Tuesday, July 3, 2012

ትውልድ ያላወቀው ኢትዮጵያዊው ሰው!



ብዙዎቻችን ኢትዮጵያዊ መሆን ማለት ኢትዮጵያ ውስጥ መወለድ ብቻ አድርገን እንቆጥራለን። ያ ግን ከእውነታው ብዙ የራቀ አስተሳሰብ ነው። በምንም መመዘኛ ኢትዮጵያ ውስጥ መወለድና ኢትዮጵያ ዜጋ መያዝ ማለት ኢትዮጵያዊ ማለት አይደለም የሚል አቋም አለኝ። ምክንያቱም ኢትዮጵያዊ ማለት በኑሮው፤ በባህሉ፤ በወጉ፤ በቋንቋው፤ በእምነቱ፤ በታሪኩ፤ በድርጊቱ ሁሉ ኢትዮጵያዊ ሆኖ መገኘት ነውና። ባህሉን፤ አኗኗሩን፤ ወጉን፤ ቋንቋውን ታሪኩንና እምነቱን፤ትውፊቱን ሁሉ ከኢትዮጵያዊነት አተያይ ውጪ ያደረገ ትውልድ እንደ ሸቀጥ /Made in………/ ተብሎ ኑረቱ የሚገለጽበትን የባእድ ሀገር የማንነት ስያሜ ይሰጠዋል እንጂ ኢትዮጵያዊ ሰው ሊባል የተገባው አይደለም። ኢትዮጵያዊ ሆኖ ከመኖር ውጪ ኢትዮጵያዊነት ሊኖር አይችልምና። ያ ማለት ግን ከሌላው ዓለም ሚዛን ጋር ራሱን እየጠበቀ፤ የጎደለውን እየሞላ፤ የጎዳውን እያረመ አይሄድም ማለት ሳይሆን ማንነቱን በሌሎች ማንነት ውስጥ በመለወጥ፤ በመተካት ወይም በመደረት  ኢትዮጵያዊ መባል እንዳይቻል  ለማሳየት ተፈልጎ ነው።

ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የተጻፉ ሰፋፊ ጥናቶች እንደተጠበቁ ሆነው በዚህ ጽሁፍ ለመዳሰስ የተፈለገው በርእሱ ላይ የተጠቀሰውን «ትውልድ ያላወቀው ኢትዮጵያዊውን ሰው» በተመለከተ በአጭር ምልከታ ለማብራራት ነው።
«ትውልድ ያላወቀው ኢትዮጵያዊ ሰው» በብዙዎች ዘንድ መምሩ/መምሬ/ ወይም ቄስ ተብሎ በማእረገ ክህነቱ የሚጠራው የኢትዮጵያው የገጠር ቤተክርስቲያን አገልጋይ /ካህን/ ነው። በእርግጥ ዘመኑ መምሩ/ መምሬ/ ወይም ቄስ የሚለውን ስመ ተጸውኦ ሲያዘምነው በከተሜው ዘንድ «ቀሲስ» መባሉ ቢታወቅም ያ የገጠሩ ቄስ/ መምሩ/፤ ከዚህ እንግዳ የዝመና ጥሪ ጋር ብዙም ትውውቅ ስለሌለው ያችን ከምንም በላይ የሚያከብራትን፤ የሚወዳትንና የሚጠብቃትን የ«መምሬ» እገሌን ጥሪ እስከዛሬ ሳይለቅ እንደያዘ ይገኛል። ቄስ እገሌ ወይም መምሬ እገሌ ተብሎ መጠራታቸው ለእነርሱ ኩራታቸውና ክብራቸው  ስለመሆኑ በቅርብ የምናውቃቸው ዘመዶቻችን እንደሚናገሩ  ለዚህ ዋቢዎች ነን።


እነ መምሩ/መምህሩ/ የሚከበሩትና  የሚወደዱት ገጠር ስለኖሩ ሳይሆን ለነግህ ኪዳን፣ ለሰርክ ጸሎት የሚተጉ ከመሆናቸው ባሻገር እንደ ተራው ህዝብ ኑረትን ኖረው፤አርሰው ቆፍረውና ጎልጉለው የሚተዳደሩ፤ የተጣሉትን አስታርቀው፤ የታመሙትን ጠይቀው፤ በቤታቸው፤ በጎረቤታቸውና በአካባቢያቸው ፈሪሃ እግዚአብሔርን ኖረውትና አስተምረው፤ ሕዝቡ በግብረ ገብነትና በመከባበር ማኅበራዊ ኑሮውን በኅሊና ዳኝነት እንዲገፋ በማድረግ ከማንም በላይ ኢትዮጵያዊነት የሚታይባቸው የሕብረተሰብእ አንጓዎች በመሆናቸው ነው።
እነመምሩ በቀደሙት ዘመናት ከቤተክርስቲያን የምትሰጣቸውን 10 ብርና 20 ብር ወይም በቁና የምትሰፈርላቸውን የእህል  የድርጎ መዋጮ እንደክፍያ ቆጥረው ሳይሆን ኃላፊነትና ግዴታቸውን አውቀው በማኅሌቱ፤ በሰዓታቱ ቆመው ሲያድሩ ብርታታቸውና ጥንካሬአቸው በእውነቱ ያስገርማል። የሀገር ዳኛ ሳለ እነመምሩ የምእመናን ዳኛ ናቸው። ቃላቸው ይፈራል፤ ይከበራል። ምክራቸውና ተግሳጻቸው በሁሉም ዘንድ ቅቡል ነው።

Sunday, July 1, 2012

አፄ ዓምደ ጽዮንና የኢትዮጵያ አንድነት

ፀሐፊ፤ ሔኖክ ጌትነት

አፄ ዓምደ ጽዮን ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ

ግዛት      ከ1314-1344 ፤  ቀዳሚ ንጉሥ  አፄ ውድም አርእድ(አባት)
ተከታይ ንጉሥ፤  አፄ ነዋየ ክርስቶስ/ ሰይፈ አርእድ ልጅ/
ባለቤት ብሌን  ሳባ/ የባሕረ ነጋሲ ንግሥት/
ሙሉ ስም፤  ገብረ መስቀል
ሥርወ-መንግሥት፤   ሰሎሞናዊ
አባት ፤     ውድም አርእድ
ሀይማኖት  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና
ቀዳማዊ አጼ ዐምደ፡ጽዮን (የዙፋን ስም ገብረ መስቀል) ከ1314 እስከ 1344 ዓ.ም. የነገሡ ሲሆን በጥንቱ ዘመን ከተነሱ ነገሥታት ውስጥ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ሰፋ ያለ አሻራ ትተው ካለፉት (ለምሳሌ፦ ዘርአ ያዕቆብ ) ጎን ወይም በላይ ስማቸው ይጠቀሳል። አጼ ዐምደ ጽዮን የአጼ ይኩኖ አምላክ የልጅ ልጅና የአጼ ውድም አርእድ ልጅ እንደሆኑ ይታመናል፡፡ ይኩኖ አምላክ አዲሱን የሰሎሞን ስርወ መንግስት ቢመሰርቱም፣ በልጅ ልጆቻቸው የነበረው ፉክክርና አዲስ ከሚስፋፋው የእስልምና ሃይማኖት የሚሰነዘረው ጥቃት ስርዓቱን ስጋት ላይ የጣለ ነበር። አጼ አምደ ጽዮን ይህን ፉክክር በማስቆምና በዘመናት በማይደበዝዘው ጀግንነታቸው የኢትዮጵያን ድንበር ከሞላ ጎደል አሁን በሚታወቀው መልኩ በማስቀመጥ፣ የአዲሱን ስርወ መንግስት መሰረት በማጽናት እንዲሁም በማረጋጋት ዝናቸው በጥንቱ አለም ክአፍሪቃ ቀንድ እስከ አውሮጳ የተንሰራፋ ነበር።
1/ የአጼ ዐምደ ጽዮን ዘመንና ዘመቻዎች
ዘመቻ ወደ ደቡብ ምዕራብና ሰሜን ኢትዮጵያ
ዓምደ ጽዮን በእንዴት መንገድ ወደ ስልጣን እንደመጡ መረጃ የለም፣ ስለሆነም ታሪክ አጥኝው ታደሰ ታምራት ንጉሱ ከአባታቸው ጋር ትግል ገጥመው ዘውድ ላይ እንደወጡ መላ ምት ያቀርባል ። ንጉሱ በመንግስታቸው መጀመሪያ (፲፫፻፲፮ ዓ.ም. ) የተሳካላቸው ዘመቻዎች በጎጃም፣ ዳሞትና ሐድያ በማድረግ እኒህ አካባቢወች እንዲገብሩ ሆነ[5]። ሆኖም በኒህ ዘመቻወች ትኩረታቸው ስለተሳበ በተገኘው ክፍተት የእንደርታ ገዢ የነበረው ይብቃ እግዚ የአምባ ሰናይት፣ ብልሃትንና ተምቤን ሰራዊትን በማደራጀት በንጉሱ ላይ ተነሳ ። በ1320ዓ.ም ንጉሱ የይብቃ እግዚን አመጽ ከደመሰሱ በኋላ በአምባ ሰናይት የጦር ዕዝ አቋቋመው ወደ ስሜን በመዝመት እስከ ቀይ ባህር ድረስ ያለውን ክፍል ለመቆጣጠር ቻሉ። በዚህ ወቅት እንደርታን እንድታስተዳድር የተሰየመችው የትግሬ ተወላጅ የነበረችው የንጉሱ ሚስት ንግስት ብሌን ሳባ ነበረች። ስልጣኗም ባልታ ብሃት በመባል ይታወቅ ነበር። ቆይቶ እንደርታን እንዲያስተዳድር የተደረገው የንጉሱ ሦሥተኛ ልጅ ባህር አሰገድ በማዕከለ ባህር ማእረግ ነበር፣ ግዛቱም እስከ ቀይ ባህር ወደብ ድረስ የተንሰራፋ ነበር ።

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዲን፤ ተመራቂ ተማሪዎችን ማደሪያ ከለከሉ!

             
   የጽሑፍ ምንጭ፤ ዓውደ ምሕረት

በቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዲን ከመመደባቸው በፊት ተማሪዎች ግቢውን መልቀቅ የለባቸውም የሚለውን መመሪያ ጥሰው ተማሪዎቹን ከግቢ አስወጡ፡፡ መነኮሳትን ጨምሮ አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ማደሪያ አጥተው እየተንከራተቱ ይገኛሉ፡፡ እስከአሁን ደረስ ባለው ሕግ መሰረት ተመራቂ ተማሪዎች ምደባ እስኪደረግላቸው ድረስ በኮሌጁ ውስጥ ማደር መብታቸው ነበር።ተማሪዎቹ ችግራቸውን ለቅዱስ ፓትርያርኩ ያስረዱ መሆናቸው ሲታወቅ እሳቸውም የኮሌጁ የበላይ ጠባቂ እንደመሆናቸው በቤታችሁ ማደር መብታችሁ ነው፡፡ መመሪያውን ማፍረስም አይቻልም ስለዚህ ሂዱ እቤታችሁ እደሩ ብለው ቢያዙም የኮሌጁ ዲን ግን ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡
   በርካታ መነኮሳት ያሉበት ተማሪች ማደሪያ አጥተው እየተንገላቱ መሆኑ የኮሌጁን ማህበረሰብ ጨምሮ በርካቶችን ያሳዘነ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ባለፈው ሐሙስ ምደባ እንደሚደረግ ተነግሮ የነበረ ቢሆንም በተለያዩ ምክንያቶች ምደባው ለማክሰኞ መዞሩ በጠቅላይ ቤተክህንት ምክትል ሥራ አስኪያጅ በኩል ተነግሮዋቸዋል፡፡
ነገሩ ግራ የገባቸው ተማሪዎች መብታችን ተነክቷል በማለት ለፖሊስ ጣቢያ ያመለከቱ ሲሆን ፖሊሶች ችግሩን መፍታት ከተቻለ ብለው አቡነ ጢሞቲዎስን ለማነጋገር ቢሞክሩም አቡኑ ግን ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡
የኮሌጁ የአስተዳደር ዲን / አባ ሃይለ ማርያምን ችግሩ መፍትሔ ሊያገኝ የሚችልበትን መንገድ ካለ እንዲፈልጉ እንደ አስተዳደር ዲንነታቸውም አንድ ነገር ማድረግ የሚችሉ እንደሆነ ተጠይቀው የነበረ ሲሆን እሳቸውም ከአባ ጢሞቲዎስ ያልተሻለ ምላሽ ሰጥተዋል።መምህራንና  ሌሎች የኮሌጁ ሰራተኞች ከተማሪዎች ጎን ቢቆሙም አቡነ ጢሞቴውና አባ ሃይለማርያም ስላልተስማሙ ግን ተማሪዎቹ ማደሪያ በማጣት በመንገላታት ላይ ይገኛሉ።
ምክንያቱ ይህ ነው ብለው ባልጸገለጹበት ሁኔታ መመሪያንን ሸሮ ቤተክርስቲያን ባሳደገቻቸው ልጆችዋ ላይ ይህን ያህል መጨከንዋ አሳዛኝ መሆኑን ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡