Tuesday, August 9, 2016

ተገቢ ትኩረት የሚያሻው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ካህናት አቤቱታ!



በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ያሉ አጠቃላይ ማኅበረ ካህናቱ በአቤቱታ ድምጻቸው  ወቅታዊ፤ ትክክለኛና አፋጣኝ ምላሽ የሚያስፈልገው አቤቱታ አቅርበዋል የሚል እምነት አለን። ይህንን አቤቱታ ዝም ብሎ ማለፍ በቤተክርስቲያኒቱ አጠቃላይ ውድቀት ላይ ከኤጲስቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ ስህተቶች ጋር ተባባሪ መሆን ብለን እናምናለን።
ዘረኝነት፤ ጉቦና የኃጢአት ገመና እንዲህ እንደዘንድሮው ታይቶም፤ ተሰምቶም አይታወቅም። ማኅበረ ቅዱሳን በትክክል ቤተ ክርስቲያኒቱን መቆጣጠሩን ያስመሰከረበት ጊዜ ቢኖር በዚህ የኮሚቴ ምርጫ የታየው የኩነኔና የፍርድ መዝገብ በአደባባይ መነገሩ ነው። ዘረኝነት ቦታውን ተረክቧል። ሙስናው በግልጽ ይታያል። ድሮም ቢሆን በእነጉድ ሙዳይ የሚመራ ኮሚቴ ከዚህ ዓይነቱ ቆሻሻ ተግባር የራቀ ሊሆን እንደማይችል የነበረን ግምት ትክክለኛ ነበር።
የኛም ግምት ስህተት እንዳልነበር የሚያሳየው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ካህናት ድርጊቱን በመመልከት ቀጥተኛ አቤቱታ ማቅረባቸው ሲሆን ለካህናት ጩኸት ጆሮ ሊሰጠው ይገባል እንላለን። ፓትርያርክ ማትያስም ለራሳቸው ክብርና ስም፤ ታላቂቱ ቤተክርስቲያኒም ከተደቀነባት ውርደት ማዳን ካለባቸው ጊዜው አሁን ነው። የካህናቱን አቤቱታ እዚህ ያንበቡ!