Wednesday, July 4, 2012

"ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ"


                                         የጽሁፍ ምንጭ፤ ዓውደ ምሕረት

ማኅበረ ቅዱሳን ደጀ ሰላም በተባለው አሸባሪ ብሎጉ ጉባኤ አርድእት የተባለ ማኅበር ተቋቋመብኝ ይህ ማኅበር ደግሞ አያያዙ በሞኖፖል ይዠው የነበረውን የቤተክህነት ሥልጣን ሊነጥቀኝ ነው። የተሰበሰቡት ሰዎችም ከኔ ጨዋና ጥራዝ ነጠቅ አመራሮች የተሻሉ ስለሆነ ግርማ ሞገሳቸው አስፈርቶኛል የሚል አንድምታ ያለው ባለ 9 ገጽ ጽሁፍ ከለቀቀ በኃላ ይህ ገና ከመቋቋሙ ማኅበሩን በጥላው ያሸበረው ጉባኤ አለማው ምንድን ነው? በማለት በቤተክህነት አካባቢ ያለውን ነገር እያጣራን ሳለ gubae ardiet የሚል የፌስ ቡክ ገጽ ላይ አላማውን የሚያስረዳ ጽኁፍ ስላገኘን አላማውን ታውቁት ዘንድ ልናቀርብላችሁ ወድደናል።
ማኅበረ ቅዱሳን በአንድ እግሩ ፖለቲካ በሌላኛው እግሩ ሃይማኖት እየረገጠና በሁለት ሀሳብ እያነከሰ ያለ እኔ ቤተክርሰቲያን ዋጋ የላትም እያለ ቤተክርስቲያንን ለዘመናት ሲጠብቅ የነበረውን መንፈስ ቅዱስን ስፍራ ልቀቅ በማለት ያለአቅሙ እየተውተረተረ በየአቅጣጫው አቧራ በመበተን ቤተክርሰቲያንን እየረበሸ በመገኘቱ ያሳዛናቸው የቤተክህነት ሠራተኞች የመምሪያ ኃላፊዎችና የደብር አለቆች የተሰባሰቡበት ጉባኤ አርድእት አላማው በጽሁፉ እንደሚነበበው ቤተክርስቲያንን ከምንደኞችና ከእበላ ባዮች ለመታደግ እና አባቶችን በሚያስፈልገው ሁሉ ለመርዳት ነው።
እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ሁላችንም የምናውቅ ኦርቶዶክሳዊ ጋብቻ የሚባሉ የቤተከርስቲያኒቱ አባለት እርስ በርስ በተገቢው የቤተክርስቲያን ሥርዓት ሲጋቡ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን እራሱን ከማኅበርነት ወደ ቤተክርሰቲያንነት ስለቀየረ ማህበረ ቅዱሳን ያልሆነ ሰው እንዳታገቡ የሚል ቀጭን ትእዛዝ ለአባላቱ አስተላልፎል። እንዲህ ያለው በቤተክርስቲያን ላይ የተቋቋመው የአንጃነት ስሜት በሙስሊሙ እንደተቋቋመውና አውነተኛ ሙስሊም ሰለፊ ነው እንደሚለው የሰለፊያ አስተሳሰብ  ሁሉ ኦርቶዶክሳዊነት ማለት ማኅበረ ቅዱሳንነት ነው ወደሚል አባዜ መቀየሩ አስጊነቱን የተረዳው መንግስት ከሁለት ሳምንት በፊት መንገድ ትራንስፖርት በማህበሩ ዋና ሰው በሆነው አቶ ካሳሁን ቢሮ የባለስልጣን መስሪያ ቤት ሠራተኞችን ሰብስቦ  “ማኅበረ ቅዱሳን ከሚባል ሃይማኖት ተጠበቁማለቱ የሚታወስ ነው። 
አሁንም ህዝቡ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚባል ሃይማኖት እራሱን እንዲጠብቅ እና በቤተክርስቲያን ጥላ ውስጥ ብቻ እንዲሰባሰብ ኃላፊነት ያለባቸው በትምህርትም በአገልግሎትም የተመሰከረላቸው እውነተኛ የቤተክርስቲያን ልጆች የሆኑ የመምሪያ ኃላፊዎች ሌሎች በቤተክርስቲያኒቱ በኃላፊነት ቦታ ላይ ያሉ አገልጋዮች ያቋቋሙት ይህ ጉባኤ በጥላው ማኅበሩን እንዲህ ያስበረገገ ሥራ ሲጀምርማ ምን ውጤት እንደሚያመጣ በጉጉት የሚጠበቅ ሆኗል። አለማውን በተመለከተ የተዘጋጀውን ጽኁፍ እንድታነቡት አቅርበናል። መልካም ንባብ ይሁንላችሁ።
ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኵሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት
ሐዋርያት በሰበሰቡአት፣ ከሁሉ በላይ በሆነች በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን፡፡
"ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ"
"የአርድእት መንፈሳዊ ኅብረትን ለመመሥረት የቀረበ መነሻ ጽሑፍ"
"ወንድሞች በኅብረት ቢኖሩ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው" (መዝ 132(133) 1)

1. መግቢያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊት፣ ታሪካዊት፣ ብሔራዊትና ሐዋርያዊት ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የሀገርን አንድነት በመጠበቅ፣ ባህልን በማሳደግና የሕዝብን ሥነ ምግባርና አንድነት በመገንባት ደረጃ ከፍተኛ ሚና እንደነበራት ታሪክ የማይዘነጋው እውነት ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝባት መንፈሳዊት ቤታችን ብቻ ሳትሆን ለዓለም አስደናቂ የሆነው ኢትዮጵያዊ ማንነታችን የተቀረጸባት የኢትዮጵያዊነት ትምህርት ቤታችንም ናት፡፡
በዚህም ምክንያት እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት፣ ይህም አንድነትዋ በሃይማኖት፣ በቀኖናና በሥርዓት፣ በሕግ፣ በመዋቅር፣ በአስተዳደር፣ በአሠራርና በአመራር አንድነት የሚገለጥ ነው ብለን ስለምናምን የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የሚያጠናክር ሁለንተናዊ አስተዋፅኦ ለማድረግ አንድነት የበለጠ ጠቃሚ ነው ብለን ይህችን መንፈሳዊት ኅብረት ፈጥረናል፡፡
ኅብረታችንን ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ተብላ እንድትጠራ ተስማምተናል፤ ምክንያቱም፡- አንደኛ፡ እኛ የዚህች ኅብረት አባላት ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት፤ በላይዋ ላይ የሚመሠረት ሌላ ባዕድ አደረጃጀትም ሆነ ማኅበር አያስፈልጋትም የሚለውን አቋማችንን በአንድነት ለማራመድ ኅብረት አስፈለገን እንጅ ራሳችንን እንደ ማኅበር ስለማንቆጥር ነው፡፡ ኅብረታችን ይህን የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የመጠበቅ ዓላማዋን ስታሳካ ወዲያውኑ እንድትፈርስና አባላቱ ወደ መደበኛ ቦታቸዉ በመመለስ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ጠብቀው እንዲያገለግሉ ብቻ እናደርጋለን፡፡
ሁለተኛ፡ እኛ የዚህች ኅብረት አባላት ምን ጊዜም የቤተ ክርስቲያን የማያልቅ መንፈሳዊ ትምህርት የዘወትር ተማሪዎች መሆናችንን ስለምናምን ነው፡፡
ሦስተኛ፡ ሰባ ሁለቱ አርድዕት ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት የሐዋርያትን ተልእኮ ከዳር ለማድረስ ሐዋርያትን የማገዝ ተግባር እንደነበራቸው ሁሉ የኅብረቱ አባላትም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ፣ ቅዱስ ሲኖዶስና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅና ተልእኮዋን ለማሳካት የሚያደርጉትን አባታዊ ሥራ ለማገዝ እንጅ ኅብረታችን የራሷ የተለየ ዓላማ የላትም፡፡ እኛ የዚህች ኅብረት መሥራች አባላት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የኃላፊነትና የልዩ ልዩ መደበኛ የሥራ ቦታና አባልነት ያለን እንደመሆኑ መጠን የቤተ ክርስቲያናችንን እምነት፣ ቀኖና፣ ታሪክ፣ የመዋቅርና የአስተዳደር አንድነት የሚያግዝ ጥናት ከማድረግ፣ አባቶችን ከመላላክ፣ ነባሩን የቤተ ክርስቲያን ሕግና ሥርዓት ከመጠበቅና ከማስጠበቅ የተለየ ተግባር አይኖረንም፡፡
2. የጉባኤ አርድእት ዋና ዋና ዓላማዎች
2.1. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በእምነት፣ በሥርዓት፣ በቀኖና፣ በመዋቅርና በአስተዳደር አንዲት (አሐቲ) መሆንዋን በልዩ ልዩ መንገድ ለምእመናን ያስተምራል፤የትምህርተ ሃይማኖት፣ የቀኖናና የአስተዳደር መዋቅር አንድነቷን ይጠብቃል፣
2.2. በቅዱስ ፓትርያርኩ ሰብሳቢነት የሚወሰኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎችን ተግባራዊ ያደርጋል፣
2.3. የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የሚጎዱ ማናቸውንም ነገሮች (እንቅስቃሴዎች) ቀኖና ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅደው መልኩ በመቃወም እርማት እንዲደረግበት ያደርጋል፣
2.4. በውጭም ሆነ በውስጥ የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ ሥርዓትና መዋቅር የሚቃወሙ ማናቸውንም አጽራረ ቤተ ክርስቲያን (የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች) ይቃወማል፣
2.5. ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ቅዱስ ሲኖዶስና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለመጠበቅና ተልዕኮዋን ለማሳካት የሚያደርጉትን ጥረት ሁሉ ያግዛል፣
2.6. የቤተ ክርስቲያንን መዋቅሮች ጠብቆ በሚሰጠው መመሪያ መሠረት መንፈሳዊ አገልግሎቶችን ይሰጣል

2.7. ለቤተ ክርስቲያን እድገት የሚጠቅሙ ጥናትና ምርምሮችን፣ የምክክር መድረኮችን (ፎረሞችን) ያደርጋል፣ ዐውደ ጥናቶችን፣ በመዋቅሯ በሚሰጠው መመሪያ መሠረት ያከናውናል፣
2.8. ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አድባራትና ገዳማት የተዘረጉ መዋቅሮችን በማጠናከር፣ የምክርና የማደራጀት ሥራ በመሥራት በማንኛውም አቅም እንዲጠናከሩና መደበኛ ሥራቸውን እንዲወጡ ያደርጋል፣ የሚፈጠርባቸውንም እንቅፋትና ድክመት በተጠና መንገድ መፍትሔ እንዲሰጣቸው ይረዳል፣
2.9. ጉባኤ አርድእት በሚያከናውነው ተልእኮ ቅደም ተከተል መሠረት የአጭር ጊዜ፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ ዕቅድ ሲኖሩት፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከተያዙት ዕቅዶች በቅርቡ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና በልዩ ልዩ ከፍተኛ ባለሙያዎች ተጠንተው ለቅዱስ ሲኖዶስ የቀረቡ ጥናቶች ተግባራዊ ስለሚሆኑበት እንዲሁም በቤተ ክርስቲያን የአሠራር መተዳደሪያ ሕጎች ውስጥ ያሉ ክፍተቶችን ስለሚሻሻሉበት ሁኔታ ሥርዓትን በተከተለ ሁኔታ መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል፡፡
3. የጉባኤ አርድእት ወሰን ወይም ድንበር
3.1. ጉባኤ አርድእት ቀደም ሲል በትርጕም እንደተገለጸው በቋሚነት የሚጸና የማኅበር ቅርጽና መዋቅር የለውም፡፡ አባላትን በቋሚነት በወጥ ሰነድ አይመዘግብም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባላት፣ መዋቅርና እምነት ውጭ ራሱን ልዩ የሚያደርግ የአባልነት መሥፈርትና መተዳደሪያ በማውጣት ልዩ አደረጃጀት አይኖረውም፡፡
3.2. ጉባኤ አርድእት በቋሚነት የሚያሰባስበው የገንዘብ መዋጮ፣ የእርዳታ አሰባሰብና የንግድ እንቅስቃሴ አያከናውንም፤ እንደአስፈላጊነቱ ጊዜያዊ ተግባራትን ለማከናወን ሲያስፈልግ አግባብነት ያለው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ /ቤት ኃላፊን በማሳወቅ፣ በሕጋዊ የቤተ ክርስቲያን ደረሰኝ፣ አመራር ሊሰጥበትና ቁጥጥር ሊደረግበት በሚችል መንገድ የባንክ ቁጥር በመክፈት የገንዘብ ማሰባሰብ ሊያከናውን ይችላል፡፡ ስለዚህ ጉባኤ አርድእት ቋሚ የገቢ ማሰባሰብ ሥርዓት አይኖረውም፡፡
3.3. የጉባኤ አርድእት የሃይማኖትና የቀኖና መተዳደሪያ ከጥንት ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዓተ አምልኮት ነው፡፡
3.4. ጉባኤ አርድእት በማናኛውም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ አይሳተፍም፣ የቤተ ክርስቲያን መዋቅርና አስተዳደራዊ ሥርዓት በምክርና በውስጥ አሠራር እንዲታረምና እንዲጠናከር ያደርጋል እንጅ የቤተ ክርስቲያንን ገመና ምእመናን እንዲያውቁት በሚል ሰበብ በአደባባይ አሳልፎ አይሰጥም፡፡
3.5. ጉባኤ አርድእት በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ከመንግሥት ጋር በመተባበር የሀገሪቱ ሕግ በሚፈቅደው መሠረት የሰላም፣ የልማት፣ የመቻቻል፣ ለሰብዓዊ ፍጥረተ ዓለም የሚጠቅሙና የቤተ ክርስቲያን ክብር የሚገልጹ የበጉ አድርጐት ሥራዎችን ያከናውናል፡፡
4. አደረጃጀት
ጉባኤ አርድእት አንድ ሰብሳቢ፣ አንድ ምክትል ሰብሳቢና አንድ ጸሐፊ ይኖሩታል፤ መደበኛና አስቸኳይ ስብሰባዎችንም በየጊዜው ያደርጋል፡፡ በውጭ ሀገር የሚኖሩ የጉባኤ አርድዕት አባላት የራሳቸው ሰብሳቢ፣ ምክትል ሰብሳቢና ጸሐፊ ይኖራቸዋል፤ ሆኖም ግን በዋናው ማዕከል የሌለ አደረጃጀትና ዓላማ በሌሎች ማእከላት ተግባራዊ አይሆንም፡፡
5. የአባልነት ሁኔታ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት፤ መዋቅሮችዋን በማጠናከር፣ የምእመናንን አንድነት ከመጠበቅ ውጭ ባዕድ ማኅበር በማደራጀት የቤተ ክርስቲያንን የገንዘብና የሰው ኃይል መከፋፈል ተገቢ አይደለም ብለው የሚያምኑ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገራት የሚኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምእመናን ሁሉ አባላት መሆን ይችላሉ፡፡ በዋናው የኅብረቱ የዘወትር ሥራዎች የሚሳተፉት መደበኛ (ዋና) አባላት ሲሆኑ ሌሎቹ ተባባሪ አባላት ይሆናሉ፡፡
ይህ ሰነድ ለሚመለከተው አካል ቀርቦ እንዲታወቅ ይደረጋል፡፡
‘ጸልዩ በእንተ ሰላመ ቤተ ክርስቲያን አሐቲ ቅድስት ጉባኤ እንተ ሐዋርያት ርትዕት በኀበ እግዚአብሔር’