Monday, March 26, 2012

«ማኅበረ ቅዱሳን» ከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ ደረሰበት

 ይህ ድንቅ ጽሁፍ በደጀብርሃን ሲገለጽ ለበጎች ነጻነት የተቆጣው እንስሳን  ያስታውሰናል ።
(የጽሁፍ ምንጭ፤http://dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com)
እውን "ማኅበረ ቅዱሳን" ከመንበረ ፓትርያርክ፣ ከቅዱስ ሲኖዶስና ከጠቅላይ ቤተክህነት በላይ የሃይማኖት ጠባቂ እና ተቆርቋሪ ነውን?
ግርግር ለሌባ ይመቻል፤ "ማኅበረ ቅዱሳን" የዝቋላን እሳት ለማጥፋት ለአንድ ጀሪካን ውኃ 40 ብር ለሁለቱ ደግሞ 80 ብር ያስፈልገኛል ብሏል
በዋልድባ፣ በአሰቦትና በዝቋላ ገዳማት ጉዳይ የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ዌብሳይቶችና ብሎጎች ለምን ተንጫጩ? ሌሎቹ ለምን እርጋታ ታየባቸው?
መንግሥት፣ ሃይማኖትና ቀጣዩ ልማታችን
"ማኅበረ ቅዱሳን" በቅርቡ ከገዳማት ሕይወት ጋር ተያይዞ በተነሳው ውዝግብ ከምንጊዜውም በላይ የፖለቲካ ኪሣራ የደረሰበት መሆኑን ልዩ ልዩ ምንጮች አረጋገጡ፡፡ ምንም እንኳን ሃይማኖታዊ ተፈጥሮ ባይኖረውም "ማኅበረ ቅዱሳን" የሃይማኖት ተቋም መስሎ በመንቀሳቀስ ብዙዎችን ቢያሳስትም፣ ዛሬ በፈጠረው የፖለቲካ ግጭት ከመንግሥትና ከሕግ ጋር ተፋጦ በመገኘቱ እውነተኛ ማንነቱ መጋለጡን የወቅቱ ሁኔታው ያስረዳል፡፡
ከአፈጣጠሩ ጀምሮ ከፖለቲካ አካሄድ ተላቆ የማያውቀው "ማቅ" ውስጥ ውስጡን ሲያተራምስ ከርሞ ዛሬ ሙሉ በሙሉ ራሱን በመግለጥ ፀረ ቤተክርስቲያንና ፀረ መንግሥት መሆኑን አሳይቷል፡፡ ይህ የሃይማኖት "ማኅበር" ነኝ ባይ ተቃዋሚ ድርጅት ቤተክርስቲያንን በእርስ በርስ ሁከት ሲያተራምስ ቆይቶ በአሁኑ ወቅት ቀይ መስመሩን አልፎ ከሕዝብና ከመንግሥት ጋር የሚያጋጨውን ድርጊት በመፈጸም ላይ ይገኛል ተብሏል፡፡
"ማኅበሩ" ከ40 ሺህ እስከ 80 ሺህ የሚሆኑ አባላት አሉኝ የሚል ሲሆን በመንግሥትም ሆነ በቤተክርስቲያን የአባላቱ ዝርዝር አይታወቅም፡፡ ይህ ኅቡዕ አደረጃጀቱም እጅግ አደገኛ፣ ለውንብድናም ለምለም ሁኔታን እንደሚፈጥር ልብ ይሏል፡፡ ስውር ኃይል እንደሚመራውም የማኅበሩ አመራር የሆነው ዳንኤል ክብረት እንዳጋለጠም የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚደረጉት የገንዘብ ዝውውሮቹ ቁጥጥር አይደረግባቸውም፡፡ ከዚህ የተነሳም አደገኛነቱን ማስተዋል ይቻላል፡፡
ቤተክርስቲያን ላወጣችው መመሪያ አይገዛም፡፡ በዚህም ምክንያት ተከታታይ መመሪያዎች ሲወጡበት ይታያል፡፡ በቤተክርስቲያን ስም የንግድ ፈቃድ ይወስዳል፡፡ ነገር ግን ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለመንግሥት ተገቢውን ገቢ አያስገባም፡፡ ገቢዎቹንና ወጪዎቹን ቤተክርስቲያን በምታሳትማቸው ደረሰኞች እንዲመዘግብ ቢነገረውም ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ሀብትና ንብረቱን በነፃና ገለልተኛ ኦዲተር እንዲያስመረምር ቢታዘዝም በእምቢተኝነቱ ጸንቷል፡፡ በአጠቃላይ ሲገመገም፣ የ"ማኅበሩ" አደገኛነት ሊለካ የማይችል እጅግ አስጊ ነው፡፡ ጉዳዩ ፈር እንዲይዝ ከተለያዩ አካላት ለመንግሥትና ለጠቅላይ ቤተክህነት ጥቆማ ቢቀርብም በተለያዩ ምክንያቶች ችግሩ ከመባባስ በስተቀር መፍትሔ አልተበጀለትም፡፡ "ማኅበሩ"ም ባላሰለሰ ጥፋት ውስጥ ቀጠለበት እንጂ የመታረም ዕድል አላገኘበትም፡፡
ምንም እንኳን "ማቅ" መቶ በመቶ ለጥፋቱ ተጠያቂ ነው ባንልም፣ ዛሬ ቤተክርስቲያናችን ለገባችበት ቀውስና አስተዳደራዊ መዋቅሯ ወደ ሁለትና ስምንት ቦታ መከፋፈሏ የ"ማኅበሩ" የሃያ ዓመታት እንቅስቃሴ ውጤት ግንባር ቀደም ተጠቃሽ መሆኑ አሌ አይባልም፡፡ "ማኅበሩ" ካህናትንና ምዕመናንን በተሃድሶነትና በመናፍቅነት በመክሰስ እና በራሱ ሥልጣን ዱላ ሁሉ በማንሳት ብዙዎችን ከየአጥቢያው በማባረር የግፉአንንና የስደተኞችን ቁጥር አበራክቷል፡፡

 የገንዘብ ክምችቱ ከቤተክርስቲያን አቅም በላይ በመድረሱ ሁሉንም በአሻው መንገድ የመጠምዘዝና ከሕግ በላይ የመሆን ልምምዶችን በማድረግ ዛሬ በፍጹም ሊጠየቅ ከማይችልበት አደገኛ የማፊያ አደረጃጀት ደረጃ ለመድረስ ችሏል፡፡ በ"ማኅበረ ቅዱሳን" አስተሳሰብ አሁን የሚቀረው የራሱን ፓትርያርክ መሰየምና የመንግሥትን ሥልጣን መረከብ ነው፣ ማለት ይቻላል፡፡
በ  (በመረዋ ብሎግ እንደተዘገበው)   እኛም ከዚያ ጠቅሰን ለአንባብያን እንደጠቆምነው "ማኅበረ ቅዱሳን" በዋልድባ ገዳም አሳብቦ ምን ዓይነት ስልታዊ ፀረ መንግሥት ውጊያ እንደጀመረ ማመላከታችን ይታወሳል፡፡ "ማቅ" በዚሁ ስልቱ የዋልድባ ገዳም መነኮሳትን ባልተገባና በተሳሳተ ቅስቀሳ አገልግል በማስያዝ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ መላኩንና ጽ/ቤቱም መነኮሳቱን ለምን ወዲያውኑ አላነጋገራቸውም ብሎ ሲያብጠለጥል መክረሙ ይታወሳል፡፡
እኛም ደረጃን ጠብቆ ባልመጣና ፕሮግራም ባልተያዘለት ጉዳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለምን አላናገሯቸውም? ተብለው ሊወቀሱ እንደማይገባ እና ከወረዳ ጀምሮ እስከ ፌዴራል የመንግሥት አስተዳደር አካላት እንዲሁም ከገዳሙ የበላይ ጠባቂ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ባሉ መዋቅሮች ታልፈው መመጣት እንደነበረባቸው ማስገንዘባችን አይረሳም፡፡ የሃይማኖት ጉዳይ "ማኅበረ ቅዱሳን"ን ብቻውን የሚያስጨንቀውና "የሀገር አለህ"!! የሚያሰኘው አይደለም፡፡ እንዲያውም ከእርሱ በላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤትና መንበረ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት ይመለከታቸዋል፡፡
ከአጥቢያ ሰበካ ጉባዔ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ያሉ የቤተክርስቲያን መዋቅሮች የሚያጋጥሙ ችግሮችን የመፍታት እና ከአቅም በላይ የሆኑ እና የመንግሥት እገዛ የሚያስፈልጋቸውን ችግሮችና ፍላጎቶች ወደ ተገቢው የመንግሥት መዋቅር በማቅረብ መፍትሔ የማፈላለግ ሕጋዊ እና ሃይማኖታዊ ሥልጣን አላቸው፡፡ ከዚህ ውጪ "ማኅበረ ቅዱሳን"ን ጨምሮ ማንኛውም ማኅበርም ሆነ ድርጅት ቤተክርስቲያንን ወክሎ ሊንቀሳቀስ ወይም ሌሎችን ሊጠይቅ አይችልም፡፡
ከዚህ አንፃር "ማኅበረ ቅዱሳን" የቱንም ያህል ለሃይማኖቴ ተቆርቁሬ ነው ቢልም ባልተሰጠው ሥልጣንና ውክልና ሥነ ሥርዓትን ባልተከተለ ሁኔታ ስለቤተክርስቲያንና ስለምዕመኖቿ መጮኽና መዋቅር ጥሶ ሌላውን መተቸትም ሆነ መንቀፍ አይችልም፡፡
ሆኖም፣ "ማኅበረ ቅዱሳን" ከዚህ ተቃራኒ በሆነ መንገድ ለቤተክርስቲያናችን፣ ለመንግሥትና ለሕዝብ በሚያስቸግር መልኩ እየተጓዘ ነው፡፡ ያለፉትን ወራትና ዓመታት ትተን አሁን በቅርብ ሳምንታት ውስጥ ከዋልድባ፣ ከአሰቦትና ከዝቋላ ገዳማት ጋር ተያይዞ ሲያራምዳቸው የነበሩ እንቅስቃሴዎች በሃይማኖት ረገድ ቢለኩ ፍሬቢስ፣ ከሀገር ልማትና ሉዓላዊነት አንፃር ቢመዘኑ ዋጋ የሌላቸው ተራና የሽብር ድርጊቶች መሆናቸውን እንገነዘባለን፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" በሃይማኖት ሽፋን ለሚያካሂደው ብጥብጥ እና ሁከት እንደመሣሪያ የሚጠቀምባቸው አካላት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ የግቢ ጉባዔ ተማሪዎችና ለቤተመቅደስ የቀረቡ ካህናት ናቸው፡፡ በተለይም የግቢ ጉባዔ ተማሪዎች በአፍላ ወጣትነት የዕድሜ ደረጃ ላይ ስለሚገኙ፣ ሃይማኖትህ ተደፈረችብህ፣ ተነስ፣ ታጠቅ ዝመት ካሉት ዘሎ ጥልቅ ይላል፡፡ አፍላ ወጣትነት ማለት ለነውጥ (Mob) የተመቻቸ ደረቅ ሣር ማለት ነው፡፡ ወዲያውኑ ተቀጣጥሎ ሰፊ ጥፋት ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡
ስለዘመናዊው ዓለም ብዙም መረጃ የሌላቸው፣ በወንጌሉም ረገድ የጠለቀ ዕውቀት የሌላቸውና የአስተሳሰብ አድማሳቸው ካሉበት ደብር ያልዘለለ፣ የተነገራቸውን እውነት ነው ብለው ለመቀበል እምነታቸው የሚያስገድዳቸው ካህናትና መነኮሳት ለልዩ ልዩ አፍራሽ ተልዕኮ እና ጥቅማ ጥቅም የተመቻቹ ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር ሥልጣነ ክህነቱ ያላቸው የየአደባራቱ አገልጋዮች "ማቅ" አውገዙልኝ የሚላቸውን ለማውገዝ፣ ርገሙልኝ የሚላቸውን ለመርገም፣ መርቁልኝ የሚላቸውን ለመመረቅ ምን ጊዜም ዝግጁ ናቸው፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" በሃይማኖት ሽፋን ለሚያካሂደው ብጥብጥ እና ሁከት እንደመሣሪያ የሚጠቀምበት ሌላው ግንባር ልዩ ልዩ ሚዲያዎች፣ ብሎጎችና ዌብ ሳይቶች ናቸው፡፡ ከማኅበራት ውስጥ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሕብረት አዲስ አበባ፣ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሕብረት አሜሪካ፣ ማኅበረ በዓለ ወልድ አሜሪካ፣  ከሕትመት ሚዲያዎች፣ ሐመር መጽሔት፣ ስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በግል ፕሬስ ከሚታተሙት መጽሔቶች መካከል ዕንቁ፣ ማራኪ፣ ሎሚ እና ቆንጆ የተባሉ ይገኙበታል፡፡ ከብሎጎች ደግሞ Dejeselam፣ አንድ አድርገን፣ ደቂቀ ናቡቴ፣ ገብር ኄር፣ አሐቲ ተዋህዶ፣ የተዋህዶ ቤተሰብ፣ የመሳሰሉት ሲሆኑ፣ ይህንን ሁሉ የሚያራግቡ እና የሚያጋግሉ ፌስ ቡኮች፣ ኔት ሎጎች፣ ትዊተሮች፣ በራሪ ወረቀቶች፣ ብሮሸሮች፣ ደብዳቤዎች፣ የቡድን (የአሥር-አሥር) ስብሰባዎች፣ ጠንካራ የግንኙነት መረብና አደረጃጀት (Highly Networked Communication & Organization)፣ የስልክ ግንኙነቶች፣ ቻቶች፣ የአውደ ምሕረት ላይ ቅስቀሳዎች ወዘተ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ሌላው የ"ማቅ" የጥቃት ስልትና ዐውደ ውጊያ ከላይ ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ ታች አጥቢያ ቤተክርስቲያን ያሉ አስተዳደራዊ ቁልፎችን በመቆጣጠር የሀብት፣ የመረጃና የሥልጣን ምንጩን መቆጣጠር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከሁሉም የከፋውና የቤተክርስቲያኗን ህልውና የተፈታተነ፣ የምዕመናንን አምልኮና መንፈሳዊ ሕይወት አቀጭጮ የገደለ፣ ሳጥናኤላዊ ተልእኮው ነው፡፡
ዛሬ የቤተክርስቲያን አፍ ተሸብቦ የሚሰማው ድምጽ የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ብቻ ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ስም ዕርዳታ ያሰባስባል፣ በቤተክርስቲያን ስም መግለጫ ይሰጣል፣ በቤተክርስቲያን ስም ያወግዛል፣ እራሱ መሠልጠን ሲገባው ለቤተክርስቲያን አገልጋዮችና ኃላፊዎች ሥልጠና እሰጣለሁ ይላል፡፡ ከቤተክርስቲያን በወሰደው ሀብት ደግሶ የቤተክርስቲያን አባቶችን በማብላት እንደ መታያ በማቅረብና በውለታ በማሰር የመልካም ገጽታ (Good will) ከገነባ በኋላ የወሳኝነት ቦታውን ይቆጣጠራል፡፡ ዛሬ ላይ የውሳኔ ሃሣቦችን አርቅቆ የሚያስፈጽመው ራሱ "ማቅ" እንጂ የቤተክርስቲያኒቱ የበላይ ኃላፊዎች አይደሉም፡፡ ሊቀጳጳሱ ወይም የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ራሱ የ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባል ሆኖ በመምራት ላይ ነው፤ ወይም የሚፈርመውና የሚፈጽመው "ማቅ" አዘጋጅቶ ያቀረበለትን የውሳኔ ሃሣብ ነው፡፡
ከዚህ አንፃር ቤተክርስቲያናችን በፍጹም ሁከትና ክፍፍል ውስጥ የምትገኝ ሲሆን፣ "ማኅበረ ቅዱሳን" ሥልጣኗንና መዋቅሮቿን ወርሶ የጉዞ ሀዲዷን ስታ እንድትንገዳገድ አፍራሽ ተልዕኮውን በመፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ ምንም እንኳን ቤተክርስቲያናችን የሲዖል ደጆች አይችሏትም፤ እርሷ ጸንታ ትኖራለች የሚል እምነት ቢኖረንም የ"ማኅበረ ቅዱሳን"ን እኩይ ድርጊት ንቆ መተው ደግሞ ህልውናችንን እንደሚያሳጣን ለአፍታም ቢሆን መጠራጠር አይገባም፡፡
ሌላው የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ስልት የመንግሥት መዋቅሮችን በስውር መቆጣጠር ነው፡፡ ይህ ስልት በሁለት መንገድ ይገለጻል፡፡ አንደኛው ስልት በፍትሕና ፀጥታ፣ በአስተዳደርና በፍርድ ቤት በኮሚሽንና በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ያሉ ባለሥልጣናትን የማኅበሩ አባል እንዲሆኑ አግባብቶ አባል ማድረግና ወይም አባላትን አስርጎ ማስመደብ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ አባል ባይሆኑም በእነዚህ ቁልፍ ቦታዎች ላይ ወሳኝ የሆኑ ባለሥልጣናትን በስውር ጥቅማ ጥቅም ደልሎ ቅን የቤተክርስቲያን አገልጋይ በመምሰልና በሌሎች ላይ የተዛባ መረጃ በመስጠት የበኩላቸውን ጫና እንዲያሳድሩ ማግባባት ነው፡፡
በእነዚህ ስልቶችና የብጥብጥ ባህርያት የተካነው "ማኅበረ ቅዱሳን" በያዝነው መጋቢት ወር ብቻ ምን ያህል ፀረ መንግሥትና ፀረ ቤተክርስቲያን ዘመቻዎችን እንዳካሄደ ቀጥለን እንመለከታለን፡፡
መንግሥት በወልቃይት ጠገዴ አካባቢ ከሚያካሂደው የስኳር ልማት ፕሮጀክት ጋር ተያይዞ በዋልድባ ገዳም ላይ አደጋ ሊያደርስ ነው በሚል ሽፋን ኡኡታውን ሲያቀልጥ ከርሟል፡፡ ፕሮጀክቱ የሚካሄድበት ቦታ ከገዳሙ ይዞታ ጋር እንደማይገናኝና ምንም ዓይነት ንክኪ እንደማይኖረው እየታወቀ ዓለም አቀፍ የተቃውሞ ጥሪ ሲያስተጋባ ቆይቷል፡፡ ይህ ለሀገራችን ኢትዮጵያ ዓይነተኛ ሚና የሚጫወተውና ለ50 ሺህ ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል የተባለው ፕሮጀክት ተግባራዊ እንዳይሆን የተቻለውን ያህል መንጠራራቱ አልቀረም፡፡ የገዳሙን መነኮሳት ስንቅ በአገልግል በማስያዝ የቤተክርስቲያንንና የመንግሥትን መዋቅሮች ዘሎ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ማነጋገር ለምን አልቻሉም ብሎ ቡራ ከረዩ ሲደነፋ የከረመው "ማኅበር" ማርች 5 ቀን 2012 "አንድ አድርገን" በተባለው ብሎጉ ልክ በየቤቱ ገብቶ በጭስ የቆጠረ ይመስል "ይህ በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ የሚገኝው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች የሁላችን ጉዳይ ነው ፡፡ ይህ በብዙ ሚሊየን የሚቆጠር የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች ጥያቄ ነው ፤  አቡነ ጳውሎስ ይህን ጉዳይ እንደ ቤተክርስትያኗ የበላይ ሀላፊ ሞግተው ለውጥ ያመጣሉ የሚል እምነት የለንም " ብሎናል፡፡ ፈረንጆቹ እንደዚህ ዓይነቱን አመለካከት "More Catholic than the Pope" ይሉታል፡፡ "ከመምህሩ ደቀ መዝሙሩ" እንደምንለው ማለት ነው፡፡
"ማቅ" ቀጠለና፣ በቅርቡ ማለትም ለዛሬ ሰኞ መጋቢት 17 ቀን 2004 ዓ.ም (ማርች 26 ቀን 2012) በዋሽንግተን ዲሲ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ፊት ለፊት ታላቅ ሕዝባዊ ሠላማዊ ሰልፍ እንደሚጠራ አስታውሶ በብሎጉ "በአሜሪካ ሊደረግ የታሰበው ሰላማዊ ሰልፍ... እኛስ በአዲስ አበባ መች ይሆን የምናደርገው"? በማለት ጠይቆናል፡፡ ለመሆኑ እኛ ሰላማዊ ሰልፍ የምናደርገው ምን ሆንን ብለን ነው? "ማኅበረ ቅዱሳን"ንስ የዚህ ሰልፍ አስተባባሪና የቤተክርስቲያናችን ወኪል አድርጎ ማን መረጠው? ልብ በሉ፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" በዚህ "አንድ አድርገን" ብሎጉ ላወጣው ዘገባ ስሙን ያልገለጸ አንባቢ (የብሎጉ ጸሐፊ ሊሆንም ይችላል) በሰጠው አስተያየት "ከዚህ በላይ ምን ሊምጣ ነው። ይህ መንግስትና ቅዱስ ፓትሪያልኩ ይህችን ቤተክርስቲያ አያደሙ አንዲኖሩ መፍቅድ መቆም ያልበት ይምስለኛል። ዛሬ ህዝበ ክርስቲያኑ በአንድ መንፈስ ሆኖ ለቤተክርስቲያ መቆም ያለበት ሲሆን አነርሱንም በቃችሁ ማለት አለብን። ከፓርቲ በፊት ቤተክርስቲያንን ማስቀድም ያለብን ጊዜ ላይ ደርሰናል በቤተክርስቲያ ላይ ስለሚደርሰው በደል ፍራቻችንን አናስወግድና ሁሉን አንጋፈጥ። የአባቶቻችን አምላክ ይርዳን" በማለት ቅስቀሳ አድርጓል፡፡
ሌላው አንባቢ "ሁሉም ነገር አብቅቷል፡፡ ኢትዮጵያ አዝና እየተከዘች ነው፤ ወንድ ጠፋ፤ የወላድ መካን፣ እንባዋን ማን ይጥረግ"? ብሎናል፡፡ ኢትዮጵያ የጨለማውን ዋሻ አልፋ ብርሃን ማየት ስትጀምር ነው የምትተክዘው? በሺህ ትውልዶች ያልተሞከረው የዓባይ ግድብ ስለተጀመረ ነው የምታዝነው? የኤክስፖርት መጠን በዓይነትና በመጠን ስለጨመረ ነው የወላድ መካን የሆነችው? በአፍሪካና በዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ መስክ ተደማጭነቷ ስለጨመረ ነው እንባዋን የሚጠርግ የጠፋው? ባልተነካ ዋልድባ ገዳም፣ የወንድ ያለህ!! "ኧረ ጥራኝ ደኑ"፣ "ኧረ ጥራኝ ዱሩ" ማለትን ምን አመጣው?
ሌላው አንባቢ የ"ማኅበረ ቅዱሳን"ን አቋም ይበልጥ በግልጽ ለማሳየት "ኧረ ጎበዝ ተባብረን ይህን መንግሥት እንጣል፡፡ ዛሬ ነገ ሳይባል አዲስ አበባም፣ የየክፍለ ሀገሩ ከተማም፣ ማንጻት አለብን፡፡ ሌላ ወሬ ይቅርና ወደ ትግሉ እናምራ" ብሎናል፡፡  አንድ አንባቢ ደግሞ "we have to be one & fight this non sense government wisely"!!!  በማለት መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡ ትርጉሙም፣ "አንድ ሆነን ይህንን የማይረባ መንግሥት በስልት መዋጋት አለብን" የሚል ነው፡፡ ይህ ቅስቀሳና አጀንዳ ሃይማኖታዊ ነው ወይስ ፖለቲካዊ? "ማኅበረ ቅዱሳን" ሃይማኖታዊ ነው ፖለቲካዊ ድርጅት? መልሱን ያገኙ ይመስለናል፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" ማርች 16 ቀን 2012 በዚሁ አንድ አድረገን ብሎጉ ሁኔታውን በማካረር የዋልድባ መነኮሳት "ራሳችንን ለሰይፍ አዘጋጀተን የተቀመጥን ሰዎች ነን" ብለዋል በማለት ዘግቦልናል፡፡ ጉዳዩን ለማጣራት ወደ ሥፈራው የሄዱት የቤተክህነት ተወካይ መነኮሳቱን "እንዴት ይህን ጉዳይ እኛ ሳናቀው የግል መገናኛ ብዙሀን ጋር ይዛችሁ ትሄዳላችሁ ይህ አግባብ  ነው  ወይ? የሚል ጥያቄ" ማቅረባቸውን የነገረን ሲሆን የዋልድባው  አንድ አባት ‹‹መንግስት ለመገናኛ ብዙሀን የመፃፍም ሆነ የመናገር መብት እስከሰጣቸው ድረስ እኛ ጉዳዩን የፈለግነው ጋር ይዘን እንሄዳለን ፤ መብታችን ነው›› የሚል መልስ ሰጥተዋል ብሎናል፡፡ አያይዞም፣ " መገናኛ ብዙሀን የህዝብን ድምጽ ተቀብሎ ለህዝብ እንዲያደርስ ፍቃድ የተሰጠው  ህጋዊ ተቋም ነው ፤ እኛ ምንም ያጠፋነው ነገር የለም ፤ ቤታችን ሲፈርስ መሬታችን ሲታረስ እያየን ቤተክርስቲያንን መጠበቅ አይጠበቅብንም፡፡ ‹‹ነጻ ሚዲያ እስካለ ድረስ ጉዳዩን ነጻ ሚዲያ ላይ ማውጣት ህገ መንግስታዊ መብታችን  ነው››  መባላቸውን  አስረድቶናል፡፡
በዘገባው መሠረት በመነኮሳቱና በቤተክህነቱ ተወካይ አባት የተደረገው ቃለ ምልልስ በትክክል የተፈጸመ ነው ብለን ብናምን እንኳን፣ ይህ ሃሣብ በመነኮሳቱ አርቆ ሃሣቢነት የተሰነዘረ ነው የሚል እምነት የለንም፡፡ ተወካዩ አባት የጠየቁት ጥያቄ እኛ እንድናውቀው ለምን አልተደረገም? እኛ እንድናውቀው ሳይደረግስ ወደ ብዙሃን መገናኛ ለምን ሄዳችሁ ብለው የሰነዘሩትን ጥያቄ "አንድ አድርገን" ብሎግ እንደ ስሕተት ቆጥሮት ወደ ግል ሚዲያ (ብዙሃን መገናኛ) ለምን ሄዳችሁ ብለው የጠየቁ አስመስሎ አቅርቦታል፡፡ በመሠረቱ በማንኛውም ደረጃ የሚገኝ የቤተክህነት ጽ/ቤት ለነገሩ ባይተዋር ሆኖ ከብዙሃን መገናኛ መስማቱ በፍጹም ትክክል አይሆንም፡፡ ይህ ብቻም አይደለም "አንድ አድርገን" ብሎግ ሊነግረን የፈለገው ስለ ግል ፕሬሱ ነፃነት ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ደግሞ "ማኅበረ ቅዱሳን" ፀረ መንግሥት ትግል ከሚያካሂድባቸው ስልቶች አንዱ ሆኖ እንጂ የዋልድባ መነኮሳት ስለ ግል ፕሬሶች ሕገ መንግሥታዊ መብት ገብቷቸውና ተቆርቁረው እንዳልሆነ በገሃድ የምናውቀው ነው፡፡
በመቀጠልም "ከቤተክህነት የተወከሉ ሰው የዋልድባው አባት በሰጡት ሀሳብ ላይ ይህ የቤተክርስትያ አስተምህሮ አይደለም  ፤ ጉዳዩን አንድ ላይ ሆነን ነበር መንግስት ዘንድ ማቅረብ የነበረብን ሲሉ ፤ ‹‹ እናንተማ ቤተክርስትያኗን ለመንግስት አሳልፋችሁ ለመስጠት ፤ ከመንግስት ጎን ተሰልፋችሁ መጣችሁ ይህን ጉዳይ ከናንተ ጋር ሆነን መንግስት ዘንድ ይዘን መቅረብ አንችልም ፤ እናንተ ሲጀምር ለቤተክርስትያን ህልውና የቆማችሁ አይደላችሁም›› ተብለዋል፤  ከተሰብሳቢ አባቶች በኩል ተገቢ አፍ የሚያስይዝ መልስ ተሰቷቸዋል" በማለት ዘግቦልናል፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ በዋልድባ መነኮሳት ካባ ውስጥ ተሸሽጎ የቤተክህነቱን አባት ያነጋገረው ከጎንደር ወይም ከአዲስ አበባ የተላከ የማኅበረ ቅዱሳን አርበኛ እንደሆነ ምንም አያጠራጥርም፡፡ የበቃ መነኩሴ ይቅርና በዘልማድ ቤተክርስቲያን የሚመላለስ አንድ ክርስቲያን እንኳን ከቤተክህነት ለመጣ እንግዳ ካህን አፍ የሚያሲይዝ  እና እንደዚህ ዓይነት ጋጠ ወጥ መልስ አይሰጥም፡፡
አንድ አድርገን በተለመደው የቅስቀሳ ዐምዱ ነውጠኛ አስተያየትን አስተናግዷል፡፡ እንዲህም ይነበባል "THEIR IS ONE IMPORTANT THING THAT ETHIOPIANS NEVER UNDERTAND.THERE SHOULD BE AN EQUIVALENT AND OPPOSITE REACTION FOR A CERTAIN ACTION.THIS IS NEWTON'S LAW.A NATURAL LAW.I CAN RECOMMEND A REACTION LIKE BURNING THE TRACTORS PLAUGHING, BURNING CAMPS, ASSASINATING THE DECISION MAKING PEOPLE, ABDUCTING THEIR FAMILY MEMBERS ETC... PROVIDED THAT THERE ARE PEOPLE WILLING TO SACRIFY FOR A SPECIFIC PURPOSE.SOME ONE IS NOT NOT SUPPOSED TO HAVE A GUN TO DO THESE.ELSE,WE WILL SEE THAT EVERYTHING WILL BE DONE AS PLANNED BY THE GOV'T BY ARRESTING SOME OF THE OPPOSING LEADERS". ሲተረጎም፣ "ኢትዮጵያውያን ያልተረዳነው አንድ ጠቃሚ ነገር አለ፡፡ ለእያንዳንዱ እንቅስቃሴ ተመጣጣኝ የተቃርኖ እርምጃ አለ፡፡ ይህ የኒውተን የተፈጥሮ ሕግ ነው፡፡ ለዚህ ልዩ ዓላማ ራሳቸውን ለመሰዋት ፈቃደኞች ሰዎች መኖራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ይህንን የተቃርኖ ሕግ የሚያርሱትን ትራክተሮች በማጋየት፣ ካምፖችን በማቃጠል፣ ውሳኔ ሰጪዎችን በማስገደል፣ የቤተሰብ አባላቶቻቸውን ጠልፎ በማገት፣ ተግባራዊ እንድናደርገው እመክራለሁ፡፡ ማንም ሰው ይህንን፣ ለመፈጸም የግድ ጠመንጃ አያስፈልገውም፡፡ ይህንን ካላደረግን ግን፣ የተቃዋሚ መሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ሁሉም ነገር መንግሥት ባቀደው መሠረት ይከናወናል"፡፡
ይህ ቅስቀሳ ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" የማፊያ ባህርያቱ የመነጨ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ በጽሑፋችን መጀመሪያ አካባቢ  እንደገለጽነው "ማኅበረ ቅዱሳን" ሃይማኖታዊ ተቋም አይደለም፡፡ ከ40 ሺህ እስከ 80 ሺህ የ"ማቅ" አባላት ስም ዝርዝር በጠቅላይ ቤተክህነትም ሆነ በመንግሥት የማይታወቅ፣ የሀብት ምንጩ እና የገንዘብ ዝውውሩ በግልጽ የማይዳሰስ፣ ማፊያ ድርጅት ስለሆነ ለሕዝባችን፣ ለመንግሥትና ለሀገራችን ሠላምና ፀጥታ ስጋት ነው በማለት በተደጋጋሚ የምናሳስበውም ከዚህ የተነሳ ነው፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" በጠመንጃ አለመታገሉ እና የአጥፍቶ መጥፋትን ስልት ካለመከተሉ በስተቀር ከአልሸባብ፣ ከታሊባን ወይም ከአልቃይዳ የተለየ አደረጃጀት ወይም ርዕዮተ ዓለም የለውም፡፡ እነዚህ ቡድኖች እኮ ሃይማኖተኞች ነን ይላሉ ግን መንፈሳዊነት አይታይባቸውም፡፡ የእስልምናውን ሃይማኖት እኛ ነን የምንመራው በማለት በኡለማዎች ቦታ ቁጭ ብለው ይፈርዳሉ፡፡ የአስተዳደር መዋቅሮችን በመቆጣጠር ሁሉም ነገር በእነርሱ ፈቃጅነነትና አመራር ሥር እንዲያልፍ ይፈልጋሉ፡፡ በመንገዳቸው የሚቆመውን ማንኛውንም አካል ከማስወገድ ወደ ኋላ አይሉም፡፡ ለሌላው ሃይማኖት፣ እምነትና አማኞች ያላቸው አመለካከት ፍጹም ግትር እና ለመቻቻል ዕድል የማይሰጡ ናቸው፡፡ የፖለቲካውን አመራር በመጨበጥ የመንግሥትን ሥልጣን ወደ ራሳቸው እጅ የማስገባት ጠንካራ ፍላጎት አላቸው፡፡
የዋልድባ ጉዳይ በእንዲህ እንዳለም በዝቋላ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ድንገተኛ ሰደድ እሳት በመነሳቱ ለ"ማኅበረ ቅዱሳን" አቧራ ማስነሻ አጋጣሚን ፈጥሮለታል፡፡ በየገዳማቱና በየአደባራቱ ለሚነሱ ቃጠሎዎች የሌሎች ቤተእምነቶች ተከታዮችንና የሃይማኖት ተቋማትን እንዲሁም መንግሥትን የሚጠረጥረውን ያህል እኛም ራሱን "ማኅበረ ቅዱሳን"ን እንጠረጥረዋለን፡፡ ምክንያቱም ለገንዘብና ለቁስ ዕርዳታ መለመኛ ያደርጋቸዋልና ነው፡፡ ለምሳሌ በዚሁ ሰሞን ማርች 20 ቀን 2012 Dejeselam በተባለው ትዊተር ገጹ "የዝቋላን ቃጠሎ ለመከላከል ዓለም አቀፍ ድጋፍ ተጀምሯል፡፡ በሰሜን አሜሪካ እና በአውሮፓ የሚኖሩ ኦርቶዶክሳውያን የገንዘብ አስተዋፅኦ እያደረጉ ነው"ብሎ ነግሮናል። እውን በቤተክርስቲያን ስም የሚሰበሰበው ገንዘብና ቁስ በትክክል ለቤተክርስቲያን ይውላል? ከልምድ እንዳየነው በፍጹም አይውልም፡፡ "ማኅበረ ቅዱሳን" በቤተክርስቲያን በሚነሱ ችግሮች ዙሪያ ዕርዳታ ለመሰበሰብና ማናቸውም እንቅስቃሴ ለማድረግ፣ ለመክሰስም ሆነ መልስ ለመስጠት ምንም ዓይነት ውክልና የለውም፡፡ ይሁን እንጂ እያደረገ ያለው ሥልጣንና ደረጃውን አልፎ ነው፡፡
ይኸው ትዊተር ገጽ ስለ ማቅ በዕርዳታ አሰባሰብ ረገድ ያቀረበው ዘገባ እንዲህ የሚል ነው፡፡ "በሰሜን አሜሪካ የማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል፣ በሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ እና በማኅበረ በዓለ ወልድ አስተባባሪነት ‹‹በዝቋላ ገዳም እና አካባቢው  ደን ላይ የተነሣውን እሳት ለማጥፋት ለሚደረገው ጥረት የግል ልገሳዎን ይስጡ›› በሚል ርእሰ ጉዳይ በተካሄደው የኦርቶዶክሳውያኑ የስልክ ጉባኤ አስቸኳይ የገንዘብ አስተዋፅኦ የማሰባሰብ ሥራ እንዲሠራ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ዓላማውም፡- ‹‹በአሁኑ ወቅት እሳቱን ለማጥፋት ከየአካባቢው በነቂስ ለወጣው ኢትዮጵያዊ ወገናችን ጉሮሮውን ማርጠቢያ ውኃ፣ ጉልበቱን መደገፊያ ዳቦ ማቅረቢያ እንዲሆን የታሰበ ነው። በባዶ እጁ፣ በቅጠል እና በአፈር ቋያ እሳት ለማጥፋት እየታገለ ላለው ወገን አለኝታነታችንን ለመግለጽ›› መሆኑ ተገልጧል፡፡ በመሆኑም ለጥረቱ በጎ ፈቃድ ያላቸው የቤተክርስቲን ልጆች ሁሉ በተከታዩ አድራሻ  በዋናው ገጹና እና በሌላኛው ገጹም በድረሱልኝ ጥሪው    በመግባት ልገሳ እንዲያደርጉ ጥሪ ተላልፏል"፡፡
ይህ ብቻም አይደለም "አሐቲ ተዋህዶ" የሚባለው የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ሌላው ብሎግ በበኩሉ እንደዘገበው በሰሜን አሜሪካን የሚገኙት ሦስት ማኅበራት ማለትም "ማኅበረ ቅዱሳን" እና እርሱ በአምሣሉ የፈጠራቸው "ማኅበረ ወልድ" እና "የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ማኅበር" በአህያ አጓጉዞ የዝቋላን እሳት ለማጥፋት ለአንድ ጀሪካን ውኃ 40 ብር ለሁለቱ ደግሞ 80 ብር ያስፈልጋል በማለት ዕርዳታ በማሰባሰብ ላይ ናቸው፡፡ እንግዲህ ይህንን ሀገር ያካለለ ሰደድ እሳት ለማጥፋት በጥቂቱ 1 ሚሊዮን ጀሪካን ውኃ ቢያስፈልግ፣ 40 ሚሊዮን ብር በቀላሉ ታፈሰ ማለት ነው፡፡ ይህ ብቻም አይደለም 1 ሚሊዮኑን ውኃ ቦታው ላይ ለማድረስ ስንት አህያ፣ ስንት መቶ ሺህ ሰው እንደሚያስፈልግ፣ ይህንን በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ ለማንቀሳቀስ ምን ያህል የትራንስፖርትና የሎጂስቲክ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ካሰባችሁ በኋላ ለአንድ ጀሪካን ውኃ 40 ብር ከተጠየቀ ለአንድ ሰው የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ ድጋፍ ምን ያህል ሊጠየቅ እንደሚችል ገምቱት፡፡ በሰው መጨናነቅ መካከል ስንት ጀሪካን ውኃ እንደሚቀዳ፣ ከእሳቱ ፍጥነትና ከግርግሩ ጋር በዓይነ ኅሊናችሁ ሳሉት፡፡ ከሁሉም በላይ፣ አህያዋ እየቃተተች እሳቱ አለበት አቀበት ድረስ እሰከምትደርስ በነፋስ ኃይል እየተወረወረ የሚገሰግሰው እሳት ቆሞ ሲጠብቃት ይታያችሁ፡፡
በዕርዳታ መሰብሰብ ሰበብ በአሜሪካ የሚገኙ ምዕመናንን ያነጋገረው "ማኅበረ ቅዱሳን" እግረ መንገዱንም የፖለቲካ ሥራውን ሲያካሂድ "በሌላ በኩል በገዳማት ህልውና ላይ የተጋረጠው አደጋ ኦርቶዶክሳውያንን በዓለም አቀፍ ደረጃ አገናኝቶ እያነጋገረ ነው፡፡ ትናንት ቀንም ማታም በሰሜን አሜሪካ የሚኖሩ ምእመናን ባካሄዱት የቴሌ ኮንፍረንስ በገዳማት አጠቃላይ ህልውና ላይ የተደቀነው  አደጋ ከፍተኛ ቁጣ መቀስቀሱን ተረድተናል፡፡ መንግሥት ከሚወተውተው የልማት አጀንዳ ባሻገር የቤተ ክርስቲያንንም ድምፅ መስማት እንደሚገባው ምእመናኑ አሳስበዋል፡፡ ወቅቱ የሚጠይቀው ሰማዕትነትም የቤተ ክርስቲያንን መብት የሚጋፉ የማንኛውም አካል ርምጃዎችን በጋራ መከላከል፣ መግራትና ማስወገድ መሆኑን በድርቡ ተሰምሮበታል" ብሎናል፡፡
አንደኛ፣ መንግሥት ስለ ልማት የሚያካሂደው ቅስቀሳ "ውትወታ" ይባላል ወይ? ሁለተኛ፣ የዝቋላ ደን ቃጠሎ በሰደድ እሳት የተነሳ ነው ብለን ብናስብ፣ ከፍተኛ ቁጣ ሊቀሰቅስ ይገባዋል? ጥያቄው እሳቱ ለምን ቶሎ አልጠፋም ከሆነ፣ በአውስትራሊያ እና እዚያው በአሜሪካ ካሊፎርኒያ፣ አላስካና በኮሎራዶ ስቴቶች ስንት ጊዜ ትልቅ ውድመት ያስከተሉ የሰደድ እሳት አደጋዎች ተከስተዋል? ለዚያውም ቃጠሎዎቹን በኤሊኮፕተር ምልልሶችና በእሳት አደጋ መከላከያ መኪናዎች ጭምር ለማጥፋት ተሞክሮ ከአቅም በላይ ሆነው ለወራት አልዘለቁም ወይ? ሆኖም፣  የዝቋላው ቃጠሎ ሆን ተብሎ በሰዎች የተለኮሰ ነው የሚባል ከሆነ "ማኅበረ ቅዱሳን" የሰዎቹን ማንነትና ምንጩን ያውቃል ማለት ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ ምዕመናንን ሰብስቦ የፖለቲካ ዓላማውን ለማራመድ ተጠቅሞበታል፡፡

"ማኅበረ ቅዱሳን" የዝቋላን እሳት አስመልክቶ ማርች 19/2012 "አሐቲ ተዋህዶ" በሚባለው ብሎጉ "የዝቋላ ገዳም ቃጠሎ ማምሻውን በቁጥጥር ስር መዋሉን የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ገለጸ" በሚል ርዕስ ባሰተላለፈው ዘገባ "ለሁለት ተከታታይ ቀናት እየተቃጠለ የሚገኘው የዝቋላ ገዳም በቁጥጥ ስር እንደዋለ የመንግስት መገናኛ ብዙኃን( ሚድያ) ማምሻውን ገልጾዋል" የሚል ዐረፍተ ነገር በጽሑፉ መጀመሪያ ላይ ከማስቀመጡ በስተቀር፣ የዘገባውን አርዕስት ሙሉ በሙሉ የተጠቀመበት መንግሥትንና ቤተክህነትን ለመንቀፍና ለመቃወም ነው፡፡ አንዳችም ነገር ስለቃጠሎው ስፋት፣ ስላስከተለው ጉዳት፣ ከገዳሙ በምን ያህል ርቀት ላይ እንዳለ፣ ወዘተ. . . የገለጸው ነገር የለም፡፡ ቴሌቪዥኑ ያሠራጨው ዘገባ ተጠቅሶ መተንተን ነበረበት ወይም ፀሐፊው አርዕስቱን ቀይሮ "መንግሥትና ጠቅላይ ቤተክህነት ለዝቋላ ቃጠሎ ተገቢውን ትኩረት አልሰጡትም" በሚል አርዕስት ቢያቀርበው ይሻል ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ የተፈለገው ሁለቱን አካላት መተቸት ስለሆነ የዜናው አርዕስትና ይዘት ሊለያዩ ችለዋል፡፡ይህ ደግሞ በአንባብያን የንባብ መብት ላይ መቀለድና የኅሊና ስርቆት ነው፡፡
እዚህ ላይ ሳይጠቀስ ሊታለፍ የማይገባው "ማኅበረ ቅዱሳን" በኃላፊነትና በተጠያቂነት ስሜት የማይጓዝ መሆኑን ነው፡፡ ከዝቋላ ገዳም ሰደድ እሳት ጋር ተያይዞ ከናዝሬትና ከአዲስ አበባ የግቢ ጉባዔ ተማሪዎችን ባንቀሳቀሰበት ወቅት ምንም ዓይነት ሕጋዊ ፕሮሴጀር (ሥርዓት) ያላሟላ ሲሆን በፖሊስ ሥራ ላይም ጫና አሳድሯል፡፡ የ"ማቅ" ሠራዊት ሕጋዊነት ይኑርህ ሲባል ያበሳጨዋል፡፡ በፌስ ቡክ ባሠራጨው ማስታወቂያም "የዝቋላ እሳትን ለማጥፋት የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ተማሪዎች ለመሄድ ተነስተው ትራፊክ ፖሊስ በጭነት መኪና መሄድ አትችሉም ብሏቸው በቁጭት ላይ ናቸው" በማለት ቀስቅሷል፡፡ ደግነቱ መልሱን እርሱ ራሱ መልሶታል፡፡ ለመሆኑ መኪናው ተማሪዎችን ጠቅጥቆ ይዞ በፍጥነት ሲበር ቢገለበጥ ተጠያቂ የሚሆነው ማነው? የመኪናው ባለንብረት? ሾፌሩ? "ማኅበረ ቅዱሳን"? ዩኒቨርሲቲው? ትራፊከ ፖሊስ ጽ/ቤቱ? የገዳሙ አስተዳደር? ወላጆች? ወይስ ተማሪዎች ራሳቸው?
"ማኅበረ ቅዱሳን" ለቤተክርስቲያናችን ገዳማትና አድባራት እኔ ነኝ ያለሁላቸው፡፡ ሌላው (ጠቅላይ ቤተክህነትን ጨምሮ) ኃላፊነት የማይሰማው ነው፡፡ ለዋልድባም ሆነ ለዝቋላ ገዳማት እኔ ነኝ የደረስኩላቸው፤ በ Dejeselam በኩል አብሪ ዜና ለቪኦኤ ጭምር ያሠራጨሁት እኔ ነኝ፤ እኔ ባልኖር ኖሮ እሳቱ መላዋን ኢትዮጵያን ያዳርስ ነበር በሚል መልኩ ፕሮፖጋንዳውን ሲያናፍስ ከርሟል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ በእሳት ማጥፋቱ የተቀናጀና ውጤታማ ሥራ የተሠራው በፈዴራልና ልዩ ኃይል ፖሊስ ነው፡፡ የአካባቢው ኅብረተሰብ አስተዋፅዖም እንዳለበት ሳይዘነጋ፡፡ በዚህ ውስጥ የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ሚና ኢምንት ነው፡፡
ለአባላቱ የሥነ ምግባር መመሪያ ያላዘጋጀው "ማኅበረ ቅዱሳን" በብዙሃን መገናኛ ጋዜጠኛ ላይ የኃይል ጥቃትና የመሣሪያ ዝርፊያ ሊፈጽሙ ሲሉ ሦስት የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እግሮቻቸው በጥይት ተመተው መቁሰላቸውንና ወደ ሆስፒታል መላካቸውን Dejeselam እና አሐቲ ተዋህዶ የተባሉት ልሳኖቹ ማርች 20/2012 ባሠራጩት ዘገባ አረጋግጠዋል፡፡ ስለግጭቱ ዝርዝር ሲያሰረዱም፣
"እንደ ዐይን እማኞች ገለጻ ተስፋዬ ፈቃዱ ቡራዩ የተባለው ጋዜጠኛ ቃጠሎው በቁጥጥር ሥር እንደ ዋለ የቀጥታ ዘገባ እያስተላለፈ ነበር፡፡ ዘገባውን የሰሙት ተማሪዎች ጋዜጠኛው የተሳሳተ መረጃ እያስተላለፈ በመሆኑ እንዲያስተካክል ያሳስቡታል፤ መታወቂያውን ይጠይቁታል፤ ካሜራውም እንዳይቀርጽ ይከላከሉታል፤ በዚህም አለመግባባቱ በመካረሩ ግርግር ይፈጠራል፡፡
ጋዜጠኛውን አጅበው የመጡት 10 የኦሮሚያ ፖሊስ አባላትም ጥይት ይተኩሳሉ፤ በዚህ መካከል ነው ሦስቱ ተማሪዎች ተመትተው የቆሰሉት፡፡ ሁሉም ተማሪዎች የቆሰሉት ከጉልበታቸው በታች ሲሆን የአንደኛው ተማሪ ከባድ መሆኑ ተገልጧል፡፡ ወጣቶቹ በአዳማ ዩኒቨርስቲ የሦስተኛ እና የአራተኛ ዓመት የኤሌክትሪካል እና መካኒካል ኢንጂነሪንግ ተማሪዎች የሆኑና የማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤ አባላት ናቸው" በማለት ሐቁን አፍርጠዋል፤ እናመሰግናለን፡፡
ጋዜጠኛ በቦታው ላይ ሆኖ የሥራ መደብ ግዴታውን በመወጣት ላይ ሳለ ትክክል አይደለህም፤ እንዲህ አድርገህ ዘግብ ብሎ ትዕዛዝ ሊሰጠው የሚችል ማነው? ማንም ተነስቶ ሐኪሙን እንዲህ አድርገህ መርፌ ውጋ፣ ዳኛውን እንዲህ አድርገህ ፍረድ፣ ፓይለቱን እንዲህ አድርገህ አብርር የሚል ማነው? የ"ማቅ" ሠራዊት  ያደረገው ግን ይህንኑ ነው፡፡ 
ምናልባት ጋዜጠኛው ችግሩን አንኳሳል፣ አጋኗል ወይም ዋሽቷል ቢባል እንኳን በርካታ የማስተባበያ አማራጭ ሚዲያዎች አሉ፡፡ በዚያ በኩል ማስተባበል ይቻል ነበር፡፡ ክስተቱ ለ"ማኅበረ ቅዱሳን" ቡችሎች ሥልጣንንና የኃላፊነት ወሰንን በአግባቡ አለመረዳት የሚያስከትለው ውጤት ከንድፈ ሃሣብ ይልቅ ተግባር ላይ ያተኮረ ትምህርት ሆኖ እንደሚያስተምራቸው ይገመታል፡፡
በዚህ የገዳማት ጉዳይ ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" በተጻራሪ ያሉ ዌብሳይቶችና ብሎጎች በተረጋጋና በማስተዋል መጓዝን መርጠዋል ለምን? አባ ሠላማ፣ ደጀ ምሕረት፣ ደጀ ብርሃን፣ ዐውደ ምሕረት፣ Dejeselaam፣ ቤተ ጳውሎስ፣ መረዋ እና ሌሎችም ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" የ"ድረሱልኝ" ጩኸት ጀርባ ያለውን ስውር ተንኮል አጥብቀው ይረዳሉ፡፡ ለአንድ ጀሪካን ውኃ 40 ብር ያስፈልገኛል የሚለውን ተረታ ተረት በማቅረብ የሕዝብንና የቤተክርስቲያንን ሀብት ለመዝረፍ የሚያስችል የድፍረት አቅም የላቸውም፡፡ ጠቅላይ ቤተክህነት ካስተባበረ የቤተክርስቲያኗ አማኞች ብቻ ሳይሆኑ እንደ ሀገር ሀብትና ቅርስም ሌሎች ዜጎችም በማጥፋቱ ዙሪያ እንደሚረባረቡ ይረዳሉ፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" እንደሚያስወራው መንግሥት ዋልድባ ገዳምን ሆን ብሎ ሊያጠፋውና ሊያርሰው ተነስቷል የሚለውን ፕሮፖጋንዳ ማናፈስና በተቀሰቀሰው አቧራ ውስጥ ዜጎች በግጭት እንዲተረማመሱ አይፈልጉም፡፡ ሁሉም ድርሻውን በኃላፊነት ስሜት ይወጣል ብለው ያምናሉ፡፡ ችግሩ አለ ቢባል እንኳን የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ጩኸት ይፈታዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ለቤተክርስቲያናችን በሕግ የታወቀ አስተዳደራዊ መዋቅር አላት፡፡ ሁሉም ችግሮች በተዋረድ ከመንግሥት አካላት ጋር በመወያየት ይፈታል የሚል ጽኑ እምነት አላቸው፡፡
"ማኅበረ ቅዱሳን" የቤተክርስቲያንን አስተዳደር ተክቶ ዘመቻ እንዲያስተባብር፣ እንዲሳደብ፣ እንዲወቅስ፣ እንዲከራከር፣ ዕርዳታና መባዕ እንዲያሰባስብ ማንም ውክልና አልሰጠውም፤ አይሰጠውምም፡፡ ማንኛውም እንቅስቃሴው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንንና 50 ሚሊዮን የሚሆኑ የቤተክርስቲያኒቱ ምዕመናንን አይወክልም፡፡ በሀገራችን የሃይማኖቶች መቻቻል እንዳይኖር ጽንፈኝነትን በማራመድ እና ፖለቲካ ውስጥ በመዘፈቅ ለሚያደርሰው ጥፋት ብቸኛ ተጠያቂው "ማኅበረ ቅዱሳን"ና ቡችሎቹ ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር ምንጊዜም ከሕጋዊው የቤተክርስቲያን አመራር ጋር የሚጓዙ ሲሆን "ማኅበረ ቅዱሳን" ለሚያወጣው መመሪያ የመታዘዝና ጉንጭ አልፋ ጩኸቱን እንደ ገደል ማሚቶ የማስተላለፍ ሞራላዊ ውድቀት የለባቸውም፡፡
የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ዌብሳይቶች፣ ብሎጎች፣ ጋዜጦችና መጽሔቶች ዓላማ ስለ "ማኅበረ ቅዱሳን" ገድል ማውሳትና ስሙን ከጠቅላይ ቤተክህነት፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ፣ ከመንበረ ፓትርያርክና ከቤተክርስቲያን በላይ ከፍ፣ ከፍ፣ ከፍ ማድረግ ነው፡፡ የመንግሥትን የልማት ፖሊሲ መቃወምና የተቃዋሚዎችን ተልዕኮ ማስፈጸም ነው፡፡ በመባዕና በዕርዳታ ስም ከሕዝብና ከቤተክርስቲያን ሀብት አሰባስቦ ተጠያቂነት በሌለው መንገድ ገንዘቡን ለውንብድና ዓላማ እንዲውል ማመቻቸትና መቀሰስቀስ ነው፡፡
እንደ ብሎጋችን አቋም ምንም እንኳን መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገቡም የሚለው ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ ቢኖርም፣ መንግሥት በሃይማኖት ሽፋን እየተንቀሳቀሱ የሕዝቡን ሠላም የሚነሱ ቡድኖችን የሃይማኖት ጉዳይ ነው ብሎ በቸልተኝነት መመልከት አለበት የሚል እምነት የለንም፡፡ የሃይማኖት ተቋማትም መንግሥት ለሕዝብ አንድነትና ለሀገር ልማት ጥሪ ሲያቀርብ የመንግሥት ጉዳይ ነው ብለው በቸልተኝነት ማየት አለባቸው የሚል እምነት የለንም፡፡ ከዚህ አንፃር መንግሥትና የሃይማኖት ተቋማት ሕዝባቸውን ሲመሩ በመናበብና በመደጋገፍ መሆን እንዳለበት ጽኑ እምነታችን ነው፡፡
ስለዚህ፣ መንግሥት ምንጊዜም የተፈጥሮ አካባቢና የሀገር ቅርስ ደህንነትንና የዜጎችን እኩል ተጠቃሚነትን  ባረጋገጠ መልኩ የጀመረውን ልማት እንዲያፋጥን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት አማንያንም ከመንግሥት ጎን በመቆም የተጀመሩትን የልማት እንቅስቃሴዎችን በመደገፍ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ እና መጪው ትውልድም "ድህነቴ  ይሻለኛል" ብሎ በባዶ እምነት የሚኮፈስ ዜጋ ሳይሆን፣ ሠርቶ ለምቶ እግዚአብሔርን የሚያከብር እንዲሆን በታላቅ አደራ እናሳስባለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
ወለወላዲቱ ድንግል!!!
ወለመስቀሉ ክቡር!!!
አሜን!!!
ምንጭ፤ http://dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com