Tuesday, July 17, 2012

የዳላሱ አቡነ አረጋዊ የማቅ ወኪል ቄስ፤ ከግንድ ላይ ተገንጥሎ በኪራይ ቤት ውስጥ ተተከለ!

የዳላስ ደ/ፀሐይ አቡነ አረጋዊ ወተ/ሃይማኖት ቤተክርስቲያን የፊት ገጽታ

በመሠረቱ ቤተክርስቲያንን ለመንፈሳዊ አገልግሎት ማቋቋም ቀና ሃሳብ መሆኑ አይካድም። ጥፋት የሚሆነው አንዲቱን ቤተክርስቲያን ለማዳከምና ምእመናን በቡድን ለመከፋፈል ሲባል ከሆነ የመንፈሳዊ ተግባርን እሳቤ በማደብዘዝ ስውር ዓላማን ለመፈጸም መንፈሳዊ ካባን የደረቡ ወረበሎች የሚጠቀሙበት ስልት መሆኑ እየታየ ነው። እናም ቄስ መሥፍን ማሞ የተባለው የዳላስ አቡነ አረጋዊ ቤተክርስቲያን ሰባኬ ወንጌል የነበረው ግለሰብእ የተሰጠውን የማቅን ተልእኰ አንግቦ በኅቡእ የቆየ ቢሆንም ሰዓቱ ሲደርስ ከዛሬ ጀምሮ ተገንጥያለሁ ማለቱ ተሰምቷል።
በኢትዮጵያ ሀገር ውስጥ  ያለ ዋና ሲኖዶስ ፤ በስደት ያለ ዋና ሲኖዶስ እና  አሁን ደግሞ በፓትርያርክ ማኅበረ ቅዱሳን የሚመራ አዲስ ሲኖዶስ በምድረ አሜሪካ እየተገነጠለና ራሱን እያራባ ወደ ሦስትነት እያደገ ይገኛል።
በዳላስ አቡነ አረጋዊ ወተክለ ሃይማኖት ቤተክርስቲያን ሰባኬ ወንጌል የሆነው የማኅበረ ቅዱሳኑ ታማኝ ሎሌ ለመገንጠልና በይፋ አውጆ በ5000 ዶላር ቤት ተከራይቶ የወጣ ሲሆን  መነሻ ምክንያት  የሆነው ነገር ሲቃኝ እንዲህ መሆኑን ምንጮቻን አረጋግጠዋል።
በታህሳስ ወር ገደማ በአዝማሪ መዘምራን ሴቶች የታጀበና በገበሬ አስደንግጥ ስብከቱ ስሙዓ ዜና  በሆነው ዳንኤል ክብረት የተመራው ከፍተኛ የማኅበረ ቅዱሳን የልዑካን ቡድን ጥቂት መርዝ ነስንሶ፤ ብዙ ምርት ማፈስ በሚል መርህ በሄዱበት የ3 ቀናት ዘመቻ ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ወቅት ከዳህጸ ልሳን በዘለለ የተነገረው ዲስኩር ለችግሩ መነሻ ምክንያት ሆኗል። ይኼው ቄስ መሥፍን የተባለው የማኅበረ ቅዱሳን አባል የደብሩ ስብከተ ወንጌል ኃላፊ እንደመሆኑ መጠን አዝማሪ መዘምራኖቹና ገበሬ አስደንግጥ ሰባኪያኑ ከደብሩ እንዲገኙ ሁኔታዎቹን በማመቻቸት ግንባር ቀደሙ ሰው ነበር።
በስብከቱ መድረክ ራሱን የሰየመው ዳንኤል ክብረት ወንጌልን እንዳያስተምር ያልዋለበት በመሆኑ በወግ ጥረቃና በምሳሌያዊ ተረት ዘመኑን የጨረሰ በመሆኑ የሚናገረው  ቢጠፋበት የተቆጣጠረውን መድረክ በመጠቀም  ሀገር ቤት አፍኖ የቆየውን የፖለቲካ  ትኩሳት አሜሪካ ሲደርስ እስኪበቃው ድረስ ሲተነፍስበት መታየቱ በምእመናኑና በደብሩ ካህናት በኩል ተቀባይነት ሳያስገኝለት  ከመቅረቱም በላይ የስብከት መድረክ የእግዚአብሔር መንግሥት የሚነገርበት እንጂ የግል ስውር ዓላማንና የፖለቲካን ትኩሳት ማስተላለፊያ መንገድ እንዳልሆነ በደብሩ አስተዳዳሪ ቀሲስ ታደሰ አርአያ በሀዘኔታ መገለጹን ተሰምቷል። 
ዳንኤል ክብረት በወቅቱ ወዴት እንሂድ? ኢትዮጵያ ውስጥ ታፍነን ተሰቃየን እኰ? ዝምታው እስከመቼ ነው? ወዘተ የሚሉ ቅስቀሳዎችን ሲያስተላልፍ የደብሩ አስተዳዳሪም የዳንኤልን  «ሁሉም ነገር ወደጦር ግንባር» ዓይነት ስብከቱን በመቃወም አሁን ይሄ ስብከት ነው? በባእድ ሀገር ለሚገኝ ምእመንና ምእመናት ከአንድ ሰባኪ የሚሰጥ የሕይወት   ቃል ይሄ ነው? ዓላማን ለይቶ ወደ ፖለቲካው መግባት አለበለዚያም ምእመናንን የሚያጽናና ትምህርት መስጠት ሲገባ ይህን ሁሉ ሀገር አቋርጣችሁ ከመጣችሁ በኋላ ህዝብን መቀስቀስ ተገቢ አይደለም ሲሉ ሀዘኔታቸውን ገልጸዋል።  ቤተክርስቲያን የሚመጣ ደጋፊም፤ ተቃዋሚም እንደመሆኑ መጠን ቤተክርስቲያን ማስተማር የሚገባት ሁሉንም የሚያንጽ እንጂ የአንድ አቅጣጫን ዓላማ ማስተጋቢያ መሆን የለበትም የተባለ ሲሆን የገበሬ አስደንግጡ ስብከት ውድቅ ተደርጓል። ማቅና ገበሬ አስደንግጥ ሰባኪያኑ ዳግመኛ እንዳይመጡ በመነገሩ ይህ ለማቅ ትልቅ ኪሳራ ሆኖ  ነበር።
የማቅ ታማኝ አገልጋያቸው የደብሩ ስብከተ ወንጌል ቄስ መስፍን ገበሬ አስደንግጦችን በማሰባሰብና በማስጮህ ብዙ የለፋበት የማቅ አገልግሎት ዋጋ በማጣቱና ተቀባይነት ባለማግኘቱ ውስጥ ውስጡን ሲቆስል ቆይቶ ከነፍስ አባቱ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ከመከረ በኋላ የደብሩን አስተዳዳሪ፤ ካህናትንና ማኅበረ ምእመናንን ቆይ ሳንሰራላችሁ ብንቀር በሚል ብቀላ አዲስ ቤት በአምስት ሺህ ዶላር ገደማ ተከራይተው እዚያው በቅርብ ርቀት የተተከለ ሲሆን ይህም በፓትርያርክ ማኅበረ ቅዱሳን የሚመራው ሦስተኛው ሲኖዶስ መሆኑ ነው።
ከሁሉም የሚያሳዝነው ደግሞ ሀገረ ስብከቱ በአቡነ ፋኑኤል የሚመራ መሆኑ እየታወቀ የሀገር ቤቱን ሲኖዶስ ከድተው ማኅበረ ቅዱሳን ቤት ተከራይቶ ሲያትል በሚያኖራቸው የሶስተኛው ሲኖዶስ ቋሚ አባል በሆኑት በአቡነ ኤዎስጣቴዎስ በኩል የቄስ መሥፍን ቤት ተመርቆ መከፈቱ ነገሩን አስገራሚ ያደርገዋል። በእርግጥ ሦስተኛውን ሲኖዶስ በምድረ አሜሪካ ቤቶችን በመክፈት ላይ የተጠመደው ማቅ ምንም ሀገረ ስብከት የሌላቸውን አቡነ ኤዎስጣቴዎስን ቤት ተከራይቶ ማስቀመጡ ምናልባት የአሜሪካ ፓትርያርክ አደርግዎታለሁ የሚል ተስፋ ሰጥቷቸው ይሆናል። በዚያ ላይም ለማቅ  አልገዛም፤ አልታዘዝም ያሉትን አቡነ ፋኑኤልን ለማናደድ ጭምር የተጠቀመበት የግንጠላ ስልት ሲሆን  ካከራየበት ቤት ጎትቶ በማምጣት ጳጳሱ ታዛዥነታቸውን ማሳየታቸው  ነገሩን አስገራሚ ያደርገዋል። አቡነ ኤዎስጣቴዎስም የጵጵስና ማእረግ ወንድማቸውን ለማቅ ደስታ ሲሉ መጥላታቸውና ሕገ ቤተክርስቲያንን ማፍረሳቸውን ስንመለከት እንዲህ ብለንለመጠየቅ እንገደዳለን።  እሳቸው ከጣሱት የትኛውን ህገ ቤተክርስቲያን  ተግባራዊ ለማድረግ ነው የጰጰሱት እንላቸዋለን?
አንዳንድ የማቅ ደጋፊዎች አቡነ ፋኑኤልም  በአቡነ አብርሃም ላይ እንደዚሁ ሰርተዋል በማለት ሊሞግቱ ይፈልጉ ይሆናል።
ያለፈ ጥፋት  ካለ፣ ላሁኑ ጥፋት እንደትክክለኛ መከራከሪያ ሆኖ ሊቀርብ አይችልም።
 ጎረምሳው ቡድን የራሱ ዓላማ ያለው ሲሆን ጳጳሱ ደግሞ  የራሳቸውን የሲኖዶስ ዓላማ ጥለው ለማቅ ዓላማ ስኬት መዞራቸው ያሳዝናል። ዘወትር የአቡነ ፋኑኤልን ስም በየድረ ገጾቹ  እያነሳ የሚያጨልማቸው አልበቃ ብሎት፤ አቡነ ኤዎስጣቴዎስን ወስዶ በአቡነ ፋኑኤል ሀገረ ስብከት ላይ ቤት እንዲመርቁ ያደረገው እርር ድብን ላድርጋቸው ብሎ እንጂ  ሕገ ቤተክርስቲያን ያንን እንዲያደርግ የሚፈቅድ ሆኖ አልበረም። ነገሩ ባልበላውም ልድፋው ነው! 

የዳላስ አቡነ አረጋዊ  ወተ/ሃይማኖት ቤተክርስቲያን ካህናትም  እንዳሻኝ የምናኝበትን መድረክ ከከለከሉኝ እነሱንም ላዳክማቸው፤ አባ ፋኑኤልንም ላቃጥላቸው ብሎ መገመቱ ነበር።  ይህንንም በ7/ 11/ 2004 ዓ/ም የሥላሴ ዕለት በስመ ሥላሴ ተገንጥለናል በማለት አውጆ ለማስመረቅ ችሏል።
ቤተክርስቲያንን  መመስረት ምክንያት፤ ዓላማና፤ ግብ አለው። መገንጠል ግን ብቀላን፤ ቁጭትንና እልክን መሰረት ያደረገ ስለሚሆን ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል። እናም ደብረ አቡነ አረጋዊን ለማዳከም እልከኛው ማቅ በታማኝ አገልጋዩ የቀድሞው ሰባኬ ወንጌል የአሁኑ አስተዳዳሪ ተገንጥሏል። ከሲኖዶስ ሁለት ቦታ መገንጠል ቤተክርስቲያን ምን አተረፈች? ምንስ አጎደለች? የማቅም ይሁን  የግለሰቦች ግንጠላስ ምን ይጠቅማል? እንዴትስ ያዳክማል? እንደምናውቀው በገንዘብ ጉዳይ የሚናጩ ቦርዶች ወይም ካህናት እንደሚገጥሉ እንሰማለን። ይህ ግን ቤተክርስቲያንን ለማዳከምና የግልን ኪስ ለማድለብ ካልሆነ ሌላ እውነትን የተከተለ አይደለም። አሁንም የምናየው ያንን ስህተት ነው።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው በምድረ አሜሪካ ማቅ በየቦታው የቤተክርስቲያን ጦርነት መጀመሩ ነው።  በኒቫዳ፤ ላስ ቬጋስ ከተማ  ሐመረ ኖኅ ቤተክርስቲያን የተጀመረው ዘመቻ ሌላው ማሳያ ሆኗል። ከእነ ቀሲስ ሳሙኤል ደጀኔ ያልተስማማ መሆኑ የሚነገርለት ጢም አልባው መነኩሴ ከማኅበረ ቅዱሳን ጉያ በመሸሸግ ድክመቱን ለማካካስ እየሞከረ መሆኑም ታውቋል። በአቡነ ፋኑኤል ላይ ወዶ ዘማች ሆኖ የተቃውሞ ደብዳቤ በደጀ ሰላም ብሎግ ላይ ማስነበቡ የሚያሳየው ፤ እኔ ይህንን ያህል ከዘመትኩላችሁ እናንተ ደግሞ ለእኔ የሚበጀውን ሁሉ ለማድረግ ከጎኔ ቁሙ በማለት ለማቅ የአቤቱታ መልእክት ለማስተላለፍ ፈልጎ መሆኑም እየተነገረ ነው።
በአጭር ቃል አቡነ ፋኑኤልን በዘመቻ እናባራቸው የሚለውን የማቅን ተልእኮ ለመፈጸም የተጎነጎነ ነው።
በሌላ ቦታም ማቅ የረጋውን ወተት እየናጠ እንደሆነ ይነገራል። በሲያትል ቅ/ሚካኤል ቤተክርስቲያንም  እየበጠበጠ መሆኑም የተሰማ ሲሆን በዚያው በሲያትል አማኑኤል ቤተክርስቲያንም በማቅ የተነሳውን ሁከት በማረጋጋት መንፈሳዊ ትምህርት ለመስጠት አቡነ ፋኑኤል ወደዚያው ማቅናታቸውን ለማወቅ ችለናል።
ማቅ በምድረ አሜሪካ ሁለት ነገር እየተገበረ ስለመገኘቱ ማሳያዎች አሉ።
አንደኛው በየአድባራቱ በተላላኪዎቹ በኩል ሁከትና መከፋፈል በመፍጠር አቡነ ፋኑኤልን በብቃት ማነስ አሳብቦ ማስነሳትና ቢቻል ታዛዥ የሆኑትን አቡነ ኤዎስጣቴዎስን እዚው የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አስደርጎ ማስመቀመጥ ሲሆን ካልቻለ የጉድ ሙዳዩን አገልጋይ ማስመለስ ነው።
ሁለተኛው ደግሞ በየቦታው ተገንጣይ አዳራሾችን በመከራየት በተገንጣይ ጳጳሳቶቹ በኩል ሦስተኛ ሲኖዶስን ማቋቋም ናቸው።
በተለይም ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙም ሊወደድ ባለመቻሉና መንግሥትም ቀን እየጠበቀልኝ ነው ከሚል ፍርሃት የተነሳ በምድረ አሜሪካ ተገንጣይ ተቋሞቹን የማስፋፋት ሂደት እንደአማራጭ እየተጠቀመ እንደሆ ነ ይገመታል። ምክንያቱም ሀገረ ስብከቱን የሚመሩ አባት እያሉ በሌላ ሀገረ ስብከት ውስጥ ተገንጣይ ቤተክርስቲያን አይተክልም ነበር። ከዚያም የባሰው ደግሞ በአንዲቱ ቤተክርስቲያን ዓላማዬን የማስፈጽምበት መድረክ ከተከለከልኩ ከፋፍዬ አዳክማችኋለሁ በሚል ስሌት በቅርብ ርቀት አዲስ ቤተክርስቲያን በመክፈት የሚጠቀምበት የብቀላ ስልት ነው። ቄስ መሥፍንም በሳምንት አንድ ቀን እሁድ ብቻ እየተገኘ ለተወሰነች ሰዓት አገልግሎት በወር አንድ ሺህ ሁለት መቶ ዶላር/ በኢትዮጵያ 21,000 ብር/ ገደማ ቤተክርስቲያኒቱ እየከፈለችውና ቀሪውን ቀናቶች ሁሉ የራሱን የግል ሥራ እንዲሰራ እድል ሰጥታው ሳለ  ለማቅ ተልእኮ ሲል ግንጠላን በመፈጸም ገበታውን መርገጡ  ምእመናንና ካህናቱ በከባድ ሀዘን እየተናገሩ ነው። በእርግጥም ያልበደለችው ቤተክርስቲያን ላይ ላደረሰው  በደል የእጁን ማግኘቱ አይቀርም።  እግዚአብሔር ልቡና ይስጠው!