Tuesday, August 27, 2013

የማይቀረው ለውጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መጎብኘቱ አይቀርም!




ባልተዘጋጀችበትና በማትፈልገው ለውጥ የሚደርስባት ጉዳት ከባድ ነው!
ክፍል ሁለት / ነሐሴ 21/ 2005/

በክፍል አንድ ጽሁፋችን ስለለውጥና የለውጥ አስተሳሰብ ጥቂት ለማለት ሞክረን ነበር። ጊዜውን ጠብቆ በመጣው ለውጥ ሳቢያ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ስላቋቋመችው የለውጥ ማስታገሻ መንገድና ስለኢየሱሳውያን/ JESUIT/ አመሰራረት መንስዔም በመጠኑ አስቃኝተናል። ስለጀስዊትስ ዓላማና ግብ በዝርዝር እዚህ ላይ እንዳንሄድ የተነሳንበት ርእስ መሠረተ ሃሳብ ይገድበናልና ትተነዋል። አንባቢዎቻችን ተጨማሪ መረጃ ያገኙ ዘንድ በዚህ ሊንክ እንዲገቡ እንጠቁማለን።/http://www.biblebelievers.org.au/jesuits.htm የጀስዊትስ መመሥረት የአዲስ አስተሳሰብና የለውጥ እንቅስቃሴን ባያቆምም የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንን ከመፈራረስ በተወሰነ መልኩ አግዟታል። ወደማትፈልገውና ወዳላሳበችው የለውጥ መንገድ እንድትንሸራተት ያስገደዳት ሲሆን የነበራትን የሮማን ህግና ደንብ በየሀገራቱ ውስጥ ከመትከል ይልቅ የየሀገራቱን ባህልና ወግ ከካቶሊክ አመለካከት ጋር እያስማማች ለመጓዝ ረድቷታል። ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ አብዛኛው ሕዝብ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ እንደመሆኑ መጠን የኢትዮጵያ ካቶሊክም ኢትዮጵያዊ ካቶሊክ እንዲመስል እንጂ ቫቲካናዊ ካቶሊክ እንዲመስል ስለማይጠበቅበት ማንኛውም የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግልባጭ ነው። ታንዛንያ ስንሄድ ደግሞ ታንዛንያዊ ቋንቋ፤ ባህልና ወግን ይከተላል። ሌላ ቋንቋ፤ ባህልና ሥርዓት አምጥቶ ከመጫን ይልቅ ሕዝቡ በሚኖርበት ቋንቋ፤ ባህልና ሥርዓት ሲያስተምሩት ውጤታማ መሆኑ አይጠረጠርም። ሐዋርያው ጳውሎስም ያደረገው እንዲሁ ነበር። ያልተገረዘ ወደ መገረዝ አይሂድ ማለቱ ወንጌል ማለት አይሁዳዊውን ሥርዓት በሌላ ሕዝብ ላይ በመጫን የሚፈጸም እንዳልሆነ መግለጡ ነበር። እንኳን ግእዝን አማርኛን በውል ለማይሰማ ለሸኮ መዠንገር ሕዝብ ሄደህ የያሬድ የቅዳሴ ዜማ ነው ብለህ ብትጮህለት ለምሥጋናህ እንዴት አሜን ሊል ይችላል? ክርስትና የሰዎችን ቁጥር የማብዛት ጉዳይ ባይሆንም ወንጌል ያልደረሳቸውን ለማዳረስ ትክክለኛው መንገድ እኛ የምንኖርበትን ሥርዓትና ሕግ በማያውቀው ሌላ ሕዝብ ላይ የመጫን ጉዳይ ሳይሆን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕይወታችን መድኃኒት መሆኑን ከማስተማር ባለፈ አሳማ በመብላትና ባለመብላት የማትገኘውን የጽድቅ መንገድ በላተኛውን በመከልከል ሊሆን አይችልም።
በዚህ አንጻር የካቶሊክ ተገዳዳሪ ሆኖ ለመጣው አዲስ የፕሮቴስታንት ዓለም ያልተፈለገውን የለውጥ መንገድ ለመጀመር ምክንያት ሆኗል። በ 12ኛው ክ/ዘመን መገባደጃ ላይ ካቶሊክ የፈጠረችውን የመካነ ንሥሐ/ purgatory/ ጽንሰ ሃሳብ የግድ ህግ እንደሆነ ማስተማርን ለመተው ተገዳለች። ኃጥእ ሰው ንስሐ ሳይገባ ከሞተ፤ የንስሐ ቦታ በሰማይ አለው የሚለው ጸረ ወንጌል አስተሳሰብ በአዲስ ለውጥ እንቅስቃሴ ተቀባይነቱን አጥቷል። በእርግጥ ይህ አስተምህሮ ዛሬም ሳይጠፋ ተጠብቆ በሀገራችን ይገኛል።  መጽሐፈ ግንዘት «እምድኅረ ሞቱ ለሰብእ አልቦቱ ንስሐ» ሰው ከሞተ በኋላ የንስሐ ጊዜ የለውም» ቢልም ፍታትና ተስካር ንስሐ ሳይገባ የሞተውን ሰው ሥርየት ለማሰጠት የሚደረገው ሥርዓት አሁን ድረስ አለ። በካቶሊክ አስተምህሮ ላይ ከተነሳው የለውጥ ጥያቄ አንዱ ይህ ነበር።

Thursday, August 22, 2013

የማይቀረው ለውጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መጎብኘቱ አይቀርም!

ባልተዘጋጀችበትና በማትፈልገው ለውጥ የሚደርስባት ጉዳት ከባድ ነው!

ክፍል አንድ፤

ለውጥና የለውጥ አስተሳሰብ
ለውጥ የሂደት ውጤት ነው። ስለወደድነው አይመጣም፤ ስለጠላነው አይቀርም። አንዳንዶች ለውጥን ለማስቀረት ይታገላሉ፤ ወይም በእነሱ ትግል የሚቀር ይመስላቸዋል። የለውጥ ህግጋት ግን አይቀሬ መሆኑን ስለሚያሳይ ይዘገይ እንደሆን እንጂ ያ የተፈራው ለውጥ እንደሚሆን አድርገው ለመቀበል ካልፈለጉት እንደማይሆን ሆኖ ይመጣል። በዚህ ምድር ላይ ባለበት ችክ ብሎ የኖረ ነገር የለም። ድንጋይ እንኳን ተፈረካክሶ አፈር ይሆናል። ፀሐይም በጭለማ ትጋረዳለች። በጋም በክረምት ይቀየራል። ብሉይም በሐዲስ ተሽሯል። ከእስራኤል ዘሥጋ ይልቅ እስራኤል ዘነፍስ የጸጋ ፍሰት ደርሶታል።በመወለድና በመሞት፤በመምጣትና በመሄድ፤ በመፈጠርና በማለፍ መካከልም የለውጥ ሕግጋት አለ። እግዚአብሔር ነገሮችን በጊዜ ዑደት ውስጥ እንዲያልፉ አድርጎ ፈጠረ እንጂ ባለበት ቆሞ እንዲቀር ያደረገው አንዳች ነገር የለም። ሌላው ቀርቶ ያለንባት ሰማይና ምድር እንኳን በአዲስ ሰማይና ምድር ትለወጣለች። መቼም የማይለወጠው እግዚአብሔር ብቻ ነው። ዘመን የማይቆጠርለትና የማይለወጥ እሱ ብቻ ስለሆነ ነብዩ ዳዊት እንዲህ አለ።
«አንተ ግን ያው አንተ ነህ፥ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም» መዝ 102፤27      
  የሀገራችን ገበሬ ክረምት ከመድረሱ አስቀድሞ የወራቶችን ለውጥ አስልቶ ቅድመ ዝግጅት አድርጎ መጻዒውን ጊዜ ይጠባበቃል። ዘመኑን ጠብቆ በሚመላለሰው ለውጥ ውስጥ ራሱን አስማምቶና ውጤታማ ሆኖ እንዲቀጥል ለማድረግ ቅድመ ዝግጅቱን በየተራ ካልፈጸመ በስተቀር የበጋው በክረምት መለወጥ በራሱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖውን አሳርፎ ያልፋል።    በሰለጠነው  ዓለም ያሉ ምሁራን በማይቀረው የለውጥ ሂደት የተነሳ ስለለውጥ ያላቸው ግንዛቤ ትልቅ ስለሆነ ሥራቸውን ከለውጥ ጠቀሜታና ተግዳሮት አንጻር ቅድመ ምልከታ በማድረግ ለምላሹ አስቀድመው ይዘጋጃሉ።                                                                                                                                    
 

Thursday, August 15, 2013

ለአቡነ ገብርኤል ጥሪ የሀዋሳ ምእመናንና የሰ/ት/ቤት ወጣቶች ምላሽ ሰጡ!

«እስከ ጥቁር ዉሃ ሄዶ የተቀበለ  ሕዝብ እስከ ጥቁር ውሃ ተሰደደ» (ደጀ ብርሃን)

 /ምንጭ፦dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com/
 በሀዋሳ በግፍ የተሰደዱት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ብፁዕ አቡነ ገብርኤል "ኑ ልጆቼ ወደ ቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ተመለሱ" ሲሉ ላደረጉት ጥሪ ምላሽ መስጠታቸውን ከስፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ ምዕመናኑ ለአቡነ ገብርኤል በአድራሻ፣ ለ17 የቤተክርስቲያንና መንግሥታዊ ተቋማት ደግሞ በግልባጭ ያሠራጩትን ደብዳቤ በብሎጋችን ፖስት እንድናደርግላቸው ለዝግጅት ክፍላችን በኢሜይል ልከውልናል፡፡ የደብዳቤው ሙሉ ይዘት የሚከተለውን ይመስላል፡፡
ነሐሴ 7 ቀን 2005 ዓ.ም
ለብፁዕ አቡነ ገብርኤል
የሲዳማ፣ ጌዴኦ፣ አማሮና ቡርጂ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ
ሀዋሳ፣
ጉዳዩ: ̶  "ወደ ቤተክርስቲያን እንድትመለሱ" በማለት ለተጻፈልን ደብዳቤ ምላሽ ስለመስጠት
በቀን 25/1/171/2005 (ቀኑን ከደብዳቤው ላይ ማየት እንደሚቻለው) በቁጥር 1459/171/2005 የተጻፈ ደብዳቤ ሐምሌ 25 ቀን 2005 ዓ.ም ከምሽቱ 1፡30 ሰዓት በሁለት ፖሊሶች እጅ ተልኮልን ወንጌል ከምንማርበት ሥፍራ ተጠርተን መተማመኛ ፈርመን በመቀበል በአንክሮ ተመልክተነዋል፡፡ ቀጥሎም ለምዕመናን ተነቦ ውይይት ከተደረገበት በኋላ የጋራ አቋም የተወሰደበት ሲሆን፣ ጥሪ ማድረግዎን በስምንቱም አጥቢያ ቤተክርስቲያናት ዐውደ ምሕረቶች እንዲነበብ እንዳደረጉት ሁሉ ይህንን የምላሽ ደብዳቤያችንንም  ለሰፊው ምዕመን በተመሳሳይ ሁኔታ እንዲያስነብቡልን አደራ እንላለን፡፡ የሰጠነውም ምላሽ የሚከተለው ነው፡፡ 
አንደኛ፣ ደብዳቤውን እንደ ወንጀል ክስ መጥሪያ በፖሊስ እጅ መላኩ እና ከመደበኛ የሥራ ሰዓት ውጪ ከምሽቱ 1፡30 ከሆነ በኋላ መምጣቱ፣ እንዲሁም መተማመኛ ፈርመን እንድንቀበል መደረጉ ከሕግ አንፃር ተገቢ ካለመሆኑም በላይ የጥሪው አካሄድ የፍቅር እንዳልሆነ ተገንዝበናል፡፡ በተጨማሪም ደብዳቤው ቅንነትና እውነት ያለበት ሳይሆን ማስመሰልና ውሸት የተሞላበት ከመሆኑም በላይ እርቅ፣ ሠላምና አንድነትን ከማምጣት ይልቅ ራስን ከሕዝብ (ከታሪክ) ፍርድ ለመከላከልና ለገጽታ ግንባታ (ፕሮፖጋንዳ ፍጆታ) ሲባል ብቻ የተዘጋጀ መሆኑን ተረድተናል፡፡
በደብዳቤው ውስጥ "የተወደዳችሁ ልጆቻችን ምዕመናንና ወጣቶች" የሚል ሐረግ ተደጋግሞ ይታያል፡፡ ልጆቻችሁ እንደሆንን ሲነግሩን ከእርስዎ ሳይሆን ከሌላ አካል የሰማነው ያህል መስሎ ነው የተሰማን፡፡ ምክንያቱም እኛ ልጆችዎ እንደሆንን ባንክድም ከእርስዎ ዘንድ ግን የአባትነት ወግ ፈጽሞ አይተን ስለማናውቅ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የደብዳቤውን ይዘት ስንመረምረው የተረዳነው ነገር ቢኖር ̶ አንዳንዴ በግልጽ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ በስውር በሀገረ ስብከታችን የሚካሄዱትን ሕገወጥ ሥራዎች ለመሸፋፈንና "ለምን አሳደዳችኋቸው? ለምን አትመልሷቸውም"? ብሎ ለሚጠይቃችሁ አካል "ይኸው፣ በደብዳቤ ጠርተናቸውም እምቢ ብለውናል" በማለት በብልጣብልጥ አካሄድ ሪከርድ ለማስያዝ እና ወደፊት ለምታደርጉት የተለመደ እንቅስቃሴ ምክንያት ለማመቻቸት መሆኑን ለማወቅ ልዩ ጥበብ አያስፈልገውም፡፡
ጥሪዎ ቅንነት ቢኖረው ኖሮና እኛን "ልጆቻችን" እንዳሉን ሁሉ እርስዎም አባትነትዎን አምነውበት ቢሆን በአባትና በልጅ መካከል አለመግባባት ተፈጥሮ ልጅ ቤቱን ለቆ ቢኮበልልና አባትም በበኩሉ የኮበለለው ልጅ ወደ ቤቱ እንዲመለስ ቢፈልግ ደብዳቤ ጽፎ በፖሊስ በኩል መላክ ትክክለኛው መንገድ አለመሆኑን ለእርስዎ መንገር ለእናት ምጥ እንደማስተማር ይቆጠራል፡፡
በተጨማሪም፣ ከቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ተባርረን ከወጣን ሁለት ዓመታት እስኪቆጠሩ ድረስ ከሀገረ ስብከቱ ውጪ ያሉ ካህናትና አገልጋዮች መጥተው ሲባርኩንና ሲያፅናኑን እርስዎና ከእርስዎ ሥር ያሉ አባቶች ግን የጠፉትን በጎች ፍለጋ ሳትወጡ ኖራችሁ፣ ዛሬ ከረፈደና ከመሸ፣ ጉዳዩም ከእጃችሁ ወጥቶ በጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤትና በቅዱስ ሲኖዶስ ከተያዘ በኋላ ድንገት ይህንን ኦፊሴላዊ ጥሪ ለማድረግ የተገደዳችሁበትን ሚስጥር ስናሸተው ጠረኑ የሚነግረን ሌላ ጉዳይ መሆኑን ነው፡፡ ደብዳቤው ሆን ተብሎ እውነታውን ለማዛባት የተደረጉ ጥረቶች እንዳሉበት ከማሳየቱም በላይ "እንዳያማህ ጥራው፤ እንዳይበላ ግፋው" እንደሚባለው ለይተበሀል ያህል ብቻ የተጻፈ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡
ሁለተኛ፣ በደብዳቤው የመጀመሪያ መሥመር ላይ፣ "ከቤተክርስቲያን ተባረናል በሚል . . .  እየተሰባሰባችሁ የምትገኙ ልጆቻችን ምዕመናንና ወጣቶች . . . " የሚል ሐረግ ሰፍሯል፡፡ ይህ የሚያሳየን እኛ ተባረናል እንላለን እንጂ እናንተ ማባረራችሁን አምናችሁ ለመቀበል እንደማትፈልጉና ዛሬም እንኳን ፀፀት እንዳልተሰማችሁ ያመለክታል፡፡  ታዲያ ከእናት ቤተክርስቲያናችን ውጪ ለመገኘታችን ምክንያቱ እርስዎ፣ የእርስዎ አስተዳደር እና እርስዎ ያደራጁት ማኅበር ካልሆነ፣ ቤተክርስቲያንና ቅጥሯ አስጠልቶን አካባቢ ለመለወጥና ለሽርሽር የሄድን መስሎዎት ይሆንን? ይሁን እንጂ እንዳባረራችሁን መላው የሀዋሳ ምዕመናን ምሥክር ናቸው፡፡