ የወንጌሉ ዘማሪ፣
አዋጅ ነጋሪ፣
የአንድ መሪ፣የአንድ አምላክ የአንድ ጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ነኝ እንጂ ""የማንም ድርጅት ወይም ቸርች"" ተከታይ አይደለሁም።

በርሱ በማመኔ ብቻ በውድ ደሙ የታጠብኩ የማይሻር ኪዳን የተገባልኝ ምጽአቱንም በማራናታ የምጠባበቅ
እእእ የደሙ ፍሬ ነኝ!!!

( Fitsum @yalkbet )

Wednesday, February 1, 2017

ፈውስ!


Tsige Sitotaw

በሁሉም ቤተ እምነቶች ዘንድ የሚታየው የፈውስ ጉዳይ ብዙ ሰዎችን ጥርጣሬ ውስጥ እያስገባ ነው ።
እስቲ እንደ እግዚአብሔር ቃል እንነጋገርበት
1. ፈውስ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ
ክርስቲያን ፦
በዚች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚታየው የፈውስ ሥነ ሥርዓት ያለ ፀበል የሚከናወን አይደለም ። ስለዚህም በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ፀበል በምንጭም ይሁን ከቧንቧ በተጠለፈ ውኃ የሚጠመቁ በርካታ ናቸው ።
እንዲሁም ፀበል እየተባለ በተለያዩ ቦታዎች እየተዘጋጄ በብዙ ሰልፍ የሚጠመቅ ሕዝብ ቀላል አይደለም ። በዚያ ቦታ ላይ የሚታዩትን ትርዒቶች ማየት አስገራሚ ነው ።
በክፉ መናፍስት የተያዙ ሰዎች አእምሯቸውን እየሳቱ እየወደቁ ከልባቸው እያለቀሱ ራሳቸውን እየሳቱ በብዙ መኃላ እየተገዘቱ ሲወጡና የታመሙት ነጻ ሲወጡ ይታያሉ ።
ይህ ሁሉ የሚሆነው በተለያዩ ቅዱሳን ስም በተሰየሙ ፀበሎች ነው ። ስለሆነም ኦርቶዶክሳውያን ትክክለኛ እምነት እንዳላቸውና ቅዱሳን ያማልዳሉ ለሚለው ማረጋገጫቸው ይኸው ተአምራት የሚታይበት ፀበል ቦታ ነው ።
በተጨማሪም ፦ በክፉ መንፈስ የተያዘው ሰው ራሱን ስቶ መንፈሱ በላዩ ላይ ሆኖ ሲለፈልፍ ከየትና ምን ሲያደርግ እንደያዘው መናገር ይጀምራል ።
ከየት ያዝኸው ሲባል ከጴንጤ ቸርች ምን ሲያደርግ ሲባል ኢየሱሴ ኢየሱሴ እያለ ሲለፈልፍ ትክክለኛው ሃይማኖት የትኛው ነው ሲባል ኦርቶዶክስ ሌላውስ ሲባል የውሼት እያሉ ካስለፈለፉ በኋላ ያንን በካሴት ቀድተው እውነተኛዋ ሃይማኖት ሰይጣን እንኳ የመሠከረላት ቅድስት ተዋሕዶ እያሉ ከሰይጣን በሰሙት መረጃ ሃይማኖታቸውን የሚሰብኩ ሰዎች አሉ ።
እንደገናም ሰይጣኑ ተቃጠልሁ ነደድሁ ልሂድ ልውጣ እያለ ሲጮህ ምስህ ምንድን ነው ? ተብሎ ይጠየቃል እሱም አመድ ወይም አተላ ወይም ደም ወይም ሌላ ነገር እንዲመጣለት ይጠይቃል ያዘዘው ነገር ሲቀርብለት ያንን ጠጥቶ ለቀቅሁ ብሎ ሦስት ጊዜ ጮኸህ ውጣ ዳግም ላትመለስ የሚካኤል ሰይፍ ይቁረጠኝ ብለህ ምለህ ተገዝተህ ውጣ ተብሎ ያንን ቃል ፈጽሞ ሄድሁ ብሎ ይጮሃል ። ከዚያ በኋላ ሕመምተኛው ጤነኛ ሆኖ በአእምሮው ይሆናል ማለት ነው ።
እሺ ነገሩን ተመልክተናል የሚካድም አይደለም ። ግን በመንፈሳዊ ዓይን ሲታይ በእርግጥ ፈውሱ ተከናውኗል ወይ ? ብለን ጠይቀን መልስ ማግኜት አንችልም ።
ምክንያቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምናደርገውን ሁሉ በማን ስም ማድረግ እንዳለብን አዝዞናል ።
ለምሳሌ ፦ እንደዚህም ያለውን አንድ ሕፃን በስሜ የሚቀበል ሁሉ እኔን ይቀበላል ። የማቴዎስ ወንጌል 18÷5
ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና ። የማቴዎስ ወንጌል 18÷ 20
የክርስቶስ ስለ ሆናችሁ በስሜ ጽዋ ውኃ የሚያጠጣችሁ ሁሉ፥ ዋጋው እንዳይጠፋበት እውነት እላችኋለሁ ። የማርቆስ ወንጌል 9÷41
ያመኑትንም እነዚህ ምልክቶች ይከተሉአቸዋል፤ በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፤ በአዲስ ቋንቋ ይናገራሉ፤ እባቦችን ይይዛሉ ። የማርቆስ ወንጌል 16÷17
በተጨማሪም የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 14, 15,16 ሁሉንም ብንመለከታቸው በኢየሱስ ስም ብቻ መለመን ወይም መጸለይ እንዳለብን ታዝዘናል።
አጋንንት የሚወጡት በእርሱ ስም ሙታን የሚነሡት ለምጻሞች የሚነጹት ማናቸውም ፈውስ የሚከናወነው በጌታ ስም ብቻ እንደሆነ ታዝዘናል ።
ታዲያ እንዲህ ከሆነ በፀበልና በቅዱሳን ስም እንደሚለቁ ሆነው የሚጮሁት ለምንድን ነው ?
እንግዲያው ሰይጣን እያታለለን እያዘናጋን እንደሆነ ልናውቅበት ይገባል ። ባልተሰበከልን ልዩ ወንጌል ታስረን ከእርሱ ጋር ወደ ገሃነም እንዳንገባ ።
ስለዚህ የምናደርገውን ሁሉ በኢየሱስ ስም ብቻ ። አሜን ። አሜን ። አሜን ። ወአሜን ለይኩን ለይኩን ።
2 . ፈውስ በወንጌላውያን ፦
በአሁኑ ሰዓት እርስ በእርሳቸው የማይተዋወቁ በፕሮቴስታንትነት የሚታወቁ በርካታ ቤተ እምነቶች እየተመለከትን ነው ። አንዳንዶች በሽማግሌዎች ሲመሩ አንዳንዶች ደግሞ በግለ ሰቦች ብቻ የሚመሩ ናቸው ።
በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ተመሳሳይነታቸው ይበዛል ። በአደባባይ የሚፈጸመውን ሥርዓተ አምልኮ ስንመለከትም ጸሎቱ ዝማሬው ስብከቱ አለባበሱ ልሣኑ ትንቢቱ ጥምቀቱ ቊርባኑ ሁሉ አንዱን ከሌላው መለየት አይቻልም ።
ሁሉም ለኢትዮጵያ እንግዶችና መጤዎች የሚያስመስላቸውን እንግዳ ነገር ሲፈጽሙ ይስተዋላል ። ምንም እንኳ ገድልና ድርሳን ባይኖራቸውም አሁን ባሉት አገልጋዮቻቸው በእጅጉ ስለሚደገፉባቸው የተሳሳቱ መልእክቶችን ሊያስተናግዱ ይችላሉ የሚል የብዙ ሰዎች ስጋት አለ ።
ለምሳሌ ፦ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንዳንድ ትላልቅ የእግዚአብሔር ባሪያዎች የተጠሩበትን ስም በባለቤትነት መያዝ "የግዚአብሔር ሰው" እንዲባሉ መፍቀድና ከሌላው አማኝ ልዩነት ማሳየት ።
ሰውነታቸው ከሁሉም በላይ ወፍሮና ገዝፎ እየታየ እነሱ ግን ከሁሉ በላይ እንደሚጾሙና እንደሚጸልዩ ራሳቸውን መስበክ ቲፎዞ ማብዛት ።
መናፍስትን ከሰው ሲያስወጡ መንፈሱ ለእነሱ እውቅና እንዲሰጥ እድሉን ማመቻቸት ከዚያም ከሕዝቡ ሙገሳን ጭብጨባንና አድናቆትን መቀበል ።
የሚያሳፍረው ግን ሰይጣኑ ሲለቅ ሦስት ጊዜ ጮኸህ ውጣ እየተባለ መታዘዙ ነው "ዝም ብለህ ውጣ" መባል ሲገባው ብዙ ምሥክርነት እንዲሰጥና ሰው ሁሉ እንዲገረም ማድረግና አጋንንትን ለደቀ መዝሙርነት እንደመጠቀም ያስቆጥራል ።
ያልተፈወሱ ሰዎችን ተፈውሳችኋል በማለትና ሐኪም ያዘዘላቸውን መድኃኒት እንዲያቋርጡ በማድረግ ለበርካታ ሰዎች ሕልፈተ ሕይወት ምክንያት መሆናቸውና ይህም በሕግ ፊት ደርሶ እያነጋገረ መሆኑ በተጨማሪም የገንዘብ ብክነት ሁሉ ደርሷል መባሉና በጉዳዩ መንግሥት ጣልቃ እንዲገባበት መገደዱ ሌላው ፈተና ሆኗል ።
እንግዲህ በዚህ ሁሉ ፉክክር እያንዳንዱ ቤተ እምነት ለመተራረም ፈቃደኛ ባለመሆኑ አንዱ በአንዱ እየሳቀ እውነተኛ ፈውስም እየጠፋ ክርስቶስን ከሚያምነው ይልቅ የሚተወው እየበዛ መጥቷል።
አሕዛብን ዝም የሚያሰኝ በሁሉም ዘንድ መገረምን የሚያመጣ ዓይን ለሌለው ዓይን እግር ለሌለው እግር የሞተንና የተቀበረን ከሞት ማስነሣት የተካተተበት ፈውስ እንጂ ጨጓራና አንጀት ብቻ እየተባለ አገልግሎቱ ጥርጣሬ ላይ ይወድቃል እንጂ የትም አይደርስም ።
ስለዚህ በሁሉም ቤተ እምነት የሚከሰቱትን ችግሮች ማስተካከልና እንደ እግዚአብሔር ቃል ማስሄድ ቢቻል ማለፊያ ነው ።
እናንተስ ምን ታዘባችሁ ?