Sunday, June 23, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ (ክፍል ሦስት )



ከባለፈው ክፍላችን የቀጠለውን በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን ጠላት አስርጎ ያስገባውን የስህተት መንፈሱን አሰራር በቀጣይነት እንመረምራለን። ጥንተ ጠላታችን በእግዚአብሔር ዋና ቃል ውስጥ ጥቂት የስህተት ቃላትን ሰንቅሮ ማስገባት መቻሉ ጠቅላላ የአምልኮ ሥርዓታችንን እንደፈለገ ለማናጋት በር ስለሚያገኝ በዚህ ዙሪያ አጥብቆ ይሰራል። ይህንን እስትንፋሰ እግዚአብሔር የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ከአበው ሲወርድ እዚህ ዘመን የደረሰውን ጠብቆና ጠንቅቆ በማቆየት፤ ስህተት ሲገኝ በማቃናት፤ የጎደለውን በማረም፤ የሁል ጊዜ አዲስነቱን እንደያዘ፤ ትውልዱን እያደሰ መቀጠል እንዲችል የማድረግ ኃላፊነቱ የቅዱስ ሲኖዶስና የሊቃውንት ጉባዔው ሥልጣን ቢሆንም ምሁራኑ በዐረፍተ ዘመን በሞት ጥላ ሥር አርፈው ቦታቸውን በመልቀቅ ለጊዜው ጥሬ ትርጉሙን እንኳን ለመረዳት አቅሙ በሌላቸውና «ከተንስኡ ለጸሎት» በዘለለ ቃለ እግዚአብሔርን ለመመርመር ድክመት ቤቱን የሰራባቸው ወንበሩ ላይ ያለአቅማቸው በመቀመጣቸው ቅዱሱ መጽሐፍ ሊበረዝ ችሏል። ሊቃውንቱ ወደዳር ተገፍተው በደጀ ጠኝነት ያንጋጥጣሉ።፤ ገሚሱም በጋዜጣ አዟሪነት ያለቦታቸው ተሰማርተዋል። እነ «በአፍ ጤፍ ይቆሉ»  በሊቃውንት ስም የቤተክህነትን ገበያ ያደራሉ። መጋቤ ብሉይ ሠይፈ ሥላሴን የመሳሰሉ ሊቃውንት የደረሱበትን እውቀትና እውነት እንዳይተነፍሱ በድንቁርና መዶሻ ተመትተው እስከወዲያኛው አሸለቡ። ድኩማነ አእምሮዎች ሲያዋክቧቸው የቆዩት ብፁዕ አቡነ መርሐ ክርስቶስ እንኳን በዚህ በጎጋ ጉባዔያተኛ መካከል ባገኙት መንገድ ሁሉ ያካፈሉት ቃለ እውነት ብዙ ዘር ያፈራ ቢሆንም የተመኙትን ያህል ሳይሰሩ ያንን ሁሉ እውቀት ይዘውት የሄዱት ለቤተክርስቲያን ትልቅ ጉዳት መሆኑን እያየነው ነው። 
   እንደው ለመሆኑ ከእሳቸው ወዲያ በነገረ መጻሕፍትና ትርጉም አዋቂነት የሚጠራ ጳጳስ ማን ይሆን? ከተረትና ከእንቆቅልሽ በዘለለ ቃለ እግዚአብሔርን በምልዓትና በስፋት ማስተማር፤ ማረቅ፣ ማቃናት የሚችል አንድም ጳጳስ በዚህ ዘመን አለመኖሩ ብቻ ሳይሆን የሚቆጨውም ሰው አለመገኘቱ በጣም አሳሳቢ ነው። ሊቃውንት ጉባዔ የተባለው የእነ ክንፈገብርኤል አልታዬና የሊቀ ሥዩማን  ራደ መሥሪያ ቤት ሊቅነቱን ሳናይለት ዘመኑን ፈጠመ።  የሚብሰው ደግሞ ትልቁንና ዋናውን ቃለ እግዚአብሔር/መጽሐፍ ቅዱስ/ ጥንታዊውን የአበው ትርጉምና ሕግጋት ጠብቆ እንደንጹህ የምንጭ ውሃ ኮለል ብሎ የምእመናን የልቡና ጥማት እንዲያረካ ማድረግ አለመቻሉ ብቻ ሳይሆን የነበረውን መጽሐፍ አደፍርሰው፤ በጥብጠውና ከመርዝ ጋር ደበላልቀው በማቅረብ ሊቃውንት የሚባለውን ክብር ትቢያ ላይ ወድቆ እንዲቀር ማድረጋቸው ሌላው አሳዛኙ ገጽታቸው ነው። 
የሊቃውንት ጉባዔነትን ሥልጣን ተሸክመው የራሳቸውን ግዙፍ ድክመትና ስህተት በማየት ከማረም ይልቅ  የመንደር ላይ ጽሁፎችንና በራሪ ወረቀቶችን እየለቀሙ  አብረዋቸው የሌሉ ሰዎችን በማውገዝ መጠመዳቸው የሊቅነት ስያሜ  አቅጣጫው የጠፋ ይመስለናል። በየተአምሩ፤ በየድርሳኑ፤ በየገድላቱ፤ በየመጽሐፍ ቅዱሱ የተሰነቀረውንና ማን እንዳስገባው የማይታወቀውን ከእግዚአብሔር ቃል ሃሳብና ትርጉም የማይስማማውን እየመረመሩ ማስተካከል ሲገባ ሊቃውንት ጉባዔው የተኛበትን ሥራ በፈቃዳቸው ተረክበው «ይህ፤ ይህ ግድፈት ነው፤ ሊታረም ይገባል፤ የቀደምት አበው አስተምህሮ ሥፍራውን ይያዝ » በማለት በማስረጃ አስደግፈው የጠቆሙ ሰዎችን ጽሁፍ እየለቀሙ አውግዘናል ማለቱ ሊቃውንት ጉባዔው ኮምፓስ እንደሌለው መርከብ ውቅያኖስ ላይ መንሳፈፉን ራሱ አረጋግጧል። ሰዎቹ ይታረም ያሉት የተጻፈውን ስህተት አንስተው እንደ ወንጌል ቃልና እንደአበው አስተምህሮ ይታረም ማለታቸው ወንጀል ሆኖ ሊያስወግዝ ቀርቶ እኛ መሥራት ያቃተንን ስለሰራችሁልን እናመሰግናለን ሊባሉ ይገባ ነበር።
እኛም አቅማችንና ችሎቻን የፈቀደውን ያህል በመረጃና በማስረጃ አስደግፈን  ሁሉም እንዲያውቀው በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን ጠላት አስርጎ ያስገባውን የስህተት ቃል ለማሳየት እንሞክራለን። 

1/ የብቻችን መጽሐፍ እንዴት?

በባለፈው ክፍል ሁለት ጽሁፋችን ለመጠቆም እንደሞከርነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በፊት እንደትርፍ የቀኖና መጻሕፍት ትቆጥራቸው የነበሩትና ከ2000 ዓ/ም መጽሐፍ ቅዱስ ህትመት በኋላ ግን እንደዋና  የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የደመረችው የመቃብያን መጻሕፍት ሦስት ክፍሎች ከአይሁዳውያን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ቁጥር ውስጥ የሌለ መሆኑን ለማሳየት ሞክረናል። በ3ኛውና በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበሩት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከኦሪት ዘፍጥረት እስከ ትንቢተ ሚልክያስ ያሉትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በ39 ክፍል መድበው ትክክለኛ የእግዚአብሔር ቃል የሆኑ የአይሁዳውያን መጻሕፍትን ሙሉ በሙሉ መቀበላቸውም ታሪክ ያስተምረናል። ከዚህ ውጪ የአይሁዳውያን መጻሕፍት ያልነበሩትን የኦሪት መጻሕፍት እንደብሉይ ኪዳን ለመቀበል የሚያስችል ሌላ ምክንያት የለም። ለእስራኤል ዘሥጋ የተሰጡ የእግዚአብሔር ቃል መጻሕፍት ሙሉ በሙሉ በአዲስ ኪዳን ዘመን ተቀባይነት አግኝተዋል። እነዚህንም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ብለን እንጠራቸዋለን። ነገር ግን ለሕዝበ እስራኤል ያልተሰጡና በብሉይ ኪዳን መጻሕፍትነት ያልተመዘገቡ መጻሕፍት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከየት አምጥታ እንደብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ቆጠረቻቸው? ምንጫቸው ከየት ነው?  እነዚህንም በትርፍነት የያዘቻቸው በእርግጥ ለዚህ ጥያቄ መልስ የሚሰጥ የለም። ስማቸውን ዘወትር የምታነሳቸው ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን/ እነአትናቴዎስ/ የማያውቋቸውና ዛሬም ድረስ እናቴ የምንላት የኮፕት ቤተ ክርስቲያን የማታውቃቸውን መቀበላችን ለምን? ብለን መጠየቅ አግባብነት አለው። ደግሞም በዓለማችን ላይ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት በአንዱም ውስጥ የሌለ መጽሐፈ መቃብያን ለኢትዮጵያ ብቻ የተሰጠው ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር? መቼና እንዴት? ለሚሉት ጥያቄዎች በእርግጥ በቂ መልስ የሚሰጥ የለም።

2/ዲያብሎስ ከክብሩ የወደቀው ለአዳም ስገድ ተብሎ አልሰግድም በማለቱ ነው። 

መጽሐፈ መቃብያን ምንጩ ያለመታወቁ አንዱ ምክንያት የያዘው ሃሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አለመሆኑ ነው። ዲያብሎስ ከክብሩ የወረደው እግዚአብሔር ለአዳም ስገድ ባለው ጊዜ ለሚዋረድልኝ ለአዳምስ አልሰግድም ብሎ እምቢተኛ በመሆኑ ነው ይለናል። ዲያብሎስ ራሱ ይህንን ቃል ሲናገር ያዳመጠው ሰው ማን እንደሆነ ለጊዜው ባይገለጽም መቃብያን ግን የዲያብሎስን ንግግር የሰማ ያህል እንዲህ ሲል አስፍሮታል።
«የሚጠፉ በኔም የሚስቱ ሰዎች ፈጽመው ይበዙ ዘንድ የአዳምም ልጆች ይጠፉ ዘንድ ይህንን በተናገሩ ጊዜ እኔ ደስ ይለኛል። ለሚዋረድልኝ ለአዳም አልሰግድም በማለቴ እግዚአብሔር ስለአባታቸው ስለአዳም ከማዕረጌ አዋርዶኛልና« 3ኛ መቃ 1፤15

ዲያብሎስ ራሱን ከፍ ከፍ ስላደረገና አምላክነትን ስለፈለገ ከማዕረጉ እንደተዋረደ የምታስተምር ቤተ ክርስቲያን፤ የለም ዲያብሎስ የወደቀው ለአዳም ስገድ በተባለ ጊዜ አልሰግድም በማለቱ ነው የሚለውን የመቃብያን መጽሐፍ፤ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለበት የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ነው በማለት ከ 81 ዱ ጋር አዳብላ ልትቆጥረው እንዴት ቻለች? ጥያቄአችን ነው። አይሁዶቹም እንደብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ያልቆጠሩት፤ ኮፕቶችና ሌሎቹም አብያተ ክርስቲያናት የማያውቁትን ይህንን መቃብያንን ከብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ጋር እንድንደምረው የሚያስገድደን መንፈሳዊ ይዘቱ ምንድነው? ስለ ሰማንያ ወአሀዱ መጽሐፍ ቅዱስ ስንናገር አሰሱንና ገሠሡን ሁሉ በመቆጠር ሊሆን አይገባውም። የአንድ መንፈሳዊ መጽሐፍ ልኬታ ምንጩ፤ መንፈሳዊነቱ፤ ተቀባይነቱና አገልግሎቱ ካልተመዘነ የጠላት አሰራር መግባቱ አይቀሬ ይሆናል። 

3/ ሳምራውያን ትንሣዔ ሙታን የለም ብለው ያምኑ ነበር ወይ?

ስለሰዱቃውያንና ስለፈሪሳውያን ትምህርተ ሃይማኖት የምናገኘው ማስረጃ ያለው በአዲስ ኪዳን ውስጥ ብቻ ነው። ሁለቱም የካህናተ ኦሪት ወገን ቢሆኑም  ሰዱቃውያን ከሞት በኋላ ስላለው ትንሣዔም ሆነ ዘላለማዊነት በፍጹም እምነት የላቸውም። ትንሣዔም፤ መላዕክትም የለም ባዮች ናቸው። ፈሪሳውያን ግን መላእክትም፤ ትንሣዔ ሙታንም መኖሩን  ቢያምኑም ይህ የሚሆነው ለአይሁዳውያን ብቻ ነው የሚል የትምክህት አስተምህሮ ስለነበራቸው ኢየሱስ ለክርስቲያኖች እንዲህ ሲል አስጠንቅቋል።
«ኢየሱስም፦ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ አላቸው። ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ እንድትጠበቁ ብዬ ስለ እንጀራ እንዳልተናገርኋችሁ እንዴት አታስተውሉምን? እነርሱም ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን ትምህርት እንጂ ከእንጀራ እርሾ እንዲጠበቁ እንዳላላቸው ያን ጊዜ አስተዋሉ» ማቴ 16፤6-12 የአዲስ ኪዳን የትንሣዔ አዋጅ ለተወሰነ ሕዝብ ስላይደለ የፈሪሳውያንን አስተምህሮ ክርስቲያኖች መቀበል ስለሌለባቸው ከዚህ ክፉ እርሾ እንዲጠበቁ አሳስቧል። እንደሰዱቃውያንም ትንሣዔ የለም ከሚል ትምህርትም ራሳቸውን እንዲጠብቁ ጳውሎስ  ሲያስረዳ የስንዴ ቅንጣት እንዴት ፈርሳና በስብሳ  ፍሬ እንደምታፈራ ትንሣዔውን በምሳሌ ሲያስተምር «አንተ ሞኝ፥ አንተ የምትዘራው ካልሞተ ሕያው አይሆንም» 1ኛ ቆሮ 15፤36 ይለናል።
እዚህ ላይ ስለሰዱቃውያንና ስለፈሪሳውያን የትንሣዔ ሙታን እምነት ማንሳት ያስፈለገው ከላይ በቁጥር 3 ላይ ላመለከትነው የጥያቄ ኃይለ ቃል መንደርደሪያ እንዲሆነን ነው። ሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ስለትንሣዔ ሙታን ያላቸው እምነት ከላይ እንደገለጽነው የአዲስ ኪዳን አስረጂ ከሆነ ሳምራውያን የሚባሉት ሕዝቦች ትንሣዔ ሙታን የለም ያሉት መቼ ነው? ብለን እንጠይቃለን። ምክንያቱም መጽሐፈ መቃብያን ሳምራውያን ትንሣዔ ሙታን የለም ብለዋል ይለናልና። 

አጭር ታሪክ፤

ሴኬም የያዕቆብ ምንጭ ያለባት የዐሥሩ ነገድ ሰሜናዊው እስራኤል መቀመጫ ከተማ ነበረች። የሰሎሞን መንግሥት በልጁ በሮብዓም/ ሁለት ነገድ/ በኢየሩሳሌም እና በአገልጋዩ በናባጥ ልጅ በኢዮርብዓም /ዐሥር ነገድ/ በሴኬም ከተከፈለ ( 1ኛ ነገ 12፤20) በኋላ ቆይቶ የሰማርያ ታሪክ ይጀምራል። እሱም የአክአብ አባት ዘንበሪ ሳምር ከሚባለው ሰው ላይ ከሴኬም ከተማ በስተቀኝ ያለውን ተራራ በሁለት መክሊት ከገዛ በኋላ በባለቤቱ በሳምር ስም ተራራ ላይ ቤት ሰርቶ ቦታውን ሰማርያ ማሰኘቱን መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። 1ኛ ነገ 16፤24 ከተማው እያደገ፤ ሀገሩም እየሰፋ ሰማርያ ስያሜውን ይዛ ዛሬም ድረስ አለች። ሰማርያ ገሪዛንና ጌባል የሚባሉ የአምልኮ ኮረብታዎቿን ይዛ በመገኘቷ ከሁለቱ ነገድ መዲና ከሆነችው ከኢየሩሳሌም ጋር ኅብረት ያልነበራቸው ከዚያን ጊዜ አንስቶ ነበር። ስለዚህም ጌታችን ከኢየሩሳሌም ወደሰሜናዊ የገሊላ አውራጃ ለመሄድ አማራጭ መንገዱ ሩቅ ስለሆነና የመጣበትም ዓላማ ስለነበረው በዚህች ከይሁዳውያን ጋር ኅብረት ባልነበራት በሰማርያ ማለፉን እናነባለን። (ዮሐ 4፤4)

ሰማርያውያን የእግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ ስፍራ ገሪዛን ተራራ እንጂ ኢየሩሳሌም አይደለችም ከማለታቸው በስተቀር፤ የትንሣዔ ሙታንና የገነትንም መኖር ያምናሉ። ይሁን እንጂ መጽሐፈ መቃብያን የተባለው የአዲስ ኪዳኑን ታሪክ እንደብሉይ ኪዳን ዘመን ትረካ ወደኋላ ጎትቶ የሌለውን ነገር ያስነብበናል።
«ሳምራውያን ግን ሥጋችን ትቢያ ይሆናል፣ አይነሳም ይላሉ» (2ኛ መቃ 14፤1-3) እዚህ ላይ ጥያቄ የሚያስነሳው መቃብያን የተባለው መጽሐፍ በአዲስ ኪዳን የተጻፈውንና ጌታችን ያስተማረውን ታሪክ ስለሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ይዞ መገኘቱ አንዱ ነጥብ ሲሆን ትንሣዔ ሙታን የለም ያላሉትንና የማይሉትን ሳምራውያንን ከሰዱቃውያን ጋር አብሮ መጨፍለቁ ታሪኩን አስገራሚ ያደርገዋል። ምክንያቱም ሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ስለትንሣዔ በጠየቁት ጊዜ ሳምራውያን ያልነበሩ ሆነው ሳለ መቃብያን ግን ልክ እንዳሉ ቆጥሮ፤ ያልተናገሩትን ስለመናገራቸው መዘገቡ ምን ይባላል? ሳምራውያን የብሉይ ኪዳን እምነት ተከታዮች ስለትንሣዔ ሙታን ያላቸው እምነት ግልጥ ነው። መቃብያን ግን የትም ያልተጻፈውን አንስቶ ይለጥፍባቸዋል።
ዛሬ በቁጥር ከ 800 የማይበልጡ ሳምራውያን በትንሣዔ ሙታንም በመላእክትም መኖር የማመን ጥንታዊ እምነታቸውን ያልተዉ የ10ሩ ነገድ ዘሮች በሰማርያ ይኖራሉ። መቃብያን ግን ይዋሽባቸዋል። ለምን?
(ይቀጥላል)