Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts
Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts

Thursday, March 28, 2024

ጸጋ ምንድነው? What is Grace?

ይህ ፅሑፍ ከባለፈው ፅሑፋችን የቀጠለ ነው። በባለፈው ፅሑፋችን "የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ግንብ ሳይሆን ሰው ራሱ ነው፣ በእግዚአብሔር የተቀደሰው" ካልን በኋላ የተቀደሰ ቤተ መቅደስ መሆን የሚቻለው እንዴት ነው? በሚለው ጥያቄ ላይ ተመርኩዘን ዛሬ ደግሞ በዚሁ ዙሪያ የተወሰነውን ሐተታ እናቀርባለን። መልካም ንባብ! በጌታችን፣ በአምላካችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑ ሁሉ የኃጢአታቸውን ሥርየት አግኝተው የዘላለምን ሕይወት ይወርሱ ዘንድ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለው ይጠራሉ። “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።” ዮሐ 3፥16 አብ በአንድያ ልጁ በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ ልጆቹ እንድንሆንለት በመፈለጉ የተነሳ ከቀዳማዊው የአዳም ኃጢአት፣ ሥርየት ያገኘንበትን ሰማያዊ ስጦታ ልጅነትን ሰጥቶናል። በዚህም የተነሳ የዐመጻ ልጆች እንዳልነበርን ሁሉ (ዕብ 8:12) አባ፣ አባት ብለን የምንጠራበትን የልጅነት መንፈስ (ሮሜ 8:15) ካገኘን በኋላ ልጅነታችንን በመጠበቅ መኖር ያለብን እንዴት ነው? የሚለው ጉዳይ የግድ ሊታወቅ የሚገባው መንፈሳዊ እውቀት ነው። በዚህ ምድር ላይ ለሚኖር ሰው ሁሉ የነፍስ የኃጢአት በሮቹ ሦስት ናቸው። አምነው ባልዳኑ ሰዎች ላይ ሦስቱም የኃጢአት በሮች ክፍት ስለሆኑ በኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት እስኪያምኑ ድረስ በዚህ ፅሑፍ ስለጸጋ አስፈላጊነት ልንመክራቸው አንደፍርም። *ሦስቱ የኃጢአት በሮች ምንድናቸው? እንዴትስ ይሰራሉ? ሦስቱ የኃጢአት በሮች የተባሉት፣ 1/ ሥጋ 2/ ዓለም 3/ የወደቀው መልአክ ናቸው። ያመኑና የዳኑ ክርስቲያኖች በሙሉ እነዚህን የኃጢአት በሮች ምንነት ማወቅና ለመዝጋት የሚችሉበት አስፈላጊ ኃይላቸው ጸጋ /grace/ይባላል። የእግዚአብሔር ልጅ መሆን የቻልንበትን ድነት/ድኅነት/ ይሄንን ምድር ለቀን እስክንሄድ ድረስ አስጠብቀን መገኘት የግድ ነው። አንዴ ድኛለሁና ከእንግዲህ የፈለኩትን መሆን እችላለሁ አይባልም። ይሄንንም ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ እያለ መንፈሳዊ ማሳሰቢያ ይሰጠናል። "እንግዲህ ለምኞቱ እንድትታዘዙ በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ፤ ብልቶቻችሁንም የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለኃጢአት አታቅርቡ፥ ነገር ግን ከሙታን ተለይታችሁ በሕይወት እንደምትኖሩ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር አቅርቡ፥ ብልቶቻችሁንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለእግዚአብሔር አቅርቡ።" (ሮሜ 6: 12—13) ስለሆነም ከድነት በኋላ አማኝ ሁሉ ራሱን በጽድቅና በቅድስና መጠበቅ አለበት። ይሄን ከባድ የሚመስል ነገር ግን የመንፈሳዊ ብቃት ኃይል የሆነውና ጸጋ የተባለው የታላቅ ምስጢር እውቀት ያስፈልገዋል። ጸጋ የሚገኘው እንዴት ነው? የሚለውን ከማየታችን በፊት ጸጋ የሚከላከላቸውን ሦስቱን የነፍስ የኃጢአት በሮችን ማወቅ አለብን። የኃጢአት በሮቹን ካወቅን በሚሰጠን ጸጋ እንዴት መዝጋት እንደምንችልና አስፈላጊ እንደሆነ በደንብ ይገባናል። 1/ ሥጋ፣ የለበስነው ሥጋ ፈራሽና በስባሽ ነው። በዳግም ትንሣኤ በአዲስ መልክ እስኪለወጥ ድረስ “እኛም ሁላችን በመጋረጃ በማይከደን ፊት የጌታን ክብር እንደ መስተዋት እያብለጨለጭን መንፈስ ከሚሆን ጌታ እንደሚደረግ ያን መልክ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንለወጣለን።”2ኛ ቆሮ 3፥18 "እንለወጣለን" የሚለውን የግሪኩ ቃል"μεταμορφούμεθα" ሜታሞርፌውሜታ ይለዋል።ይህም ከአንድ ከነበረበት ሁኔታ ወዳልነበረበት ሌላ ሁኔታ መለወጥ ማለት ነው። ለምሳሌ ቢራቢሮን ለመወጥ ይመለከቷል! ነፍስ ወደተገኘችበት ወደሰማይ ስትወጣ ሥጋ የምትኖረው በዚህ ምድር ነው። ምክንያቱም ሥጋ የተሠራችው ከዚሁ የምድር አፈር ስለሆነ ነው። እግዚአብሔር ያበጀውን የምድር አፈር ሕይወት የሰጠው የሕይወትን እስትንፋስ እፍ ባለባት ጊዜ ነው። ሥጋ በራሱ ሕይወት የለውም። የሥጋ ሕይወቱ ነፍስ እስካለበት ድረስ ብቻ ነው። ከደቂቃዎች በፊት አንድ ወንበር ላይ ቁጭ ብላ ስታወራ የነበረች ሥጋ፣ ነፍስ ትቷት ቢወጣ በድን ሆና ትቀራለች። ነፍስ ከመለየቷ በፊትና ከተለየች በኋላ ሥጋ እዚያው ወንበሩ ላይ ቁጭ ብሎ ይገኛል። ልዩነቱ ነፍስ ስለሌለበት ሥጋው ሕይወት የለውም። ነገር ግን ነፍስ እስካለችበት ድረስ ሥጋ ሕይወት ስለሚኖረው የተዋቀረችበት የዐራት ባህርያቷ መሻትና አደገኛ የማይስማሙ ፍላጎቶች አሏት። መሻቷንና ፍላጎቶቿን ማወቅና መቆጣጠር ያለበት ባለቤቷ የሆነው የዳነው ሰው ራሱ ሲሆን ይህም ኃይል የእግዚአብሔር ጸጋ ይባላል። ሰው የነፍስና የሥጋ ውሁድ ሆኖ ድነቱን/መዳኑን/ መጠበቅ የሚችለው በመንፈሱ ነው። በኢየሱስ አምኖ የዳነ ሰው ሥጋውን መቆጣጠር የሚችለው ከእግዚአብሔር ጋር ባለው መንፈስ ሲሆን በየዕለት ግንኝነቱ የሚያግዘውንና የሚረዳው ጸጋ እንዲበዛለት ያደርጋል። “እንግዲህ ምሕረትን እንድንቀበል በሚያስፈልገንም ጊዜ የሚረዳንን ጸጋ እንድናገኝ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ።” ዕብ 4፥16 ምክንያቱም ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ እያለ አበክሮ የሚነግረን ራሳችንን ማሸነፍ የምንችልበት ይህ ጸጋ ከውድቀት ይታደገናልና ነው። "ነገር ግን እላለሁ፥ በመንፈስ ተመላለሱ፥ የሥጋንም ምኞት ከቶ አትፈጽሙ። ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስም በሥጋ ላይ ይመኛልና፥ እነዚህም እርስ በርሳቸው ይቀዋወማሉ፤ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም።" (ገላ 5:16—17) ሥጋ ከምትበላውና ከምትጠጣው ሙቀት የተነሳ ወሲባዊ ፍላጎቷ ተቀስቅሶ ከትዳር በፊት ይሁን በኋላ ከተመኘኋት ጋር ላመንዝር ትላለች። የነፍስ መንፈሳዊ እውቀት ደግሞ “ከዝሙት ሽሹ። ሰው የሚያደርገው ኃጢአት ሁሉ ከሥጋ ውጭ ነው፤ ዝሙትን የሚሠራ ግን በገዛ ሥጋው ላይ ኃጢአትን ይሠራል።” (1ኛ ቆሮ 6፥18) ብሎ ይቆጣጠራታል። ሥጋ ልስረቅ፣ ልዋሽ፣ ላታልል፣ መሻቴን ሁሉ እንድፈፅም አትከልክሉኝ ትላለች። ጾም፣ ጸሎት አድካሚ ነው። ይሄ ሁሉ ለምኔ ነው? ልቀቁኝ፣ በአምሮቴ ልኑርበት ትላለች። ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ "“በሥጋ ያሉትም እግዚአብሔርን ደስ ሊያሰኙት አይችሉም።” ሮሜ 8፥8 በማለት እቅጩን የነገረን። ለዚህም ነው፣ የሥጋን አምሮትና የመሻት በር ለመዝጋት ጸጋ የተባለው ኃይል የሚያስፈልገን። የእግዚአብሔር የበዛው ደግነቱ፣ በልጁ ሞት የዘላለምን ሕይወት ከሰጠን በኋላ የተፈጠርንበትን የሥጋ ፍላጎት መቆጣጠር የምንችልበትን ጸጋ የተባለውን ኃይልም አብሮ ሰጥቶናል። ወሲብ ለሥጋ የተሰጠ የአምላክ ፈቃድ ነው። ነገር ግን ኃጢአት የሚሆነው አለቦታውና አለጊዜው ስንጠቀመው ነው። ቅድመ ይሁን ድኅረ ጋብቻ ወሲብ ሁሉ ዐመፅ ነው። ምክንያቱም፣ “እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ።”ሮሜ 8፥13 “ዳሩ ግን ማግባት ወደሚገባው ዕድሜ በደረሰ ጊዜ ስለ ድንግልናው ያፈረ ሰው ቢኖር፥ የወደደውን ያድርግ፤ ኃጢአት የለበትም፤ ይጋቡ።”1ኛ ቆሮ 7፥36 መብልና መጠጥ የሥጋ ባሕርያት ናቸው። ነገር ግን የምንበላውንና የምንጠጣውን መለየት፣ ሆዴ ይሙላ፣ ደረቴ ይቅላ ባለማለት ሥጋን ለመጎሰም በጾምና ጸሎት የምንጠመድበትን ኃይል ለማግኘት ጸጋ የተባለ ጉልበት ያስፈልገናል። “መብል ለሆድ ነው፥ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል። ሥጋ ግን ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሥጋ ነው፤”1ኛ ቆሮ 6፥13 እዚህ ላይ በኢየሱስ አምነው ያልዳኑ ሰዎች ማለትም ሥጋና ነፍሳቸው ከእግዚአብሔር ባልሆነ መንፈስ ቁጥጥር ሥር የሚገኙ ስለሆነ ከጸጋው ተለይተው ስለወደቁ ሁሉም ኃጢአቶች በነሱ ላይ አቅም ኖሮት የፈለገውን ይሰራል። “ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፥ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና።” (1ኛ ዮሐ 3፥8) (...ይቀጥላል%)

Tuesday, March 12, 2024

እግዚአብሔር ሰው በሠራው ቤተ መቅደስ አይኖርም!

ይህ አባባል እግዚአብሔር ሰው በሠራው መቅደስ ዛሬ ይኖራል ብለው ለሚያምኑ ሰዎች ጆሮን ጭው የሚያደርግ ቃል ነው። ነገር ግን እውነቱ እግዚአብሔር ዛሬ ሰው በሠራው መቅደስ አለመኖሩ ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር አዝዞት፣ ወርድና ቁመቱን ነግሮት የተሠራ ምድራዊ ቤተመቅደስ ዛሬ የለምና ነው። የቀደመችቱን የእስራኤል ቤተ መቅደስ ወርዱንና ቁመቱን፣ ስፋትና ርዝመቱን፣ ጽላቱንና ታቦቱን፣ ኤፉዱንና አልባሳተ ካህናቱን፣  መጋረጃዎቹንና ቀለማቱን፣ በአጠቃላይ የቤተ መቅደሱን ንዋያተ ቅድሳት የመረጠው እግዚአብሔር ራሱ ነበር እንጂ ምድራውያን ሰዎች አልነበሩም። ያቺ እግዚአብሔር ይገለጽባት የነበረችው ቤተ መቅደስ ዛሬ የለችም። በሙሴ የነበረው የመገናኛው ድንኳን እግዚአብሔር ራሱ ባዘዘው መሠረት የተሠራ ነው። (ዘጸ36:1) በሰሎሞን ዘመን ወደሕንጻ ቤተ መቅደስ ሲቀየር ለዳዊት ከወገቡ የሚወጣው ልጁ እንደሚሰራለት እግዚአብሔር ራሱ ተናግሮ ስለነበር እንጂ ሰሎሞን ከልቡ አንቅቶ የሰራው አልነበረም። (2ኛ ዜና 6:9) ይህ ሰሎሞን ያሠራው ቤተ መቅደስ የፈረሰበትን ታሪክ መጽሐፍ ቅዱሳችን ሲነግረን ሕዝቡ እንደአሳቡ፣ እንደፈቃዱና እንደትእዛዙ ባለመሄዱ የተነሳ የደረሰባቸውን መከራ እንዲህ ይተርክልናል።  “ሴዴቅያስም በነገሠ በዘጠኝኛው ዓመት በአሥረኛው ወር ከወሩም በአሥረኛው ቀን የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆርና ሠራዊቱ ሁሉ ወደ ኢየሩሳሌም መጥተው ከበቡአት፤ በዙሪያዋም ዕርድ ሠሩባት።  (2ኛ ነገሥት ምዕራፍ 25ን  ያንብቡ) ቤተ መቅደሱ በናቡከደነጾር ፈርሶ፣ ንዋያተ ቅድሳቱ ተዘርፎ፣ ሕዝቦ ለባርነት ተግዞ ከተወሰደ በኋላ ኢየሩሳሌም ዳዋ ወርሷት ነበር። “እናንተንም ከአሕዛብ መካከል እበትናችኋለሁ፥ ሰይፍንም አስመዝዝባችኋለሁ፤ ምድራችሁም የተፈታች ትሆናለች፥ ከተሞቻችሁም ባድማ ይሆናሉ።”   ዘሌ 26፥33 ያለው ቃል ተፈጽሟል። ሁለተኛው ቤተ መቅደስ ተመልሶ የተሠራው በታላቁ ሄሮድስ ሲሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሞቱ በተናገረበት አንቀጽ የ2ኛውንም ቤተ መቅደስ መፍረስ ሲተነብይ እንዲህ ብሎ ነበር። “ኢየሱስም መልሶ፦ ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ አላቸው።” ዮሐ 2፥19 አይሁዶችም ሲመልሱለት፣ "ወይቤልዎ ፡ አይሁድ ፡ በአርብዓ ፡ ወስድስቱ ፡ ዓመት ፡ ተሐንጸ ፡ ዝንቱ ፡ ቤተ ፡ መቅደስ ፡ ወአንተሰ ፡ በሠሉስ ፡ መዋዕል ፡ ታነሥኦ?" ይህ ቤተ መቅደስ ለማነጽ 46 ዓመት ፈጀ፣ አንተ በሦስት ቀን መልሰህ ትሰራዋለህን? ብለው ጠይቀውታል። ዋናው መልእክቱ ለሰውነቱ ቤተ መቅደስ ቢሆንም ከሕንጻው ቤተ መቅደስም መፍረስ ትንቢት ነበር። ይህ በሄሮድስ የታነጸው ሁለተኛው ቤተ መቅደስ 46 ዓመት የፈጀ ሲሆን ሰሎሞን ካሰራው ቤተ መቅደስ የተለየ ነበር። ምክንያቱም እግዚአብሔር ያዘዘው ቃል ሥርዓት የሚፈጸምበትና የሚከናወንበት ቤተ መቅደስ አልነበረም። ታቦቱ የለም። ታቦቱና ጽላቱ በሌለበት የእግዚአብሔር ክብር አይታይም ማለት ነው። የቤተመቅደሱ ሥርዓት የሌለበት፣ ታቦቱና ጽላቱ የማይገኝበት፣ እግዚአብሔርም በሁለቱ ኪሩብ መካከል በሚታየው የክብር ደመና መካከል  ተገልጾ በአሮን የክህነት ማዕረግ ተሹመዋል የተባሉትንና በወቅቱ ሊቀካህናት የነበሩት ሐናንና ቀያፋን የሚያናግርበት ቤተ መቅደስ አልነበረም። የእግዚአብሔር ድምጽ የሚሰሙበት ቤተ መቅደስ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ስለኢየሱስ ድምጽ ይመጣላቸው ነበር። ከዚያ ይልቅ በዚህ በሄሮድስ ቤተ መቅደስ አደባባይ የሕዝቡ የኃጢአት ሥርየትና የደኅንነት መስዋዕት ሳይሆን ይቀርብ የነበረው የገንዘብ ለዋጮችና የርግብ ሻጮች ገበታ ነበር። ገንዘብ ለዋጮቹ ለበዓል ከተለያዩ ሀገራት የሚመጡትን ሰዎች ገንዘብ የሚመነዝሩ /money exchangers/ ሲሆኑ ርግብ ሻጮቹ ደግሞ ለበደል ሥርየት የሚሆኑ ርግቦችን ለሚመጡ ለእንግዶች የሚሸጡ የነጋዴዎች አደባባይ ሆኖ ነበር። ይህ ተግባር እግዚአብሔር አዝዞ በተሠራው በሰሎሞን ቤተ መቅደስ አደባባይ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ የሚለውን ቅጣት ያስከትል ነበር። ኢየሱስም፣ በዚህ ድርጊታቸው በተበሳጭቶ “ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች ተብሎ ተጽፎአል፥ እናንተ ግን የወንበዶች ዋሻ አደረጋችኋት አላቸው።” (ማቴ 21፥13) ይህ ቤተ መቅደስ እግዚአብሔር የማይከብርበት፣ ሥርዓተ መቅደሱ የማይፈጸምበት ስለነበረ መፍረስ ነበረበት። ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ቤተ መቅደሱ እንደሚፈርስ በተናገረው ቃል መሠረት ባረገ በዐርባኛው ዓመት፣ የሮማው ንጉሥ ጥጦስ በ70 ዓ/ ምህረት ገደማ ካፈረሰው በኋላ ላለፉት 2000 ዓመታት ቤተ መቅደስ የሚባል ታሪክ የለም። ከዚያ በኋላም  እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ስሩልኝ ያለው የተለየ ሕዝብና ሀገርም የለም። የቤተመቅደሱን ስፋትና ቁመት፣ የንዋያተ ቅድሳቱን ዝርዝርና ዓይነት የነገረው አንድም ሕዝብ ስለሌለ እግዚአብሔርን ለመገናኘት የምንሄድበት ቤተ መቅደስ በዓለም ላይ የትም ሀገር የለም። ልባቸው ያፈለቀውን፣ ኅሊናቸው ያሰበውን፣ ያላቸው የገንዘብ አቅም የፈቀደላቸውንና በሕንጻ አሠሪ ኮሚቴ በተፈቀደ ዲዛይን በተሠራ ሕንጻ ውስጥ እግዚአብሔርን ይገባበት ዘንድ በወይራና በቅብዐ ሜሮን ግንቡን ረጭተው እግዚአብሔር ሆይ ቀድሰነዋልና ና ግባበት እያሉ ሲጣሩ ውለው ቢያድሩ በዚያ በሰዎች ሃሳብ ሕንጻ ውስጥ እግዚአብሔር የለም። እግዚአብሔር እንደዚያ አድርገው እንዲሰሩለት ያዘዘው ሕዝብና ሀገር ስለሌለ፣ ሰዎች በልባቸው መሻት በሰሩት ቤተ መቅደስ ውስጥ በተሽሞነሞነ ጥሪና ልመና  የሚገባ አምላክ አለ ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል። የሚገባ ካለም ሌላ መንፈስ ይሆን ይሆናል እንጂ የሰማይ አምላክ አይደለም። ሐዋርያት 17፣ 24—25 "ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤ እርሱም ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣልና አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም"። አሁን ቤተ መቅደሱ አንተ ነህ። ይሄን አንተ ቤተ መቅደስ የሆነው ሰውነትህን አቆሽሸህ ስታበቃ ሕንጻውን ቀድሼዋለሁ ብትል ስህተትም፣ ክህደትም ነው። ለዚህም ነው፣ የቆሸሹ፣ ከኃጢአት ያልተመለሱ፣ ለመመለስም ፍላጎት የሌላቸው ዐመጸኞች ቤተ መቅደስ በሚሉት ሕንጻ ውስጥ ተሰግስገው መደበኛ ኑሮአቸውን የሚኖሩት። እግዚአብሔር እኔ ውስጥ የለም፣ እዚያ እኔ በሠራሁት ሕንጻ ውስጥ አምላኬ ስላለ ጥዋትና ማታ እየሄድኩ ኃጢአቴን ይቅር እንዲለኝ እነግረዋለሁ ብትል ሕንጻ ውስጥ ቁጭ ብሎ የአንተን ኃጢአት የሚሰማ የሰማይ አምላክ ስለሌለ መጀመሪያ ራስህን ቀድስ። ኢየሱስ ከኦሪቱ ቤተ መቅደስ አገልግሎት ይልቅ ወደበለጠው የአዲስ ኪዳን አገልግሎት የመጣው አንተን አማኙን ለመቀደስ እንጂ በድንጋይ የተሠራ ቤት ለመቀደስ አይደለም። “ኢየሱስም መለሰ አለውም፦ የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።”   — ዮሐንስ 14፥23 እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ ስለተባለ ቤተ መቅደሱ አንተ ራስህ ነህ። ቃሉን ጠብቅ፣ አብ ይወድሃል። ወልድም ይወድሃል። አንተም መኖሪያው ትሆናለህ። አንተ መኖሪያው ካልሆንክ የእግዚአብሔር መኖሪያ የሆነ ሌላ ሕንጻ የለም። ሕንጻው አንተ ነህ። ይሄንን ሕንጻ የሠራው ኢየሱስ ነው። (በቀጣይ ፅሑፋችን "ሰው የእግዚአብሔር መኖሪያ ሕንጻ መሆን እንዴት ይችላል?") የሚለውን እንመለከታለን።

Wednesday, January 17, 2024

“መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።” ሐዋ 4፥12

አዳም ከአምላኩ ትዕዛዝ በወጣ ጊዜ፣ ከሔዋን ጋር ከገነት ተባሮ አሜከላና እሾህ ወደምታበቅለው ምድር መጣሉን መጽሐፍ ቅዱሳችን ይነግረናል። ዘፍ 3:1—24 ይህ የአዳም በደል ከእሱ በተወለዱ ዘሮቹ በሙሉ በውርስ ሲተላለፍ ኖሯል። ከሰማይ ከወረደው ሁለተኛው አዳም/ ኢየሱስ/ በቀር ያለ ውርስ ኃጢአት የኖረ ማንም አልነበረም። የኢየሱስም ከሰማይ ወርዶ ሰው የመሆን ምስጢሩም የሚነሳው፣ የአዳም ዘር በሙሉ በሞት ፍርድ ሥር ያለ በመሆኑ ከሥጋ ለባሽ አንድም ሰው ዘሩን ነጻ ማድረግ ስለማይችል ነበር። ይህንንም ሐዋርያው ጳውሎስ አስረግጦ ሲያስረዳ ወደ ሮሜ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ እንደዚህ ብሎታል። “ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፥ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፤” ሮሜ 5፥12 ስለዚህም ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል "ወልድ" በሥጋ ሰብእ ከድንግል ማርያም ተወልዶ፣ ከኃጢአት ብቻ በቀር አዳማዊ ባህርይን ተዋሕዶ ሰው ሆነ። አዳምንና ልጆቹን ከዘላለም ሞት ማዳን የሚችለው ከኃጢአት ነጻ መሆን የቻለ ብቻ ስለነበር ኢየሱስም የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ለኃጢአተኞች ነጻ መውጣት የአብ መስዋእት ሆኖ ቀረበ። “በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።”ዮሐ 1፥29 ይህ የዓለምን ኃጢአትን የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ (ካልቪኒስቶች ለዓለሙ ሁሉ አልሞተም ይላሉ) መስቀል ላይ ውሎ የኃጢአት ሥርየት እርሱ መሆኑን አምነው፣ በስሙ ለተጠመቁና እስከመጨረሻው እምነታቸውን አጽንተው ለተጠበቁ በሙሉ እንጂ ለተወሰነ ዘር፣ ነገድ፣ ጎሣ፣ ብሔር ወይም ለተወሰነ ወገን የተፈፀመ ማዳን አልነበረም። ሐዋርያው ጳውሎስ ሞት ወደዓለም በአንዱ አዳም በኩል ለሁሉ እንደደረሰ ሕይወት ደግሞ በአንዱ በኢየሱስ በኩል ለተቀበሉት ሁሉ ሆነ በማለት ያስረዳናል። “በአንዱም በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፥ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ።” ሮሜ 5፥17 እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ወደዓለም የላከውና ለመስቀል ሞት የታዘዘው የአዳም ዘር በሙሉ በእርሱ አምነው እንዲድኑበት እንጂ የተወሰነ ቡድን ወይም በምርጫ ለተለየ ወገን ለይቶ ለማዳን አይደለም። በዚህ ዘመን ጆን ካልቪን የተባለ የ17ኛው ክ/ዘመን የተነሳ የአዲስ ሃይማኖት አስተማሪ ደቀመዛሙርት ነን የሚሉ በዚህ ዘመንም ኢትዮጵያ ውስጥ ሃይማኖታዊ ክሂዶትን አጠናክረው በመቀጠል ኢየሱስ የሞተልን ለእኛ ለተመረጥን፣ አስቀድሞ ለተለየንና ለተጠራን ብቻ እንጂ ለአዳም ልጆች ሁሉ ኃጢአት አይደለም እያሉ በታላቅ ድፍረት ሲናገሩ ይደመጣሉ። ብዙዎችንም እያሳቱ ይገኛሉ። በመጥምቁ ዮሐንስ የተመሰከረልንና "የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ" ዮሐ 1:29 የሚለው ቃል በካልቪኒስቶች አስተምህሮ "ለኛ ለተመረጥነው እንጂ ለዓለሙ ሁሉ አይደለም" በሚለው መቀየር አለበት እንደማለት ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ በአዳም አለመታዘዝ ሞት ለሁሉ እንደደረሰ፣ በአንዱ በኢየሱስ መታዘዝ ሕይወት ለሁሉ እንደበዛ እንዲህ በማለት ይነግረናል። “በአንዱ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ኃጢአተኞች እንደ ሆኑ፥ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ።” ሮሜ 5፥19 ከእኛ ከኃጢአተኞቹ የሚጠበቀው እግዚአብሔር በልጁ ሞት እንዳዳነን፣ ሕይወትም እንደሰጠን ማመንና መቀበል ብቻ እንጂ ከእኛ በሆነ ሥራ አይደለም። "ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም" ኤፌ 2:8—9 ነገር ግን ካልቪኒስቶች ሥራም፣ እምነትም፣ ማወቅም፣ መረዳትም፣ ማመንም ሳይጠበቅብን አስቀድሞ በእግዚአብሔር የተመረጥነውና የተለየነው እኛ ብቻ /predestination/ የተሰጠን ስንድን ለሲኦል የተዘጋጁት ደግሞ ያልተመረጡና አስቀድሞ የተፈረደባቸው ናቸው በማለት አምላካዊ ምህረቱን ለግላቸው በመውሰድ በሌሎች ላይ የፍርድ ቃል በድፍረት ሲናገሩ አይሰቀጥጣቸውም። ይህ አባባላቸው ኢየሱስ የተሰቀለው አስቀድሞ ለተመረጡና ለተወሰኑ ሰዎች እንጂ በእርሱ አምነው ለሚመጡ ለዓለሙ ሁሉ አይደለም ለማለት የሚረዳቸውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥቅስ ቦጭቀው ሲጠቀሙ ይህንን ይጠቅሳሉ። “አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው።” ሮሜ 8፥30 ይሄንን ቃል ሲያብራሩ እኛ /ካልቪኒስቶቹ/ ራሳቸውን ማለታቸው ነው። አስቀድሞ እንድንድን የተወሰነልን ነን። ከእንግዲህ የትኛውንም ኃጢአት ብንሰራ አንጠፋም። አስቀድሞ በተሰወነልን መሠረት የጠራን አንዴ ልጆቹ አደረገን። አፅደቆም በሰማይ አከበረን ይላሉ። ከዚህ ከእግዚአብሔር ቃል እውነት ፍፁም ተቃራኒ በሆነ ክህደት ውስጥ እንዲዘፈቁ ያደረጋቸው ሰይጣናዊ ትርጉም ሁለት መሰረታዊ ነገርን ከመሳት የመጣ ነው። እሱም፣ 1/ የእግዚአብሔር ሁሉን አዋቂነት ወደሰውኛ እውቀት ማውረድና 2/ የእግዚአብሔርን ምሕረትና የይቅርታ ሚዛን አለመረዳት ናቸው። እግዚአብሔር አምላክ የማያውቀውና የተሰወረበት ምን ምስጢር አለ? እግዚአብሔር ፍጥረትን ከፈጠረበትና ዓለማትን ከሚያሳልፍበት ሁሉን ቻይነቱ፣ የሉዓላዊነት ሥልጣን ውጪ የሆነና መሆን የሚቻለው አንዳችም ፍጥረት የለም። ይህም የእግዚአብሔር የሁሉን አዋቂነቱ /Omniscient/ እና የከሃሌ ኩሉነት /Omnipotent/ በራሱ አምላካዊ ባህርይው የሚገኝ ነው። ከዚህ ተነስተው እነዚህን ጥያቄዎች ብናነሳ የምናገኛቸው ትክክለኛ መልሶች ያሉት በእርሱ ዘንድ ብቻ ናቸው። የሰው ልጅ ከተፈጠረ ጀምሮ ስንት ሰው ተወልዷል፣ በፆታ ስንቱ ወንድ ስንቱስ ሴት ነው? ስንትስ ሰው ሞቷል፣ ስንት ሰውስ በሕይወት አለ? ስንቱ ገነት ገባ? ስንቱስ ሲዖል ወረደ? የሚሉትን ጥያቄዎች ብንጠይቅ ይህንን በትክክል የማወቅ ኃይሉ ያለው በእግዚአብሔር ዘንድ ብቻ ነው። በዚህም እግዚአብሔርን ሁሉን አዋቂ አምላክ እንለዋለን። “ፍጥረታችንን እርሱ ያውቃልና፤ አቤቱ፥ እኛ አፈር እንደ ሆንን አስብ።” መዝ 103፥14 “የጠለቀውንና የተሠወረውን ይገልጣል፤ በጨለማ ያለውን ያውቃል፥ ብርሃንም ከእርሱ ጋር ነው።”ዳን 2፥22 የእግዚአብሔርን ሁሉን አዋቂነት ካልቪኒስቶቹ ራሳቸውን ከፀደቁት ጎራ ጨምረው እግዚአብሔር ዓለም ሳይፈጠር የፈረደባቸውንና በሰማይ ያፀደቃቸውን ስለሚያውቅ እኛን ከፀደቁት አድርጎ አስቀድሞ ወደፅድቁ ስለጨመረን ኩነኔ የሚባለው ነገር አይመለከተንም እያሉ በአስቀድሞ መወሰን/Predestination/ ውስጥ ራሳቸውን ያስቀምጣሉ። እግዚአብሔር ሁሉንም አዋቂ ነው ማለት ጄምስን ኮንኜዋለሁ፣ ገብረማርያምን ደግሞ አፅድቄዋለሁ ብሎ አስቀድሞ ውሳኔ የሰጠበት ሰው የለም። እንደዚያ አስቀድሞ ከተወሰነ የኢየሱስ ሰው መሆን ለምን አስፈለገ? ለምንስ ተሰቀለ? እምነትስ ምን ሊጠቅመን? እምነትንስ በሥራ መግለፅ ምን ሊጨምር? አስቀድሞ ለፅድቅ የተወሰነ ሰው ስለኃጢአት የሚከፈል ዋጋስ ለምን አስፈለገው?ቢከፈልለትም ሆነ ባይከፈልለት አስቀድሞ የተወሰነለትን ከመቀበል የሚያግደው ነገር ምን አለ?የሚሉ ጥያቄዎችን ብናነሳ መሆን የሚገባቸው ትእይንቶች/ ትርኢቶች/ እንጂ በመሰረታዊ የሰው ልጆች የመዳን መንገድ ላይ ትርጉም የሌላቸው ሆኖ እንዲታዩ የሚያደርግ ነው። ውሳኔው ቀድሞ ስለተሰጠ መዳኑ አይቀርበትም። ቀራንዮ ላይ የተፈፀመው ስቅለት አስቀድሞ የተነገረለትን ለማሳየት የተደረገ ትርኢት ነው ማለት ነው። ይህ የጆን ካልቪን ትምህርት አደገኛና የእግዚአብሔርን ፍፁም የሆነ ፍቅር በመሻር ሰው የሚፈረድበት በራሱ ምርጫ ሳይሆን ለሲዖል እሳት እንደማገዶ እንጨት አስቀድሞ አዘጋጅቶት የነበረውን ሰው ወደእሳት በመወርወር የሚደረግ ድምዳሜ እንጂ በማመኑ ወይም ባለማመኑ የሚደረግ ፍፃሜ አይደለም የሚል ክህደት ነው። ይህም እግዚአብሔር ሰው በምርጫው እንዲወስን ነባቢት፣ ለባዊትና ሕያዊት ነፍስ አልሰጠውም የሚል አምላክን እንደጨካኝ ገዢ የሚስል ሰይጣናዊ ትምህርት ነው። ዮሐንስ በራእዩ የጻፈልን ቃል፣ "ዓመፀኛው ወደ ፊት ያምፅ፥ ርኵሱም ወደ ፊት ይርከስ፥ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅ ያድርግ፥ ቅዱሱም ወደፊት ይቀደስ አለ። እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ። አልፋና ዖሜጋ፥ ፊተኛውና ኋለኛው፥ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ"ራእይ 22:11—13 የሚለው ቃል አስቀድሞ በተወሰነ ነገር ላይ ዝም ብሎ የተጻፈ እንጂ ፅድቅም፣ ርኩሰትም በማድረግ እንደሥራው የሚባል ክፍያ የለም እያሉን ነው ካልቪኒስቶቹ። የጆን ካልቪን ክሂዶተ እምነትና አስቀድሞ የመወሰን /predestination/ ስህተቶች በ5 ነጥቦች የተመደቡ ናቸው። 1/ Total Depravity/ የሰው ልጅ ከውድቀት በኋላ በጭራሽ ጻድቅ መሆን አይችልም የሚል ነው። ይህ የስህተት ትምህርት በአዳም ስህተት የተላለፈው ውድቀት የሰውን ልጅ ከነአካቴው የክፋት ሁሉ ባለቤት ነው ብሎ በሰው ጆሮ የሚያንቃጭል የሰይጣን ውንጀላ ሲሆን ሰው ሁሉ እኔን መስሏል የሚል ሰይጣናዊ ድምፀት ያለበት ክስ ነው። ከውድቀት በኋላ ለአዳም ልጆች ሁሉ የተላለፈውን ሞት የሚያስቀር የጽድቅ ሥራና ወደወጣበት ገነት የሚመልስ ማንነት በሥራው አያገኝም ማለት፣ ሰው በጎነት፣ ደግነት፣ በፈሪሃ እግዚአብሔር መኖር፣ የጽድቅ ሥራ መፈፀም አይችልም ማለት አይደለም። በመጽሐፍ ቅዱሳችን በዚህ ተግባር የተመሰከረላቸው ሰዎች ነበሩ። ለምሳሌ ሄኖክ፣ ኖኅ፣ አብርሃም፣ ሎጥ፣ ሳሙኤል፣ ኤልያስ፣ ኤልሳዕ፣ ዳንኤል፣ ሠለስቱ ደቂቅ ወዘተን መጥቀስ ይቻላል። ከዚህም የተነሳ የካልቪኒስቶች ስሁት ትምህርት በምድር ላይ የጽድቅ ስራን መሥራት በመቻልና በሥራ በመጽደቅ መካከል ያለውን ልዩነት አቅላቅለው እውነትን ደፍጥጠው ይክዳሉ። 2/ Unconditional Election /አስቀድሞ መመረጥ/ እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የሚድኑትን አስቀድሞ መርጧቸዋል። ሲመርጣቸውም ምንም ዓይነት መስፈርትና መለኪያ አላደረገም። በቃ! ጻድቅ እንዲሆኑ ተፈጠሩ የሚል ነው። ኃጢአት፣ ሥርየት፣ እምነት፣ የሚባል ነገር ለፎርማሊቲ እንጂ ከተመረጡበት አያስቀራቸውም፣ አይጨምርላቸውም። የትኛውም ኃጢአት ከምርጫው አያስቀራቸውም የሚል ሲሆን እግዚአብሔር ለሲዖል መርጦ ያስቀራቸው አሉ በማለት ፍፁም ፍቅር የሆነውን የእግዚአብሔር ፍቅር ከሰው ልብ አውጥቶ የሚጥል ሰይጣናዊ ትምህርት ነው። ሲጀመር ሲዖል ለሰይጣንና ለመላእክቱ እንጂ ለሰው ልጅ አልተፈጠረም። ማቴ 25:41 3/ Limited Atonement የኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል ላይ ሞት የተከናወነው ለእኛ አስቀድሞ ለተመረጥነው ብቻ ነው የሚል አስተምህሮ ነው። ለዚህም እንዲረዳቸው ይህንን ጥቅስ ይጠቅሳሉ። “መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።”ዮሐ 10፥11 ኢየሱስ ነፍሱን የሰጠው ለእኛ ለተመረጥነው በጎቹ ብቻ ነው የሚል ነው። ሲጀመር ካልቪኒስቶች በ/Limited Atonement/ /ለበጎቹ ብቻ/ በሚለው አስተምህሮአቸው ውስጥ ሁለት ነገር ይስታሉ። አንደኛው በማይቀየር ማዳኑ ውስጥ አስቀድሞ በጎቹ ከተመረጡ ኢየሱስ ለምን መሰቀል አስፈለገው? ዝም ብሎ እነሱን እየለየ ወደገነት ማስገባት ተገቢ በሆነ ነበር። ሲቀጥል ካልቪኒስቶች የስህተት ትምህርታቸውን ተርጉመው የኢየሱስ በጎች እኛ ነን ያሉት ራሳቸው እንጂ ካልቪኒስቶች ብቻ የተመረጡ ናቸው የሚል ማረጋገጫ በመጽሐፍም፣ በመላእክትም የተመሰከረ አይደለም። ደግሞ የተነገረን እውነት የተለየ ወንጌል የሰበከ የተረገመ ይሁን የሚል ነው። ገላ 1:8 እኛ ግን እንዲህ ብለን እናምናለን። “በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤” ገላ 3፥26 በኢየሱስ አዳኝነት ያመነ፣ የተጠመቀና እምነቱን በሥራ የገለፀ አማኝ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኗል ብለን እንናገራለን እንጂ ኢየሱስ የዓለም መድኃኒት የተባለበትን ሞትና ትንሣኤውን የካልቪኒስቶች ብቻ መድኃኒት ብለን ስለሁሉ የሞተበትን ምስጢር አንክድም። 4/ Irresistible Grace/ የካልቪኒስቶች ሌላው ስሁት አስተምሮአቸው አስቀድሞ በፀጋው የተጠሩት መቼም እንዳይጠፉ ሆነው የሚል ነው። ለዚህም ደጋፊ እንዲሆናቸው ዮሐንስ በወንጌሉ የጻፈውን የራሳቸው ብቸኛ ማረጋገጫቸው አድርገው ያቀርባሉ። “አብ የሚሰጠኝ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፥ ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም” ዮሐ 6፥37 የሚገርመው ነገር በ30 ጠገራ ብር ኢየሱስን የሸጠው ይሁዳ ከተጠሩት ሐዋርያት መካከል አልነበረም ወይ? ሲባሉ ከሐዋርያነት የተደመረው ሽያጩን እስኪፈፅም እንጂ በዘላለማዊ ጥሪ ውስጥ አልነበረም ይላሉ። ለያህዌ ስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ካልቪኒስቶች እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ላይ ቁማር ይጫወታል፣ ያለምርጫህ ብትጠፋም ላንተ መጥፋት ግድ አይሰጠውም ወደሚል የአምላክን ባህርያዊ ፍቅር ወደማስካድ ይወርዳሉ። እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ ስለሆነ የሚጠፉትንና የሚድኑትን ያውቃል ማለት የሚጠፉትና የሚድኑት እግዚአብሔር አስቀድሞ ስለወሰነባቸው ሳይሆን ሰዎች በሚያደርጉት የራሳቸው ውሳኔ የተነሳ መሆኑን አይቀበሉም። አዳም ከገነት ከመባረሩ በፊት ፍጻሜውን እግዚአብሔር ያውቅ ነበር ማለት አትብላ ያለውን እፀ በለስ በግድ እንዲበላ ስለወሰነበት ነበር ብሎ ማቅረብ አደገኛ ክህደት ነው። ይህም የሰው ልጅ በራሱ ማሰብና መወሰን የማይችልና አስቀድሞ በተገጠመለት የውሳኔ ሶፍትዌር የሚንቀሳቀስ ቁስ ነው እንደማለት ነው። የተወሰነብህን ትኖራለህ እንጂ በእውቀትም፣ በእምነትም የምትጨምረውና የምትቀንሰው ነገር የለም ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችን የሚነግረን አንዴ በተሰጠ ምርጫ የለሽ ውሳኔ ሳይሆን የምናምነው አምላክ አውቀን በዚሁ በእምነታችን ፀንተን ስንቆይ እንደሆነ በግልፅ ይነግረናል። “የመጀመሪያ እምነታችንን እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ፥ የክርስቶስ ተካፋዮች ሆነናልና፤” ዕብ 3፥14 እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ከወጡ በኋላ ወተትና ማር ወደምታፈሰው ምድር ሳይገቡ በምድረ በዳ የቀሩት እግዚአብሔር በረሃ በልቷቸው እንዲቀሩ አስቀድሞ በወሰነባቸው ውሳኔ ሳይሆን ድንቅና ተአምራትን አድርጎ ከሰማይ መና፣ ቀን በደመና፣ ሌሊት በብርሃን ዓምድ እየመራቸው በነበረው አምላካቸው ላይ በማመፃቸው ነበር። " ዛሬ ድምጹን ብትሰሙት፥ በማስመረር እንደሆነ ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ። ሰምተው ያስመረሩት እነማን ነበሩ? በሙሴ ተመርተው ከግብጽ የወጡ ሁሉ አይደሉምን? አርባ አመትም የተቆጣባቸው እነማን ነበሩ? ሬሳቸው በምድረ በዳ የወደቀ፥ ኃጢአትን ያደረጉት እነርሱ አይደሉምን? ካልታዘዙትም በቀር ወደ እረፍቱ እንዳይገቡ የማለባቸው እነማን ነበሩ? ባለማመናቸውም ጠንቅ ሊገቡ እንዳልተቻላቸው እናያለን" ዕብ3: 15—19 5/ PERSEVERANCE OF THE SAINTS ይህ ማለት አንዴ ከዳንክ ለዘላለም ድነሃል። በየትኛውም ኃጢአት ወይም በዓመጻ የሚጎድልህ ማንነት አይኖርህም ማለት ነው። Once saved, always saved ይሉሃል። በካልቪኒስቶቹ ዘንድ በዕብራውያን 10:36 ላይ የተመለከተው በእምነት ፀንቶ፣ ፈቃዱን እያደረጉ መኖር ነገር እርባና የለውም። “የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና።” ዕብ 10፥36 አንዴ የዳነ፣ ለዘላለም የማይጠፋ ስለሆነ በካልቪኒስቶች ዘንድ የሐዋርያው ጴጥሮስ ምክር ምንም አያስቀርበትም። “ስለዚህ፥ ወዳጆች ሆይ፥ ይህን እየጠበቃችሁ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ ሆናችሁ በሰላም በእርሱ እንድትገኙ ትጉ፥” 2ኛ ጴጥ 3፥14 የእግዚአብሔር ፈቃድ ብታደርግም፣ባታደርግም አንዴ ድነሃልና አትጠፋም፣ አትጨነቅ። ዮሐንስ በመልእክቱ የፃፈው ካልቪኒስቶችን አይመለከትም። ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው የሚለው ቃል ቢኖርም አንዴ ስለዳንክ ችግር የለውም ይሉሃል። “ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፥ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና።”1ኛ ዮሐ 3፥8 አንዴ ስለዳንክ በኃጢአት የተነሳ ከዲያብሎስ ብትሆንም አትጨነቅ፣ አትጠፋም እያሉ ለድፍረት ኃጢአት ያበረታቱሃል። ኃጢአት መስራት፣ አለመስራትህ የሚቀንስብህ ወይም የሚጨምርልህ ነገር የለም ይሉሃል። “ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።”1ኛ ዮሐ 2፥17 ፈቃዱን ብታደርግ ጥሩ ነው። ሳትፈፅመው ብትቀርም ችግር አያስከትልብህም፣ አትጨናነቅ፣ አንተ ለዘላለም የተመረጥህ ነህና። ዮሐንስ በእግዚአብሔር ዘላለማዊ ዓላማ ውስጥ ለመኖር ፈቃዱን መፈፀም ተገቢ ነው ያለው የራሱ ግምት በመሆኑ ካልቪን ያሻሻለውንና አንዴ የዳነ፣ ለዘላለም ዳነ የሚለውን ትምህርት ተከተል ይሉሃል ከሃዲዎቹ! ማጠቃለያ፣ ካልቪኒስቶቹ የሳቱት እውነት፣ የምሥራቹ ቃል የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል እንጂ የጆን ካልቪን ትርጉም፣ አባባል፣ አገላለፅ ወይም የአስተምህሮ አቋም አለመሆኑን አለማወቃቸው ነው። ካልቪን በአንድ ወቅት የተለየ የወንጌል አስተምህሮ ተገልጾልኛል ብሎ የራሱን ትርጉም ይዞ የመጣ ሰው እንጂ የምሥራቹ ቃል ምንጭ ስላልሆነ ካልቪኒስት ነኝ ብሎ እሱን መከተል አደገኛ ስህተት ነው። ማንም አማኝ የወንጌልን ትምህርት በብዙ መንገድ፣ ከብዙ ሰዎች ሊሰማ ወይም ሊያገኝ ይችላል። ያ ማለት ግን የወንጌል እውነት እሱ ከሰማበት ቦታ ብቻ ይገኛል ማለት አይደለም። የየትኛውም ትምህርት ማረጋገጫና መመዘኛ መንፈስ ቅዱስና የምሥራቹ ቃል እውነት መሆኑን አለማወቃቸው ነው። ሉተር፣ ካልቪን፣ ዝዊንግሊ፣ ኤራስመስ፣ ኖክ፣ ዊክሊፍ፣ ኸስ፣ ሜላንክቶን ወይም ቲንዳል የእውነት ቃል ምንጭ ወይም የመጨረሻው የእውነት ማረጋገጫ ሊሆኑ እንደማይችሉ አለመረዳታቸው ነው። ከኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ይልቅ ግለሰቦቹ በሰጡት ትንታኔ ላይ በመመስረት ለማመን መሞከራቸው ነው ካልቪኒስት ሆነው ለመኖር የወሰኑት። እኛ ግን የተሰቀለልንና ከሞት ያዳነን የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይና ደቀመዛሙርት እንጂ የአጵሎስ ወይም የጳውሎስ አይደለንም። ከሰማይ በታች እንድንበት ዘንድ የተሰጠን ስም ማነው? ከሰማይ በታች ሊድኑበት ለወደዱና ወደእርሱ ለመጡ በሙሉ የሚያድነው ስም ኢየሱስ ብቻ ነው። ከሰማይ በታች የተሰጠ የካልቪን አስተምህሮ፣ ለካልቪኒስቶች ሊኖር ይችላል። እኛን ክርስቶሳውያንን አይመለከትም። የካልቪን የሚባል አስተምህሮም፣ መምህርም የለንም።

Saturday, January 13, 2024

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዋና ችግር ጳጳሳት ናቸው!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዋና ችግር ራሳቸው ጳጳሳቱ ናቸው። ምክንያቶቹ፣ 1/ አንድ ወጥ የሆነ የቀደምት አበው መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ የለውም። ተረት፣ ተረት፣ እንቆቅልሽና እንቶ ፈንቶውን ስህተት አርሞ በትክክለኛው የወንጌል ጎዳና ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትሄድ ማድረግ አልቻለም። ዳንኤል 5፣ 24—28 ስለዚህም እነዚህ የእጅ ጣቶች ከእርሱ ዘንድ ተልከዋል፤ ይህም ጽሕፈት ተጽፎአል። የተጻፈውም ጽሕፈት፦ ማኔ ቴቄል ፋሬስ ይላል። የነገሩም ፍቺ ይህ ነው፤ ማኔ ማለት፥ እግዚአብሔር መንግሥትህን ቈጠረው ፈጸመውም ማለት ነው። ፋሬስ ማለት፥ መንግሥትህ ተከፈለ፥ ለሜዶንና ለፋርስ ሰዎችም ተሰጠ ማለት ነው። ከዚህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል አንፃር ቤተክርስቲያኒቱ መፈረካከሷ ገና ይቀጥላል። 2/የጳጳሳቱ ጉባዔ በቤተ ክርስቲያኒቱ ትልቁ የሥልጣን ማዕከል ነው። ነገር ግን ቤተ ክርስቲያኒቱን በመንፈሳዊ ምሳሌነት፣ በእውቀት፣ በዘመናዊ አስተዳደርና መዋቅር መምራት አልቻለም። በዚህም የተነሳ ዘረኝነት፣ ሌብነት፣ ዘረፋ፣ ጉቦ፣ የፍትህ መጓደል፣ ጥንቆላና አስማተኝነት ከጳጳሳቱ ጀምሮ እስከታችኛው መዋቅር ድረስ የዕለት ከዕለት ተግባር ነው። ከዚህ የተነሳ የሚከናወነው አምልኮተ እግዚአብሔር ከምእመናኑ የሚገኘውን ገንዘብ ለመሰብሰብና ጥቅም ማስገኛ ምንጭ ከማድረግ ባለፈ እግዚአብሔርን ከመፍራትና ለቃሉ ለመገዛት ካለ መንፈሳዊ ብቃት የተነሳ አይደለም። 3/ ቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ፣ የቅርስ፣ የሥነ ፅሑፍ፣ የሰነድ ባለቤት ሆና ሳለ ይህንን ሁሉ አራግፋ በመጣል የገዢዎች ባለሟል፣ ትዕዛዝ ፈጻሚ እና የመከራ ጽዋ የምትጎነጭ እርስ በእርሷ የምትባላ ሆና እያየናት ነው። ሲጠቃለል፣ ቤተክርስቲያኒቱ ጥቋቁር ጨርቅ በተሸፋፈኑ ጳጳሳት ከመፍረስ አትድንም። ወደቀደመ ክብሯ አትመለስም። ከተረት፣ ተረት እና ከፈጠራ የስህተት አስተምህሮ ወጥታ ወደእውነተኛ የወንጌል መንገድ ልትገባ አትችልም። ቢመርም እውነቱ እሱ ነው።

Monday, May 2, 2022

ነብይ ቡላ

አብይ አህመድ ያፈራልን የዘመኑ እብዶች

Saturday, April 16, 2022

ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር ማቴ ፳፩፣፱

«ሆሳዕና» ቃሉ ከሁለት አረማይክ ቃላት የተሰራ ሲሆን ትርጉም «እባክህ እርዳ፣ አሁን አድን» ማለት ነው። እብራይስጡም ይህንኑ ቃል ወርሶ «הושענא » ሆሻአና ሲል ይገኛል። አዎ «አሁን አድን፣ እባክህ እርዳን» ብሎ የአዳም ዘር ያጣውን ልጅነትና የደረሰበትን ሞት ለመላቀቅ የሚያሰማው የጩኸት ድምጽ ነው፣ «ሆሳዕና»!!! ዳዊት ነቢይ በመንፈስ ቅዱስ ተመልክቶ ማዳኑን ሲጣራና አሁን ናልን ሲል ከዘመናት በፊት አድምጠነዋል። የውስጥ ዓይኖቹ ሩቅ አይተዋል። ማዳኑንም ሽተው እንዲህ ሲል ዘምሮለታል። «አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አድን አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አቅና» መዝ ፻፲፰፣፳፭ ያ ማለት ደግሞ « אָנָּ֣א יְ֭הוָה הֹושִׁ֘יעָ֥ה נָּ֑א אָֽנָּ֥א יְ֝הוָ֗ה הַצְלִ֘יחָ֥ה נָּֽא » አና ያኽዌ ሆሳአና አና ያኽዌ ሆስሊኻ ና» የሚለው የእብራይስጡ ቃል ነው። አበው የማዳኑን ነገር አስቀድመው አይተው በተስፋ «ሆሳዕና» እያሉ ዘምረዋል። የእግዚአብሔር የማዳን ሥራ በክርስቶስ ኢየሱስ እስኪገለጥ ዘወትር በእንባና በዝማሬ ወደ ተስፋው ፍጻሜ ድምጻቸውን ያሰሙ ነበር። አዎ ንጉሥ ክርስቶስ ከዘጠና ዘጠኙ በጎች መካከል የጠፋውን አንዱን በግ ፍለጋ ንጉሥ ሆኖ ሳለ እንደንጉሥ ያይደለ በአህያ፣ ለዚያውም በውርንጫ ተቀምጦ «የአሁን አድን (ሆሳዕና)» ጩኸት ሊመልስ በጽዮን ከተማ ይመጣል፤ ይህንንም ዘካርያስ ከዘመረው ዘመናት ተቆጥረው ነበር። «አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ትሑትም ሆኖ በአህያም፥ በአህያይቱ ግልገል በውርጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል» ዘካ ፱፣፱ ምንኛ ይደንቅ? ምንኛስ ይረቅ? ንጉሥ ስለመምጣቱ አስቀድመው የተናገሩለትና ከዘመናት በፊት ማዳኑን አይተው በእልልታ የዘመሩለት!! ሰማያዊ ንጉሥ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ያለዘርዓ ብእሲ ከስጋችን ተዛምዶ ማዳኑን ሲጠብቁ፤ ከሩቅ አይተው ሲጣሩ፣ ሲዘምሩለትና አንድ ቀን ማዳኑ እንደሚሆን ተስፋ ሲያደርጉት የነበረው ሰዓቱ ደርሶ በመካከላቸው ሲገኝ ይጠብቁት የነበረው ዓይነት ሳይሆን ውበት የሌለውን ንጉሥ ለመቀበል የገዛ ወገኖቹ ተቸግረው ነበር። አዎ የደም ግባት ብቻ ሳይሆን የንጉሥ ወግ የሌለው፣ በአህያ ለዚያውም በውርንጫ የሚመጣ ንጉሥ እንዴት ይቀበሉት? «በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅም መሬት እንደ ሥር አድጎአል። መልክና ውበት የለውም፥ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም» ኢሳ ፶፫፣፪ አባቶቻቸው ለዘመናት «ሆሳዕና፣ ማዳንህ አሁን ይሁን» ያሉለትና የዘመሩለት በዕለተ ቀጠሮው ማዳኑን ሊያሳይ ከጽዮን ደጃፍ ቀርቦ ሳለ የማያውቁት፣ ያልሰሙት፣ ትንቢቱን ያላነበቡት «ሆሳዕና» ሲሉ ትልልቆቹ ዕብራውያን ግን ዝም አሉ፣ ዝም በሉም አሉ! «ነገር ግን የካህናት አለቆችና ጻፎች ያደረገውን ድንቃ ድንቅ በመቅደስም፣ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ የሚጮኹትን ልጆች ባዩ ጊዜ፥ ተቈጥተው፣ እነዚህ የሚሉትን አትሰማምን? አሉት» የማዳኑ ጌታም፣ «እሰማለሁ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራስህ አዘጋጀህ የሚለውን ቃል ከቶ አላነበባችሁምን? አላቸው» ማቴ ፳፩፣ ፲፭-፲፮ ኢየሱስ ክርስቶስ የእነዚህን ሕፃናት ዝማሬና ምስጋናን የሰማው ከቤተ ፋጌ ወደ ኢየሩሳሌም ማዳኑን ሊፈጽም በመጣ ጊዜ ነበር። ቤተ ፋጌ ከኢየሩሳሌም ከተማ ምሥራቃዊ አቅጣጫ በቢታንያና በደብረ ዘይት ተራራ መካከል የምትገኝ መንደር ነበረች። ቤተ ፋጌ ማለት በአረማይክ «ያልበሰለ በለስ ቤት» ማለት ነው። ርቀቱም ከኢየሩሳሌም የሰንበት ያህል ምዕራፍ ነበር። ጌታ ኢየሱስም ከኢያሪኰ ከተማ ወደኢየሩሳሌም ሲወጣ ካረፈባት ከቤተ ፋጌ መንደር ሁለቱን ደቀ መዛሙርት ልኰ ውርንጫይቱን ከታሰረችበት ፈትተው እንዲያመጡለት አዟል። «ወደ ኢየሩሳሌምም ቀርበው ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ ሲደርሱ፥ ያንጊዜ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ላከ፥እንዲህም አላቸው፦ በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርስዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ» ማቴ ፳፩፤፪ ያን ጊዜም በቀደምት አበው የተነገረው ትንቢትና ዝማሬ ፍጻሜ አገኘ ማለት ነው። «የሚቀድሙትም ሕዝብ የሚከተሉትም። ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር» ማቴ ፳፩፣፱ ይሁን እንጂ ኢየሩሳሌም ለሆሳዕና አልተዘጋጀችም ነበር። ይልቁንም ቤተ መቅደሱ አካባቢ ስለማዳኑ ዝማሬ በማቅረብ ፋንታ የጦፈ የንግድ ገበያ ደርቶበት ነበር። ቤተመቅደሱ የጸሎት ሥፍራ መሆኑ ቀርቶ የሻጮችና የለዋጮች መድረክ ሆኖ ነበር። ያኔ ማዳኑ የቀረበላት ኢየሩሳሌም በመቅደሱ በራፍ ስትሸጥ፣ ስትለውጥ መድኃኒቱን ሆሳዕና እያለች መቀበልን እንዳልቻለች ሁሉ የዛሬዋ ቤተክርስቲያንስ ንግድና ሸቀጥ የሌለበትን «ሆሳዕና» እያከበረች ነው ወይ? ብለን ብንጠይቅ ራስን ማታለል ካልተጨመረበት በስተቀር፣ መሸጥ መሸቀጡ የሌለበትን «ሆሳዕና» የሚያከብር የለም ነው መልሱ። ዐውደ ምሕረቱ ሱቅ በደረቴ ያልሆነበትን ሥፍራ ማግኘት ከባድ ነው። ኢየሱስ ማዳኑን ከመፈጸሙ በፊት እነዚህን ነጋዴዎች አስወግዷል። ገበታቸውን ገልብጧል። እየገረፈ አስወጥቷል። የወንበዴዎች ዋሻ የሆነውን የጸሎት ቤት ጠራርጓል። ዛሬስ ቤቱ ስንት ወንበዴ መሽጎበት ይሆን? ወንበዴዎቹ ይዘምራሉ፣ ሆሳዕና ይላሉ፣ የዘንባባ ዝንጣፊ ይይዛሉ፣ በጣታቸው፣ በግንባራቸው ያስራሉ። ወንበዴዎች ናቸው ተብለው እንዳይርቋቸው የአምልኰ መልክ አላቸው። ቤተመቅደሱን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁ ያለው በግብር ውንብድና በመልክ ግን አገልጋይ ይመስሉ የነበሩትን የመቅደሱን ሰዎች ነበር። ዛሬም እንደዚያው!! በሌላኛው ቀንም በዚያው በመቅደሱ ሲያስተምር ዋለ። የወይኑ ጌታ ስለወይኑ ደኅንነት የላካቸውን አገልጋይ ሠራተኞች ታሪክ አወጋቸው። የሕይወት ለውጥ ለወይኑ ባይሆንለት ይፈሩት እንደሆነ አንድ ልጁን ቢልክም ገበሬዎቹ ወራሹ ይህ ነው እንግደለው ብለው መከሩበት፣ መክረውም አልቀረም፣ ከወይኑ አውጥተው ገደሉት። ስለዚህ የወይኑ ጌታ ገዳዮቹን ምን የሚያደርግ ይመስላችኋል? ሲል ይጠይቃቸዋል። እነሱም መልስ መለሱ። መልሱ ግን በራሳቸው ላይ የሚሆን የምስክርነት ፍርድ ነበር። «ፍታሕ በርእስከ» ማለት ይህ ነው። እነሱም እንዲህ ሲሉ በራሳቸው ፈርደው ተናገሩ። «እርሱም፦ ክፉዎችን በክፉ ያጠፋቸዋል፥ የወይኑንም አትክልት ፍሬውን በየጊዜው ለሚያስረክቡ ለሌሎች ገበሬዎች ይሰጠዋል አሉት» ማቴ ፳፩፤፵፩ የአይሁድ ፋሲካ ከመሆኑ ሶስት ቀን ቀደም ብሎ ደብረ ዘይት ተራራ ላይ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ይነጋገር ነበር። ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይወድቅ የማይቀረው ለምድነው አሉት? ስለረገማት በለስና ስለኢየሩሳሌም ጥፋት ተናገረ። ኋላም በሮማዊው ጥጦስ ትንቢቱ ተፈጸመ። ፍሬ አልባዋ በለስ እስራኤል ጠፋች። ጴጥሮስ ደብረ ዘይት ላይ ሌላ ጥያቄ አነሳ። «እርሱም፦ መምህር ሆይ፥ እንግዲህ ይህ መቼ ይሆናል? ይህስ ይሆን ዘንድ እንዳለው ምልክቱ ምንድር ነው? ብለው ጠየቁት» የቅርቡን ጊዜና መጨረሻውን ዘመን ምልክቶች ነገራቸው። የቅርቡ ጊዜ የኢየሩሳሌም መከበብ የበለስ መድረቋ ጊዜ መሆኑን እንዲህ አለ። «ኢየሩሳሌም ግን በጭፍራ ተከባ ስታዩ በዚያን ጊዜ ጥፋትዋ እንደ ቀረበ እወቁ» ሉቃ ፳፩፤፳ በዚህ የኢየሩሳሌም የመጥፊያ የፍርድ ቀን መድረሱን አሳይቷል። እንደገናም የኋለኛውንም ዘመን ትንቢት ደግሞ ይህች የተረገመች በለስ ስታቆጠቁጥ በጋ እንደ ደረሰ ታውቃላችሁ፤ ያኔ ደግሞ የመጨረሻው የፍርድ ቀን እንደደረሰ ምልክት ይሆናል አላቸው። «ምሳሌንም ነገራቸው እንዲህ ሲል፦ በለስንና ዛፎችን ሁሉ እዩ፣ ሲያቈጠቍጡ ተመልክታችሁ በጋ አሁን እንደ ቀረበ ራሳችሁ ታውቃላችሁ።እንዲሁ ደግሞ እናንተ ይህ ሁሉ መሆኑን ስታዩ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ ቀረበች እወቁ» ሉቃ ፳፩፤፳፱-፴፩ አዎ ! የመጨረሻው ዘመን ዋናው ምልክት ፍሬ አልባዋና የደረቀችው በለስ ማቆጥቆጥ መጀመሯ ነበር። ያኔ የአጨዳው መከር ስለመድረሱ ጫፏ ሲለሰልስና ማቆጥቆጥ ሲጀምር በጋ እንደደረሰ እወቁ« ተብሏል። እናም የምንዘምረው ዝማሬ ትልቅ ትርጉም አለው። ማዳኑን አይተናል። «ሆሳዕና በአርያም » እያሉ መዘመር ብቻውን ግን ዋጋ የለውም። ኢየሩሳሌም ተዘምሮባት ነበር። ግን ፍሬ የሌለባት በለስ በመሆኗ ደረቀች። በሚያምር ውብ ድንጋይ ፵፮ ዘመን የታነጸውን መቅደስ ማዳን አልቻለም። ተራሮችን ውደቁብን እስኪሉ ድረስ የወረደውን መከራ መሸሸግ የቻለ ዝማሬ አልተገኘም። መቅደሱ በወንበዴዎች ተሞልቶ ነበር። ወንበዴዎቹ ልጁን አልተቀበሉትም። የተቀበሉትም ፍሬ አላፈሩም። ስለዚህ በጭፍራ ተከበው ለሺህ ዘመናት ጠፉ። ዛሬ በኛ የሚሆን ፍሬ አልባነት ጥፋቱ ለሺህ ዘመን አይደለም። ለአልቦ ማኅለቅት እንጂ!! በእድሜአችን ስንት «ሆሳዕና በአርያም» አሳለፍን? ማዳኑ በተደረገለት ማንነታችን ውስጥ ስንት ፍሬ አፈራን? የተራበው ኢየሱስ ከእኛ የሚፈልገውን ፍሬ ይዘናል? ወይስ ፍሬ አልባ ሆነን ለቁጣ የተዘጋጀን እንሆን? «ሆሳዕና በአርያም» ማለቱ ብቻውን አያድንም፣ ማዳኑንም አያመጣም። የወንበዴ ዋሻ ማንነታችንን እናጽዳ። ከዚህ ዓለም ሽቃጭና ልዋጭ ማስመሰያ ማንነት እንውጣ! በጎ ፍሬ እንዲያፈራ ለተላከው የወይኑ ባለቤት ወራሽ እንገዛ! ያኔ «ሆሳዕና በአርያም» ስንል ማዳኑ ፈጥኖ ይሆንልናል። ከኢየሱስ በቀር ማዳን የሚቻለውና ተስፋ የሚሆነን ማነው? ከሥጋ ለባሽ ማንም የለም። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “በሰው የሚታመን፣ በሥጋ ለባሽ የሚመካ፣ ልቡንም ከእግዚአብሔር የሚያርቅ የተረገመ ነው። አዎ ሆሳዕና በአርያም! በዚህም አንተ ብቻ መታመኛ ነህ፣ በወዲያኛውም አንተ ብቻ! ሆሳዕና በአርያም። ሃሌ ሉያ!!!!!!!!

Friday, April 8, 2022

ቻት ላይ ነን አትረብሹን!

ዮሐንስ 10 ¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯ ¹¹ መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል። ¹² እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ሞያተኛ ግን ተኵላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ ይሸሻል፤ ተኵላም ይነጥቃቸዋል በጎቹንም ይበትናቸዋል። ¹³ ሞያተኛ ስለ ሆነ ለበጎቹም ስለማይገደው ሞያተኛው ይሸሻል።

Friday, February 4, 2022

የኦሮሙማ ህልመኞችና የኦርቶዶክስ ጳጳሳት!

የኦሮሙማ ሀገር ምስረታ ህልመኞች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን የሚቆጥሯት የአማራና የትግሬ ንብረት እንደሆነች አድርገው ነው። የሁለቱ ብሄሮች ደናቁርት የፖለቲካ ኤሊቶች ደግሞ ለስልጣን ካላቸው ጉጉት አንዱ ለአንዱ ጠላት መሆን ከጀመረና በሴራና ተንኮል መተላለቅ ከጀመረ ግማሽ ክፍለ ዘመን ተቆጥሯል። ሰርቶ ከመኖር በስተቀር ስለፖለቲካው ምንም እውቀት የሌለው ደሃው ህዝብ በማያውቀው የፖለቲካ እሳት እየተጠበሰ ህይወቱን እየተነጠቀ: ሀብትና ንብረቱ ወድሞ ባዶ እጁን ቀርቷል። ይሄ እድል እጁ ላይ የወደቀው የኦሮሙማ መንግስት ከአማራና ከትግራይ እልቂትና ውድመት በኋላ ስልጣኑን አደላድሎ የተረፈችው ኦርቶዶክስን ሰባብሮ ለማጥፋት በቅጥረኞቹ በአባ ገዳ በላይ መኮንንና ወታደራዊ ሹመት ብቻ በቀረው ጀነራል አባ ዮሴፍ (እንኳን ጳጳስ የተመሰከረለት ወንበዴ ለመባል ይበዛበታል) በኩል ወጥሮ ይዟታል። ፊደል ተራራው አባ ወ/ኢየሱስ እና ቄሮ ኃይሉ ጉተታ የኦሮሙማው መንግስት ጉዳይ አስፈፃሚዎቹ ናቸው። ቤተክርስቲያኒቱ በአፄው ዘመን የአፄዎቹ አጋፋሪ ነበረች። በዘመነ ኢህአዴግ የህወሀት አለቅላቂ እንደነበረች ይታወቃል።  በደርግ ዘመን ፓትርያርኩ አባ መርቆርዮስ የሸንጎ አባል ነበሩ።
ዛሬ ደግሞ የኦሮሙማው መንግስት የብልፅግና ወንጌል አራማጅ ስለሆነ ቤተክርስቲያኒቱን ለቀብር እየገነዛት ነው። 
ይህ ሁሉ ሲሆን ጳጳሳቱ በየወሩ ረብጣ ደመወዝ እየበሉ በወንበራቸው ላይ ተቀምጠዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ጉዲትን ቢሮአቸው ድረስ ብትጠራቸውም ሆቴል እንገናኝ ብላ አላግጣባቸዋለች። ሀገሪቱ አሁን ለደረሰችበትና ኦርቶዶክስ እየፈራረሰች ለምትገኝበት ሁኔታ ግንባር ቀደም ተጠያቂዎቹ በመንፈስ ቅዱስ እየመራናት ነው ብለው በመንፈስ ቅዱስ ላይ የሚሳለቁ እነዚህ ጳጳሳት ናቸው። መቼም ቢሆን በነዚህ ምንደኞች ቤተ ክርስቲያን ፈውስ አታገኝም። ምንደኛ ስለደመወዙ እንጂ ስለበጎቹ አይገደውምና በነዚህ ጳጳሳት ኦርቶዶክስ ከሞት አትድንም። የበጎች እውነተኛ እረኛና ስለበጎቹ ራሱን አሳልፎ የሰጠ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው!


 

Sunday, August 22, 2021

በድንግል ማርያም የትንሣኤና የእርገት ታሪክ ላይ ችግር አለ!

ቅዱሳንን ስለማክበር ምንም ጥያቄ የለንም። ለቅዱሳንም መታሰቢያ ማድረግ የነገሮች ሁሉ ባለቤት የሆነው ኢየሱስን እስካልተካ ድረስ ችግር የለውም። ለክርስትና አስተምህሮና ለተጋድሎ ጽናት አርአያ ይሆኑናልና ታሪካቸውን እንናገራለን። ነገር ግን በሃይማኖታዊ አስተምህሮ ወቅት በወንጌል ላይ ብዙ ጥያቄዎችን የሚያስነሱትና የስህተት ችካሎች አልነቀል ያሉት በመታሰቢያና በአክብሮት ምክንያት ስር ተወሽቀው ኢየሱስን እየጋረዱ ስላስቸገሩ ነው። ከነዚህ የስህተት አስተምህሮዎች መካከል አንዱ የሆነው በማርያም እረፍት፤ ቀብር፤ ትንሣኤና እርገት ላይ ያሉ አስተምህሮዎች ሰዎች ዓይናቸውን ከኢየሱስ ላይ አንስተው ወደሌላ የመዳን መንገድ እንዲመለከቱ ያደረገው ተጠቃሽ ነው።

ስለማርያም እረፍት፤ትንሣዔና እርገት አብያተ ክርስቲያናት አንድ ዓይነት የእምነት አቋም የላቸውም። እንዲያውም ስለማርያም ሞትና የእርገት ዕለት በግልጽ የሚታወቅ ማስረጃ እንደሌለ በ5ኛው ክ/ዘመን የኖረው የሳላሚሱ ኤጴፋንዮስ ተናግሯል። ዕረፍቷና እርገቷ በኢየሩሳሌም እንደሆነ  የሚናገሩ ቢኖሩም  ይህንን አባባል የማይቀበሉ አብያተ ክርስቲያናትና የቴኦሎጂ ምሁራን ሞልተዋል። በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚለውን አባባል የማይቀበሉበትን ማስረጃ ሲያቀርቡም ዮሐንስ በወንጌሉ ላይ እንደተናገረው «እናትህ እነኋት አለው። ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት» ዮሐ19፤27 ባለው መሠረት ማርያም እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ ከዮሐንስ ጋር ስለኖረችና ወንጌላዊው ዮሐንስም ከጌታ ሞት በኋላ በኢየሩሳሌም  ጥቂት ዓመታትን ከቆየ በኋላ በ37 ዓ/ም ገደማ ወደ ቤዛንታይን ከተማ ኤፌሶን ሄዶ ወገኖቹን ወንጌል እያስተማረ መቆየቱንና  ማርያም በሞት እስከተለየችው ድረስ  ከ48-52 ዓ/ም እዚያው እንደነበር ብዙ ተጽፏል።
በኋላም በቅርብ ርቀት ባለችው ደሴተ ፍጥሞም  በግዞት መኖሩንና በመጽሐፍ ቅዱሳችን የተጻፈውን ራእይ የተመለከተውም እዚያ እንደሆነ ይታወቃል ። አንዳንዶች ከዶሚኒሽን አገዛዝ ቀደም ብሎ የራእይ መጽሐፉን  ከ55-65 ዓም ገደማ እንደጻፈም በታሪክ አስቀምጠዋል።

ዋናው ነገር  ማርያም በኤፌሶን ከዮሐንስ ጋር ኖራለች ወይስ አልኖረችም? ነው ጥያቄው። በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚሉ ሰዎች አንድም ጊዜ ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን ኖራለች ሲሉ አይደመጥም። ለምን?  ዮሐንስ ማርያምን እንደእናት ሊይዛት አደራ ተሰጥቶታል የሚባል ከሆነ ከዮሐንስ ጋር ኤፌሶን ስለመቀመጧ የማይነገረው ለምንድነው?  ዮሐንስ እስከ 96 ዓመቱ ድረስ ከኤፌሶንና ከደሴተ ፍጥሞ ውጪ ስለመኖሩ የተነገረ ታሪክ የለም። ማርያም ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን አልኖረችም ብሎ በመከራከርና በኢየሩሳሌም ኖራ፤ እዚያው ማረፏን በግልጽ በመናገር መካከል ትልቅ ልዩነት አለ። «እነኋት እናትህ» ባለው መሰረት አብረው ኤፌሶን ኖረው እዚያው ማረፏን በሚያምኑና ኢየሩሳሌም ኖራ እዚያው አርፋለች በሚሉት ሰዎች መካከል ያለው ልዩነት የማይታረቅ ነው።
ሮበርት ክሬው የተባለ የነገረ መለኮትና የታሪክ ጸሐፊ ዮሐንስ ወንጌላዊ ዘመኑን ሁሉ በኖረበት ከኤፌሶን ከተማ 8 ኪሎ ሜትር ወጣ ብላ ባለች ኰረብታ ላይ በተሰራ ቤት ውስጥ እንደኖረና ማርያምም እዚያ ማረፏን ጽፏል።  ይህንን በኤፌሶን ያለውን የማርያምን መቃብር የዓለም ክርስቲያኖች እንዲሆም ሙስሊሞች ሳይቀሩ ይጎበኙታል፤ ይሳለሙታል።  በቱርክ ግዛት ያለው ይህ ስፍራ በቱርካውያን ሙስሊሞች ዘንድ «ሜሪዬማና» ተብሎ ይጠራል።
ቅድስት ማርያም ከዚህ ዓለም የተለየችው መቼ ነው? ለሚለው ጥያቄ ጥንታዊያን አብያተ ክርስቲያናት የሚባሉት የምሥራቁና የምዕራቡ ጎራዎች የተለያየ አመለካከት አላቸው።
በተወለደች በ58 ዓመቷ ዐርፋለች የሚሉ አሉ። በ72 እና 63 እድሜዋም አርፋለች የሚሉ መረጃዎች አሉ። እንደ ግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ግን የሚታመነው በ64 ዓመት እድሜዋ ማረፏ ነው።  ኖረችበት ተብሎ ከሚገመተውና አርፋለች ከሚባለው ቦታ ያለው ልዩነት እንዳለሆኖ በጥር ወር ከዚህ ዓለም ተለይታ በ40ኛው ቀን ማረጓን የሚናገሩ አሉ። ይህም ሞትና ትንሣኤዋን ከልጇ ጋር ለማመሳሰል የተደረገ ጥረት ነው። በነሐሴ ወር አርፋ ከተቀበረች በኋላ ትንሣዔዋን ሳያዩ መቃብሯ ባዶ ሆኖ ስላገኙት ሐዋርያት ሱባዔ ይዘው በሦስተኛው ቀን ተገለጸችላቸው የሚሉም አሉ። እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ደግሞ በጥር ሞታ፤ በነሐሴ ተቀበረች የሚል ትምህርት አለ። በጥር ወር አርፋ፤ በነሐሴ ተቀብራለች የሚሉ ሰዎች ሥጋዋ በገነት ዛፍ ስር ለስምንት ወራት መቀመጡንና በሱባዔ ጸሎት በተደረገው ልመና የተነሳ ሥጋዋ ከሰማይ ወርዶ ለመቀበር መቻሏን አስፋፍተው ጽፈዋል።
በጥር ወር እንዳረፈች ያኔውኑ ለምን አልተቀበረችም?፤ ተብለው ሲጠየቁ ወደ ቀብር ሥጋዋን ተሸክመው ይሄዱ የነበሩት ሐዋርያት ላይ ታውፋንያ የሚባል ወንበዴ ጎራዴ ሲመዝባቸው ዮሐንስ ብቻ ሲቀር ሐዋርያቱ ጥለዋት በመሸሻቸውና ዮሐንስ ብቻውን ቀርቶ ወደ  መቃብር ሳትገባ ወደ ገነት ዛፍ ስር በመወሰዷ እንደሆነ ይነገራል።  ዮሐንስም ወደቤት በተመለሰ ጊዜ ሸሽተው የነበሩት ሐዋርያት ሥጋዋስ የታለ? ብለው ቢጠይቁት በገነት ዛፍ ስር መቀመጧን ስለነገራቸው ዮሐንስን ገነት ዛፍ ስር ሬሳዋ መቀመጡን አይቶ ለምን እኛስ ይቀርብናል በማለት ነሐሴ 1/ ቀን የጾም የጸሎት ሱባዔ ጀምረው በ15ኛው ቀን ትኩስ ሬሳ ከገነት ዛፍ ስር እንደመጣላቸውና እንደቀበሯት ይናገራሉ።
እዚህ ላይ ይሄንን ታሪክ የሚያፈርሰውና ተረት እንደሆነ የሚያሳየንን ነገር እናንሳ!
ገነት ውስጥ የሰው ሬሳ የሚቀመጥበት ዛፍ ስለመኖሩ ማስረጃችን ምንድነው? ሬሳውን ተሸክመው ገነት የገቡት ኃይሎች ታውፋንያ የተባለውን ሽፍታ ማስወገድ ለምን አልቻሉም? እጁን ቆረጡት የተባለው ተረት ለምን አንገቱን አልሆነም? ከሐዋርያቱ ተለይቶ ብቻውን የቀረው ዮሐንስ ከሽፍታው ሰይፍ እንዴት ተረፈ?  ይሄ ሁሉ ውጣ ውረድ ሲከናወን ሐዋርያቱ: መላእክቱ: ኢየሱስም አብረዋት ከነበሩ ከማርያም ሥጋ መንከራተት ጋር ምን ትርፍ አላቸው? 
ታሪኩን በሚያማልልና ልብን በሚቦረቡር ተረት መቀባባት ያስፈለገው ሰዎች ከወንጌል እውነት እንዲወጡና ልብን በተረታ ተረት በመሙላት በከንቱ ሃሳብ ውስጥ አስጥሞ ለማስቀረት ነው።
ሌላው ጥያቄ የሚያስነሳው ነገር  በጥር ወር አርፋ  ከቀብር በፊት ወደገነት ዛፍ ስር ስለመወሰዷና  ዮሐንስ ወደ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ከነገራቸው በኋላ እሱ ያየውን እኛም ማየት አለብን ያሉትና የጾም: የጸሎት ሱባኤ የገቡት ነሐሴ 1 ቀን ነው ይባላል። በጥር ወር  ገነት ገባ ለተባለ ሬሳ ምላሽ ለማግኘት ሐዋርያቱ ለምን እስከነሐሴ መቆየት አስፈለጋቸው? ሥጋዋስ 8 ወር ሙሉ ለምን ሳይቀበር ቆየ?  ሐዋርያቱ ሱባዔ ባያደርጉና እንዲቀብሯት ሬሳዋ ባይሰጣቸው ኖሮ የማርያም ሥጋ ከገነት ዛፍ ስር አይንቀሳቀስም ነበር ማለት ነው?
ለማርያም ሥጋ መቀበር ምክንያት የሆነው የሐዋርያቱ ሱባኤ መያዝ እንጂ ከቀብር ተለያይቶ የሚቀር ሆኖ ነበር ማለት ነው።
እንደሰዎቹ አባባል በጥር ወር አርፋ ሳይቀበር የቀረውን የማርያምን ሥጋ በስምንተኛው ወር ከገነት ወጥቶ ከተሰጣቸውና ከቀበሯትም በኋላ ቢሆን ወደሰማይ ስታርግ ሐዋርያቱ ለማየት አልቻሉም። የተረቱ ባለቤቶች እርገቷን ያየው ቶማስ ብቻ ነው ካሉን በኋላ ለተረቱ የታሪክ ፍሰት ውበት ሲሰጡት እንዲህ ነበር ይሉናል። ሐዋርያቱ ማርያምን ቀብረዋት ወደቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቶማስ በደመና ተጭኖ ከሀገረ ስብከቱ ከሕንድ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለስ በሦስተኛው ቀን ወደ ሰማይ ስታርግ የዳመናው ጎዳና ላይ ማርያም ስታርግ አገኛት። ቀድሞ የልጅሽን እርገት ሳላይ ቀረሁ አሁን ደግሞ ያንቺን ሳላይ ልቀር ነው? ብሎ ቢያዝን ትንሣኤዬን ያላንተ ማንም አላየም ካለችው በኋላ የተገነዘችበትን ጨርቅ እና ሰበን ለምልክት ሰጥታው እንዳረገች በሰፊው ይተረታል።
ሰዎቹ ነገሩን ሁሉ ለማጣፈጥ የሚጠቀሙበት ተረት አስገራሚ ነው። የሰው ልጅ ከትንሣኤው በኋላ የዚህን ዓለም ጨርቅና ልብስ እንደተሸከመ ወደ ሰማይ ይገባል የሚል ክርስቲያናዊ አስተምህሮ አለ ወይ?
ወንጌል ከትንሣኤ በኋላ ክርስቶስን እንመስል ዘንድ እንለወጣለን ይላል እንጂ የመቃብሩን ልብስና ሰበን እየተሸከመ ሰው ወደሰማይ ያርጋል የሚል አስተምሮ የለውም።
« 2ኛ ቆሮ 3፤18
እኛም ሁላችን በመጋረጃ በማይከደን ፊት የጌታን ክብር እንደ መስተዋት እያብለጨለጭን መንፈስ ከሚሆን ጌታ እንደሚደረግ ያን መልክ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንለወጣለን»
ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን በመቃብሩ የተገነዘበትን ጨርቅ ትቶ መነሳቱን እንጂ  ያንኑ ለብሶ መነሳቱን አላነበብንም።
ዮሐ20፤6—8 
«ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት መጣ ወደ መቃብሩም ገባ፤ የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፥ ደግሞም በራሱ የነበረውን ጨርቅ ለብቻው በአንድ ስፍራ ተጠምጥሞ እንደ ነበረ እንጂ ከተልባ እግሩ ልብስ ጋር ተቀምጦ እንዳልነበረ አየ»
የሁላችን አማኞች ትንሣዔ የክርስቶስን ትንሣዔ መምሰል ካለበት በቀብር ወቅት ከዚህ ዓለም ጉድጓድ የገባ ጨርቅ ወደ ሰማይ አብሮን የሚያርግበት ምንም መንገድ የለውም።
ተጠራጣሪ እንደሆነ ሁል ጊዜ የሚነገርበት ቶማስ በማርያም እርገት እሱ ብቻ የተለየ ተጠቃሚ እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ ሲባል የማስረጃ ጋጋታ ሲፈለግ የማርያም የግንዘት ጨርቅ ተገኘና ወደሰማይ ከማረጉ በፊት ቶማስ ተቀበለ የሚል ተረት  አቀረቡልን። ሌላው አስገራሚው ነገር በደመና ተጭኖ የመሄድ ተረት ነው።  በመንፈስ ተነጠቀ የሚል መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት በደመና ተጫነ ከሚለው ጋር የትርጉም አንድነት የለውም። (የሐዋ 8:39)
ቶማስ በደመና ተጭኖ ሲጓዝ የሚለውን አባባል እንደፊልጶስ መነጠቅ አድርገን ብንቆጥረው እንኳን የቶማስ ሰብአዊ ማንነትና የማርያም ሰማያዊ የእርገት ማንነት የተለያየና ፈጽሞ የማይገናኝን ነገር ነው።  የቶማስን የዳመና ላይ ውይይትን ከረቂቅ  ክርስቶሳዊ አዲስ ፍጥረት ጋር ለማገናኘት መሞከር የጥንቶቹን የሮማውያን የቬነስ ወጎች/fable story/ እንድናስታውስ ያደርገናል።

በሞት: ትንሣዔና በእርገት መካከል እንደዚህ ዓይነት ተረቶችን በሰውኛ ትረካ መጫወት እግዚአብሔር ስለሞትና ትንሣዔ በተናገረው ላይ መቀለድ ነው። ከሁሉ የሚገርመው ደግሞ ማርያምን በጥር ሞታለች ያሉ ሰዎች፤  በመጀመሪያው ሞት ዮሐንስ ብቻ እድለኛ ሆኖ በገነት ዛፍ ስር ለማየት በመቻሉ ይሄንን እድል እነርሱም ለማግኘት ሐዋርያቱ ሱባኤ ነሐሴ 1 ቀን ገቡ ያሉን ሰዎች ማብቂያ በሌለው ተረታቸው እንዲህ በማለት ሆዳችንን በተረት ይነፉናል።  ከቀበሯት በኋላ ቶማስ ብቻ ያየውን እርገቷን እኛም ማየት አለብን ብለው ሐዋርያቱ በድጋሚ በዓመቱ ነሐሴ 1 ቀን ሱባኤ ገቡ ይሉናል። ሐዋርያቱ ነሐሴ ወር ላይ ሙጭጭ ያሉበት የሱባኤ የፍቅር ጊዜ ለምን ይሆን? ደግሞስ እርገቷን ለሁለተኛ ጊዜ ለማረጋገጥ ለምን አንድ አመት መቆየት አስፈለጋቸው? 
ማርያም አንዴ ካረገች በኋላ በሱባኤ የሚደገም ሁለተኛ እርገት አለ ወይ?  እንደዚህ ዓይነት ተደጋጋሚ ሞትና እርገት እንዲደረግላቸው ሐዋርያቱ ይጠይቁ ነበር ብሎ ለመቀበል ይቸግራል። ከጌታ የተማሩት ትምሕርት በእንደዚህ ዓይነት ጥያቄ እንዲዋከቡ የሚያደርግ አልነበረም። ማርያምን በመቅበር: በማንሳትና በማሳረግ ጣጣ ውስጥ ሐዋርያቱ ለምን እንዲህ ተጨነቁ? የተረት አባቶቹ ለዚህ ጥያቄ መልስ ባይኖራቸው ሐዋርያቱ ወንጌልን ለዓለም ያዳርሱ ዘንድ የተሰጣቸውን ሰማያዊ ተልእኮ ትተው ዋሻ ተወሽቀው የሆነ ሥጋ ከሰማይ እስኪወርድላቸው ጊዜያቸው ፈጁ የሚለውን ተረት  ሰይጣን ለሚያዳምጡት ከሚረጨው  በስተቀር የክርስቶ አማኝ የሆነ ሰው እውነት ነው ብሎ በጭራሽ ሊቀበል አይችልም።
የሚያሳዝነው ነገር ሐዋርያቱ ሱባኤ ከገቡ በኋላ የማርያም ሥጋ ከሰማይ እንደገና ወረደ የሚሉን አሳፋሪ ታሪክ ነው። እንዲያውም ኢየሱስ ራሱ ማርያምን ሥጋ መንበር (የቁርባን መቀመጫ) አድርጎ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፤ እስጢፋኖስን ገባሬ ዲያቆን ሆነው ቀደሱና ቆረቡ ይሉናል።  የማርያም ሥጋ እንዴት መንበር መሆን ቻለ? ምን የሚባለውን ቅዳሴ ቀደሱ? ኢየሱስ ሰራዔ ካህን ሆኖ ከቀደሰ የማንን ሥጋ ቆረበ? የራሱን?  ለየትኛው ድነት ይሆነው ዘንድ ሊቆርብ ይችላል? 
አልቆረበም የሚባል ከሆነም ሰራዔ ካህናት በዚህ ምድር መቅደስ ውስጥ ከመቀደስ ባሻገር መቁረብ አይጠበቅባቸውም በማለት አብነታዊ የክህነት አስተምህሮን አያይዞ ማቅረብ  የተገባ ይሆናል።
ኢየሱስ የቀደሰው ቅዳሴ ከ14ቱ ቅዳሴያት መካከል የትኛውን ይሆን? ያኔ ቅዳሴያት ተደርሰው ነበር? ወይስ የመጀመሪያው ደራሲ ኢየሱስ ነው?
  እንደተለመደው አባባል ቅዳሴ እግዚእ ነው የተቀደሰው የሚሉ ቢኖሩም ክርስቶስ ራሱን በሁለተኛ መደብ አስቀምጦ « ነአኩተከ አምላክ ቅዱስ፤ ፈጻሜ ነፍስነ፤ ወሀቤ ሕይወትነ ዘኢይማስን»  (ትርጉም) "የማይጠፋ ሕይወት የሰጠኸን: የነፍሳችን ፈጻሚ: ቅዱስ አምላክ እናመሰግንሃለን" ብሎ እንደእሩቅ ብእሲ ( እንደምድራዊ ሰው ሲማፀን አይገኝም። የማይጠፋ ሕይወት ራሱ ሰጪ ሆኖ ሳለ የዘላለም ሕይወት ይሰጠው ዘንድ ኢየሱስ ወደሰማይ አይማፀንም።
“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።”ዮሐ 6፥47 ያለን ጌታ ሕይወት ከሱ ቁጥጥር ውጪ ያለ የሚያስመስለው ቅዳሴ እግዚእ የሰዎች ድርሰት እንጂ የኢየሱስ አይደለም።
እንደዚህ ዓይነቱ አደገኛ ክህደት፤ ሰዎች ለማርያም ባላቸው ፍቅር ውስጥ ተደብቆ ለዘመናት ሕይወትን ከመዳን መንገድ ሲያጠፋ ቆይቷል።
ደግሞም በምሴተ ሐሙስ በጉ የመስዋእቱን ሥርዓት ለሕይወታችን ድኅነት ከሰጠ በኋላ ወደምድር መጥቶ ሁለተኛ ማእድ የሚያዘጋጅበት ምንም መጽሐፍ ቅዳሳዊ አስረጂ የለም። እውነታውን ስናነብ እንዲህ የሚል ቃል ተቀምጦልናል።«ሰዓቱም በደረሰ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር በማዕድ ተቀመጠ። እርሱም፦ ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር፤ እላችኋለሁና፥ በእግዚአብሔር መንግሥት እስኪፈጸም ድረስ፥ ወደ ፊት ከዚህ አልበላም አላቸው። ጽዋንም ተቀበለ አመስግኖም። ይህን እንካችሁ በመካከላችሁም ተካፈሉት» ሉቃ 22፤14-17
"የእግዚብሔር መንግስት እስኪፈጸም ድረስ ከዚህ ማእድ ድጋሜ አልበላም" ያለውን ቃል ያጥፍ ዘንድ ኢየሱስን ዋሾ ማድረግ አደገኛ ክህደት ነው።
በጉ መስዋዕቱን ሕይወት ይሆናቸው ዘንድ ለሰዎች ከሰጠ በኋላ፤ በፍርድ ቀን  የደሙን ምልክት ለተቀበሉት ሁሉ ዋጋቸውን ይሰጣቸዋል እንጂ እሱ የመስዋእቱ ተካፋይ ስላልሆነ፤ ክርስቶስ በቀዳሽነት  ቆርቦ፤ ማቁረብ የሚባል ታሪክ ከወንጌል ቃል የተገኘ ሳይሆን ክፉ ጠላት በጭለማ የዘራው ዘር ነው።

ወደዋናው ሃሳባችን ስንመለስ ለመሆኑ በማርያም ላይ ስንት ቀብር፤ ስንት ትንሣዔና ስንት እርገት ተደረገ? ብለን ብንጠይቅ እንደሚነገረው  ከሆነ ፤

1/ዮሐንስ ያየውና አፈር ያልነካው እርገት በገነት ዛፍ ስር

2/ አፈር የነካው የሐዋርያቱ ቀብር በነሐሴ 14 ቀን /ከስምንት ወር በኋላ/

3/ ቶማስ ያየው የትንሳዔ እርገት፤ ከቀብር በኋላ በሦስተኛው ቀን ነሐሴ 16

4/ ከአንድ ዓመት በኋላ ሐዋርያት ያዩት የነሐሴ 16 ትንሣዔና እርገት ናቸው።
እንግዲህ በማርያም ሞትና እርገት መካከል አራት ትእይንት መከሰቱን ዛሬም ድረስ ከሚሰጡት የቃል አስተምህሮዎችና የተዘጋጁ ጽሁፎች ውስጥ በግልጽ እናገኛለን። ማርያምን መውደድ አንድ ነገር ነው። ማርያምን ግን እየቀበሩና እያነሱ በቀብርና ትንሣኤ ማሰቃየት ደግሞ ሌላ አሳዛኝ ክስተት ይሆናል። እንዲያውም  ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻልኩ ሰባት ጊዜም ቢሆን እሞታለሁ ብላ ለልጇ ተናግራለች የሚሉት ተረትም በተዛማጅ ትምሕርትነት ይሰጣል። የእሷ መሞት የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻለ የክርስቶስ ከእሷ መወለድ አስፈላጊ አይደለም የሚል ሃሳብን የሚያንጸባርቀው ይህ አባባል ከአሳሳች ትረካዎች ውስጥ የሚደመር ከመሆን አያልፍም።
እኛ  ማርያምን ብንወዳትና ብጽእት ብንላት «እናትህንና አባትህን አክብር»  ያለውን  የአምላክ ቃል መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ለእርሷ  የተነገረ ቃል ስላለም ጭምር ነው። ከዓለመ አንስት መካከል በድንግልና መውለድ የሷ የተለየ ስጦታ ነው። በዚህም መመረጥ መቻሏን እናከብረዋለን። ነገር ግን የዘላለማዊ አምላክ የክርስቶስ ፤ እናቱ ስለሆነች በማዳላት ወይም አምላካዊ ባህርይውን በሰውኛ ጠባይ በመለወጥ ከፍርድ ሚዛኑ በማጉደል  የእሷን ሞትና ትንሣዔ የተለየ ያደርጋል ብሎ ማሰብ ስህተት ነው። የእሷ ሞትም የመድኃኒትነትን ውክልና ለሰው ልጆች የያዘ እንደሆነ ማሰብ ክህደት ነው። ብቸኛው መድኃኒት አንዱ ኢየሱስ ብቻ ነው። ማርያምም ይህንን አሳምራ ስለምታውቅ
«ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች» ብላ ተነግራለች። ምክንያቱም ኢየሱስ ከእርሷ የተወለደ ቢሆንም ዓለሙን በማዳን ማንነቱ ውስጥ ለእርሷም አምላኳና መድኃኒቷም ስለሆነ ደስ እንደሚላት መስክራለች። የትንሣዔ በኩር የሆነው ሁላችንም በሞቱ እንድንመስለው እንጂ የተለየ አድሎአዊ ጥቅምን/ favour/ ለተለዩ ሰዎች በመስጠት አይደለም።ወንጌል የሚናገረው ይህንን ነውና። የክርስቶስ ሕይወት ተካፋዮች የምንሆነው በሞቱና በትንሣኤው እርሱን ስንመስል ብቻ ነው።

ሮሜ 6፥5 «ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን»

 ስለዚህ ደጋግሞ መሞት፤ መነሳትና ደጋግሞ ማረግ አለ ከተባለ ያ ነገር ከክርስቶስ ትንሣዔ ጋር ያልተባበረ ስለሆነ አንቀበለውም። እንዲያውን ይህ ኑፋቄና ወንጌልን መካድ ነው።  ሐዋርያው ጳውሎስም የተናገረው ስለክርስቶስ ወንጌል በሞቱም ክርስቶስን እንዲመስል ነበር።

ፊልጵ 3፥10-11  «እርሱንና የትንሣኤውን ኃይል እንዳውቅ፥ በመከራውም እንድካፈል፥ ወደ ሙታንም ትንሣኤ ልደርስ ቢሆንልኝ፥ በሞቱ እንድመስለው እመኛለሁ»
የማርያም ሞትና ትንሣዔ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ካዘጋጀው የትንሣዔው በኩር አንድያ ልጁ የተለየ አያደርገውም። ከመግቢያችን ላይ ጀምሮ ለመግለጽ እንደሞከርነው የኤፌሶኑና የኢየሩሳሌሙ ታሪክ እንዳለ ሆኖ አብያተክርስቲያናት ሁሉ የተለያየ የሞትና የትንሣዔ አስተምህሮ ከመያዛቸው አንጻር  ኤጲፋንዮስ እንዳለው ትክክለኛው የታሪክ ቀን አይታወቅም። ቢታወቅም ስለድነታችን የሚጨምረውም: የሚቀንሰውም ነገር የለውም። አሁን የሚደረገውም ፍልሰታ ለማርያም በዓል ከልምድና ትውፊት ከተረትና ክህደት ጋር በማር የተለወሰ መርዝ ስለሆነ መጠንቀቅ አለብን።
ማርያምን እንወዳለን እያሉ በጥር ሞተች፤ ገነት ዛፍ ስር ስምንት ወር በሬሳ ቆየች፤ በስንት ሱባዔ ስጋዋ መጥቶ ነሐሴ ተቀበረች፤ እስከነ ምድራዊ ልብሷ አረገች፤ በዳመናው ጎዳና  ላይ ከቶማስ ጋር ጨርቅ ተለዋወጠች፤ እድል ላመለጣቸው ሐዋርያት ዳግመኛ በስንት ሱባዔ በሌላ ትንሣኤና እርገት ተረጋገጠች፤ መንበር ሆና ተነጠፈች ወዘተ በማለት እየገደሉና እያነሱ በማርያም ላይ መጫወት ተገቢ ነው ብለን አናምንም። የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤንም ማፋለስና መካድ ይሆናል። የማርያም ትንሣኤና እርገት ለክርስትና ከታሪክ ባለፈ ለሕይወት የሚሰጠው የሕይወት ዋስትና የለውም። ሕይወት ኢየሱስ ብቻ ነው።  ሕይወት እንዲሆንላችሁ ከፈለጋችሁ ከተረት ዓለም ውጡ።
“ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም።” ዮሐ 5፥40  የተባለው እንዳይፈፀምባችሁ በሕይወት መኖር አይሻላችሁምን?
ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር የሌላ የማንም ሞትና ትንሣኤ  ለሰው ልጆች መዳን የቀረበ መስዋእት የለም።
የማርያምም ሞትና ትንሣኤ ማንንም ሊያድን አይችልም።
የተነገረን በማርያም ትንሣኤ እንድናምን ሳይሆን “በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።”
  ዮሐ 3፥36 ተብሎ እንደተነገረው የቤዛነት ምትክ በሌለው በኢየሱስ ብቸኛ አዳኝነት ልናምን ይገባል!
መጽሐፍ እንዳለው "“መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።”ሐዋ 4፥12
ከላይ የተጻፈው ጽሑፍ ዋና መልእክት ማርያንም ለመቃወም ወይም ንጽሕት: ቅድስት ማርያምን ከመጥላት የተነሳ አይደለም። ማርያም ራሷ የማትቀበለው ከእውነትና ከወንጌል ቃል ተቃራኒ አስተምህሮን በእግዚአብሔር ቃል ለማፈረስና ሰዎች ሁሉ ባልተሸቃቀጠው ወንጌል ብቻ እንዲኖሩ ለማስቻል ነው። በዚህም እውነት ለመገዛት እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን!



















Friday, May 14, 2021

ኦርቶዶክስን የማፍረስ ዘመቻ!

 


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስን ተዋሕዶን የማፍረስ ዘመቻ ዛሬ የተጀመረ አይደለም። አብዛኛዎቹ ዘመቻዎች ውጫዊ ነበሩ። የዮዲት ጉዲት ዘመቻ: ከደቡብ ወደሰሜን የተካሄደው የገዳዎች ወረራ: የግራኝ: የማህዲስት: የካቶሊክ ሚሲዮናውያን: የፋሺስት ጣሊያን ዘመቻዎች ሁሉ መሰረታቸው ኢትዮጵያን የመቆጣጠርና ግዛት የማስፋፋት ቢሆንም ቤተ መንግስቱንና ቤተ ክህነቱን ትቆጣጠር የነበረችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ግብ የሁሉም ወራሪዎች ተመሳሳይ አላማ ነበር። የሕዝቡን እምነትና ለመንግስት አሜን ብሎ የመገዛት ስነልቦናውን ለማፍረስ መጀመሪያ ኦርቶዶክስን ማጥፋት የሁሉም ግብ ነበር። የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከውጪ የመጣባትን ጥቃት ሙሉ በመሉ በመቋቋም ከመጥፋት ተርፋ ይሄን ሁሉ ዘመን መዝለቅ የቻለችው ውስጣዊ አንድነት ስለነበራት ብቻ ነው። ነገር ግን ከ1966 ዓ/ም በኋላ የኦርቶዶክስ ሲሶ መንግስትነት ተንኮታኩቶ ፈጣሪ የለሽ መንግስት በቦታው ሲተካ ከውጫዊ ጥቃት ይልቅ ውስጣዊ አንድነቷን የሚፈታተን አደጋ ተጋርጦባታል። ለሁለተኛው ፓትርያርክ በደርግ መገደል መነሻው ምክንያት የውስጠኛው አመራር  የሆነው የሲኖዶሱ መከፋፈል ነበር። ለአራተኛው ፓትርያርክ ሹመት የነመላኩ ተፈራ ደርጋዊ እጅ ቤተ ክህነቱ ውስጥ ዘልቆ መግባቱና ለአምስተኛው ፓትርያርክ ሹመትም ተረኛው የወያኔ እጅ እንደፈለገው ማቡካት መቻሉን ስለምናውቀው እውነቱን መካድ አይቻልም። 

ደርግ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብትና ንብረት ወርሶ ለ17 ዓመት: ህወሀት ለ27 ዓመት የቤተ ክርስቲያኒቱን የውስጥ አመራር ተቆጣጥረውት የቆዩት ለፖለቲካዊ አላማቸው የማታስቸግር ቤተ እምነት እንድትሆን ቀፍድዶ ለመያዝ እንደነበር ይታወቃል። 

ለኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የውስጥ አስተዳደር መበላሸትና ለጥቃት ተጋላጭ ያደረጋት ዋናው ምክንያት ቅዱስ የተባለው ሲኖዶስ በሚጠበቀው ደረጃ አስተዳደሩን በቅድስና መምራት አለመቻሉ እንደሆነ እርግጥ ነው። ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለፉት 30 ዓመታት ውስጥ ከ25ሚሊዮን በላይ አማኞቿ ትተዋት የኮበለሉት በቁጥርም: በዝናም ሲኖዶስ የተባለው ማኅበር በጨመረ ቁጥር ነው። ለምን? ብሎ መጠየቅ የግድ ይላል። ይሄ ሲኖዶስ የሚባለው ማኅበር ትክክለኛው የበጎች እረኛ ሳይሆን የበጎቹን መንጋ ለቀበሮ አሳልፎ የሚሰጥ ለደመወዝ የሚኖር ቅጥረኛ ስለሆነ ብቻ ነው። በነቀዘ የአስተዳደር መዋቅር: በጉቦና በዘረፋ የተሰማራ አመራር: ዘመኑን የሚዋጅ ሃይማኖታዊ አስተምህሮ አለመኖር:  ፍትህ በአፍጢሙ በመደፋቱና በሌሎች ውስጣዊ ገፊ ምክንያቶች የተነሳ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያኒቱን ለቀው ሄደዋል።  ያሉትም በሚያዩት ነገር ተስፋ ቆርጠው ቤታቸው ተቀምጠዋል። በአንድ ወቅት አንድ የሙስሊም ስኮላር ያለውን አስታውሳለሁ። እስልምና የምስራቅ አፍሪካ ሀገሮች በሙሉ ሲቆጣጠር የነቢያችንን ዘመዶች የተቀበለችው ኢትዮጵያን መቆጣጠር ያቃተን በኦርቶዶክስ የተነሳ ነበር። እኛ ያቃተንን ጳጳሳቶቿ ራሳቸው እያዳከሙልን ስለሆነ ምስጋና ይገባቸዋል ሲል ተደምጧል።  ነገሩን ቆም ብለን ስንመረምር ቤተክርስቲያኒቷ ጳጳሳት በበዙ ልክ ማደግ ሲገባት ጳጳሳቱ በበዙ መጠን እያሽቆለቆለች መገኘቷ የስጋውያን መሪነት የመንገሱ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። 

በአጠቃላይ ከ1966 ዓ/ ም በፊት የነበሩ ውጫዊ አደጋዎቿን በውስጣዊ አንድነቷ መቋቋም የቻለችው ቤተ ክርስቲያን ውስጣዊ አንድነቷን የሚያናጋ ውስጣዊ ችግሮችን እያመረተች በመገኘቷ በምእመናኖቿ ቁጥር የቁልቁለት ጉዞዋን ተያይዛዋለች። በመንፈሳዊ ወሥጋዊ ዘመናዊ አስተዳደር አለመኖርና የፋይናንስ ስርአቱ ብልሹነት የተነሳ ዘረፋ: ጉቦ: ዘረኝነትና ዐመፃ በመንሰራፋቱ ራሷን ከውጪ ጥቃት እንዳትከላከልና ውስጣዊ ተጋላጭነቷ ከፍ እንዲል አድርጓታል።

ይህ ሁሉ ዐመፃና ስርአተ አልበኝነት ነግሶ እያለ አንዳንዶች እግዚአብሔር ስለሚጠብቃት ኦርቶዶክስ አትፈርስም ሲሉ ይደመጣሉ። ይሄ ግን በስመ እግዚአብሔር የሚፈፀም ራስን የማታተል ግብዝነት ነው። በራእየ ዮሐንስ ላይ የተመለከቱት ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ዐመጽና በደልን እንዲተዉና ወደእግዚአብሔር የቀደመ መንገዳቸው እንዲመለሱ ቢነገራቸው መስማትና ንስሐ መግባት ባለመፈለጋቸው የተነሳ አብያተ ክርስቲያናቱ በሙሉ ፈራርሰው ዛሬ በሙዚየምነት የሚጎበኙ የእስላማዊ ቱርክ የገቢ ምንጭ ፍርስራሽ ሆነው ቀርተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም መጨረሻ በዚህ መልኩ እንዳይደመደም የሚያስችል ሁኔታ እየታየ አይደለም። ሲኖዶስ የተባለው በስመ ቅድስና የተሰየመው የበላይ አካል በቅድስና እየመራት ከሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ዐመጽ: ዘረፋ: ጎጠኝነት: የአመራር ክፍፍልና ልዩነት ለምን መለያዋ ሊሆን ቻለ? 

አሁን በቅርቡ በታየው የቤተ ክርስቲያኒቱ መግለጫ በተባለው ጉዳይ ላይ (አባ) ወ/ ኢየሱስ ወይም ህፃን የተባለው ጎረምሳ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክሎ ያደረገው ንግግር የሚያሳየው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓትና ሕግጋት እየፈረሰ መሆኑን ያመላክታል። ይህ ሰው በመኪና ስርቆት ወንጀል ተፈርዶበት 4 ዓመት ከርቸሌ የከረመ መሆኑ እየታወቀ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዓመታዊ በዓላት በልደት: በጥምቀት: በዘመን መለወጫ: በከፍተኛ ስብሰባዎች እየተገኘ በውክልና መግለጫ የሚሰጠው በምን አግባብ ነው?



 አባ ሕጻን (በአማን ዘውእቱ ሕጻን) ከዘመናዊ ትምህርት ይሁን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ትምህርት ሩቅ ነው። ግን መግለጫ በመስጠት ቀዳሚ ነው። እውነት ነው: ሲኖዶሱ በዝምታ ድባብ ሲዋጥ አላዋቂዎች ቢሰለጥኑባት አይገርምም። "ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ" እንዲሉ!

የዓሳ ግማቱ ከጭንቅላቱ ነው እንደተባለው በመላው ሀገሪቱ እየታየው ባለው የቤተ ክርስቲያን መቃጠልና የምእመናን እልቂት ፊት ለፊት መናገር ሲገባቸው እንደቀንድ አውጣ አንገታቸውን ቀብረው የቆዩ ሁሉ ቅዱስ ፓትርያርኩ በትግራይ እየተከሰተ ያለውን እልቂት ማውገዛቸውን ተከትሎ ፓትርያርኩ ላይ አፋቸውን ሲከፍቱ ስናይ ቅጥረኞች ቤተክርስቲያኒቱን እንደወረሯት ማሳያ ነው። በልብስ ሰፊነት ባደለቡት ገንዘብ ያገኙትን ሹመት በመንፈሳዊ ብቃት ያገኙት ያህል እንድንቆጥርላቸው ይፈልጋሉ። የብርሃኑ ጁላ ታናሽ ወንድም 



ሆነው ፓትርያርኩ የተናገሩትን የግላቸው አቋም ነው ብለው የማን ቅጥረኛ እንደሆኑ ሲያሳብቁ እነርሱ በማን ፈቃድ? የማንን አቋም? እንዳንፀባረቁ ድንቁርናቸው ራሱ ያጋልጣቸዋል። ጊዜ ወለድ የሆኑ ጳጳሳት ባሉባት ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገርመው ውድቀቷ ቶሎ አለመፈፀሙ ብቻ ነው። 

የኦሮሚያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መስራቹ አቶ በላይ መኮንን ባቋቋመው ቲቪ ላይ ከጀነራል ጳጳሳቱ ጋር ተሰይሞ እንደሕዝብ አማራን: እንደተቋም አሁን ያለው ሲኖዶስ ሲያዋርዱና ሲዘለፉ ተመልክተናል።  


ፓትርያርኩ የትግራይ ህዝብ እየተጨፈጨፈ ነው ብለው መናገራቸው ስህተት ተደርጎ የተቆጠረው የኦሮሚያ ኦርቶዶክስን ለማቋቋም እንደእጅ መንሻ ለመንግስት ለማቅረብ መሆኑ ያልገባው ካለ እሱ ጅል መሆን አለበት። ፓትርያርኩ የአስተዳደር ብቃት ችግር እንዳለባቸው ይታወቃል። ነገር ግን ለቤተክርስቲያን ባለመቆርቆር ወይም በዘረኝነት እሳቸውን ለመክሰስ ብቃት ያለው አንድም ጳጳስ እንደሌለ እርግጠኞች ነን።

የአቶ አሻግሬ መንግሥት ተለያይቶ የነበረውን ሲኖዶስ ያሰባሰበው በተለያየ ጎራ በፖለቲካ ውጊያ እንዳያስቸግሩትና ሰብሰብ ባለ ጠላት ላይ ኃይሉን በሙሉ ለማሳረፍ እንዲያስችለው እንጂ መንፈሳዊ መልእክት ከሰማይ ወርዶለት አይደለም። በአጠቃላይ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የማፈራረስ እቅድ በመንገድ ላይ ይገኛል። ውስጣዊ አንድነቷ የለም። ሲኖዶሱ እንደእከ " እኔን ነው?" ከማለት  የእንቅልፍ አዚም መውጣት አልቻለም።

ምእመኑ የተመሪነት ፍላጎቱ ቢኖረውም መሪ እንደሌለው የበግ መንጋ በሃዘንና በስቃይ እየተቅበዘበዘ ነው። የጊዜ ጉዳይ እንጂ ኦሮሙማ ቤተ መንግሥቱንና ቤተ ክህነቱን ከመዋጥ ከመሰልቀጥ አይመለስም። መጨረሻውስ ምን ይሆን?

እድሜ ይስጠን ገና ብዙ እናያለን: እንሰማለን!

Saturday, February 22, 2020

ጉባዔ ከለባት እና የዘመኑ ሆድ አደር ሲኖዶስ!

ፓትርያርኩ እድል ይሁን የችሎታ ማነስ ቤተ ክርስቲያን በዘመናቸው እየፈረሰች ነው።
ጳጳሳቱስ ችግር ፈቺ ናቸው ወይስ ችግር ፈጣሪ? ሁሉም ቤተ ክርስቲያንን በማፈራረስ የየድርሻቸውን እየተወጡ ናቸው።
አቡነ ጃዋር: አቡነ ጃዊሮስ ቀውስ በላይንና ሌሎች ሃይማኖት የለሽ ኦነጋውያንን ማስቆም ያልቻለ ሲኖዶስ ጥጉን ይዞ ይስቃል።


Tuesday, January 2, 2018

ኢየሱስ አዳነን እንጂ ከአብ ጋር እንታረቅ ዘንድ አላማለደንም ማለት ኑፋቄ ነው!!


****************
አንድ ሰው በፌስቡክ ገጹ ላይ "ኢየሱስ አዳነን እንጂ አላማለደንም" የሚል የስሕተት ትምህርት ፅፎ ስላየኹ ይቺን አጭር ፅሑፍ ለመጻፍ ተነሳሳሁ። ማስረጃችንም ቅዱስ መጽሐፍ ነው።

መልሴን በጥያቄ ልጀምር። " አዳነን እንጂ አላማለደንም" ማለት ምን ማለት ነው? ይህ አባባል "ኢየሱስ ይፈርዳል እንጂ አያማልድም" የሚሉ ሰዎች ለሞገት የሚያቀርቡት ክርክር እንደሆነ እረዳለሁ። ይህ የስነ ሞገት ክርክር ጥያቄ ማስከተሉ የግድ ነው። እርግጥ ነው: ኢየሱስ ፈራጅ አምላክ ነው። ታዲያ ፈራጅ አምላክ ሆኖ ሳለ እኛን የአዳም ልጆች ከዘላለማዊ ቁጣ ለማዳን ለምን ሰው መሆን ይጠበቅበታል? በሰማያዊ አምላካዊ ሥልጣኑ " ድናችኋል" የሚል ቃል ቢሰጥ የሚቃወመው ማነው? መከራና ሞት ወደሚያስከትል ደካማ ሥጋ በመምጣት ሰው መሆን ምን ያደርግለታል?
  ያዳነን በፈራጅነቱ እንጂ በምልጃ አይደለም የሚሉ ሰዎች አምላክ ሰው መሆን ሳያስፈልገው በለይኩን ቃሉ ለምን እንዳላደን ወይም ከፈራጅነቱ ምን ጎድሎበት ሰው ወደመሆን እንደወረደ ሊገልፁልን ይገባል።
ከአብ ጋር ለማማለድ ካልሆነ በስተቀር የማዳን ሥልጣን አንሶት ነው ሰው የሆነው? ብለን እንጠይቃለን። ያለምልጃውም አልዳንም: መዳንም የለም እንላለን።

Sunday, November 5, 2017

እውነቱን ፈልፍለን ለማግኘት መጸሐፎቹን እንመርምር!


መነሻ ሃሳብ «ገመና ዘ81ዱ» መጽሐፍ (ጽሑፉ በድጋሚ ተስተካክሎና ረዘም ተደርጎ የቀረበ ስለሆነ በትዕግስት እንዲያነቡ ይጠየቃሉ።)

ሀተታ፤
በኦርቶዶክሳውያን ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከታች ጀምሮ እስከላይኛው እርከን ድረስ ያለው ሰው ስህተት ይኖርብናል ወይም ልንሳሳት እንችላለን ብሎ የሚያስብ ሰው ማግኘት ከባድ ነው። በክርስቶስ ደም የተመሰረተችው ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗን በመቀበል  መሪውና ተመሪውም በዚያው ዓይን ራሱን እያየ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን፣ የስህተት አስተምህሮ አይነካካንም በሚል ሰውኛ ተመካሂነት ራሱን በማስጠለል፤ ስህተትን አምኖ ለመቀበል አይፈልግም። ነገር ግን ትውልዱ አንባቢ፣ ጠያቂ፣ ስንዴውን ከእንክርዳዱ በመለየት ንጹሑን ቃለ እግዚአብሔር መመገብ የሚፈልግ በመሆኑ የስህተት አስተምህሮ አለ፤ በእግዚአብሔር ቃል ሲመረመር አደጋው የከፋ ነው፤ የክፉ መንፈስ አሰራር ወደማወቅ እንዳንደርስ ቃሉን በክሏል በማለት ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ተሳስቶ ከሆነም በየዋህነት መንፈስ በማቅናት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ "2000 ሺህ ዘመን የኖረችን ቤተክርስቲያን ዛሬ የተነሱ አፍቃሬ ተሐድሶ መናፍቃን ሊያርሟትና ሊበርዟት ይፈልጋሉ" በማለት መጥፎ ስም በመለጠፍና ምላሽ መስጠት ሲከብዳቸው ሽልማት የሚያሰጥ ቢሆን ኖሮ የስም አጥፊዎችን ዋንጫ ያለተቀናቃኝ የሚቀበሉበትን የተመረጡና ለመስማት የሚዘገንኑ ስድቦች፣ ዛቻዎችና ውግዘቶችን በማዥጎድጎድ የሚጠይቅ እንዲሸማቀቅ፣ አዋቂ ጠያቂ እንዳይኖር  አንገት  ማስደፋትንና ማስወገዝን እንደበቂ መልስ ሲቆጥሩ ኖረዋል። ዛሬም በዚሁ ግብራቸው አሉ።
በእርግጥ የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት የመሆኗ ምስጢር የመሠረታት በዓለቱ ላይ በፈሰሰው ደሙ ነውና የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ህፀፅ አልባ ናት። ነገር  ግን የአክሌሲያ ጉባዔ አባላት  የአዳም ልጆች መሆናቸውን በመዘንጋት የቤተክርስቲያኗን መንፈስና ባህርይ እንዳለ ወደሰዋዊ ማንነት በመውሰድ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በማለት ከስህተት አልባ ማንነት ጋር ራስን መቁጠር ትልቁ የስህተት መጀመሪያ ነው።  ምክንያቱም ዓለም ላይ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት የተከፋፈሉት  የአስተምህሮ ስህተቶች ወደክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ሰተት ብሎ በመግባቱ የተነሳ ነው። የሚገርመው ደግሞ ሁሉም አብያተ ክርስቲያን ለራሱ ትክክል ሲሆን ሌላውን እንደስህተተኛ የመቁጠሩ ችግር ስህተቱን እንዳያውቅ አድርጎታል። ሌላውን ስህተተኛ ማለት እኔ ብቻ ትክክል ነኝ ከሚል ነጥብ ይጀምራልና ስህተቱን መቀበል አይችልም።
ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነን በቀደመው ዘመን በገላትያ ቤተክርስቲያን የገባውን የስህተት መንፈስ በሐዋርያው ጳውሎስ ሲጠቀስ እናነባለን። የገላትያ ሰዎች በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ወደ ሕይወት መንገድ የተመለሱ ሕዝቦች ነበሩ። ፍጽምትና ንጽሕት ወደሆነችው የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተጨምረው የቆዩ ሆነው ሳለ ሰብአዊ ማንነታቸው አሸንፎአቸው ወደስህተት መንገድ በመግባታቸው በሐዋርያው ጳውሎስ እጅግ የተወቀሱ ሕዝቦች ሆነዋል።

«የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?» ገላ 3፤1

ክርስቶስ ኢየሱስ በፊታቸው የተሰቀለ ሆኖ በእምነት ይታያቸው የነበሩት ሕዝቦች የያዙትን  የሕይወት ማንነትና እውነትን በመተው፤ የጠላት አዚም ሸፍኖአቸው ለእውነት እንዳይታዘዙ እስከመሆን መድረሳቸውን  እናያለን። ሥራቸውን ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የጀመሩ ሆነው ሳለ ቁልቁል ተመልሰው የሥጋን ሃሳብና የስህተትን አስተምህሮ ወደማመን መመለሳቸው በእርግጥም አሳዛኝ የሰው ልጆች ማንነት ማሳያዎች እንደሆኑ የሚያስገነዝበን ነገር ነው።

«እንዲህን የማታስተውሉ ናችሁ? በመንፈስ ጀምራችሁ አሁን በሥጋ ትፈጽማላችሁን?» ገላ 3፤3

እንግዲህ ክርስቲያኖች ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እምነታቸውን ሊጀምሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ይህንን ፍጽምና ወደአለማወቅ በመመለስም ስህተት ሊታይባቸው እንደሚችል አስረጂ ነው። ምን ጊዜም ቢሆን የስህተት መንፈስ አገልግሎት የሚገባው፤ የእውነቱን መንፈስ ከሰው ልቡና ላይ በመውሰድ ወደስህተት መንገድ በማምራት ስለሆነ በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ ሰዎች ውስጥ የስህተት አስተምህሮ ሊገባ እንደሚችል እናረጋግጣለን።
ብዙዎች የአብያተ ክርስቲያናት አባላት በክርስቶስ ፍቅር ላይ ጸንተው ከመቆም ይልቅ ወደ ምድራውያንና ሰማያውያን ፍጥረቶች ፍቅራቸውን ስለለወጡ የሕይወት መንገድን ስተው መገኘታቸው እውነት ነው።
በሌላ ቦታም እንዲህ የሚል አስረጂ እናገኛለን። ሐዋርያው ጳውሎስ መንፈሳዊ ልጁ የሆነው ጢሞቴዎስን በተሰሎንቄ ለነበረችው ቤተክርስቲያን የላከበት ዋናው ምክንያት ተሰሎንቄዎች ከእምነት ጽናታቸው ወደኋላ እንዳይመለሱ በመንፈስ ያበረታታቸው ዘንድ ነበር። ምክንያቱም ፈታኝ የምንጊዜም አዚሙን የሚያፈሰው የአማኞችን ልቡና በማደንዘዝ ወደ አልሆነ አቅጣጫ በመመለስ ስለሆነ ከዚህ ፈታኝ ይጠበቁ ዘንድ ነበር።

«ስለዚህ እኔ ደግሞ ወደ ፊት እታገሥ ዘንድ ባልተቻለኝ ጊዜ። ፈታኝ ምናልባት ፈትኖአቸዋል ድካማችንም ከንቱ ሆኖአል ብዬ እምነታችሁን ለማወቅ ላክሁ» 1ኛ ተሰ 3፤5

የስህተት መንፈስና አስተምህሮ በጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን አጋጥሞ እንደነበር ስንረዳ 2000 ዓመታትን በመጥፋትና በመነሳት፣ በመለያየትና በመታወክ በጦርነትና በመከራ ባሳለፈች ቤተ ክርስቲያን ውስጥማ እንዴት ብዙ አይገኝ?  የስህተት አስተምህሮ ማስተካከያ ሚዛኑ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው።
ከከሳቴ ብርሃን አባ ሰላማ ወዲህ ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል ተብለው የሚጠሩ መነኮሳት በዋሻና በፍርክታ ገዳም መስርተው ሰው ሁሉ ወደዚያው እንዲከትም ከማድረግ ውጪ ሀገር ላገር ዞረው፤ እንደሐዋርያቱ ወንጌል ላልበራለት ሕዝብ ወንጌልን ስለማስተማራቸው ከአፋዊ ትውፊት በዘለለ መሬት ላይ ያለው እውነታ ያንን አያሳይም። ወንጌል ለሕዝቡ የበራ ቢሆንማ ኖሮ እስከዛሬ በዛፍ ስር ቡና የሚደፉ፤ ደም የሚያፈሱ፤ቅቤ የሚቀቡ፤በጨሌ፤ ቆሌና የቤት ጣጣ አምልኮ ሰርጾባቸው የሚኖሩ ባልኖሩ ነበር። እምነት አለን፤ አውቀናል የሚሉት እንኳን እስከፕሮቴስታንት መምጣት ድረስ መጽሐፍ ቅዱስን አያውቁትም። በመላዋ ኢትዮጵያ ይቅርና ክርስትና አስቀድሞ ገብቷል በተባለባት በትግራይ  እንኳን ከአደይ ማርያምና ከአቡነ አረጋዊ በዘለለ የኢየሱስን ወንጌል በደንብ የሚያውቁ ምእመናን ቀርቶ ካህናቱ ቁጥር ስንት ይሆን?
ደረትን ነፍቶ ኦርቶዶክሳዊ ስለመሆን አረጋጋጭ ከሆኑት ከድርሳናት ውጪ መጽሐፍ ቅዱስን ይዞ መገኘት በራሱ ኮትልኳል ወይም ጰንጥጧል የሚያሰኝ በመሆኑ ይዞ መገኘት ቀደም ሲል ያሳፍር ነበር። ይህ በእድሜአችን ያየነው እውነት ነው። አንዳንዶች «ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው» የሚለውን ቃል ጠምዝዘው ለራሳቸው መሸንገያነት በመጠቀም አንድም ሐዋርያ ሳይመጣ ያመንን ስለሆንን ቃሉ እኛን ኢትዮጵያውያንን ያመለከታል ለማለት ቢፈልግም የሐዋርያ ወይም የሰባኬ ወንጌል አለመምጣት እንደ ጉዳት እንጂ እንደጠቃሚ ነገር መቁጠር ስንፍናን መደገፍ ነው። መጽሐፍ የሚለን እውነት ይህንን ነው።

«እንግዲህ ያላመኑበትን እንዴት አድርገው ይጠሩታል? ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ? ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ?» ሮሜ 10፤14

እንደዚሁ ሁሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እውነተኛ ወንጌል በማስተማርና ሕዝቡን ከክርስቶስ ወንጌል ጋር በማስማማት እንዲኖር ለማድረግ እስከሞት ድረስ ከታገለው ከአባ እስጢፋኖስ ዘጉንዳጉንዶ በስተቀር ግብጻውያን ጳጳሳት ይሁኑ ተከታዮቻቸው ከልምድ አምልኮ በዘለለ የሰሩት የወንጌል አገልግሎት አልነበረም ማለት ይቻላል። ወንጌል በመጽሐፈ ግጻዌ በጥቅስ ደረጃ በየሥርዓተ ቅዳሴው ላይ ተመርጦ ከሚነበብ ውጪ ከተአምረ ማርያምና ከድርሳናት እኩል በመድረክ ተሰብኮ አያውቅም። አቡነ ቴዎፍሎስ የወንጌልን አስፈላጊነት በማመን አዳሪ ት/ቤቶችን በማጠናከር፤ ሰንበት ት/ቤቶች በማቋቋምና በቃለ ዓዋዲ እንዲደነገግ እስኪያደርጉ ድረስ አብያተ ክርስቲያናት በግእዝ ቀድሰው፤ በግእዝ አንብበው፤ ለዓለመ ዓለም ካሉ በኋላ እግዚኦ መኀረነ ክርስቶስ እንበል 12 ጊዜ ብለው ጣት ከማስቆጠር ባለፈ ህዝቡ ወንጌልን እንዲያውቅ መርሐ ግብር ተቀርጾለት የስብከት መድረክ እንዳልነበረው ጠንቅቀን እናውቃለን።
እንዲያውም ወንጌል እቃ ግምጃ ቤት ገብቶ የሸረሪት፤ የአቧራና የአይጥ ቀለብ ሲሆን በአንጻሩ ልፋፈ ጽድቅ በየአንገት ላይ የሚንጠለጠል ክቡር መጽሐፍ ሆኖ ለዘመናት ኖሯል። ዛሬም እስከመቃብር ድረስ አብሮ የሚወርድ፤ ክቡር አዳኝ መጽሐፍ ሆኖ መቆጠሩን አላቋረጠም። የዲቁናም ይሁን የቅስና ማእርግ የሚሰጠው ሥርዓተ ቅዳሴውንና ኩሳኩሱን ከመልክዓ መልክዑ ጋር መሸምደዱ እንጂ ወንጌልን ተንትኖ ሕይወት የሚገኝበትን ቃል ማስተማር ስለሚችል የሚሰጥ ማእርግ አይደለም።
በዚህም የተነሳ ቀደምት የሆነችው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዘርዓ ያዕቆብና ተከታዮቹ ፀረ ወንጌል አድናቂዎቹ ባስገቡት የሕጸጽ አስተምህሮ ከዘመን ዘመን ድምፅና ተሰሚነቷ እየቀነሰ ቁጥሯ እየተመናመነ ከመገኘቷ ባሻገር ዛሬም ህፁፀ አእምሮ በተሸከሙ ዘርዓ ያዕቆባውያን የተነሳ ወንጌል ተገቢውን ስፍራ መያዝ አልቻለም። ከዚህ በታች የምናቀርባቸው መጽሐፍ ቅዱሳችን በምንለው መጽሐፍ ውስጥ የሚገኙ ስህተቶች፤ ነገር ግን እውነት እንደሆኑ ቆጥረን የምንከራከርላቸው ሲሆኑ ችግሩን እንደችግር ያለመቁጠራችን ዋና ምክንያት ከላይ በሐተታ እንደዘረዘርነው  አንድም እኛ ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ ያለን ስህተት አልባዎች ነን ከማለት የመነጨ ሰውኛ ማንነትን ካለመቀበል ችግር፤ አለያም- ክርስቶስ ከፊታቸው ተስሎ የነበሩት ገላትያውያን እንደሆኑት የሆነ አዚም አደንዝዞን እውነትን ለመቀበል ባለመፈለግ፤ አለያም ሳያዩ የሚያምኑ……በሚለው የሽንገላ ቃላት ተታለን እውነተኛውን የክርስቶስ ወንጌል የሚሰብክ እንዲኖረን ባለመፈለግ ራሳችንን ስናሞኝ በመኖራችን የተነሳ ነው።
የስህተት ትምህርት አስረጂዎች፤
ብዙውን ጊዜ «ከእውነተኛ የወንጌል አስተማሪዎች እጦት የተነሳ» /ከአስተማሪዎች እጦት የተነሳ አላልኩም/ ሕዝቡ እስካሁን ለወንጌል ቃል አዲስ በመሆኑ አሳማኝ መልስ መስጠት ስለማይችል እንደችግር መፍቻ መፍትሄ የሚጠቀምበት መንገድ በመሳደብ፤በማሳደድ፤በማሽሟጧጥ፤ በመደባደብ ብሎም በመግደል ልዩ ለሆነ ሃሳብ ሁሉ ምላሽ ሲሰጥ ቆይቷል። አሁንም ይህ አድራጎት አላቋረጠም። ከዚህ በታች ለሚቀርቡ አስረጂዎች ምላሽ መስጠት የሚችል አንድም ሰው እንደሌለ እርግጠኞች ስንሆን የሚሳደብ ወይም የሚያንቋሽሽ ክርስቲያን ነን ባይ ፍልፍሎችን ግን በሺህዎች እንጠብቃለን።

ጥያቄ 1፣
ስለታቦተ ጽዮን ትረካ፤
****************
1.1 ስለታቦተ ጽዮን አመጣጥ ታሪክ "በታቦተ ጽዮን ፍለጋ" መጽሐፍ፣

የታቦተ ጽዮን ፍለጋ መጽሐፍ አስተርጓሚ የሆነው ማኅበረ ቅዱሳን የሚናገረው ትረካ «ክብረ ነገሥት» የተባለውን መጽሐፍ ውሸታም ነው ብሎ ከቆሻሻ ቅርጫት ውስጥ ሲወረውረው እናያለን። ከክብረ ነገሥት በተለየ መልኩ አዲስ ግኝት አለ ብሎ መናገር ወይም ማስተዋወቅ ማለት ክብረ ነገሥት ተአማኒ አይደለም ወይም ላይሆን ይችላል ብሎ መመስከር ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን ትውፊትንና ባህልን፤ ልምድንና አምልኰትን ለይቶ የማያውቅ የጅምላ እምነት አራማጅ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ራሱ እገዛበታለሁ የሚለውን የቤተክርስቲያኒቱን የትውፊት መጽሐፍ ሲሽር  ሃይ ባይ ከልካይ የለውም። እንደሚታወቀው ግራሃም ሐንኰክ የተባለ እንግሊዛዊ ምሁር /The sign of the seal/ በሚል ርእስ እ/ኤ/አ በ1992 ዓ/ም ያሳተመውን
መጽሐፍ ይህ የትውፊት ጠበቃ ነኝ የሚለው የጅምላ እምነት አራማጅ ማኅበር፤ /ታቦተ ጽዮንን ፍለጋ/ በሚል ርእስ በጌታቸው ተስፋዬ አስተርጉሞ ያሳተመው መጽሐፍ እንደሚተርከው ታቦተ ጽዮን ወደኢትዮጵያ የመጣችው በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን በልጁ ኢትዮጵያዊ ንጉሥ ቀዳማዊ ምኒልክ እጅ ሳይሆን  በግብጽ በኩል ኤሌፋንታይን አቋርጣ ከዓመታት ቆይታ በኋላ የዓባይን ሸለቆ ተከትላ ቀስ በቀስ በጣና አድርጋ ነው በማለት የመጽሐፉን ትርክት በትርጉም ሥራው አጽድቆ ገበያ ላይ ካዋለው አመታት ተቆጥረዋል። በዚህ መጽሐፍ ጥናት መሠረት ክብረ ነገሥት ውሃ በልቶታል። «ክብረ ነገሥት» ስለታቦተ ጽዮን አመጣጥ የሚተርከው የእነ ቀዳማዊ ምኒልክ ታሪክ በውሸታምነቱ ተመዝግቧል ማለት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን የታቦተ ጽዮንን አመጣጥ በግራሃም ሃንኰክ አተራረክ መሠረት የሚያምን ከሆነ የክብረ ነገሥትን ትረካ ዋጋ ቢስ በማድረጉ ለምን? ተብሎ ሊጠይቀው በተገባ  ነበር። የሚገርመው አንድም የሊቃውንት ጉባዔ ይሁን የጳጳሳቱ ዓለም የክብረ ነገሥትን ትረካ የሚቃወመውን የማኅበረ ቅዱሳን እትም መጽሐፍ ሲያወግዝ ወይም ታሪካችንን አፋልሷል ሲል አልተሰማም። ሁሉም ስለታቦተ ጽዮን አመጣጥ አንድ የሆነ እምነት የላቸውም ማለት ነው።  ከዚህ አንጻር ስለታቦተ ጽዮን አመጣጥ የሚናገር የተለያየ ሃሳብ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ ስላለ እውነተኛው የትኛው እንደሆነ ስለማይታወቅ ሁለቱንም ሃሳብ ላትስማሙ ተስማሙ ብለን ቤተ ክርስቲያኒቱ ለምትቀበለው  ወደሌላ ሦስተኛ ተቃራኒ ትረካ አልፈናል።

1.2/ የኢት/ ኦር/ ቤተ ክርስቲያን ታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ አልመጣችም የሚልና የምታምነው መጽሐፍም አላት!

ከላይ እንዳስቀመጥነው ማኅበረ ቅዱሳን ክብረ ነገሥትን ውሸታም በማለት በግብጽ በረሃ አድርጋ ነው ታቦተ ጽዮን የመጣችው የሚለውን የግራሃም ሃንኰክን መጽሐፍ ለተከታዮቹ ሲያከፋፍል የምንረዳው ሁለት የተለያየ የአመጣጥ ትረካ መኖሩን ነበር። ይሁን እንጂ ሰማንያ አሀዱ በተባለው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በመጽሐፈ እዝራ ካልዕ ምዕራፍ 1 ቁጥር 54 ላይ እንዲህ በማለት ከላይ የቀረቡትን ሃሳቦች ሁሉ ውድቅ በማድረግ ታቦተ ጽዮን ወደኢትዮጵያ እንደመጣች ሳይሆን ወደባቢሎን መሄዷን በግልጽ ይናገራል።

«እግዚአብሔርን የሚያገለግሉበትን ንዋየ ቅድሳቱንና ጥቃቅኑንና ታላላቁን ዕቃ ሁሉ የእግዚአብሔር ማደሪያ ታቦትንም፤ ከቤተመንግሥት ዕቃ ቤት ያለውን ሣጥኑንም ሁሉ ማርከው ወደ ባቢሎን ወሰዱ» እዝራ ካልዕ 1፤54

ናቡከደነጾር ከ634-562 ዓ/ዓ የነበረ የባቢሎን ንጉሥ ኢየሩሳሌምን ጥሶ፣ ቤተ መቅደሱን አፍርሶ፣ እስራኤላውያንን በባርነት አግዞ እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። እንደመጽሐፈ እዝራ አተራረክ ከቤተ መቅደሱ ንዋያተ ቅድሳት መካከል ታቦቱን ጨምሮ ወደባቢሎን ያልተወሰደ እንደሌለ እናነባለን። ይህ መጽሐፍ ታቦተ ጽዮን በግብጽም ሆነ በቀዳማዊ ምኒልክ በኩል ወደኢትዮጵያ መጥታለች የሚለውን ታሪክ ውድቅ ያደረገ ትርክት ነው። እርስ በእርሳቸው ያልተስማሙት የክብረ ነገሥትና የታቦተ ጽዮንን ፍለጋ መጻሕፍት ትረካ ውድቅ በማድረግ ወደ ባቢሎን ማርኰ ስለመውሰዱ ሰማንያ ወአሀዱ የተባለው መጽሐፍ ቅዱስ አፖክሪፋ መናገሩ ነገሩን ሁሉ መያዣ መጨበጪያ የሌለው አድርጎታል። አሁን እንግዲህ ሊነሳ የተገባው ጥያቄ፤
ሀ/ ክብረ ነገሥት የተባለው መጽሐፍ ታሪክ ትክክል ነው?
ለ/ ታቦተ ጽዮንን ፍለጋ የተባለው መጽሐፍ ትረካስ ትክክል ነው? ወይስ
ሐ/ ታቦቱ ወደባቢሎን በምርኰ ተወስዷል የሚለው የመጽሐፈ እዝራ ካልዕ ቃል ትክክል ነው ወይ? ብለን እንጠይቃለን። መላሽ የለም እንጂ ጥያቄስ ሞልቷል።

1.3 ታቦቱ ከሰሎሞን ሞት በኋላ እስከ 300 ዓመት ድረስ በኢየሩሳሌም እንደነበረ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል።

 አፖክሪፋ ወይም ቀኖና መሰል መጻሕፍት ወይም ታሪክ ቀመስ መጽሐፍ በመንፈስ ቅዱስ ምሪት የተጻፉ ስላልሆኑ ሊሳሳቱ ይችላሉ። የኢት/ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዘመኗ ሁሉ ከሰራችው ስህተት ከሁሉ የከፋው እንደቀኖና መጻሕፍት እንጂ እንደምሉዕ የቤተ ክርስቲያን ዶግማዊ መጻሕፍት ቆጥራቸው የማታውቃቸውን መጻሕፍት በ2000 ዓ/ም ባሳተመችው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስርዋጽ በማስገባት ዶግማዊ መጻሕፍት አድርጋ መቁጠሯ የቁልቀሊት መሄዷን ማፋጠንዋ እንጂ የቅዱሳት መጻሕፍትን እውነት አይለውጠውም። ቅዱስ አትናቴዎስን አደንቃለሁ፣ እወዳለሁ እያለች በአደባባይ የምትለፍፍ ቤተ ክርስቲያን እነቅዱስ አትናቴዎስ በቅርጣግና ጉባዔ ላይ ካጸደቋቸውና በእስትንፋሰ እግዚአብሔር ተጽፈዋል ከተባሉት 39 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውጪ ለመያዝ ድፍረቱን ከየት አገኘች? ለመሆኑ አትናቴዎስን ከስም ውጪ ተግባሩን ተረክባለች ወይ ብለን እንድንጠይቅ የምንገደደው በእነቅዱስ አትናቴዎስ ቅቡል የተደረጉት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን ቁጥር ለመቀበል ለምን አመጸኛ ሆንሽ? እያልን ነው።
ወደጀመርነው ሃሳብ ስንመለስ መጽሐፈ ነገሥት እስከ ባቢሎን ምርኰ ድረስ ታቦቲቱ ኢየሩሳሌም እንደነበረች ይናገራል።
 ታቦተ ጽዮን በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ወደኢትዮጵያ መጣች የሚለውን አባባል ውድቅ የሚያደርገው ሌላው አስረጂ ከ300 ዓመት ቆይታ በኋላም በኢዮስያስ ዘመን/ ከ649-609 ዓ/ም/ ኢየሩሳሌም እንደነበረች መጽሐፍ ቅዱስ መናገሩ ነው። ኢዮስያስ ንጉሥ ሰሎሞን ከሞተ ከ300 ዓመት በኋላ በኢየሩሳሌም የነገሠ ንጉሥ ነበር።  የሚከተሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች የሚነግሩን የሕጉ መጽሐፍ መነበቡን/ 2ኛ ነገ 22፤8/ ንጉሡ የሕጉን መጽሐፍ ሲሰማ ልብሱን መቅደዱን /2ኛ ነገ 22፤11/ የእግዚአብሔር ቤት ይጠገን ዘንድ ማዘዙን /2ኛ ዜና 34፤10/ ከዚያም የእግዚአብሔርን ታቦት በመቅደሱ እንዲያኖሩት ማድረጉን መጽሐፍ ቅዱስ እናነባለን።
«እስራኤልንም ሁሉ ያስተምሩ ለነበሩት፥ ለእግዚአብሔርም ለተቀደሱት ሌዋውያን እንዲህ አለ፦ ቅዱሱን ታቦት የእስራኤል ንጉሥ የዳዊት ልጅ ሰሎሞን በሠራው ቤት ውስጥ አኑሩት ከዚህም በኋላ በትከሻችሁ ላይ ሸክም አይሆንባችሁም አሁንም አምላካችሁን እግዚአብሔርንና ሕዝቡን እስራኤልን አገልግሉ» 2ኛ ዜና 35፤3
እንደእኛ እምነት የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ስለማይሳሳት መጽሐፍ ቅዱስን የሚቃወሙ መጻሕፍት ሁሉ ስሁታን ናቸው እንላለን። በዚሁ መሠረት ታቦቲቱ ወደኢትዮጵያ መጥታለች የሚለውን ትረካ ከ300 ዓመት በኋላ እዚያው ኢየሩሳሌም መኖሯን መጽሐፍ ቅዱስ ስለሚነግረን የሰውን ትርክት ትተን የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት እንቀበላለን። ለሰው ሊነገር የሚገባው የማኅበረ ቅዱሳንን? ወይስ የክብረ ነገሥት? ወይስ የእዝራ ካልዕን? ወይስ የመጽሐፈ ነገሥትን እውነት? ሁሉም ታሪኮች ስለአንዱ ታቦት የተለያየ ነገር ያወራሉና ቤተ ክርስቲያን ሆይ የትኛውን ቃል ለሚጠይቁሽ ትናገሪያለሽ?  ሌላው ማፈሪያ ትምህርትሽ ደግሞ የሙሴ ሁለት ጽላት ( የማርያምና የሚካኤል) ነው የሚለው ተረትሽ ነው። ዐሥርቱ ትእዛዛት  በሁለቱ ሰሌዳ ላይ በቀኝና በግራ ከመጻፉ በስተቀር የሚካኤልና የማርያም የሚባል ጽላት አልነበረም።

"ታደርጉትም ዘንድ ያዘዛችሁን ቃል ኪዳን አሥሩን ቃላት ነገራችሁ፤ በሁለቱም በድንጋይ ጽላቶች ላይ ጻፋቸው። " (ዘዳ 4: 13)

 ድንግል ማርያም ከመፈጠሯ ከ2000 ዓመት በፊት ለድንግል ማርያም  ጽላት ተቀረላት የሚለው ተረት ገደብ ይበጅለት።  ሲጀመር ጽላት የትእዛዛቱ ቃል ማክበሪያ እንጂ የሰው ምስልና የሆነ ያልታወቀ ኅቡዕ ጠልሰም መቅረጫ አልነበረም። ቤተ ክርስቲያኒቷ መጻሕፍትን መርምረው ከሚጠይቋት የምትሰጠው  መልስ እውነቱን በመግለፅ ነው ወይስ ተሐድሶ መናፍቅ በሚል የውግዘት ማስፈራሪያ?

2/ ቤተ ክርስቲያን ዲያብሎስን ክብሩ የወደቀው በምንድነው ብላ ታስተምራለች? ዲያብሎስ የወደቀ በትዕቢቱ አምላክ ለመሆን ስለፈለገ ነው ወይስ ለአዳም ስገድ ተብሎ እምቢ በማለቱ ነው?
እንደቤተክርስቲያን አስተምህሮ ሰይጣን እስከነሠራዊቱ የወደቀው በመታበዩ ምክንያት እንደሆነ ነው የሚታመነው።

ትንቢተ ኢሳይያስ 14፥12
«አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ፥ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! አሕዛብንም ያዋረድህ አንተ ሆይ፥ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቈረጥህ!»
ይለዋል።
ራሱን የሁሉ ገዢ ለማድረግ ክሳደ ልቡናው ስለተነሳሳ በስሁት መንፈሱ ለውድቀት ተዳርጓል የምትል ቤተክርስቲያን፤ «የለም! ሰይጣን የወደቀው በትእቢቱ መላእክትን እኔ ፈጠርኳችሁ ስላለ ሳይሆን ለአዳም አልሰግድም ስላለ ነው» የሚል አስተምህሮ ይዛ መገኘቷ ነገሩን ሁሉ አስገራሚ ያደርገዋል።
 መጽሐፈ መቃብያን ለአዳም ስላልሰገደ ዲያብሎስ ወደቀ ይለናል።
እንደዚህ የሚል ትምህርት በቤተክርስቲያናችን የለም የሚል ሰው ቢኖር ቁጥሩ ከአፖክሪፋ የሆነውንና እንደመጽሐፍ ቅዱስ አንድ ክፍል እንዲቆጠር በግድ የተበየነበትን መጽሐፈ መቃብያንን አያነብም ወይም ስለተሸከመው ብቻ የገባው ይመስለዋል ከማለት ውጪ ምን ልንል እንችላለን?

«የሚጠፉ በኔም የሚስቱ ሰዎች ፈጽመው ይበዙ ዘንድ፤ የአዳምም ልጆች ይጠፉ ዘንድ፤ ይህንን በተናገሩ ጊዜ እኔ ደስ ይለኛል፤ ለሚዋረድልኝ ለአዳም አልሰግድም በማለቴ እግዚአብሔር ስለአባታቸው ስለአዳም ከማዕረጌ አዋርዶኛልና፣ 3ኛ መቃ 1፤15

እንዲሁም በ2ኛ መቃብያን ላይ በተጨማሪ እንዲህ የሚል እናገኛለን።

«ክሳደ ልቡናውን በማጽናትና ራሱን በማኩራት ፈጣሪው ለፈጠረው ለአዳም መስገድን እንቢ እንዳለ»2ኛመቃ 9፤1-3

የጥንቱ ተጨማሪ ቀኖና የአሁኑ የቤተ ክርስቲያኒቱን የዶግማ መጽሐፍ ክብርን የተጎናጸፈው መቃብያን፣ ዲያብሎስ የወደቀው ለአዳም አልሰግድም ብሎ እምቢ በማለቱ ነው ይለናል። ይህ የመቃብያን መጽሐፍ ዲያብሎስ የወደቀው ለአዳም አልሰግድም ብሎ እንጂ ራሱን ከፈጣሪ ጋር አስተያይቶ በትእቢት አይደለም ከሚለው ከቁርአን ጋር ተመሳሳይ ሃሳብ አለው። ሱረቱል አልበቀራህ ወይም የላም ምዕራፍ 2፤ 34
وَإِذْ قُلْنَا لِلْمَلَائِكَةِ اسْجُدُوا لِآدَمَ فَسَجَدُوا إِلَّا إِبْلِيسَ أَبَى وَاسْتَكْبَرَ وَكَانَ مِنَ الْكَافِرِينَ ንባቡም ።
Waith qulna lilmalaikati osjudoo liadama fasajadoo illa ibleesa aba waistakbara wakana mina alkafireena
ወደአማርኛ ሲመለስ፤
«ለመላእክትም ለአዳም ስገዱ ባልን ጊዜ (አስታውስ) ሁሉም ወዲያው ሰገዱ። ኢብሊስ (ዲያብሎስ) ብቻ ሲቀር እምቢ አለ፤ኮራም ከከሀዲዎቹ ሆነ»  የቁርአንና የመቃብያን መመገጣጠም የአጋጣሚ ነው ወይስ የክርስትና ቁርጥራጭ ሃሳቦችን ለመሀመድ ያስተማረ የመቃብያን አቀናባሪ ግብፃዊ መነኩሴ ይኖር ይሆን?
(የጥቅሱ መጨረሻ)
 ይህንን የመቃብያን መጽሐፍ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር በእኩል ደረጃ አትቀበለውም።  እነሱ ያልተቀበሉትንና ያልፈለጉትን መጽሐፍ ጭነውብን ነው ወይስ ለእኛ ለኢትዮጵያኖች ለብቻችን መቃብያን መጽሐፍ ከሰማይ የወረደልን ሆኖ ይሆን?
ዲያብሎስ ክብሩ የተዋረደው ለአዳም አልሰግድም ብሎ እንቢ ስላለ ነው? ለአዳም እንዲሰግድ የታዘዘውስ መቼ ነው? ይህስ ከየት የተገኘስ አስተምህሮ ነው? ብሎ ለሚጠይቃት አንድ ምስኪን ልጇ ቤተ ክርስቲያን ምን ብላ ትመልስለታለች?  መቃብያንን የምትመድበው እስትንፋስ እግዚአብሔር ካለበት መጽሐፍ ወይስ ከህፁፅ አፖክሪፋ?

3/እንጠይቃለን መላሽ ከተገኘ፣ ለሰዎች በቀይና በጥቁር መጻፍን ያስተማረው ማነው?

ለሰዎች በጥቁርና በቀይ ቀለም መጻፍ ያስተማረው አጋንንት ነው ትይናለሽ። ይህንን እንዴት እንመን።
ለዚህ ጥያቄ አዎን አጋንንት ነው ያስተማሩት የሚል ምላሽ ቢሰጥበት ሰዎች መቃወማቸው እርግጥ ነው። ምክንያቱም ቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ በጥቁር ወይም በጥቁርና ቀይ መጻሕፍት እያዛነቁ መጻፍ የተለመደ ስለሆነ የጥቁርና ቀይ ቀለማትን ምንጭ ከአጋንንት ጋር ማያያዝን ማንም አሜን ብሎ አይቀበልም። ምክንያቱም የአጋንንት ተማሪና መንገዱንም ተቀባይ ፈቃደኛ ሰው መቼም የእግዚአብሔር መሆን አይችልም። ይሁን እንጂ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከቅዱሳት መጻሕፍት ዝርዝር ውስጥ የማትቆጥረው መጽሐፈ ሄኖክ የተባለው አፖክሪፋ / */በቀይና በጥቁር ቀለም መጻፍ ለሰው ልጆች ያስተማረው አጋንንት ነው ይለናል። መጽሐፈ ሄኖክ 19፤22-24 ይመልከቱ። እንግዲህ ለመልካም ይሁን ለጥፋት በዚህ ዘመን የሰው ልጅ የሚጠቀምበት የመጻፊያ ጥቁርና ቀይ ቀለም ተጠቃሚዎች ሁሉ የአጋንንት ተማሪዎች ናቸው ማለት ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ ተስፋ ገ/ሥላሴ ዘብሔረ ቡልጋና ትንሣዔ ዘጉባዔ ማተሚያ ቤቶች ይበልጥ የአጋንንትን ትምህርት ፈፃሚዎች ናቸው ማለት ነው።
ይሁን እንጂ የጽሕፈት፤ የፊደላትና የእውቀት ባለቤት የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንጂ አጋንንቶች ሊሆኑ በፍጹም አይችሉም። አጋንንት የበጎ ነገር ጠላቶች እንጂ ለሰው ልጅ የእውቀት ምንጮች የመሆን ተፈጥሮ የላቸውምና። ሰዎች የተሰጣቸውን እውቀት ላልተፈለገ ዓላማ ሊገለገሉበት ይችላሉ እንጂ አጋንንት የአዳምን ልጆች የጽሕፈት እውቀት አስተማሩ ማለት ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለውና ሰውን የአጋንንቶች ወዳጅ አድርጎ የሚያቀርብ የክህደት አስተምህሮ ነው። ጥቅመ ሰናኦር ቋንቋን የሰጠ እግዚአብሔር፤ የቋንቋ መጻፊያ ቀለማትን ደግሞ ሰይጣን በመፍጠር በምንም መልኩ የፈጣሪ አጋዥ ሊሆን አይችልም። ቤልሆር ከክርስቶስ ጋር ምንም ኅብረት የለውምና።
መጽሐፍ ቅዱስ ግን እግዚአብሔር ለነቢያቱ ይህን ጻፉ፤ እንዲህም ጻፉበት እያለ የጽሕፈት ባለቤትነቱን ይመሰክርለታል። «ሙሴም የእግዚአብሔርን ቃሎች ጻፈ ማለዳም ተነሣ» ዘጸ 24፤4
«ሙሴም በዚያ ቀን ይህችን መዝሙር ጻፈ፥ ለእስራኤልም ልጆች አስተማራት» ዘዳ 31፤22
«አንድ የመጽሐፍ ክርታስ ውሰድ፥ ለአንተም ከተናገርሁበት ቀን ከኢዮስያስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በእስራኤልና በይሁዳ ላይ በአሕዛብም ሁሉ ላይ የተናገርሁህን ቃል ሁሉ ጻፍበት» ኤር 36፤2
«ዳግመኛም ሌላ ክርታስ ውሰድ፥ የይሁዳም ንጉሥ ኢዮአቄም ባቃጠለው ክርታስ ላይ የነበረውን የቀድሞውን ቃል ሁሉ ጻፍበት» ኤር 36፤28
እጅግ ብዙ አስረጂዎችን ማቅረብ ይቻላል። እውነትን ለመግለጥ በቂ ነውና በሄኖክ ስም ራሱን በእግዚአብሔር ቦታ አስቀምጦ እኔ ለሰው ልጆች እውቀትን የሰጠሁ ነኝ የሚለው ክፉ መንፈስ ግን በእግዚአብሔር ቃል የተሳሳተ አስተምህሮ ነው። አጋንንት ጽሕፈትን እንዴትና መቼ እንዳስተማረ ማስረጃ ከሚያቀርቡ የቅርብ ወዳጆቹ ለመስማት ዝግጁ ነን። ይሁን እንጂ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እጅግ የምታደንቀው የሃይማኖት አባት አትናቴዎስ የማያውቀውንና የኮፕት ቤተክርስቲያንም እንደቅዱሳት መጻሕፍት የማትቀበለውን መጽሐፈ ሄኖክ የመምህርነቱን ስፍራ ለአጋንንት ሰጥቶት ይገኛል። የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንስ ያልተቀበለችው ለምን ይሆን? አጋንንት እስከተጠበቀላቸው የፍርድ ቀን ድረስ የሰው ልጆች ተቃዋሚዎች እንጂ በጎ አድራጊዎች ሊሆኑ አይችሉም።  በእርግጥ በቀይና በጥቁር ቀለም ለሚፅፉ፣ ቃል ኪዳን ለገቡ ደብተራና ኅቡእ ስም ደጋሚ ባለተዋርሶ የቤተክርስቲያን ሰዎች በትርፍ ጊዜአቸው ለመስተሐምም፣ ለመቅትል፣ ለመስተአብድ፣ ለመስተባርር፣ ለአምጽኦ ብእሲት፣ ለመስተፋቅር፣ ለመስተጻልእ፣ ለመንድግ ወዘተ ሰይጣናዊ ሥራ ያገለግሉ ይሆናል።

4/ የቤተክርስቲያኒቱ ዲያቆናት ሲኦል ውስጥ ለሚቃጠሉ ሰዎች ምሳሌ ናቸው!

ቤተ ክርስቲያኒቱ ካልጠፋ ምሳሌ ዲያቆናቱን ወደእሳት ከሚወረወሩት መካከል አድርጋቸዋለች። አስፀያፊ ምግባር ያለው በፍርድ ቀን እግዚአብሔር ፊት ሲቆም ጳጳስም ቢሆን ከቅጣት ሊድን አይችልም። ፍርድ በክርስቲያናዊ ማንነት የሚሰጥ ዋጋ እንጂ በማእረግ ሚዛን የሚደረግ ማበላለጥ አይደለም። ለእያንዳንዱ እንደስራው የሚከፍል እግዚአብሔር ዲያቆናትን  ብቻ ለይቶ ወደእሳት አይጥልም።
ዲያቆናት ጥርስ ማፋጨትና እሳቱ ወደማይጠፋ ቅጣት ይወርዳሉ የሚል የዉሸት ምሳሌ የመጣው ከየት ነው?
በማቴዎስ ወንጌል ላይ የተሰጣቸውን መክሊት ከሦስተኛው በስተቀር ሌሎቹ አራብተው ለባለቤቱ ዋናውን የመለሱ ሠራተኞችን ማንነት የሚገልጽ ቃል አለ።
(የማቴዎስ ወንጌል 25፤14-30 ያለውን ይመለከቷል)
በቁጥር 15 ላይ «ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ፥ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ» ይላል። እነዚህ ሰዎች በተሰጣቸው መክሊት አትርፈው ዋናውን ለባለዋናው መመለስ በሚገባቸው ወቅት የተገኘባቸው ትጋት እንዲህ ተቀምጧል።
« አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ። ጌታ ሆይ፥ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ። ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው። ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ። ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው። አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ»
በዚህ ውስጥ ያተረፉት ሲሾሙና ሲሸለሙ፤ ያላተረፈውን ባለአንድ መክሊት ባሪያ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት እሳት መጣሉን ቃሉ ይናገራል። ይህንን ቃል አንድምታ በተባለው ትርጉም ውስጥ እንዲህ የሚል ቃል ተቀምጧል።
ባለአምስት መክሊቱ ሊቀጳጳስ ነው፤ ባለሁለቱ መክሊት በቄስ ይመሰላል። ባለአንድ መክሊቱ ደግሞ በዲያቆን ይመሰላል በማለት እጣ ፋንታውን በቤተክህነቱ የስልጣን እርከን መሠረት ይደለድልና ዲያቆናትን « ወለገብርሰ ዘእኩይ» ተብለው እድል ፈንታቸውም የዘላለም እሳት እንደሆነ በምሳሌ የተቀመጡበት የሥልጣን እርከን ትርጉም በፍጹም ትክክል አይደለም እንላለን። (ወንጌል ቅዱስ ንባቡና ትርጓሜው 1916 ዓ/ም)
በዚህ ዘመን ያለውን ግብር ተመልከተን ብንመዝን በያዙት ሥልጣንና ኃላፊነት ደረጃ ተጠያቂ በመሆን የሚወዳደራቸው የማይኖረው ለራሳቸው የባለአንድ መክሊቱን ሥፍራ ቆርሰው የያዙት ጳጳሳቱ በሆኑ ነበር። ለተልእኰ በመፋጠንና ከሙጋድ ጢስ ጋር ሲታገል የሚኖረውን ዲያቆን የገብር ዘሀካይን ደረጃ በማጎናጸፍ  መክሊቱን የቀበረ፣ በተሾመበት ያልታመነ፣ ክፉና ተንኮለኛ አድርጎ መተርጎም የጤነኛ ቤተ ክርስቲያን አስተምሀሮ አይደለም። ስልጣኑም፣ ሚስቱም፣ ቤቱም፣ መኪናውም ብሩም ሁሉን ሰብስቦ ነፍሴ ሆይ እረፊ፣ ደስ ይበልሽ  የሚል ጳጳስና አለቃ ባለባት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሌሊት ለሰዓታት፣ ቀን ለቅዳሴ የሚባትለውን ዲያቆን ገብርሰ ዘለእኩይ ማለት ተሳልቆ ነው።  እንደዚህ ጽሁፍ አቅራቢ "ገብርሰ ዘለእኩይ" የሚባለው በብዙ የተሾመ፣ በብዙ የሚጠበቅበትና በብዙ ሊሰራ ሲገባው ስጋውን በምቾት  ያሰረ ሹም ነው።
ስናጠቃልል እስካሁን ለዘረዘርናቸው መጠይቅ መላሾች እውነቱ የቱ ነው? በማለት እንጠይቃለን። ስህተት ካለብን  ስለሃይማኖት ከማሽሟጠጥ ይልቅ እውነቱ ሊነገረን ይገባል።  ያ መሆን ካልቻለ እውነቱን ለመቀበል ባንፈልገውም እውነት ምን ጊዜም እውነት እንደሆነ ሲኖር ውሸትም ለእውነት ጊዜውን ጠብቆ ሥፍራውን መልቀቁ አይቀርም።
«ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልምና» 2ኛ ቆሮ 13፤8





Wednesday, September 6, 2017

«አማለደ» ያለው አማለደ ለማለት ሳይሆን . . . » ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ሦስተኛውና የመጨረሻው ክፍል )





Kesis Melaku Terefe

መነሻው እንደጰላድዮስ በጥያቄ፥ እንደንስጥሮስ በክርክር ቢሆንም፥ ለተነሡት ጥያቄዎችና ክርክሮች መልስ እንዲሆን ቅዱሳን አባቶቻችን ጽፈውልን የተዉልን ጦማሮችና ድርሳናት ፥ ዛሬ በጨለማ እንዳንዳክር መንገድ ጠቋሚዎች ሆነው፥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በሚገባ እንድንመረምርባቸው ረድተውናል። ዛሬም በስሕተት ጎዳና ካሉት ጋር የምናደርገውን ክርክር የምንመራው ፥ እነዚህ አባቶቻችን የቀደዱልንን ፈር በመከተል ነው። ምስክራችን ቅዱሳን ሐዋርያት፥ ሐዋርያውያን አበው፥ የኋላ ሊቃውንት እና ሲኖዶሶቻቸው ነው። ከሳሾቻችን ክርክሩን ለማሸነፍ እየሞከሩ ያሉት፥ በቃላት ስንጠቃና በብልጣ ብልጥነት ነው። ቢታጣ ቢታጣ፥ የግእዙንም ሆነ የአማርኛውን ሰዋስው ተጠያቂ የሆኑትንና በዚህም የኢትዮጵያውያን ሁሉ ባለውለታ የሆኑትን አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌንና ደስታ ተክለ ወልድን ለአማርኛ ቃል ክርክር ምስክር ስላደረግናቸው፥ የቦሩ ሜዳውን ክርክር ወደኛ ለማምጣት እየሞከሩት ነው። ትንሽ ቆይተው ደግሞ ኪዳነ ወልድ የተረጎሙት ሕዝቅኤል ይቃጠልልን ብለው ቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ አቧራ እንደሚያስነሱ እንጠብቃለን። ለነገሩ ይህን የሚያውቁት አይመስለንም። አለቃ ግን  አፉ ያልተገራ ጨዋ እንዲህ ሲሰድባቸው ቢሰሙ ኖሮ በአጭሬ ግጥማቸው ያቀምሱት ነበር። ግን ምን ያደርጋል!
እኛ ግን የተዋህዶ ማኅተም እየተባለ የሚጠራው፥ የእስንድርያው ፓትርያርክ ቅዱስ ቄርሎስ፥ « ከመ አሐዱ ክርስቶስ» የተሰኘውን ተዋህዶን ያመሠጠረበትን ድንቅና ታላቁን ድርሰቱን ሲጀምር፥ « ለትምህርተ ቅዱሳት መጻሕፍት አልቦ ዘይጸግቦን ግሙራ ወኢመኑሂ፤ የቅዱሳት መጻሕፍትን ትምህርት ማንም ማን አይሰለችም።» በማለት እንደተናገረው ያለ መሰልቸት፥ ከአበው የተማርነውን እንጽፋለን እንናገራለን። የእግዚአብሔር ቃልን ከመናገር ቸል አንልም አንሰለችም። ይኸው ሃይማኖቱ የቀና ( ኦርቶዶክሳዊ) አባት፥ « ሲሲተ ልብ ቃላቲሁ ለእግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ቃል የልቡና ምግብ ነው» እንዳለው፥ በዚህም ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሕይወታቸውን እንደሚመግቡ ተስፋ እናደርጋለን።
ወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥ ባለፈው በክፍል ሁለት ጽሑፋችን አራት ዋና ዋና ነገሮችን አንሥተናል፥ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናትነት ፍጹም ሰው በመሆኑ እንደሆነ፤ ሊቀ ካህናትነቱ በሹመት እንደሆነ፥ ሊቀ ካህንነቱ ለማስታረቅ እንደሆነ፥ በመጨረሻም ሊቀ ካህናትነቱ እንደ መልከ ጼዴቅ እንደሆነ ተመልክተናል። በዚህ ክፍል ሦስት ጽሑፋችን ደግሞ የአውጣኪን የስህተት ጎዳና በመከተል፥ የክርስቶስን የሊቀ ካህናትነቱን የማስታረቅ አገልግሎት የካድክባቸውን ነጥቦች በማንሳት፥ አንድ በአንድ መልስ እንሰጣለን።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ «ከዚህም አያይዞ፡-“እርሱም በሥጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚ ችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤”ብሎአል። የቅዱስ ጳውሎስ የትርጓሜ መጽሐፍ፡-ይኸንን ገጸ ንባብ ሲያብራራው፡-“ወእመ ሀሎ በመዋ ዕለ ሥጋሁ፥ ጸሎተ ወስኢለ አብአ፥ በዐቢይ ገዓር ወአንብዕ።ይኸውም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነትን ሥራ በሠራበት ወራት (ከቤተል ሔም እስከ ቀራንዮ ባደረገው የማዳን ጉዞ) ጸሎ ትን፡-እንደ ላም፥ምልጃን(ልመናን)፡-እንደ በግ አድ ርጎ፥በፍጹም ሐዘንና በብዙ ዕንባ አቀረበ ፤”ብሎአል።ምክንያቱም፡-የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ለል መና እና ለምልጃ የሚያቀርቡት የበግ እና የላም መሥዋዕት ነበር።በመሆኑም፡-በንባቡ ጸሎትና ምልጃ የተባለው፡-“አማለደ፤” ለማለት ሳይሆን፥እንደ ላምና እንደ በግ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን እንደሆነ ማስተ ዋል ይገባል » ብለህ ነበር።
ይህ ጽሑፍህ  ከእግዚአብሔር ቃልና ከአባቶች ትርጓሜ ጋር ሙግት የያዘ ነው። አንደኛ፥ ጸሎት እና ምልጃ ተብሎ የተጻፈውን  ጸሎትና ምልጃ ብላችሁ አታንብቡ ትለናለህ። የእግዚአብሔርን ቃል ታጣምም ዘንድ እንዴት ደፈርህ። በዚህ አላበቃህም።  ሁለተኛ፥ አባቶች « ጸሎትን እንደ ላም ምልጃን እንደ በግ አድርጎ አቀረበ» ብለው የተረጎሙት፥ ጸሎትና ምልጃ ለማለት አይደለም  በማለት ምልጃና ጸሎት ተብሎ የቀረበው ሥጋው ነው በማለት ነበር ያስቀመጠው። ይህ ሁሉ ግን ፥ ክርስቶስ በሊቀ ካህንነቱ አልማለደም አልጸለየም ለማለት ነው።  ያንተን ትርጓሜ የማንቀበልበትን በዝርዝር እናስረዳ፤
፩ኛ. ንባቡ የሚለው « ጸሎትንና ምልጃን» አቀረበ ነው።
« እርሱም ሥጋ ለብሶ በዚህ ዓለም በነበረበት ጊዜ፥ በታላቅ ጩኸትና እንባ ከሞት ሊያድነው ወደሚችለው ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤ ጽድቁንም ሰማው» ነው የሚለው። በዚህ ንባብ ውስጥ ጌታ በመዋዕለ ሥጋዌው ያደረጋቸው ነገሮች በግልጥ ተቀምጠዋል። ጩኸት ( ገዓር) እና እንባ (አንብእ) ጸሎት እና ምልጃ ተነግረዋል።  ምንም እንኳ ሙሉ በሙሉ ወልድ በሥጋው ወራት ወደ አባቱ እንደጸለየ ብትክድም፥ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባብ ይህን በግልጥ ያስቀምጣሉ።

ስለ ጸሎቱ ለምሳሌ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ጌታ በጌቴሴማኒ ሲጸልይ የነበረውን ሁኔታ ሲገልጥ እንዲህ ይላል። የሚያበረታታው የእግዚአብሔር መልአክም ከሰማይ ታየው። ፈራ መላልሶም ጸለየ ላቡም በምድር ላይ እንደሚወርድ እንደ ደም ነጠብጣብ ሆነ» ይላል፤ ሉቃስ ፳፫፥፵፬። እዚህ ላይ ከመጸለይ ባሻገር፥ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ « ፈራ» ብሎ ሲናገር እናያለን። ቀሲስ ደጀኔ ባንተ አተረጓጎም ከሄድን « ፈራ ሲል ፈራ ማለት አይደለም» ብለን የፈጠራ ትርጉም መስጠት እንችል ነበር። ግን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲህ በማድረግ አናጣምም። ፈራ ሲል ፈራ ነው። አማለደ ሲል አማለደ ነው። ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ? የእግዚአብሔር ልጅ እንዴት ፈራ ይባላል፥ አባቶች በሚገባ መልሰውታል። « በሰው ልማድ ፈራ፤» አሉ፤ ትርጓሜ ወንጌልን ተመልከት። ማለትም በእውነት ፍጹም ሰው ስለሆነ ማናቸውም ሰው እንደሚፈራው ነው የፈራው። ከኃጢአት በቀር እንደኛ የሆነ ሰው ነውና። ነገር ግን ከዚያ በላይ ታላቅ የሆነ መልእክት አለ። ለምን ፈራ? እኛን ሆኖ፥ ስለ እኛ ብሎ ስለሆነ የወደቀውና የተነሣው፥ የፈራውም የእኛን ፍርሃት ነው። በእውነት እኛን ሆኖ የእኛን ፍርሃት ፈራ። « ሶበሰ ኢፈርሃ እምኢሰሰለ ፍሃት እምኔነ፤ ባይፈራ ኖሮ ( የምትሃት ቢሆን ኖሮ፥ ወይም በእውነት ሳይፈራ ለትምህርት ብቻ ያሳየው ቴያትር ቢሆን ኖሮ) ፍርሃት ከእኛ ባልተወገደ ነበር።»  የጸለየውም መላልሶ ነው። አባቶች እንዳስቀመጡት፥ « ወጸርሐ ኀበ አቡሁ ከመ ትምጽኦ ረድኤቱ፤ ረድኤቱ ትመጣለት ዘንድ ወደ አባቱ ጮኸ፤» እንዴት ይህ ሊሆን ቻለ ቢባል በለበሰው ሥጋ።
ይህ የአባቶች ትርጓሜ፥ ከነባቤ መለኮት ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ትምህርት ጋር አብሮ የሚሄድ ነው። አቡልናርዮስ ጌታ ነፍስን አልነሣም ብሎ የኑፋቄ ትምህርቱን ይዞ ሲነሣ ቅዱስ ጎርጎርዮስ የሰጠው መልስ «What has not been assumed has not been healed; it is what is united to his divinity that is saved. ያልነሣውን አልፈወሰውም፤ ከመለኮትነቱ ጋር የተዋሃደውን ያንን  ነው የዳነው» ነበር ያለው። ይህ የነባቤ መለኮት ጎርጎርዮስ አባባል የሚያስረግጥልን፥ ጌታ የኛን ባሕርይ የተዋሃደው ሊያድነን ነው።
ያዳነን የተዋሃደውን ባሕርይ ነው። ከኃጢአት በቀር፥ የሚዝል፥ የሚደክም የሚፈራ፥ የሚራብ የእኛን ባሕርይ ነው የተዋሃደው። በእውነት የሰውን ባሕርይ ገንዘብ አድርጎአልና።
ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ይህን የቅዱስ ሉቃስን ንባብ ሲተረጉመው እንዲህ አለ። « እርሱ እንደፈራ በተናገረ ጊዜ ጌታ የተዋሐደውን የሰውን ባሕርይ አስረዳ፤ እውነተኛ ሰው እንደሆነም አስረዳ። በዚህም ጌታ የተዋሐደው ኃጢአት የሌለበትን የሥጋን ሥራ ሰው መሆኑንም አስረዳ፤ ፍርሃት ከመለኮት ባሕርይ አይደለም። ወዙ እንደ ደም ነጠብጣብ በዝቶ እስኪወርድ ድረስ አለ፤ ደም መስሎ መውረድም የሥጋ ገንዘብ ነውና። የሚያጽናናው የእግዚአብሔር መልአክም ከወደ ሰማይ መጣ አለ።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ም. ፶፮. ክፍል ፫ ቍ. ፵፪- ፵፫
፪ኛ. የአባቶች ትርጓሜም ትኩረት የሚያደርገው  « ጸሎትንና ምልጃን» ነው።  
ይህን እንደገና አባቶች በትርጓሜያቸው እንዴት እንዳስቀመጡት እንመለከት፦  « ሰው ኾኖ የስውነት ሥራ በሠራበት ወራት፤ጸሎትን እንደላም ስኢልን እንደበግ አድርጎ አቀረበ።በፍጹም ኀዘን በብዙ ዕንባ አቀረበ። የልቡና ነውና፥ ግዳጅ ይፈጽማልና፥ አንድ ጊዜ ነውና በታላቅ ጩኸት ( ኀዘን) እና በእንባ አለ። ከሞት ሊያድነው ወደሚቻለው ወደ አብ አቀረበ። የምእመናንን ድኅነት ለራሱ አድርጎ፥አንድም ምእመናንን ከሞት ሊያድንለት ወደሚቻለው ወደ አብ አቀረበ። ቁርጥ ልመናውንም ሰማው። የባሕርይ ልጅ ሲሆን፥ ታዞ መከራ ስለተቀበለ፥ መታዘዝን አመለከተ ( ዐወቀ)። ትንቢተ ነቢያትን፥ ዘመንን፥ ቀጠሮን፥ አሥሩ ቃላትን፥ ሕማማተ መስቀልን ፈጽሞ፥ ለሚያምኑበት ኹሉ ሕይወትን የሚያድል ኾነ። የዘላለም ሕይወት ሆነ»
በግዴለሽነት የአባቶችን ትርጓሜ « ለማቃናት » የጮሌነት አካሄድ ብትሄድም፥ ትርጓሜው አይሰድህም። « « ጸሎትን እንደላም ስኢልን እንደ በግ አድርጎ አቀረበ» ሲል ላምና በግ ስለተጠቀሰ « ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን የሚያመለክት ነው» ያልከው መሥዋዕት ያለ ምልጃና ያለጸሎት እንደማይቀርብ ባለማስተዋልህ ነው። ያው የአባቶች ትርጓሜ ትኩረቱ ምን ላይ እንደሆነ፥ በጥንቃቄ ትረዳው ነበር። ለምሳሌ « በፍጹም ኀዘን በብዙ ዕንባ አቀረበ» የሚለውን ሲተረጉሙ የሚያሳየው ይህን እውነት ነው። እነርሱ ያሉት « የልቡና ነውና፥» ማለት የመታየት፥ የምትሃት አይደለም፤ « ግዳጅ ይፈጽማል » ማለት የቤዛነት ሥርየተ ኃጢአትን የሚያሰጥ ነው ል  « አንድ ጊዜ ነው» አንድ ጊዜ ለዘላለም የከናወነው ነው የሚል ነው። ይህ ብቻ አይደለም ። « ወሰምዖ ጽድቆ፥ ጽድቁ ተሰማለት» የሚለውን « ቁርጥ ልመናውንም ሰማው» ብለው ነበር የተረጐሙት። ንባቡ ልመናው ስለመሰማቱ ፥ ስለመታዘዙ ነው የሚናገረው። እንህ   « ቁርጥ ልመናውን ሰማው ማለት፥ ቁርጥ ልመናውን ሰማው ለማለት አይደለም» ካላልክ በስተቀር፥ የቀረበffው ቁርጥ ልመና ነው፤ የቀረበው ምልጃ ነው።

፫ኛ. ዓለም የታረቀው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበው ጸሎትና ምልጃ ነው።
ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ የጸለየው ጸሎት የምልጃ ጸሎት ነው። ይህን በተለይ ዮሐንስ 17 በግልጥ ያሳየናል። በዚያ ጸሎት ውስጥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ለነበሩት ደቀመዛሙርቱ ብቻ ሳይሆን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ ነበር የጸለየው። በመስቀል ላይ የነበረው ጩኸቱም በመስቀል ላይ የቀረበ የምልጃ ጩኸት ነው። ይህን ከእኔ ይልቅ አለቃ አያሌው ውበት ባለው አገላለጥ አስቀምጠውታል። አስተውል አለቃ እንዴት አድርገው ይህን የቤዛነት ሥራ እንደገለጡት በጥንቃቄ ተከታተለው።
አለቃ አያሌው እንዲህ ይላሉ፦ « በዕለተ ስቅለት በካህኑ ፋንታ ሆኖ « እኔ ስለ እነዚህ እለምናለሁ፤ ስለ ዓለም አልለምንም፤ ስለሰጠኸኝ እንጂ፡ የአንተ ናቸውና የእኔም የሆነ ሁሉ ያንተ ነው። የአንተውም የእኔ ነው። እኔም ስለእነርሱ ከብሬአለሁ፤ ከዚህም በኋላ በዓለም አይደለሁም። . . . ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑትም ደግሞ እንጂ ስለእነዚህ ብቻ አልለምንም» ብሏል። ( ዮሐ ፲፯፥፱-፳) ስለጠቅላላ ምእመንን ባቀረበው ጸሎትም በመስቀል ላይ ሳለ አባት ሆይ የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» « አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ» ብሎ በመናገር፥ « ራሴን ስለበጎቼ አሳልፌ እሰጣለሁ እሺ በጄ ብዬ መጣሁ ብሎ የተናገረው ቃል ሲፈጸም « አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ እሰጣለሁ ብሎ ነፍሱን ከሥጋው በመለየቱ፥ ከአሮን ክህነት በላቀና በረቀቀ የክህነት ሥርዓት ካህን፥ አስታራቂ መታረቂያ መሥዋዕት ሆኖ በፈጸመው በሞቱ የሰውና የእግዚአብሔር እርቅ ከፍጻሜ ደረሰ። ከአብ፥ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም ይቅር ባይ፥ ታራቂ፥ መስዋዕት ተቀባይ ፥ ሕይወትን አዳይ ዋጋ ከፋይ በመሆኑ በኃጢአት ምክንያት ተቋርጦ የነበረው የሰውና የእግዚአብሔር አንድነት በተዘምዶውና ( ሰው በመሆኑንና) በቤዛነቱ ታደሰ። » ( ምልጃ እርቅና ሰላም፤ ገጽ ፳፩- ፳፪) ይህ የአለቃ አገላለጥ ሰፊ ትንታኔ የሚያስፈልገው ብቻ ሳይሆን፥ በዝምታ ( በጽሞና) ልናሰላስለው የሚገባን ድንቅ የመዳናችን ምሥጢር ነው።
ቤተ ክርስቲያን ስቅለቱን በየዓመቱ ስታከብር፥ የስቅለቱን ንባብ ካህኑ ካነበበ በኋላ ባለው የወንጌል መርገፍ ላይ « ጊዜ ተሰዓቱ ሰዓት ገዓረ ኢየሱስ በቃሉ ወወጽአት መንፈሱ ሶቤሃ፤ በዘጠኝ ሰዓት ኢየሱስ በታላቅ ድምጽ ጮኸ፤ ያን ጊዜም ነፍሱም ወጣች» ብሎ አሰምቶ በዜማ ይናገራል። ይህም ከማር ፲፭፥፴፯ ላይ ያለው ነው። ይህ ጩኸት የህመም ጩኸት ነው። ይህ ጩኸት የተራ እሩቅ ብእሲ ( ተራ ሰው) ጩኸት ስላይደለ ግን አባቶች እንደሚሉት፥ « ግዳጅ የሚፈጽም» ለቤዛነት የሆነ፥ ኃጢአትን የሚያስተሠርይ ለዘላለም የሆነ ጩኸት ነው።
፬ኛ. የሰውነቱንና የአምላክነቱን ሥራዎች እንዴት እንደምንናገር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የሰጠን ምክር
እዚህ ላይ፥ ቀሲስ ደጀኔ ትልቁ ስህተትህ መለኮት ገንዘብ ያደረጋቸውን የትስብእትን ሥራ በሚገባ ለይተህ ለመዘርዘር አለመቻልህ ብቻ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ የትስብእቱን ሥራ መካድህ እንደሆነ ደጋግሜ ተናግሬአለሁ ። ይህም አውጣኪን ወደ ስህተት የወሰደ መንገድ ዛሬም አንተን ወደ ከባድ ስህተት እየወሰደህ ነው።
በሰውነቱ የሠራቸውን ሥራዎች፥ በአምላክነቱ የሠራቸውን ሥራዎች እንዴት መናገር እንችላለን? እዚህ ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዕብ ፭፥፭ንና የመሳሰሉትን ኃይለ ቃላት በእንዴት ያለ መንገድ መተርጎም እንዳለብን የሰጠውን ምክር፥ ማለትም የቅዱስ ጳውሎስን አካሄድ በጥንቃቄ ያብራራበትን ብትይዝ ኖሮ ወደ ብዙ ስህተት አትገባም ነበር። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ አጻጻፍ ሲናገር እንዲህ ይላል ፦ « የጳውሎስ ልማድ አንድም ትምህርቱ እንዲህ ነው። የጌታን ልዕልናውን አንድም የአምላክነቱን ነገር ልናገር ባለ ጊዜ፥ (ይመጽእ ለኰንኖ ዓለመ) በዓለም ላይ ለመፍረድ ይመጣል አለ። ትህትናውን አንድም የሰውነቱን ነገር ልናገር ባለ ጊዜ ፥ (አብአ ጸሎተ ወስኢለ) ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤(ወሰምዖ ጽድቆ) ቁርጥ ልመናው ተሰማለት፤ ( ወሰመዮ ሊቀ ካህናት) ሊቀ ካህናት አድርጎ ሾመው፥ ( ወፈጺሞ ኮነ ዐሣዬ ሕይወት) ሁሉን ከፈጸመ በኋላ ሕይወትን የሚያድል፥ የዘላለም ሕይወት ሆነ አለ።»  ይህን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን የአተረጓጎም ስልት ብትይዝ ለወደፊቱም ከብዙ ስህተት ትድናለህ።


፭ኛ. አማለደ . . . ይማልዳል ስንል ምን ማለታችን ነው?
ስለ ክርስቶስ ምልጃ ስንነጋር ብዙ ጊዜ ከቅዱሳን ጸሎትና ልመና ጋር ስለሚያያዝ ልዩነቱን በግልጥ ለማስቀመጥ የሚከተሉትን ነጥቦች ማስቀመጥ አለብን። የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት የምንጠቅሰው የቅዱሳንን ጸሎትና በረከት ለመካድ ከሆነ እንግዲያውስ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት ፈጽሞ አልተረዳንም። እንዲሁ፥ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት የምንክደው የቅዱሳንን ክብር ያጎላን መስሎን ከሆነ ከባድ የሆነ ስህተት ውስጥ ወድቀናል። ሁለቱ ፈጽሞ የተለያዩ ናቸውና ። የሚከተሉትን ነጥቦች በጥንቃቄ ተመልከት።
አንደኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ፥ ክርስቶስ የእኛ ሊቀ ካህናት በመሆኑ የሚያከናውነው ነው። በሌላ አነጋገር ማላጅነቱ የትስብእቱ ( የሰውነቱ) ሥራ ነው።  እርሱ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል መካከለኛ ነው።መካከለኛነቱም ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑ ነው። የቅዱሳን ጸሎት፥ ከቅዱሳን ጋር ካለን ሕብረት ( communion of saints) የሚመነጭ ነው። በሰማያት ያለችው ድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን እና በምድር ያለችው አንድ ናትና። አባቶቻችን « እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ» እንዳሉ።
ሁለተኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ በደም የሆነ ነው። ማለትም ክርስቶስ ጸሎቱንና ምልጃውን ያቀረበው ራሱን መሥዋእት አድርጎ በማቅረብ ነው። ዓለምን ለማዳን የፈሰሰ ደም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። የእሩቅ ብእሲ ( የሰው ብቻ ደም) ዓለምን ስለማያድን፥ የፈሰሰው ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ የሆነ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። ከአቤል ጀምሮ እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ድረስ የፈሰሰው ደም አለምን አልጠቀመም። ዓለምን ያስታረቀው የምልጃ ደም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው። ሰማዕታት ደማቸውን ቢያፈሱ ለምስክርነት ነው። « ሰማዕታት ከዓዉ ደሞሙ በእንቲአሁ፤ ሰማዕታት ስለእርሱ [ ምስክርነት] ደማቸውን አፈሰሱ» እንደተባለ። የእርሱ ግን የመሥዋዕትነት ነው። የመታረቂያ ነው።
ሦስተኛ ፥ የክርስቶስ ምልጃ ለቤዛነት ነው። ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የታረቀበትና የሚታረቅበት ነው። ዛሬም በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት ነው። ቤዛ ማለት «ለውጥ፥ ምትክ» ማለት ነው። በእኛ ፈንታ ገብቶ የእኛን ጩኸት የጮኸልን ክርስቶስ ነው። የቅዱሳን ምልጃ ግን ወደ ክርስቶስ የሚደረግ ልመና ነው። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ እንደተናገሩት « The intercessions of the saints for us are merely praying for us; ቅዱሳን ስለ እኛ የሚማልዱት ስለ እኛ የሚጸልዩት ነው። they are of the pleading type, which is completely different to Christ’s atoning mediation» ይህ የቅዱሳን ጸሎት የልመና ዓይነት ሲሆን፥ ለኃጢአት ሥርየት ከሆነው የክርስቶስ መካከለኛነት ፈጽሞ የተለየ ነው» ይሉናል።
አራተኛ፥ የክርስቶስ ምልጃ እምቢ ያልተባለ አዎን አሜን የሆነ ነው። ክርስቶስ ያማረ ሽቱ አድርጎ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ በማቅረቡ አባቱ በደስታ ተቀብሎታል። ከስሞች ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ተቀብሎአል።
አምስተኛ የክርስቶስ ምልጃ አንድ ጊዜ ለዘላለም የሆነ ነው። በዕለተ አርብ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ባከናወነው እርቅ፥ ለዘላለም መታረቂያ ሆኖልናል። ዛሬ እንደገና ክርክር፥ ዛሬ እንደገና መውደቅና መነሣት አያስፈልገውም። መሥዋዕቱ ሞቶ የቀረ አይደለም። ሊቀ ካህናቱ ሞት የገደበው አይደለም። የታረደው በግ ዛሬም ሕያው ስለሆነ፥ ሊቀ ካህናቱም ለዘላለም በሕይወት ስለሚኖር፥ ወደ እርሱ የሚመጡትን ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው።
አለቃ አያሌው የተናገሩትን እዚህ ላይ እንደገና መድገሙ መልካም ነው። « እኔ ስለ እነሱ እለምናለሁ» ያለው ቃሉ ጊዜ የሚወስነው ሳይሆን እስከ አለም ፍጻሜ የሚሠራ ነው። ይህንንም « እኔ የምለምንህ ስለ እነዚህ ብቻ አይደለም። በቃላቸው ስለሚያምኑብኝም ጭምር ነው እንጂ ያለው ቃሉ ያጸናዋል። ዓለምን ሲፈጥር የተናገረው ቃሉ እስከ ዛሬ በመሥራት ላይ እንዳለ፥ እስከ ዓለም ፍጻሜ ሲሰራ እንደሚኖር፥ ይህም « እኔ ስለ እነሱ እለምናለሁ» ያለው ቃሉ እስከ ዓለም ፍጻሜ ሲሰራ ይኖራል። እንግዲህ ቅዱስ ጳውሎስ « እርሱ ቢያጸድቅ የሚኮንን ማነው? ሞቶ የተነሣው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በአብ ቀኝ ተቀምጦአል። ስለ እኛ ይከራከራል» ይላል። ( ሮሜ 8፥34) እንዲሁም « እነዚያን ብዙዎቹን ካህናት ሞት ይሽራቸዋልና ( ያልፋሉና) ለዘለዓለም አይኖሩም። እኔ ሕያው ነኝ ያለ እሱ ግን ለዘለዓለም ይኖራል። ክህነቱም አይሻርም። ፈጽሞ ሕያው ነውና ያስታርቃቸውማልና። በሱ አስታራቂነትም ወደ እግዚአብሔር ለሚቀርቡት ሁሉ ፍጹም ድኅነትን ሊሰጣቸው ይችላል። እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባናል። እውነተኛ የዋህ ከኃጢአት ሁሉ የራቀ፥ ንጹሕ ከሰማየ ሰማያት የመጠቀ» ያለ ስለዚህ ነው። እስከ ዓለም ፍጻሜ በመሥዋዕትነት በሚቀርብባት በቤተ ክርስቲያን ሲሠራ የሚኖር የማያቋርጥ ኃይል ነውና። ዕብ 7፥23_26) እንግዲህ ጌታ « አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ህልቀተ ዓለም፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ» ( ማቴ 28፥20) ሲል በተናገረው ቃል መሠረት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን በምታስተምርበት መልእክቱን በምታስተላልፍበት ጊዜና ሥፍራ ሁሉ የሚረዳት፥ በልዩ ልዩ አደባባይም የሚከራከርላት መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ በጻፈው መእክቱ « ይትዋቀስ በእንቲአነ» ስለ እኛ ይከራከራል ብሎ እንደጻፈ፥ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር አምላኪየ ናሁ ወልድከ መሥዋዕት ዘያሰምረከ ወበዝንቱ አናህሲ ሊተ ኵሎ ኃጢአትየ» እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ አንተን ደስ የሚያሰኝህ መሥዋዕት ልጅህ እነሆ፤ በዚህም ኃጢአቴን አስተስርይልኝ» እያለች መሥዋዕቷን በምታቀርብበት ጊዜ ሁሉ « ወአንሰ በእንቲአሆሙ እስዕል» ያለው ቃሉ ስለሚረዳቸው ለዘለዓለም ሕያው ነውና ይማልድላቸዋል» ብሎ ጻፈ።»
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « ጌታችን አምላካችን መድኃኒ ታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡-በመዋዕለ ሥጋዌው(በተዋህዶ ሰው በሆነበት ዘመን) ለአብነት(ምሳሌ ሊሆነን) ያደረገውንና ለድኅነታችን ብሎ የፈጸመውን መለ የት ያስፈልጋል። ብዙዎች እነዚህ ሁለት ነገሮች እየተደባለቁባቸው ነው፥“ዛሬም ያማልዳል፤” የሚሉት።ጌታችን አምላካ ችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡-እከብር አይል ክቡር፥እጸ ድቅ አይል ጻድቅ ሲሆን፡-የጾመው፥የጸ ለየው፥የሰገደው፥ለእኛ፡-አብነት(ለበጎ ነገር ሁሉ አርአ ያና ምሳሌ) ሊሆነን ነው። ለምሳሌ፡-አልዓዛርን ከማ ስነሣቱ በፊት ወደ አብ ከጸለየ በኋላ፡-“ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ፤”ብሎአል። ከዚያ በፊት የኢያኢሮስን ልጅ፡-ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንዲት በሆነች ሥልጣኑ አስነሥቶአል። ጥምቀታችንን በጥምቀቱ ቀድሶ የሰጠን፥ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንድንጠመቅም ያዘዘን፥ሕገ ወንጌልን የሠራልን፥ኅብስቱ ተለውጦ ሥጋ መለኮት፣ደሙም ተለውጦ ደመ መለኮት የሚሆ ንበትን ሥርዓተ ቍርባን ሠርቶ ያሳየን ፥ምሥጢሩንም በመስቀል ላይ የፈጸመልን ለድኅነታ ችን ነው።» ብለሃል
ይህ ያስቀመጥከው ቃል በቤተ ክርስቲያናችን ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ ትምህርት ነው። የምትጽፋቸውን ጽሑፎች ስመለከት ሁለት አደገኛ የሆኑ ሐሰተኛ የመከራከሪያ መንገዶችን ትጠቀማለህ። የመጀመሪያው የማከፈለውን የማይለያየውን መለያየት ( false dichotomy) ነው። ሁለተኛው ደግሞ ፥ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያላሉትን እንዳሉ አድርጎ በማቅረብ ( false premise) ፥ በዚያ ላይ የቅዱሳት መጻሕፍትን ማስረጃ ማቅረብ ነው።

በመጀመሪያ ደረጃ ጌታ ከጽንስ እስከ እርገት ያደረጋቸው ነገሮች በሙሉ ለቤዛነት ለደኅንነታችን ያደረጋቸው ሥራዎች ናቸው።  እነዚህ የቤዛነት ሥራዎች  ደግሞ አብነትም ሆነውናል።  ለምሳሌ ጾሙን፥ ጸሎቱን ስግደቱን ለአብነት እንደሆነ ተናግረህ፥ በመስቀሉ የተከናወነው ግን ለድኅነታችን እንደሆነ ተናግረሃል። ይህ ፍጹም ክህደት ነው። በመስቀሉ ላይ የተከናወነው ለደኅንነታችንም ለአብነታችንም መሆኑን ሲገልጥልህ፥ ቅዱስ ጴጥሮስ « የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና። እርሱም ኃጢአት አላደረገም፥ ተንኰልም በአፉ አልተገኘበትም፤ ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤» ብሎአል። ፩ ጴጥ ም. ፪፥፳፩
ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነው፥ « የጾመው የጸለየው የሰገደው ለእኛ አብነት ነው» በማለት በጾሙና በጸሎቱ ውስጥ ያለውን  የቤዛነቱን ሥራ ሙሉ በሙሉ ወደጎን ማድረግህ ነው። ቅዱሳት መጻሕፍትም የአበው ትርጓሜዎችም የጸለየው ወደ አብ መሆኑን ተናግረዋል። በመስቀል ላይ « የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ የጸለየው ለአብነት ለምሳሌ ብቻ ነውን? ይህን ከቶ ከየት አመጣኸው? በጾሙ ቢያስተምረንም፥ በዚያው በጾሙ ደግሞ ዲያብሎስን ድል ነስቶልናል። ጾሙ የምሳሌ ብቻ አይደለም። የቤዛነትም ነው።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያከናወነው ሥራው ብቻ ሳይሆን፥ ቃሉም ትምህርቱም ሥራውም የቤዛነት እንደሆነ፥ ይህም እስከ አለም ፍጻሜ እንደሚሠራ፥ አለቃ አያሌው ሲናገሩ፥ « እኔ በምድር ላይ ልሠራው የሰጠኸን ሥራ ፈጽሜ አከበርኩህ አሁንም አንተ አባት ሆይ ዓለም ሳይፈጠር ከአንተ ጋር በነበረኝ ክብር ግለጠኝ» በማለት ጌታችን ወደዚህ ዓለም ከመምጣቱ አስቀድሞ ወደነበረበት ካረገ በኋላ ምእመናን ኃይሉን፥ ጌትነቱን፥ ምልዓቱን፥ ስፋቱን፥ ርቀቱን፥ ጥንታዊና ዘለዓለማዊነቱን ለማወቅ ችለዋል። ተአምራት ብቻውን አይረዳም፤ ኃይል ካልተሰጠው በቀር። ከሙሴ ጀምሮ ብዙ ነቢያት ተአምራት ሲያደርጉ ኖረው አልፈዋል። ሥራቸውም ታሪክ ሆኖአል። ሠርተዋል፥ ሠርተው ነበር በማለትም ተወስኖአል። የጌታ ሥራ ግን ቃሉም ሥራውም ለዘላለም እንዲሆን እስከ ዓለም ፍጻሜም እንዲሠራ የተነገረና የተደረገ በመሆኑ በመዋዕለ ስብከቱ ብቻ ታይቶ የቀረ፥ ተሰምቶ ያለፈ አይደለም።»  ካሉ በኋላ « ከዕለተ ጽንስ እስከ ዕለተ ዕርገት የፈጸመው የቤዛነት ሥራ በየጊዜው የተነሡ ምዕመናን ወደ እግዚአብሔር ሊያቀርባቸው  ፍጹም ድኅነት ሊሠጣቸው ይችላል።»
መደመደሚያ፤ ምልጃ ለምን አስቸጋሪ ሆነ?
ባለፉት ሦስት ተከታታይ ጽሑፎች ቀሲስ ደጀኔ የገባበትን ስህተቶች ለማሳየት ሞክሬአለሁ። በዚህም ውስጥ እግዚአብሔር ወልድ በሰውነቱ ያከናወናቸው ሥራዎች ለድኅነታችን ወሳኝ የሆኑ ሥራዎች ስለሆኑ ስለእነዚህ ነገሮች ስንናገር በግዴለሽነት ልንናገር እንደማይገባ አመልክቼአለሁ። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ እንደተናገሩት እኛ ክርስቶስን « አንድ ባሕርይ » ስንል የሚያስረዳው ፍጹም የሆነ ተዋህዶን ነው እንጂ የአምላክነትና የሰውነት መቀያየጥና መደባለቅ አይደለም። አምላክነቱ ወደ ሰውነቱ አልተለወጠም፤ ሰውነቱም ወደ አምላክነቱ አልተቀየረም። በኦርቶዶክሳውያኑ እና በአውጣኪ መካከል የነበረው ትልቅ ልዩነት ይህ ነው። አውጣኪ የቄርሎስ ጠበቃ እንደሆነ አድርጎ ራሱን ቢያስቀምጥም፥ ለቄርሎስ « አንድ ባሕርይ» ማለትና ለአውጣኪ አንድ ባሕርይ ማለት የተለያየ ነበር። ለቄርሎስ አንድ ባሕርይ ማለት ክርስቶስ በፍጹም ተዋህዶ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው እንደሆነ ነው። በዚህም ተዋህዶ ያለመቀላቀል እና ያለመደባለቅ የቃልና የትስብእት መገናዘብ ስላለ፥ መከፈልና መለየት የለም። ለአውጣኪ ግን እንዲህ « አንድ ባሕርይ ሲል ትስብእትንና መለኮትን አንድ ላይ አጣፍቶ ነው። በመሆኑም ለእርሱ የሰውነቱን ነገር ለመናገር ቋንቋ የለውም።




ይህን ባለፉት ሦስት ክፍሎች በተነተንነውና መልስ በሰጠንበት የቀሲስ ደጀኔ ጽሑፎች ውስጥ በግልጥ አይተነዋል። ኢየሱስ ክርስቶስ በላ፥ ጠጣ፥ ማለደ፥ ጸለየ ለቀሲስ ደጀኔ ስድብ ነው። ምክንያቱም እንዴት አምላክ በላ ይባላል። እንዴት አምላክ ጸለየ ይባላል። እውነቱን ነው። የረሳው ግን ያ አምላክ የእኛን ባሕርይ ገንዘብ አድርጎአል። በመሆኑም በልቷል፥ ማልዷል፥ ጸልዮአል። አንቀላፍቷል። ሞቶአል። በሰውነቱ።
በአሁኑ ወቅት ጥቂቶች ያይደሉ፥ ራሳቸውን ሰባኪና ሊቅ ያደረጉ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን መድረክ ላይ ሆነው የሚናገሩትና ትምህርት ብለው የሚያቀርቡት ነገር፥ አንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን የማታውቀው ትርኪ ምርኪ ሲሆን ፥ አንዳንዱ ደግሞ የለየለት ፍጹም ክህደት ነው።
ለምሳሌ በቅርቡ አንዱ በአውደ ምሕረት ላይ ቆሞ በሥነ ሥርዓት የሰበከው እንዲህ ይላል። « ተአምረ ማርያም ከሌለ፥ ማርያም የለችም፥ ማርያም ከሌለች፥ ክርስቶስ የለም፥ ክርስቶስ ከሌለ ሥላሴ የለም፤ ሥላሴ ከሌለ እግዚአብሔር የለም።» ይላል። ይህ የኑፋቄ ሁሉ ኑፋቄ ነው። ይህ ሰባኪ እንዲህ ብሎ የሰበከው፥ ነገር አሳምራለሁ፥ የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት የማይቀበሉ ሰዎችን እቃወምበታለሁ ብሎ ነው።  ነገር ግን ያስተማረው ሀልዎተ እግዚአብሔርን ገደል የከተተ ትምህርት ነው።
ታዲያ ብዙዎቹ ወደዚህ ዓይነት ክህደት ውስጥ የሚገቡት ትምህርታቸውን ቤተ ክርስቲያኒቱ ባስቀመጠችው ቀዋሚ ትምህርት ላይ ስለማይመሠርቱና  ፕሮቴስታንቶችን ወይም ሌሎች የእምነት ድርጅቶችን በማየት እምነታቸውን ለመቅረጽ ስለሚሞክሩ ነው።
ለምሳሌ አንዳንድ ፕሮቴስታንቶች የቅዱሳንን ጸሎትና ምልጃ በመካድ የሚጠቅሱት ሮሜ 8፥34ን፥ ዮሐ 2፥1ን ነው። እነዚህ ንባቦች ክርስቶስ ለእኛ አስታራቂያችን፥ ተከራካሪያችን ጠበቃችን እንደሆነ የሚገልጡ ንባቦች ናቸው። ታዲያ ጥቂት ያይደሉ የኛዎቹ መልስ ሰጪዎች የሚያደርጉትና እያደረጉ ያሉት፥ አንደኛ ሙሉ በሙሉ የክርስቶስን ማስታረቅ፥ምልጃውን፥ ጠበቃነቱን መካድ፥ ከዚያ አልፎ ደግሞ እነዚህን ምንባቦች ለመቀየር ወይም ለማደብዘዝ መሞከር ነው። ይህ በእግዚአብሔር ቃል ላይ የሚሠነዘር ወንጀል ነው።
ማድረግ ያለብን ምን ነበር ? ማድረግ ያለብን ፥ የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት፥ የክርስቶስን መካከለኛነት መካድ ሳይሆን በክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት እና በቅዱሳን ጸሎት መካከል ያለውን ልዩነት ማሳየት ነው፤   የክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት መዳናችን የተመሠረተበት ታላቅ ምሥጢር ነው። በግዴለሽነት ወደጎን የምናደርገው አይደለም። ለድርድርም የሚቀርብ አይደለም።

የክርስቶስ የማስታረቅ ሥራ ከፍጡራን የልመና ጸሎት ፍጹም የተለየ ነውና። ከዚህ በፊት በሌሎች ጽሑፎቻችን ላይ የጠቀስነው ቢሆንም ሊቀ ሊቃውንት አባ መልአኩ ታከለ የተናገሩትን እንደገና እንጥቀስ ፥ « ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅም፥ ጳውሎስን አራቂ ዘውእቱ አምሳሊሁ ለክርስቶስ፤ በክርስቶስ አምሳል አስታራቂ ( አማላጅ) ነው ብሏል የክርስቶስ አራቂነት በሞቱ ሲሆን የጳውሎስ ግን በጸሎቱና በትምህርቱ። ስያሜው በመገናኘቱ ምንም አያስደንቅም ተግባሩ የተለያየ ነውና ከዚህ የተነሳ ትምህርቱን መመለክቱ ተገቢ ነው። ይህን ለመረዳት የቤተክርስቲያንን ትምህርት ማወቅ ያስፈልጋል።» ብፁዕ አቡነ ሽኖዳ ያሉት ይህን ነው።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳም ለፕሮቴስታንቶች በሰጡት መልስ የቅዱሳንን ምልጃ እና የክርስቶስን ምልጃ ለይተው በሁለቱ መካከል ያለውን ልዩነት ሲያብራሩ በመጥቀስ ጽሑፋችንን እንደምድም። በነገራችን ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ ከክርስቶስ ምልጃና መካከለኛነት ጋር አዛምደው የጠቀሱአቸውን ንባቦች በጥንቃቄ ተመልከቱ እና የዘመናችን አውጣኪዎች እንዴት እንደሚክዷቸውና ለመቀየር እንደሚሞክሩ አስተውሉ። ከ
The mediation of the Lord Jesus Christ is an atonement, which means that He mediates for the forgiveness of our sins, being the Atoner who paid our debts on our behalf. His mediation means that He says to the Father: “Do not count their transgressions because I have carried their iniquity” (Is.53: 6). Thus He stands as a Mediator between God and men; or rather, He is the only Mediator between God and men; He fulfilled God’s Divine Justice and granted people the forgiveness of sins, by dying for them.
የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ፥ ለኃጢአት ሥርየት ( atonement) ነው። ይህም ማለት፥ ስለ እኛ ዕዳችንን የከፈለ ማስተስረያ በመሆን፥ ለኃጢአታችን ይቅርታ መማለዱ ነው። የእርሱ ምልጃ ማለት፥ ለአባቱ « አባት ሆይ በደላቸውን አትቁጠርባቸው፤ ምክንያቱም በደላቸውን እኔ ተሸክሜአለሁ» ማለቱ ነው። ( ኢሳ ፶፫፥፮) በመሆኑም፥ እርሱ በሰዎች እና በእግዚአብሔር መካከል መካከለኛ ሆኖ ቆሞአል። ወይም በሰዎችና በእግዚአብሔር መካከል ብቸኛው መካከለኛ ነው። እርሱ ስለ ሕዝቡ በመሞት፥ የእግዚአብሔርን ፍትሕ ያረካና ለሕዝቡ የኃጢአት ሥርየትን የሰጠ ነው። This is what St. John the Apostle mea
nt when he said: “And if anyone sins, we have an Advocate with the Father, Jesus Christ the righteous. And He Himself is the propitiation for our sins, and not for ours only but also for the whole world”(1John.2: 1,2). Here, the atoning mediation is very clear. It is a mediation for the sinner: “If anyone sins”, and this sinner needs atonement. The only One who offered this atonement was Jesus Christ the righteous. Hence He can mediate for us through His blood which was shed for us.
ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ «ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።እርሱም የኃጢአታችን ማስተስሪያ ነው፥ ለኃጢአታችንም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኃጢአት እንጂ።»  በማለት የተናገረው ይህን ነው ፩ ዮሐ ፪፥፩፡፪። በዚህ፥ የማስተሥረያ መካከለኛነቱ ግልጥ ነው። መካከለኛነቱ ለኃጢአተኛ ነው። « ማንም ኃጢአት ቢያደርግ»፤ ይህ  ኃጢአተኛ የኃጢአት ሥርየት ያስፈልገዋል። ይህን የኃጢአት ማስተስሪያ ማቅረብ የሚችል ጻድቅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። በመሆኑም እርሱ ስለ እኛ ባፈሰሰው በደሙ በኩል ይማልድልን ዘንድ ይችላል።

The same meaning is given in the words of St. Paul the Apostle about the Lord Jesus Christ being the only Mediator between God and men. He says: “For there is one God and one Mediator between God and men, the Man Christ Jesus, who gave Himself a ransom for all” (1Tim.2: 5,6). The Lord Jesus Christ mediates for us as the Redeemer who sacrificed Himself and paid the price of our sins. This type of mediation is utterly unquestionable. It is attributed to Christ only, whereas the intercessions of the saints has no connection with atonement or redemption. It is intercessions for us to the Lord Jesus Christ Himself.
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ብቸኛው መካከለኛ ስለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውም ተመሳሳይ ትርጕም አለው። «አንድ እግዚአብሔር አለና፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ፥» ፩ ጢሞ ፪፥፭፡፮። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛ የሚሆንልን፥ ራሱን መስዋዕት ያደረገና የኃጢአታችን ዋጋ የከፈለልን ቤዛ ሆኖልን ነው። እንዲህ ዓይነቱ መካከለኛነት ጥያቄ ውስጥ የማይገባ ነው። የሚሰጠውም ለክርስቶስ ብቻ ነው። የቅዱሳን ምልጃ በአንጻሩ፥ ከቤዛነት ( redemption) እና ከኃጢአት ማስተስሪያ ( atonement) ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። የቅዱሳን ምልጃ ስለ እኛ ወደ ራሱ ወደ ጌታ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የመለመን ነገር ነው።» በማለት አብራርተው ተናግረዋል።
እኛም በዚሁ ለቀሲስ ደጀኔ የሰጠነውን መልስ እንደመድማለን። ይህን እንድንጽፍና ስለ እምነታችን እንድንመሰክር አቅምና ጉልበት የሆነን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይክበር ይመስገን።