Wednesday, January 2, 2013

አቡነ አብርሃም ቃለ ዐዋዲን ጥሰው ሕገ ወጥ ሥራ እንዲሠራ ትዕዛዝ አስተላለፉ!

 በአዲስ አበቤው ካህን ዘንድ «የጉድ ሙዳይ» የሚል ስመ ተጸውዖ አላቸው። በየሄዱበት የራሳቸውንና የማቅን ስርወ መንግሥት ማደራጀት ተቀዳሚ ተግባራቸው ነው። ከአሜሪካ ተነስተው ሐረር ከወረዱ አንስቶ እንደ በቆሎ የሚጠብሱት የሐረር ምእመናንና ካህናት ፍዳውን እያየ ነው። ከብዙ ወሰን አልባና ጠያቂ የለሽ እርምጃዎቻቸው መካከል በ /www.deselaam-dejeselaam.blogspot.com/ ያገኘነውን  መረጃ፤ አካፍለናችሗል።። መልካም ንባብ!

በሐረር መድኃኔዓለም ደብር አስተዳዳሪ ላይ ሥልጣነ ክህነት እስከመያዝ የሚያደርስ እርምጃ እንደሚወስዱ አስጠነቀቁ
የዘረኝነት መንፈስ የተጠናወታቸው አቡነ አብርሃም ከጉርሱም ያመጡትን ጎጃሜ የቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ነፃነትን የሐረር መድኃኔዓለም ስብከተ ወንጌል ኃላፊ ሆኖ እንዲመደብ አስገዳጅ ትዕዛዘ አስተላለፉ፡፡ ሊቀጳጳሱ ይህንን ትዕዛዝ ከማስተላለፋቸው በፊት በዓመታዊው የቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ላይ ለመገኘት ወደ ቁልቢ የሄዱ ሲሆን ወደ ሐረር እስከሚመለሱ አላደርስ ብሏቸው ካሉበት ሆነው የመድኃኔ ዓለም አስተዳዳሪውንና የሰበካ ጉባዔው ምክትል ሰብሳቢውን ጠርተው ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል፡፡
ለማስጠንቀቂያው የተጠቀሰው ዋና ምክንያት የደብሩ ሰበካ ጉባዔ በውስጥ ካሉት ካህናት መካከል በማስታወቂያ አወዳድሮ መመደቡ ሲሆን፣ ደብሩ ይህንን ሽሮ የሥራ መደቡን ለጉርሱሙ የራጉኤል ደብር አለቃ ክፍት አድርጎ ለምን አልተቀበላቸውም የሚል ነው፡፡ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤቱ የደብሩን ስብከተ ወንጌል ኃላፊ ቀሲስ ፋሲል አጥናፉን በዕድገት ወደ ራሱ ጽ/ቤት ስብከተ ወንጌል ክፍል ሲወስድ በተፈጠረው ክፍት መደብ ላይ የደብሩ ሰበካ ጉባዔ አወዳድሮ መቅጠሩ በአቡነ አብርሃም ዘንድ እንደ ጥፋትና ድፍረት ተቆጥሯል፡፡
ቃለ ዐዋዲው የደብሩ ሰበካ ጉባዔ ከካህናት መካከል አወዳድሮ በደብሩ ስብከተ ወንጌል ኃላፊነት የሥራ መደብ ላይ የመመደብ ሙሉ ሥልጣን ያለው ሲሆን የተመደቡት ካህንም ሙሉ መስፈርቱን አሟልተው ዕድገቱን እስካገኙ ድረስ አቡነ አብርሃም በሥራ አስኪያጃቸው በኩል ይህንኑ ተቀብለው ማፅደቅ ነበረባቸው፡፡ ይሁን እንጂ፣ እርሳቸው ይህንን በጉልበት ሽረው "የጉርሱሙን አስተዳዳሪ ተቀበሉ"! ብለው ትዕዛዝ ሲያስተላልፉ በየትኛው ማስታወቂያ አወዳድረው እንደቀጠሩ ሲጠየቁ "ዕወቅ እንጂ፣ አትመራመር" በሚል አምባገነናዊ አስተሳሰብ ያሻኝን አደርጋለሁ በሚል ስሜት ቀጭን ትዕዛዝ በማስተላለፍ ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የጉርሱሙ የደብር አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ነፃነት ወደ ሐረር መድኃኔዓለም ደብር ስብከተ ወንጌል ኃላፊነት መደብ ተዛውረው ሲመጡ የሽረት(የዝቅታ) ያህል ነው፡፡ "አቡነ አብርሃም ለሰውዬው ካዘኑላቸው ለምን እዚያው ሀገረ ስብከት ጽ/ቤቱ ውስጥ ቦታ አልፈለጉላቸውም"? ብለው ብዙዎች ይጠይቃሉ፡፡ ነገር ግን አቡነ አብርሃምም ሆኑ አስተደሳዳሪው ያንን መደብ ለመያዝ የቋመጡበት ምክንያት በይፋ ባይታወቅም፣ ቤተክርስቲያንን በጎጃሜዎች ለመሙላት እና እግረ መንገድም አድባራትንና ገዳማትን በ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባላት ለማስያዝ  ነው ሲሉ ብዙዎች አስተያየት ይሰጣሉ፡፡


አቡነ አብርሃም ይህንን ፍላጎታቸውን ለማሟላትም ቁልቢ ሆነው የመድኃኔዓለም አስተዳደሪውንና ምክትላቸውን የጠሩ ሲሆን ተጠሪዎቹ ይህንን የጉርሱም አስተዳዳሪ ተቀብለው የማይመድቡ ከሆነ በተለይ የአስተዳዳሪውን ሥልጣነ ክህነት በመያዝ ከደመወዝና ከሥራ እንደሚያሰናብቷቸውና አልከስክሰው እንደሚያስቀሩአቸው የዛቱባቸው መሆኑን በዚያ የነበሩ እማኞቻችን ገልጸውልናል፡፡
ይህም ብቻ ሳይሆን፣ የትም ቢሄዱ ሰሚ ሳያገኙ ለፍተው ብቻ እንደሚቀሩ፣ "ከላይ እስከ ታች እኛው ነን የምንወስነው፣ ላይ ብትሄዱም ከእኛ አትወጡም"፤ በማለት ማስፈራራታቸው ተገልጿል፡፡ ከዚያም በመቀጠል ተጠሪዎቹን "ወደ ደብራችሁ ተመለሱ ደብዳቤ እልካለሁ" ያሏቸው ሲሆን ሰዎቹ ወደ ደብራቸው ከተመለሱ በኋላ አቡነ አብርሃም አከታትለው ደብዳቤ ጽፈዋል፡፡ የደብዳቤው ፍሬ ነገርም ከደብሩ ሰበካ ጉባዔ ጋር በተስማማነው መሠረት መልአከ ምሕረት ነፃነት የመድኃኔዓለም ስብከተ ወንጌል ክፍል ኃላፊ ሆነው የተመደቡ መሆኑን አስታውቃለሁ የሚል ትዕዛዝ መሆኑ ምንጮቻችን አረጋግጠዋል፡፡ ጠያቂ ቢኖር አቡነ አብርሃም ከየትኛው ሰበካ ጉባዔ ጋር ተስማምተው እንደመደቡ "ቃለ ጉባዔውን አሳዩ" ቢባሉ ዓይናቸው ይፈጥ ነበር፡፡
አቡነ አብርሃም በዚህ ብቻ ሳይወሰኑ የቅዱስ ሚካኤልንና የመድኃኔዓለም ካህናትን የተሐድሶ ጥርቅም በማለት መዝለፋቸው እምብዛም በማያውቋቸው ካህናት ዘንድ ያስናቃቸው ሲሆን፣ ይህንን ቃል በትዕቢት የሰነዘሩት በማንአለብኝነት በ"ማኅበረ ቅዱሳን" የተሰጣቸውን የቤት ሥራ ለመወጣት ነው ተብሏል፡፡ ይህ አስተያየታቸውና አመለካከታቸው በሁሉም አጥቢያዎች ባሉ አገልጋዮች ዘንድ ቁጣ መቀስቀሱ ታውቋል፡፡
ሊቀጳጳሱ ወደ ሀገረ ስብከቱ ከሄዱበት ጊዜ ጀምሮ ሰበካ ጉባዔዎችንና አገልጋዮችን ሰብስበው "ምን ችግር አለባችሁ" ብለው መፍትሔ ከመፈለግና ከመማከር ይልቅ አዲስ አበባ ላይ ቁጭ ብለው "ይህንን አውርዱ፣ ያንን አውጡ" በማለት በቀጭን ትዕዛዝ ማሽቆጥቆጥ አስተዳደራዊ ፈሊጣቸው መሆኑ ይነገራል፡፡ ከዚህም በላይ "ደብዳቤ ስትጽፉ የቃለ ዐዋዲም ሆነ የፍትሐ ነገስት አንቀጽ አትጥቀሱ" በማለት የሚያስጠነቅቁ መሆናቸው ታውቋል፡፡