Wednesday, October 5, 2011

መላእክት የሚወጡበትና የሚወርዱበት የሰማይ መሰላል
















"አሁንም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:-


ልባችሁን በመንገዳችሁ ላይ አድርጉ::" ሐጌ 1፣5


የእግዚአብሔር ቃል ልባችንን በመንገዳችን ላይ እንድናደርግ ይመክረናል:: በምን አይነት መንገድ ላይ እየተጓዝን እንዳለን ልንመረምር ይገባናል:: ከሁሉም በላይ መንገዱ ወዴት እንደሚወስድና እንደሚያመራ በትክክል ማወቅ አለብን:: በምድር ላይ ብዙ መንገዶች አሉ፣ ሁሉም ግን ያሰብነው ስፍራ አያደርሱንም:: ስለዚህ ትክክለኛውን መንገድ መምረጥና መጓዝ ከዚያም ልባችንን በመንገዳችን ላይ አድርገን መመርመር ይገባናል::

ዛሬ ብዙ ሰዎች በመኪናቸው ወዴት እንደሚሄዱ ያውቃሉ፣ የተሳፈሩትም አውቶቡስ የት እንደሚያደርሳቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ፣ እንዲያውም አንዳንድ ሰዎች እጅግ የሚያስገርም የመንገድ እውቀት አላቸው:: ነገር ግን ብዙዎቹ የሕይወታቸው ጉዞ ወዴት እንደሚያደርሳቸው አያውቁም:: የመረጡት ሕይወት መጨረሻው ምን እንደሆነ እርግጠኞች አይደሉም:: የተሳሳተ መንገድ ላይ ይሁኑ አይሁኑ የሕይወታቸውን መንገድ የማይመረምሩ ጥቂቶች አይደሉም::

ወገኔ ሆይ፣ ወዴት እየሄድክ ነው? ይህ አኗኗርህ ወዴት ያደርስሃል? ትክክል ነው ብለህ የምትከተለው ሕይወትህና ሃይማኖትህ መጨረሻው ምንድነው? የተሳፈርክበት የሕይወትህ አውቶቡስ ወዴት እንደሚወስድህ በእርግጥ ታውቅ ይሆን? ወይስ ወዴት እየሄድክ እንደሆነ ቆም ብለህ አትመረምር ይሆን? ምናልባትም የትኛውንም መንገድ ብመርጥ ግድ የለም ትል ይሆናል:: የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ሲል ይመክረናል:-
"ልባችሁን በመንገዳችሁ ላይ አድርጉ"!

Tuesday, October 4, 2011

መጥተህ እይ


አንድ ጊዜ ኢየሱስን ሊሰሙትና ከእርሱ ሊማሩ፣ ከበሽታቸውና ካለባቸው ስቃይ ሁሉ ነፃ ሊወጡ ወደ እርሱ ብዙ ሕዝብ ይቀርቡ ነበር:: ከእነዚህም ውስጥ የታወቁ ኃጢአተኞች ይገኙበት ነበር:: ጌታም እነዚህን ሲቀበላቸው፣ ከእነርሱም ጋር ሲበላና ሲጠጣ የዚያን ዘመን የሃይማኖት ሰዎች አይተው እርስ በርሳቸው አንገራገሩ "ይህስ ኃጢአተኞችን ይቀበላል፣ ከእነርሱም ጋር ይበላል" አሉ:: ሉቃ 15፣1-2 እስከ ዛሬ ድረስም የተለያዩ የሃይማኖት ተከታዮችን ወይም ሃይማኖተኞችን ግራ የሚያጋባቸውና የሚገርማቸው አንዱ ነገር ይሄ ነው:: እንዴት ታላቅ ነብይ በኃጢአተኞች መካከል ይቀመጣል? እንዴት የእግዚአብሔር ልጅ በተናቁ መካከል ያስተምራል? እንዴት ጻድቅ የሆነው ኢየሱስ ከኃጢአተኞች ጋር ይበላል? እንዴትስ ከእነርሱ ጋር ይጠጣል? ይሄ ነው እንግዲህ በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጸውን አምላክ ከሌሎች አማልክቶች የሚለየው:: ለሰው አዕምሮ ከባድ የሆነውና ሊቀበለው የሚያስቸግረው፣ ዮሐንስም ደግሞ ሊገልጽልን የሚፈልገው ትልቅ ቁም ነገር ይህ ነው::
"ቃልም ሥጋ ሆነ ጸጋንና እውነትንም ተሞልቶ በእኛ አደረ፣ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነውን ክብሩን
 አየን::" ዮሐ 1፣14

እጅግ የሚገርመው ነገር ቃል ከሁሉ በፊት ከእግዚአብሔር ጋር መኖሩና ሁሉ ነገር በእርሱ መፈጠሩ ብቻ አይደለም:: በጣም የሚያስደንቀው፣ ለብዙ የሃይማኖት ሰዎችም ግራ የሚያጋባውና ለመረዳት የሚከብደው፣ ይህ ራሱ አምላክ የሆነው ቃል (ኢየሱስ ክርስቶስ) ሥጋ መሆኑ ነው:: አምላክ እንዴት ሰው ይሆናል? እንዴት ሥጋ ይሆናል? እንዴትስ በኃጢአተኞች መካከል ይመላለሳል? የእግዚአብሔርን ፍቅር የተለየና ከመታወቅም በላይ የሚያደርገው አንዱ ነገር እንግዲህ ይህ ነው::



«ሲያያት በሕይወት ይኖራል»








ወገኔ ሆይ፣ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ:- ታምመህ ታውቃለህ? በእርግጥ የበሽታን ምንነት በሕይወትህ ቀምሰህ ይሆን? መልስህ አዎን እንደሚሆን እገምታለሁ:: በሽታን የማታውቅ ከሆንክ ደግሞ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን:: በሽታ መልካም አይደለምና:: የሰውን ሙሉ ጤንነት እያናጋ፣ ሰዎች እንደሚገባው እንዳይኖሩና እንዳይሠሩ የሚያደርግ ትልቅ እንቅፋት ነው:: ብርታትን ወደ ድካም፣ ውፍረትን ወደ ክሳት፣ ደስታንም ወደ ሃዘን የሚለውጥ በመጨረሻም ለሞት የሚያበቃ ክፉ የሰዎች ጠላት ነውና::

በአሁኑ ዘመን ግን ለብዙ በሽታዎች መድኃኒት ስላለ እግዚአብሔር ይመስገን:: ያለ መድኃኒት እንዴት እንሆን ነበር? ያለ መድኃኒትና ያለ እርዳታ እናቶች የልጆቻቸውን በሽታና ስቃይ እየተመለከቱ እንዴት ይሆኑ ነበር? የምንወዳቸው ወገኖቻችን በትንሹም በትልቁም በሽታ ሲሰቃዩና ሲረግፉ ማየት እንዴት ያሰቅቃል:: ዛሬም መድኃኒትና ሕክምና በሌለባቸው ቦታዎች፣ ሕጻናት ገና በለጋ እድሜያቸው በበሽታ ይቀጫሉ:: ሕክምናና መድኃኒት ባለማግኘት ሕይወታቸው የሚያልፈው የወጣቶችና የጎልማሶች ቁጥር ጥቂት አይደለም::


ሕክምና ባለበት አካባቢ ግን የሰዎች እድሜ የረዘመና ሽማግሌዎችና አዛውንት የበዙበት ይሆናል:: ሕጻናት በጤንነት ሲጫወቱና ሲቦርቁ ማየት እንዴት ደስ ይላል:: ሰዎች ያለ ስቃይ ሲወጡና ሲገቡ በደስታም ሲመላለሱ ማየት እንዴት መልካም ነገር ነው::