Tuesday, April 22, 2025

“እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” ቆላስ 1፥13-14

"ለእኔ ኃጢአት ሥርየት ከሞተልኝ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ ቤዛ የለኝም" “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” — ቆላስይስ 1፥13-14 ቤዛ የሚለውን ቃል አባ ገብርኤል የተባሉ ሊቀጳጳስ ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ብለው ለምን ተናገሩ? የሚል ንትርክ ተነስቶ በኦርቶዶክሶች መንደር ጩኸቱ በርክቷል። ይሄ ቤዛ በእንግሊዝኛው/ransom,redemption,deliverer/ በማለት ሲተረጉመው ግሪኩ ደግሞ (λύτρον)ሉትሮን ማለት የተከፈለ ዋጋ፣ (λύτρωσις) ሉትሮሲስ ነፃ መውጣት፣ ከእስራት፣ ከባርነት ለመፈታት የተሰጠ ክፍያ፣ ነጻነት ማለት ነው። የጌታችን፣ የመድኃኒታችንና የአምላካችን ቤዛነት ከየትኛው ምትክነት፣ ነጻ አውጪነት፣ አዳኝነትና ከሞት ታዳጊነት ጋር ለንጽጽር የሚቀርብ አይደለም። በዘመነ ኦሪት በባርነት የተሸጠ ሰው ለባርነቱ ዋጋ የሚከፍል ከተገኘ ነጻ ሊወጣ ይችላል። ለሰው ነፍስ ቤዛው ሀብቱ ነው። ምሳሌ13፣8 የመሳሰሉ ስለቤዛ የተነገሩ የቤዛ ቃል ንግግሮች በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ ተፅፈው እናገኛለን። እነዚህ ሁሉ የቤዛነት ትርጉሞች ኢየሱስ ክርስቶስ ካደረገልን ቤዛነት ጋር ለክርክርም፣ ለንጽጽርም፣ ለትርጉም አቻነት የሚቀርቡ አይደለም። የኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ከዘላለማዊ ድኅነት፣ ከአብ ጋር እርቅ የተደረገበት፣ መርገመ አዳም የተወገደበት፣ የገነት በር የተከፈበት ስለሆነ ከሰማይ በታች የተነገሩ፣ የተጻፉ፣ የተወሩ ስለቤዛ የተተረጎሙ ቃላት፣ ሃሳቦች ለንጽጽር ሊቀርቡ አይችሉም። በእውቀት ለመገራትና ለመመራት እምቢተኛ አእዱገ ገዳም የሆኑ የኦርቶዶክሶች ምእመናን፣ በተረት ተረት ትምህርት ሊቅ የሆኑት ዘበነ ለማ፣ አዋቂ መስሎ ለመታየት ብዙ የሚደክመው ኄኖክ ኃይሌ፣ ክንድ ከስንዘር መስቀል ጨብጠውና አንጠልጥለው ብዙ የሚያጓሩ፣ የተለሰኑ መቃብር መምህራን፣ ቀሳውስትና መነኮሳት ነን ባዮች የጌታችን፣ የመድኃኒታችንና የአምላካችንን ቤዛነትን ከሌሎች ቤዛነት ጋር ለማነጻጸር ወይም ስለቤዛነት የተነገረው ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ አይደለም ለማለት ከሰሜን ዋልታ እስከ አንታርክቲካ ሮጠው ያልቆፈሩት ጥቅስ፣ ያልዘበዘቡት ፅሑፍ፣ ያልተረተሩት ትርጉም፣ በእልህና ብስጭት መንጋጋቸው በመንጋ ያላፋጩት ጥርስ የለም። በየፌስቡኩ፣ ቲክቶኩና በየድረገጾቹ ላይ የታየው ጩኸት ተአምር የሚያስብል ነው። እነዚህ ስብስቦች ከኛ ወዲያ እውቀት ላሳር ነው ብለው የአእምሮአቸውን በር የዘጉት ድሮ ነው። ከእነዚህ ሰዎች ጋር ተነጋግሮ መተማመን ላይ መድረስ አይቻልም። አንዳንዴማ ከእኛ በስተቀር የሚጸድቅ የለም ብለው በድፍረት ሲናገሩ መንግሥተ ሰማያት በር ላይ ቆመው አንተ ተመለስ፣ አንተ ግባ ብለው የማዘዝ ስልጣን ያላቸው ያህል ያስባሉ። መንግሥተ ሰማያት የፍትሐት ድግስ የሚበሉበት የደጀሰላም በር ይመስላቸዋል። ለነገሩ አይሁድ ፈሪሳውያን መምህራንና ጻፎችም እንደዚሁ ያደርጋቸው ነበር። እነዚህን መሰል ሰዎች ጌታ በአንድ ወቅት እንዲህ ሲላቸው እናገኛለን። (ማቴ23፣27-32) እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ፥ ወዮላችሁ። እንዲሁ እናንተ ደግሞ በውጭ ለሰው እንደ ጻድቃን ትታያላችሁ፥ በውስጣችሁ ግን ግብዝነትና ዓመፀኝነት ሞልቶባችኋል። ብሏቸው ነበር። እነዚህኞቹ ወደመንግሥተ ሰማይ ወይ እነሱ አይገቡ፣ ወይ ተከታዮቻቸውን አያስገቡ መንገዱን በተረትና እንቆቅልሽ ስብከት ዘግተውታል። በዚያ ላይ እውቀት አለርጂክ የሆነበት ተከታያቸው ምዕመን በጩኸት ስለሚያጅባቸውና አዋቂ ነን ብለው ስለደመደሙ ከእነሱ የተለየውን ቃል እውነት ቢሆን እንኳን አይቀበሉም። ምእመኖቻቸውም ከመምህራኖቻቸው የባሱ ስለሆኑ ያንኑ የአለቆቻቸውን ትምህርት መልሰው ይጓራሉ። ይጮሃሉ። ማርያም ቤዛ ናት፣ ገብርኤል ቤዛ ነው። ገንዘብ ቤዛ ነው። ወንድምህ ቤዛ ነው፣ ጓደኛህ ቤዛ ነው የሚሉ ቃላትን ለቃቅመው በማምጣት ከኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ጋር ለንጽጽር፣ ለትርጉምና ለማብራሪያ በማቅረብ ይንጫጫሉ። አንዳንዴ ስትመለከታቸው ክርስቲያን የሚለውን መጠሪያ አምኖ ለመቀበል እስኪከብድህ ድረስ አንደበታቸውና ጽሑፋቸው ልቅ ነው። እነዚህ ተጯጯኺዎች በዘመቻ የተነሱት የቤተክርስቲያኒቱ ጳጳስ አባ ገብርኤል የተባሉት ሰው "ተቀዳሚ፣ ተከታይ የሌለው፣ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻውን የዘላለም ቤዛ ነው" ብለው ስላስተማሩና ማርያምም የዘላለም ቤዛችን አይደለችም ስላሉ ነበር። የዚህን ትምህርት ቃል ለማፍረስና ሌሎችም ቤዛ አሉን ለማለት ያልቆፈሩት የሙግት ትርጉምና ጥቅስ የለም። ዘቤ የተረት አባት በአንድ ወቅት "ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም" ብሎ ሲያስተምር ነበር። ማርያም ማዳን ከቻለች የኢየሱስ ሰው ሆኖ መምጣት ሳያስፈልግ በማርያም ይፈጸም አልነበረም ወይ? ተብሎ ሲጠየቅ እነዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም ማለት ስህተት ነው ብለው ለማረም ቢሞክሩም ዘቤ የተረት አባት ስህተቱን ሳያምን ዛሬም በተመሳሳይ ስህተት ላይ ይገኛል። ዘበነ ለማን ያክል ቤተክርስቲያኒቱን በአስተምህሮ ስህተት የገደለ ማንም የለም። እነኄኖክ ኃይሌ ላይገባቸው የማሉ ያህል የሚከራከሩት ስለቤዛነት የተሰጠው ትርጉም ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ሳይሆን ማርያምን ይጨምራል፣ ሌሎችን ብዙዎችንም በተጨማሪነት ያጠቃልላል ብለው ለመከራከር ሲንደፋደፉ አይተናል። እዚህ ላይ አስረግጠን የሊቀጳጳሱን ትምህርት የተቀበልነውና ስለኢየሱስ ክርስቶስ ብቸኛ አዳኝነትና ቤዛነት ያስተማሩት ትክክል ነው ያልነው ጳጳሱን በተለየ ስለወደድን ሳይሆን ያስተማሩት እውነት ስለሆነ ነው። ለእውቀት አእዱገ ገዳም ለሆኑት ሰዎች የምንነግራቸው ነገር ስለቤዛ የተጻፈና የተነገረ አንድ መቶ ሺህ ጥቅስና ትርጉም ቢኖራችሁ ለንጽጽር የማይቀርብበት የኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ብቸኛው ነው። የወደቀውን የሰው ልጅ ወደቀደመ ክብሩ ለመመለስ፣ ለበደለው ኃጢአት የተሰጠ ሥርየት፣ የተከፈለ የሞት ዋጋ ምትክ የሆነው ቤዛነት የኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ይሄንን የሚተካ፣ የሚያክል፣ የሚወዳደር፣ የሚቤዥ ሌላ ቤዛ ከሰማይ በታች የለም። ይሄ ቤዛነት ትልቅነቱ ዘላለማዊ፣ መድኃኒትነቱ ሕያው፣ አዳኝነቱ ሞት ያላሸነፈው ነው። ስለቤዛ በትርጉምም፣ በፍቺም በንፅፅርም ከኢየሱስ ቤዛነት ጋር ሊቀርብ የሚችል ሌላ የለም። ስለቤዛ የተነገረ ሌላ ቃል አለ ብለህ ጭንቁር የቃል ክርክር ታቀርብ ይሆናል። ያንን እያነሳህ እንደዚህ ማለት ነው፣ እንደዚያ ማለት ነው እያልክ ውሃ ወቀጣ ክርክር የማንሳት መብት ይኖርሃል። የጻፎችና የፈሪሳውያን ክርክር የወንጌል እውነት ሊቀይረው እንደማይችለው ሁሉ የትኛውም ስለቤዛ የሚሰጥ፣ የተሰጠ ትርጉምና ንጽጽር ጌታችን ካደረግልን ቤዛነት ጋር አይነጻጸርም፣ ለትርጉም ክርክር ሊቀርብ አይችልም። ለነዚህ የተለሰኑ መቃብሮች የምነግራቸው በኔ በኃጢአተኛው ምትክ ቤዛ ሆኖ የሞተ ከኢየሱስ ክርስቶስ በስተቀር ሌላ ቤዛ ማንም የለም ነው የምንላቸው። ቅድስት ማርያም ቤዛ ናት የሚሉ ሰዎችን ታድናለች ወይ? ተብለው ሲጠየቁ አታድንም፣ ግን መድኃኒትን ወልዳልናለች፣ ስለዚህ ቤዛ እንላታለን ይሉናል። በምትክነትና ለኃጢአት ሥርየት እንዳልሞተችልን ከታወቀ በመጽሐፍ እንደተፃፈ "የጌታ እናት" ማለታችን በቂ አይደለም ወይ፣ ባልተፃፈ የቤዛነቷ ትርጉም ላይ ጉንጭ አልፋ ክርክር ለምን ያስፈልጋል? ሲባሉ ጴንጤ፣ ከሀዲ፣ ጸረ ማርያም የሚሉ ስድቦቻቸውን በእውቶማቲክ ይተኩሳሉ። እነዚህ ለእውቀት አእዱገ ገዳም የሆኑ ሊቀ ሊቃውንትና መተርጉመ መጻሕፍት ነን ባዮች በማርያምም፣ በኢየሱስም ሁለት አዳኝ እንዳላቸው ለጎጋ ምዕመኖቻቸው ያለከልካይ እየጮሁ መገኘታቸው ስናይ በነሱ ዘንድ ኢየሱስ ሌላ ብዙ ቤዛ እንዳላቸው እንረዳለን። አሁንም ደግመን እንላለን፣ ለአዳም ልጆች ቤዛ ሆኖ የሞተና ያዳነን ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ ቤዛ የለንም። ስለቤዛ ሚሊየን ትርጉም ቢኖርህ እሱን እያመነዠክ መኖርህ የኢየሱስን ብቸኛ ቤዛነት አይቀይረውም። የኢየሱስን ቤዛነት አምናለሁ ያለ ሰው በኢየሱስ ብቸኛ የቤዛነት ሥራ ላይ ሌላ ትርጉምና ንጽጽር ለምን ይዞ ሊመጣ አይችልም። የሚመስለው፣ የሚተካከለው፣ የዘላለም የሆነ ቤዛነት ከኢየሱስ ውጪ አለ? የለም!!! አዎ! እናውቃለን፣ የኢየሱስን ዘላለማዊ የቤዛነቱን ሥራ በፍጡራንና በምድራዊያን የትርጉም ቃላት ሸፍኖ ለማሳነስና ሰው ሁሉ ወደአንድያ ቤዛው ዓይኑን እንዳያነሳ ለመጋረድ ጠላት በስንዴው መካከል የዘራው እንክርዳድ ነው። እኛ ግን በየትኛውም የቤዛ ትርጉም ሳንወጣ፣ ሳንወርድ፣ ሳንደክም "እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” እንላለን። ቆላስይስ 1፥13-14 ሊቀጳጳሱ ስለኢየሱስ ብቸኛና ዘላለማዊ ቤዛነት የተናገሩት ትክክል ነው። ከፍጡራን መካከል ሌላ የዘላለም ቤዛ የሆነልን፣ መሆን የሚችልም የለም። ከሰማይ በታች ቤዛ መሆን የሚችል ስለሌለ ነው አብ አንድያ ልጁን የላከልን። ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

Saturday, December 21, 2024

ታቦትም ጽላትም ዛሬ የሉም!

ታቦትና ጽላት ዛሬ የሉም! በዚህ ርዕስ ላይ ብዙ ጊዜ ፅፈናል። አብዛኛው ሰው የሚያምነው የነገሩትን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተፃፈውን ባለመሆኑ ዛሬም ስለታቦትና ጽላት ሲከራከር ይውላል። ስለታቦትና ጽላት ምንነትና እንዴትነት ከመናገራችን በፊት አንድ ነገር በመጠየቅ ልጀምር። አንድ ሰው ናይሮቢ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ነው ቢላችሁ መልሳችሁ ምን ሊሆን ይችላል? በእርግጠኝነት መልስ ከመስጠታችሁ በፊት ፊቱን በደንብ ታዩታላችሁ፣ ፈገግ ልትሉ ትችላላችሁ፣ ምን እያልክ ነው ብላችሁ መልሳችሁ ልትጠይቁት ትችላላችሁ። ከመቼ ወዲህ? ልትሉትም ትችላላችሁ። ምክንያቱም ናይሮቢ ከኬንያ ዋና ከተማነት ተዛውሮ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ሆኖ የተቆጠረበትና ሊሆን የሚችልበት እድል ስለሌለ ጠያቂያችሁ እያሾፈ ወይም እየቀለደ እንደሆነ መገመታችሁ የሚጠበቅ ነው። አብዛኛው ሕዝብ የሚረዳው እውነት ናይሮቢ የኬንያ ዋና ከተማ እንጂ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ አለመሆኑን ነው። አሁን ባለንበት ሁኔታ ይሄ የተረጋገጠ እውነት ነው። እንደዚሁ ሁሉ ከእስራኤል ውጪ ታቦትና ጽላት ነበረኝ ወይም አለኝ የሚል ሁሉ ናይሮቢ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ነው ብሎ የሚናገርን ሰው ይመስላል። ምክንያቱም እነዚህን ነገሮች እየነገራችሁና እንደሆነ እየመሰከረላችሁ መሆኑ ነውና። እኔ እግዚአብሔር በምድር ላይ ከአህዛብ መካከል ከመረጣቸው ከእስራኤል 12ቱ ነገድ አንዱ ነኝ፣ በኮሬብ ተራራ የኪዳኑ ፅላት ሲሰጥ ነበርኩ፣ ከ40 ዓመት በኋላ ርስት ምድርን ዘመዶቼ በኢያሱ እጅ ሲወርሱ ድርሻ መሬት አግኝቻለሁ፣ ኢየሩሳሌም የንጉሡ ከተማ ከተማዬ ነበረች፣ ሥርዓተ ቤተ መቅደሱ ሲፈፀም እስከናቡከደነጾር ውድመትና ዘረፋ ድረስ እዚያው ሳከናውን ነበርኩ። ወገኖቼ ለ70 ዓመት በባርነት ባቢሎን ሲወርዱ ነበርኩ። በሄሮድስ ዘመን ቤተመቅደሱ ተሰርቶ ሥርዓተ ታቦቱ ባይፈፀምም እየሄድኩ እጸልይ ነበር። በአጭር ቃል እኔ ከተመረጡት ከእስራኤል ወገን እንጂ ከአህዛብ አይደለሁም እያላችሁ ነው። ከዚህ ሰው ጋር ስለታቦትና ጽላት አሰራርና ሥርዓት ጋር መነጋገር የምትችሉት በመጀመሪያ በዚህ ጉዳይ ላይ መግባባት ስትችሉ ብቻ ነው። የታቦትና የጽላት ሥርዓት እንኳን የካም ነገድ እንደሆነ በሚነገርለት በአፍሪካ ይቅርና የሴማውያን ድንኳን መገኛ በሆነችው በኢየሩሳሌምም ዛሬ የለም። ባልተመረጥክበት፣ የተለየ ኪዳን ባልተቀበልክበት፣ የመቅደሱ አገልግሎት በሌለበት ሁኔታ ራስህን በራስህ ስትመርጥ ማድረግ የምንችለው ነገር ጤንነትህን በመጠራጠር ወደምታምንበት ፀበል ሂድ እንልሃለን እንጂ ላንተ ታቦትና ጽላት የምንደፋበት ምንም ምክንያት ሊኖረን አይችልም።ምክንያቱም እኛ በመንፈስ ቅዱስ የታተምን ጤነኞች ስለሆንን ለበኣል መሰዊያና ለማመለኪያ አጸድ የምናፈነድድበት ዜሮ ምክንያት የለንም። እነዚህ ሰዎች ተረፈ ምናሴ ናቸው። ምናሴ የተባለ የይሁዳ ንጉሥ እንዲሁ አድርጎ ነበር። "ያዘዝኋቸውንም ሁሉ፥ ባሪያዬም ሙሴ ያዘዛቸውን ሕግ ሁሉ ቢያደርጉ ቢጠብቁም ለአባቶቻቸው ከሰጠኋት ምድር የእስራኤልን እግር እንደ ገና አላቅበዘብዝም ባለው ቤት የሠራውን የማምለኪያ ዐፀድን የተቀረጸውን ምስል አቆመ። ነገር ግን አልሰሙም፤ እግዚአብሔርም ከእስራኤል ልጆች ፊት ካጠፋቸው ከአሕዛብ ይልቅ ክፉ ይሠሩ ዘንድ ምናሴ አሳታቸው።" (2ኛ ነገ 21፣8-9) ሊቁ የተረት አባት ዘበነ ለማ በአንድ ወቅት "ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም" ብሎ ያስተምር ነበር። ከወገኖቹ በኩል ወቀሳ ሲበዛበት እንደዚህ ብሎ የማስተማር ጩኸቱን ቢቀንስም በትምህርቱ የተበከሉት ግን ዛሬም ድረስ "ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም" የሚለው ስሁት ትምህርት ስር እንደሰደደ አለ። የተረት ሊቁ ዘቤ ለማ ታቦትና ጽላት የወረስነው ከሙሴ ሥርዓት ነው የሚለው ጩኸቱ ዛሬም እንደቀጠለ ነው። የታቦት ቁመቱ፣ ርዝመቱ፣ ክብደቱ፣ አሸካከሙ፣ አቀማመጡ፣ ጽላቱ ላይ ምን ተጻፈ፣ ማን ጻፈ፣ ወዘተ የሚለው ጥያቄ ለደፋሩ ዘቤ ጉዳዩ አይደለም። የመናገር እድልና ሥፍራ ስላገኘ የስህተት መርዙን መርጨት ለሱ የተሟላ እውቀት ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ በግልጽ ቋንቋ የዘበነ ለማን አስተምህሮ የሚቃወም ትምህርት ሲሰጥ ሰምቸዋለሁ። ትምህርቱ የተሟላ ባይሆንም በትክክል ያንፀባረቀው አቋም ግን ይበል የሚያሰኝ ነው። የኦሪቱ ታቦትና ጽላት ዛሬ የለንም ብሏል። ይሄ ናይሮቢ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ አይደለም ብሎ ሀቁን እንደመመስከር ይቆጠራል። ነገር ግን የተጓደለው ነገር ቢኖር በቤተመቅደሱ ውስጥ መስዋእት እንሰዋበታለን በማለት የተናገረው የተሟላ መልስ አይደለም። ሲጀመር እሱ ከኦሪቱ ኪዳን ጋር በተመሳሳይ ስም ጽላት መባል የለበትም። በሌሎች አብያተክርስቲያናት እንደሚደረገው ለምሳሌ በግብጽ ኦርቶዶክስ ጠረጴዛ፣ መሰዊያ ተብሎ ይጠራል። ከዚያ ባለፈ ተሸክመውት መንደር ለመንደር አይወጡም፣ ገብርኤል ጡጦስ፣ ጣንጦስ፣ ኤፈራንጦስ እያሉ ሕዝቡን በጻድቅ ስም አያደነዝዙበትም። በእልልታና በጩኸት አያሰግዱትም፣ ይቀስፍሃል፣ ይሰነጥቅሃል እያሉ አያስፈራሩበትም። አይሸጥም፣ አይለወጥም። የኢትዮጵያው ግን ምናሴ በእግዚአብሔር ቤት ከፈፀመው አምልኮ ጋር ተመሳሳይ ነው። በዚህ ዘመን የተሰረቀው ታቦት በተለይም ብዙ ዘመን የቆየው ከተገኘ ብዙ ዋጋ እንደሚያወጣ ይታወቃል። ስናጠቃልል፣ ኢትዮጵያ እስራኤል አይደለችም፣ ሆናም አታውቅም። ኪዳን አልተሰጣትም፣ ታቦትም ጽላትም የእርሷ አልነበረም። የአህዛብ ሀገር ነበረች። ክርስትና እንዴት እንደገባ ራሷ በምትተርክበት ታሪክ በፍሬምናጦስ በኩል አብርሃና አፅብሃ የመጀመሪያውን ክርስትና መንግሥታዊ ሃይማኖት አድርጋ ተቀበለች። ስለዚህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን በኦፊሴል መናገር ያለባት የኦሪቱ ታቦትና ጽላት የለኝም፣ አሁን ያለው መሰዊያ ወይም መስዋእት ማቅረቢያ ጠረጴዛ እንጂ የተለየ አምልኮ፣ ስግደትና ምስጋና የሚቀርብለት ነገር አይደለም ብላ ማወጅ አለባት። መሰዊያ የቀረበበትን ማክበር እያለች 365 ቀን በሙሉ ሕዝቡን ማሰገድ ትክክል አይደለም። ሕዝቡ መስዋእቱን ከመብላት ይልቅ የመስዋዕቱን መክተፊያ ይዞ በመውጣት ሕዝቡን በእልልታ፣ በዝማሬ፣ በቅኔና በስግደት ማሳሳት ወንጀልም፣ ኃጢአትም፣ ክህደትም ነው። ሕዝቡ የእግዚአብሔር ታቦት ይህ ነው ብሎ ያምናል። ለዚህ ታቦት ሲል ለመግደልም፣ ለመሞትም አይመለስም። እንደእውነቱ ከሆነ የሕዝቡን አእምሮ በዚህ መልኩ ቀፍድዶ በማሰር ወደሞት ከመንዳት የባሰ ከዚህ በላይ ጥፋት የለም። እውነቱ ግን እግዚአብሔር አብ ለኛ የሰጠን መዳኛችን፣ ጽላታችን፣ አምልኮና ስግደታችን በኢየሱስ በኩል እንጂ በቁሳቁስና ሰዎች ባዘጋጇቸው ምናምንቴ ሥርዓቶች በኩል አይደለም። ዓይናችንን ከኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነቅለን ወደሌላ ወደማንም ለመዳን አናማትርም። ሌላ መንገድ በጭራሽ የለምና ነው። የታቦት፣ የጽላት፣ የተክልዬ፣ የአቦዬ፣ የሳምርዬ፣ የክርስቶፎሎስ፣ የአርሳዲ፣ የፈለቀች፣ የዘነበች፣ የአርሴማ፣ የንፍሮ፣ የዳቦ፣ የአፈር፣ የአመድ የሚባል የመዳኛ ዘዴ እና 20 እና 30 ትውልድህን የሚያስምር መንገድም፣ ኪዳንም ከሰማይ በታች ሌላ ስም በጭራሽ የለም። “ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።” — ዮሐንስ 14፥6 የተባልነው ይህንን ነው። የምንድነው፣ የዳንነው በዚህ ስም ብቻ ነው።

Tuesday, December 17, 2024

ኪዳነ ምሕረት ኢየሱስ ነው!

ኪዳነ ምሕረት ኢየሱስ ክርስቶሰ ነው! ከዚህ በላይ የሚታየው ስእል የጣኦት አምላኪዎች እንጂ የሌላ የማንም ስእል አይደለም። በጣኦት አምላኪዎቹ ልብ ሰይጣን ያስቀመጠው ትርጉም እንደምንገምተው ልጅ እግሩ ሰው የኢየሱስ፣ ሽማግሌው ደግሞ የአብ መሆኑ ነው። በእግዚአብሔር መንግስት ሦስት ምስሎች በአኀዝ የሚቀመጡበት ወይም በወጣትና በሽማግሌ የሚመሰልበት መለኮታዊ ማንነት የለም። ከእግዚአብሔር ያልሆነ የሰው ልብ ያመነጨው ስእል ሁሉ ከተመለከ፣ ከተወደሰ እሱ ጣኦት ነው የሚባለው። “እንዳትረክሱ፥ የተቀረጸውን ምስል የማናቸውንም ነገር ምሳሌ፥ በወንድ ወይም በሴት መልክ የተሠራውን፥” (ዘዳግም 4፥16) አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ምሕረትና ይቅርታ የአዳም ልጆች እንዲያገኙ ለማንም ኪዳን አልሰጡም። መጽሐፍ ቅዱስ ለሰው ልጆች የምሕረትን ኪዳን ሞታችንን ከሞተልን ከኢየሱስ በቀር ለፍጡራን እንደሰጡ አንድም ቦታ ተጽፎ አናገኝም። “ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም እስከ ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን።” ነው የተባለው። (ይሁዳ 1፥25) እውነቱ ይህ ከሆነ የመዳን ኪዳን ያገኘነው እንዴት ነው? ኪዳነ ምሕረት ማለት የምሕረት፣ የይቅርታ፣ የሥርየት ቃል ድምዳሜ ወይም ፍጻሜ ማለት ነው። ምሕረት የማይገባው ጥፋተኛ፣ በምሕረት አድራጊው እቅድ ከእዳ፣ ከበደል፣ ከወንጀል ነጻ አድርጌሃለሁና የነጻነትህን አዋጅ በዚህ ደብዳቤ አረጋግጬልሃለሁ ብሎ የሚሰጠው የአርነት ሰነድ ነው። የዚህ ፅሑፍ ዓላማ ወደሆነው ዝርዝር ጉዳይ ከመግባታችን በፊት ራሱ "ኪዳን" የሚለው ቃል ምንን ያመለክታል የሚለውን ለመመልከት እንሞክር! ውል በሁለት ተዋዋይ ወገኖች መካከል በቃል ወይም በፅሑፍ የሚደረግ አሳሪ ሕግ ነው። በውሉ ላይ ተዋዋይ ወገኖችን መብትና ጥቅም በማካተት የሚደርሱበት ስምምነት ሲሆን መሠረታዊው የውል አስፈላጊነት ጥቅምንና መብትን ለማስከበር መርህ አድርጎ የሚነሳ ቢሆንም ውል ሁልጊዜ አዋጭ ወይም ዘላቂ ላይሆን ይችላል። ውል በዓለማችን ላይ እየተሠራበት ያለው የተዋዋይ ወገኖች አሳሪ ስምምነት ከመጽሐፍ ቅዱሳዊ ኪዳን በጣም የተለየ ነው። የእግዚአብሔር ኪዳን ወይም (Covenant) በእግዚአብሔርና በሰው ልጆች መካከል የሚደረግ የአቻ ስምምነት አይደለም። ኪዳን ማለት በጥሬ ትርጉሙ ውል:ስምምነት ቢሆንም ኪዳኑ በምድር ላይ ሰዎች እንደሚያደርጉት በሁለት እኩል ተዋዋይ ወገኖች መካከል እንደተደረገው አይደለም። በውል ሰጪ(በእግዚአብሔር) እና በውል ተቀባይ (በሰው ልጆች) መካከል የተደረገው ኪዳን እግዚአብሔር መብትና ጥቅሙን ለማስከበር ወይም ከሰው ልጆች የሚያገኘው የተለየ መብት እንዲጠበቅለት የተደረገ ኪዳን ሳይሆን እግዚአብሔር በባህርይው ፍቅር ስለሆነ የጠፋውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ በክንዱ ተጠብቆ እንዲኖር ሲል እግዚአብሔር ፍቅሩን የገለፀበት መንገድ ነው። ሌላውን ወገን የሚጠቅም ኪዳን ማድረግ የሚችለው እግዚአብሔር ብቻ ነው። እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር የሚገባው ኪዳን አምላክነቱን አስገድዶ ለመጫን ሳይሆን ጌትነቱን ለተቀበሉት ሁሉ ከአምላክነቱ በረከት እንዲትረፈረፍላቸው ከፍቅሩ የተነሣ የሚደረግ ኪዳን ነው። “በጭንቃቸው ሁሉ እርሱ ተጨነቀ፥ የፊቱም መልአክ አዳናቸው፤ በፍቅሩና በርኅራኄውም ተቤዣቸው፥ በቀደመውም ዘመን ሁሉ አንሥቶ ተሸከማቸው።” (ኢሳ 63፥9) እግዚአብሔር አዳምን የፈጠረው ማንንም ሳያማክር ከአምላካዊ ክብሩ ሕያውነት እንዲካፈልና በዘላለማዊ ፍቅሩ እንዲኖር ነው። “ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም። (1ኛ ዮሐ 4፥10) ለአዳም የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ያሟላለት በአዳም ጥያቄ አልነበረም። እንዲያውም አዳም የተፈጠረው የአምላክን ባሕርይ ተካፋይ እንዲሆን፣ ክብሩ በሱ እንዲታይ በአርአያውና በምሳሌው ነው። እግዚአብሔር ከፈጠረውና ገዢ እንዲሆን በፍጥረቱ ላይ ካሰለጠነው ከአዳም ጋር የገባው ኪዳን ከሰጠሁህ እልፍ አእላፍ ፍጥረት መካከል ይሄን አንዱ ከበላህ ሞትን ትሞታለህና እንዳትበላው የሚል ትእዛዝ ነበር። አዳም ሞትን የሞተው ባልተነገረውና በማያውቀው ነገር ሳይሆን ራሱ ሞትን በመምረጡና የእግዚአብሔርን ድምጽ በመጣሱ የተነሳ ነው። ይህ የመጀመሪያ ኪዳን የፈረሰው ውል ተቀባዩ ውሉን በማፍረሱ ስለሆነ ውሉ የሚያስከትለው ቅጣት በአፍራሹና በልጆቹ ላይ ሞት ተግባራዊ ሆኗል። ከአዳም ውል አፍራሽነት በኋላ እግዚአብሔር ከአዳም ልጆች ጋር የገባው ሌላኛው ኪዳን ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ በኮሬብ ተራራ ነው። ልቅሷችሁንና ጩኸታችሁን ሰምቻለሁ ከባርነት አወጣችኋለሁ፣ ወተትና ማር የምታፈስ ሀገር አወርሳችኋለሁ ብሎ በታላቅ ድንቅና ተአምራት ከግብጽ ከወጡት እስራኤላውያን ጋር ያደረገው ኪዳን ኮሬብ ላይ ተገልጿል። (ዘጸ19፣4—5) ❝በግብፃውያን ያደረግሁትን፥ በንስርም ክንፍ እንደተሸከምኋችሁ፥ ወደ እኔም እንዳመጣኋችሁ አይታችኋል። አሁንም ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፥ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፤❞ ብሏል። ይህ ኪዳን ዘላለማዊው ኪዳን እስኪፈጸም ድረስ በምድራዊ ርስት የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከሌሎች ለይቶ የሚያቆይበት የኪዳን ሕግ ተሰጥቶ ነበር። እግዚአብሔር ከመረጠው፣ ራሱ ከሚመራው፣ የተሻለ ሀገር አወርስሃለሁ ካለው ከዚህ ሕዝብ ጋር ኪዳን አደረገ። ይህ ኪዳን እግዚአብሔር የመረጠው ሕዝብ ከአህዛብ የሚለይበት፣ ደግሞም ከእግዚአብሔር ጋር በድምፅና በመልእክት የሚገናኝበት የሕግ ኪዳን ነበር። በአድርግና አታድርግ የተሠጠው የኪዳኑ ስምምነት በተጻፈው የጽሌ ሠሌዳ ላይ እንዲህ የሚል ተፅፎበት እንመለከታለን። 1/ ከኔ በስተቀር ሌሎች አማልክት አታምልክ፣ 2/ የእግዚአብሔርን ስም በከንቱ አትጥራ፣ 3/ የሰንበትን ቀን አክብር፣ 4/ እናትና አባትህን አክብር፣ 5/ አትግደል፣ 6/ አታመንዝር፣ 7/ አትስረቅ፣ 8/ በሀሰት አትመስክር፣ 9/ የባልንጀራህን ገንዘብ አትመኝ፣ 10/ ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ የሚል የኪዳን ሕግ ነበረ። ይህ ኪዳን ይጠበቅ ዘንድ የሚከናወንበት መንገድ የኃጢአት፣ የደኅንነት፣ የሚቃጠል መስዋዕት በማቅረብና ትዕዛዛትን በመጠበቅ ነበር። “እንዲህም ይሆናል፤ ይህችን ፍርድ ሰምተህ ብትጠብቃት ብታደርጋትም፥ አምላክህ እግዚአብሔር ለአባቶችህ የማለውን ቃል ኪዳንና ምሕረት ለአንተ ይጠብቅልሃል፤” ( ዘዳግ 7፥12) ይህ ሕግና ትዕዛዛቱ ምድራዊ ሥርየትን ያስገኝለታል እንጂ አዳም ትቶ ወደወጣበት ገነት መልሶ የሚያስገባ አልነበረም። ይህንን በእግዚአብሔር ቁጣ የተዘጋውን የገነት በር መልሶ በመክፈት አዳምንና ልጆቹን ማስገባት የሚችል ከሰው ልጆች አንድም ሰው ስላልነበረ በሌዊ ወገን በሚሾሙ ካህናት በኩል ደም በመርጨት ጊዜያዊ ሥርየትን እያገኙ እስከአማናዊ የተሻለ ኪዳን ድረስ ለመቆየት ችለዋል። ምክንያቱም ሰው በጥፋት ሥራው የተረገመ በመሆኑና ምድርም በተረገመው ሰው ምክንያት የተረገመች በመሆኗ ከሰው ልጆች መካከል ከእርግማን ነጻ የሆነ ሰው ስላልነበረ ዘላለማዊ ድነት ማስገኘት የሚችል አንድም ጻድቅ አልነበረምና ነው። “አዳምንም አለው፦ የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና፥ ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝሁህ ዛፍም በልተሃልና ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤” (ዘፍ 3፥1) እግዚአብሔር ሌሎች ንዑሳን ኪዳናት ከወደዳቸው ጋር ኪዳን አድርጓል። ከኖኅ ጋር በቀስተ ደመና (ዘፍ9፣11-12)፣ ከሙሴ ጋር (ዘጸ34፣27)፣ ከአብርሃም ርስቱን ሲሰጠው(ዘፍ15፣28)፣ የቁልፈታቸው ግርዛት እንዲወድቅ (17፣11)፣ ከይስሐቅ (ዘፍ17፣19)፣ ከያዕቆብ (ዘፍ35፣10-15)፣ ከዳዊት ጋር (ኤር33፣17) ኪዳን አድርጓል። ይህ ኪዳን በዘመናቸው እግዚአብሔርን ለታዘዙበትና ለፈፀሙበት ፍቅር የተነገረላቸው የመኖር ኪዳን እንጂ የአዳምን በደል የሚሽር ወይም ለሰው ልጆች የዘላለም ሕይወትን የሚያስገኝ ኪዳን አልነበረም። “የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ብትጠብቅ፥ በመንገዱም ብትሄድ፥ እግዚአብሔር እንደ ማለልህ ለእርሱ የተቀደሰ ሕዝብ አድርጎ ያቆምሃል።” (ዘዳ 28፥9) እግዚአብሔር የምወደው ልጄ... ያለው ከሰማይ ከወረደው በስተቀር ወደሰማይ የወጣ የለም የተባለለት ባለሙሉ ሥልጣን ዘላለማዊ ሊቀካህን፣ በደሙ በሰማያዊቷ መቅደስ የገባ ኢየሱስ ብቻ ነው። ሞትን አሸንፎ በሞት የተሸነፉትን ሁሉ ከምርኮ ነፃ ማውጣት የቻለ ከኢየሱስ በቀር ማንም የለም። ይህንንም ሐዋርያው ጳውሎስ በኤፌሶን መልዕክቱ እንዲህ ሲል አስረግጦ ይነግረናል። (ኤፌሶን 4፣8-10) ስለዚህ፦ ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ ይላል። ወደ ምድር ታችኛ ክፍል ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ፥ ይህ ወጣ ማለትስ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው። ይህ ኪዳን፣ አዲስ ኪዳን፣ የሕይወት ኪዳን ይባላል። አብ በአዳም ልጆች ላይ የነበረውን ቁጣ ያበረደበት፣ የተወደደ መስዋዕት፣ በደሙ በኩል ዘላለማዊ የማዳን ሥርየት የተፈፀመበት ኪዳን ይህ ነው። “እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።” ( ዮሐ 6፥47 ) ከዚህ ኪዳን ውጪ እግዚአብሔር ሌላ ኪዳን የለውም። “ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን፤” (ሮሜ 5፥10) ከዚህ የምሕረትና የይቅርታ ኪዳን ውጪ እግዚአብሔር የተቀበለውና ደስ የተሰኘበት ሌላ ኪዳን የለም ብቻ ሳይሆን ይሄንን ኪዳን ማሟላት የሚችል ከሰው ልጆች መካከል አንድም ሰው አልነበረም። ቢኖርማ ኖሮ ኢየሱስ ሰው ሆኖ መወለድ ባላስፈለገው ነበር። ስለዚህ ለሰው ልጆች የተሰጠ የምሕረት ኪዳን ኢየሱስ ብቻ ነው። ሌላ ኪዳነ ምሕረት የለም! ይህንን ኪዳን የሚተካ፣ ማዳን የሚችል፣ አብ የወደደው መስዋእትና የምወደው ልጄ ያለው ከኢየሱስ በቀር ማንም ስለሌለ ኪዳነምሕረት በማለት በቅድስት ማርያም በኩል ዘላለማዊ ድነት አገኛለሁ በሚል ተስፋ ወደ ማርያም የሚለምን ሁሉ ከሕይወት ኪዳን የጎደለ፣ እግዚአብሔር የሰጠውን የመዳን ኪዳን ያቃለለ ሰው ነው። ድንግል ማርያም ቅድስትና ብፅእት እንጂ እግዚአብሔር አብ የምሕረቴን ኪዳን በሷ በኩል አድርጌአለሁ ብሎ ኪዳን የሰጠበት ሁኔታ የለም።አንዳንዶች በማርያም ጉዳይ ስለጥንተ አብሶ (የቀደመ በደል) እያነሱ ጉንጭ አልፋ ክርክር ሲያደርጉ ይታያሉ። ይሄ የማይረባ ክርክር ነው። ከአዳም ጀምሮ እስከ ክርስቶስ ኢየሱስ መምጣት ድረስ ለሰው ልጆች ሁሉ ገነት ተዘግታበት ይኖር ነበር። በገነት የሌለ ሰው ሁሉ በደለኛ ነው። በሕይወት አኗኗሩ ጻድቅና ንፁህ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ከገነት ውጪ ስላለ በደለኛ ነው። በአጭሩ በኪሩብ የምትጠበቀው ገነት የተዘጋበት የሰው ልጅ ሁሉ በደለኛ ነው። እንዲያውም ብፅእት ማርያም ራሷ ነፍሷ ጌታን እንደምታከብር፣ መድኃኒቷም እንደሆነ እንደዚህ በማለት መስክራለች። “ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች፥ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች፤” (ሉቃስ 1፥47) እግዚአብሔር የብሉይን (አሮጌውን) ኪዳን ከተመረጡት ከእስራኤላውያን ጋር፣ አዲሱን ኪዳን በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ ካመኑት ጋር የሕይወትን ኪዳን አድርጓል። ሌላ ከማንም ጋር የማዳን፣ የሕይወት ኪዳን አላደረገም። “ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።” (ዮሐ 14፥6) ኪዳነ ምሕረት ኢየሱስ ነው!