Saturday, September 6, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶችና ነብያት!


አን ኤልዛቤጥ  ሊ (1736-1784)
በእንግሊዝ አገር የተነሳችና «ተንቀጥቃጮች» የተሰኘ ሃይማኖት የፈለሰፈች፤ ተከታዮቿም «እናታችን» እያሉ የሚጠሯት ሀሳዊ ክርስቶስ ሆና ተነስታ ነበር። ስታስተምርም ራሷን የምትገልጸው እኔ በሴት መልክ የተገለጥኩ ሁለተኛው ኢየሱስ ነኝ እያለች ብትሰብክም እንኳን ለሌላው ልትተርፍ ይቅርና እራሷን ማዳን ሳትችል ቀርታ እስከምጽአት የመጨረሻውን ፍርድ ድረስ ላትነሳ ሞታ በድንጋይ ታትማለች።


        **************************************************


ጆን ኒኮላስ ቶም (1799-1838)
በእንግሊዝ ሀገር ኮርንዎል ተወልዶ ያደገና  የወይን ነጋዴ ሆኖ ሲሰራ የቆየ ሰው ነው። በሥራውም ላይ በታክስ ማጭበርበር ተከሶ እንደነበር የህይወት ታሪኩን የመዘገበው የኮርንዎል ቤተ መዛግብት ፋይል ያስረዳል። ቶም ሽቅርቅርና መዓዛው በሚያውድ ሽቶ ልብሱን ነክሮ፤ ጢሙን አሳድጎ የሚዞር ሰው ሲሆን የብዙዎችንም ቀልብ መሳብ የቻለ ነበር። ቶም ከወይን ነጋዴነት፤ ከጋዜጣ አዘጋጅነትና ገበሬዎችን ከአነስተኛ ንግድ ባለቤቶች ጋር በጥምረት የዐመጽ መሪነት ድረስ ሲ,ሰራ ቆይቷል። የሕይወት ስኬት ሲጎድለው ከእለታት አንድ ቀን ድንገት ተነስቶ «ሁለተኛው ኢየሱስ ሆኜ በሥጋ ተገልጫለሁ» በማለት ወደስብከት የገባ ሲሆን ተከታዮችን ካፈራ በኋላ በ1834 ዓ/ም ጀምሮ ወደቅዱስ መንፈስ ተቀይሬአለሁ ቢልም ባልተላቀቀው የዐመጽ መሪነቱ ተግባሩ ቀጥሎ በግንቦት 31/1838 ኬንት ከተማ ላይ በጥይት ተገድሎ እስከወዲያኛው ላይነሳ ያሸለበ ሰው ነው።

**************************************************


አርኖልድ ፖተር (1804-1872)
«የኋለኛው ቀን ቅዱሳን» የተባለው የክርስትና ክፍል መሪ የነበረ ሰው ነው። ፖተር በኒውዮርክ ተወልዶ፤ በኢንዲያና ውስጥ በኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለ ቤተ ክርስቲያን የተጠመቀ ሲሆን በኢሊኖይስ ላይ ደግሞ የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን መሥራች በሆነው በጆሴፍ ስሚዝ «ካህን፤ ሽማግሌና የቡራኬ አበው» ተብሎ ደረጃ በደረጃ የተሾመ ሰው ነበር። እስከአውስትራሊያ ድረስ ለስብከት የተጓዘው ፖተር «የኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ በኔ ውስጥ በመግባቱ ከዛሬ ጀምሮ እኔ ሌላው ኢየሱስ ነኝ» እያለ ሲያስተምርና ተከታዮችን ሲያፈራ ቆይቷል። በኋላ ላይ ወደካሊፎርኒያ ተመልሶ በ1872 ዓ/ም ወደሰማይ የማርግበት ሰዓት ደርሷል በማለት የአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ከገደል አፋፍ ላይ በደመና ለማረግ ሲጋልብ ወደላይ መውጣቱ ቀርቶ ቁልቁል እስከነ አህያዋ በመምዘግዘግ  ፖተር ዳግም ላይመለስ እስከወዲያኛው አሸልቧል።

         **************************************************

ጆንስ ቬሪ 1813-1880
 ፀሐፊ ተውኔት፤ ገጣሚና በሐርቫርድ የግሪክ ቋንቋ መምህር የነበረ ሰው ነው። ቬሪ እጅግ የጠለቀ እውቀትና ሙያ ያለው ሰው ቢሆንም ከእለታት አንድ ቀን  ለተማሪዎቹ «በማቴዎስ 24 ላይ ዳግም ይመለሳል የተባለው ኢየሱስ እኔ ነኝ» በማለት የተናገረ ሲሆን ይህንኑ ስብከቱን ቀጥሎበት ቀይቷል። በኋላ ላይ  በአእምሮ በሽታ ክፉኛ በመጠቃቱ ለከፍተኛ ጭንቀት ህመም ተጋልጦ  እህቱ እሱን የማስታመም ኃላፊነት ወድቆባት ነበር።  ቬሪ «ኢየሱስ ነኝ» እያለ ቢሰብክና ብዙዎችንም ቢያታልል ከአእምሮው በሽታ ሳይድን  በ1880 ዓ/ም በተወለደበት በማሳቹሴትስ ሞቶ በትልቅ ሃውልት መቃብሩ ተደፍኖ ዛሬ ድረስ ይታያል።




******************************************



ባሃ ኡላህ (1817-1892)
የእስልምናው አንዱ ክንፍ ከሆነውና በዛሬይቱ ኢራን ያለው የሺአይት እስላም ቤተ ሰብ የተወለደው ባሃኡላህ በዚሁ እምነት ስር ያደገ ሲሆን ሃይማኖታዊ ፍልስፍናው በፈጠረበት ስሜት ተነሳስቶ ዓለም በአንድ እምነትና መተሳሰብ ስር መጠቃለል አለባት ብሎ በመነሳት ራሱን «የባቢ እምነት» ፍጻሜ ነብይ አድርጎ በመቁጠር ከሺአት ተገንጥሎ በስሙ የባሃኡላህ እምነትን የመሠረተ ሰው ነው። ትምህርቱንም በባግዳድ ጀምሮ በእስልምና ህግ ተይዞ በሃይፋ/ እስራኤል/ እስከተሰቀለበት ቀን ድረስ እኔ የመጨረሻው የእግዚአብሔር ነብይ ነኝ፤ በኋለኛውም ቀን ለፍርድ እመጣለሁ ሲል የነበረ ሰው ነው። ይህ የሃይፋው ዋናው የባሃኢ እምነት ማእከል በዓለም ላይ ላሉ የእምነቱ ተከታዮች ቅዱስ ስፍራ ሲሆን አጠቃላይ መመሪያው የሚመነጨው ከዚሁ ከሃይፋው ማእከል ነው። 
 እግዚአብሔር ራሱን በሰው አምሳል ከገለጸባቸው መንገዶች አንዱ ባሃኡላህ ሲሆን የሰዎችን ነፍስ በማጥራት ምድርን ወደገነት የመቀየር ተልዕኮ ያነገበ እሱ ብቻ መሆኑን ሲሰብክ ቆይቷል። ባሃኢዎች እንደመንፈስ አባታቸው ሲዖልና ገነት ተብለው በሰዎች አእምሮ የተሳሉ ግምቶች እንጂ በእውን ሰዎችን ለመቅጫ በእግዚአብሔር የተፈጠሩ አይደለም ይላሉ። ባሃኡላህ የሞተው በ1892 በስቅላት ነው።
ሃይፋ/እስራኤል የባሃኢ ዋና ማእከል


*******************************************


ዊሊያም  ዳቪየስ (1833-1906)
የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን ቅርንጫፍ በሆነውና የኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መሪ የነበረ ሰው ነው። በደቡብ የዋሽንግተን ስቴት ዋላዋላ ከተማ ላይ «የእግዚአብሔር መንግሥት» ማኅበርን መስርቷል። ተከታዮቹንም «እኔ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚካኤል ነኝ» በማለት ያስተማረ ሲሆን «አዳም፤ አብርሃም፣ ዳዊት» ሆኖ ከዚህ በፊት በምድር ላይ የመጣውም እሱ ራሱ መሆኑንም በድፍረት ይናገር ነበር። በኋላ ላይ ሚስት አግብቶ በየካቲት 11/1868  «አርተር» የተባለ ልጁን እንደወለደ  ልጁን «በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ» ነው በማለት ሲናገር «ዴቪድ» የተባለ ሁለተኛ ልጁን ሲወልድ ደግሞ እኔ ወደ «እግዚአብሔር አብነት» ተቀይሬአለሁ እያለ ይሰብክ ነበር። ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ ሁለቱም ልጆቹ በጉሮሮ በሽታ ሲሞቱ ተከታዮቹ ባቀረቡበት ክስ የቤተ ክርስቲያኑን ንብረት ሸጦ በመክፈልና ከተማውን ለቆ ወደካሊፎርንያ በመሰደድ መልሶ ለመደራጀት ሞክሮ ሳይሳካለት ልጆቹን እንደቀበረ ሁሉ እሱም ሞቶ ድንጋይ ተጭኖት ይገኛል።



 ይቀጥላል%