Tuesday, August 28, 2012

ሚዲያ ጥሩና ሌላ ዐቃቤ መንበር ሹሙ! ብጹእ አቡነ ናትናኤል

   ድግሷ እንዳማረላት የሴት ወይዘሮ የቤተክህነቱን ወጥ የሚወጠውጠው ማኅበረ ቅዱሳን ነገሮች ሁሉ እንዳሰበው  ሊሄዱለት እንዳልቻሉ ሁኔታዎች እያመላከቱ  ናቸው። መንፈስ ቅዱስን በስም እንጂ በእምነት የማያውቀው ማኅበር ሲኖዶሱ በመንፈስ ቅዱስ ይመራናል እያለ፤ የራሱን ዓላማና ግብ ለማስፈጸም ባሰባሰበው የሰሞኑ ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ  ፍትጊያውና ሩጫው ያላማራቸው ዐቃቤ መንበር አቡነ ናትናኤል ፤ እኔ በስተርጅና ስምና ክብሬን አዋርጄ፤ ቤተክርስቲያንንም ለማንም መጫወቻ እንድትሆን አሳልፌ ሰጥቼ ታሪኬን አላበላሽም፤ ነገረ ሥራችሁም ደስ አላለኝም በማለት ዐቃቤ መንበርነቱን ተረከቡኝ ብለው ጉባዔውን ትተው መውጣት ከጀመሩ በኋላ በእድሜ የገፉ አባቶች ባቀረቡላቸው ልመናና ተማጽኖ ለመመለስ ችለዋል። 

ወጣቶቹ ጳጳሳት 7ቱ ኮሚቴዎች የምንመራበት የራሳችንን አዲስ ሕግ እናውጣ፤ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ካህናትንም ለስብሰባ እንጥራ በማለት ማስቸገራቸው የተሰማ ሲሆን በብጹእ አቡነ እስጢፋኖስ በኩል ተሰጣቸው የተባለው መልስ እንደሚያስረዳው ሕግን በተመለከተ ከሲኖዶስ ሕግ ውጪ ዛሬ የምናወጣው ሕግ አይኖርም፤ አዲስ አበባ ሀ/ስብከትም  የራሱ ሊቀጳጳስ እያለው ጣልቃ በመግባት የካህናት ስብሰባ እኛ ማድረግ አንችልም በማለታቸው  የእነ አቡነ ነደ እሳት ጥያቄ ተቀባይነት ሳይኖረው ቀርቷል። በእድሜ የገፉትን እኒህን አባት ዐቃቤ መንበር ማድረግ ያስፈለገው እንዳሻን እንነዳቸዋለን፤ እየጠመዘዝን እንሰራለን ከሚል የሥጋዊ አእምሮ ስሌት የነበረ ቢሆንም ለጊዜው አቡነ ናትናኤል አይተው የማያውቁት ሩጫና ግርግር አስደንግጧቸዋል።  ደጀ ብርሃን ብሎግ  «የፓርትርያርክ የምርጫ ግርግር ለማኅበረ ቅዱሳንና ለወዳጅ ጳጳሳት ጥቅም እንዳይውል ያስፈራል!» በሚል ርእስ ያወጣችው ጽሁፍ በተግባር እየታየ መሆኑን አመላካች ነው።  በሌላ መልኩም አቡነ መልከ ጼዴቅ ከወደ አሜሪካ በአቡነ ጳውሎስ እረፍት ላይ ውግዘታቸው ሳይነሳ የሞቱ መሆናቸውን በመናገራቸው  መሳሳብ ማስከተሉ ተነግሯል። ሁለቱም ወገን መወጋገዛቸው አይካድም። የውስጥና የውጪው ሲኖዶስ የተወጋገዙት ቃል ሳይፈታ አቡነ ጳውሎስ ማረፋቸውም እውነት ነው። እንደእኛ እምነት አሁንም ቢሆን ለእርቁ መንገድ እንዲሆንና እንደተወጋገዙ ሌሎች አባቶችም በመሐል በሞት እንዳይለዩ ከሁሉም ቅድሚያ ውግዘቱን ማንሳት አለባቸው እንላለን። ወንጌሉም የሚለው ይህንኑ ነው። ሉቃ 1126 እናንተ ግን ይቅር ባትሉ በሰማያት ያለው አባታችሁም ኃጢአታችሁን ይቅር አይላችሁም።
ከዚህ አንጻር የአቡነ መልከ ጼዴቅ ተወጋግዘን በሞት ተለያየን የሚለው ቃል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ እንጂ እንደስህተት ቃል ማስተባበያ የሚያስፈልገው አይደለም። እንደተወጋገዙ በሞት መለያየት ጥሩ ነው የሚል ይኖር ይሆን?
ለቀሪ መረጃ የዓውደ ምሕረትን ዘገባ እነሆ ብለናልና መልካም ንባብ ይሁንላችሁ።

 awdemihret.blogspot.com// awdemihret.wordpress.com)
ባለፈው ሳምንት ሐሙስ የቅዱስነታቸው የቀብር ሥነ ስርዓት ከተፈጸመ በኋላ በነጋታው ሲኖዶሱ ወደ መደበኛ ሥራው ተመልሷል። ከተመለከታቸው ጉዳዩች አንዱም የእርቁ ሁኔታ ነበር። የቅዱስነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ቀን ማታ አቡነ መልከ ጼዴቅ ቅዱስነታቸው ተወግዘው ነው የሞቱት ብለው መናገራቸው የእርቁን ሀሳብ አደጋ ላይ ጥሎታል።
አርብ ዕለት በነበረው ስብሰባ የእርቁ ሀሳብ ሲነሳ በርካታ ጳጳሳት የአቡነ መልከጻዲቅን ንግግር ማዘናቸውን ገልጸዋል። በተለይም የአቡነ እስጢፋኖስ አቋም ጠንካራ እና የሁሉንም ልብ ማሸነፍ የቻለ ነበር። ብጹዕነታቸው ሲናገሩቀብቶ የሾመን ተወግዞ ሞተ ከተባለ እኛም የተወገዝን ነን ማለት ነው። ስለዚህ የምን እርቅ ነው የሚደረገው? እኛ የእርቅን ሀሳብ መነጋገር ከጀመርን ጀምሮ ከቅዱስነታቸው ጀምሮ ሁላችንም ስለ እነርሱ መወገዝ አንስተን አናውቅም። ምክንያቱም እርቅ የሚመጣው ያሉበትን አቋም ትቶ ነው እንጂ የወሰድኩት አቋም አይለወጥም ብሎ አይደለም። ስለዚህ ቅዱስነታቸው ሲያርፉ መነሳት የሌለበትን ርዕስ አቡነ መልከጻዲቅ ሰላነሱ በአደባባይ የተናገሩትን ንግግራቸውን በአደባባይ እስካላስተባበሉ ድረስ የእርቅ ሀሳብ አይኖርምበማለት በአጽንኦት ተናግረዋል። ይህንንም ሀሳብ አብዛኛዎቹ ጳጳሳት ተቀብለውታል።


   ከዚህም ጋር ተያይዞ አቡነ ሳሙኤል አቡነ ሉቃስ እና አቡነ ህዝቅኤልየስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስለሆንን የአዲስ አበባ አድባራትን አስተዳዳሪዎችን እና የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞችን ሰብሰብን ማናገር አለብን።በማለታቸው በብዙሀኑ ዘንድ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።የጠቅላይ ቤተክህነቱን ሰራተኞች ማነጋገር ጠቅላይ ስራ አስኪያጁ ስራ ነው የአዲስ አበባ አድባራትን እና ገዳማትን ስራ አስኪያጆች ማናገር የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ሥራ ነው። ያለስራችሁ አትግቡ።ተብለዋል።  የቀድሞውንም ቢሆን ይህ ጊዜያዊ ኮሚቴ የተቋቋመበት አላማ የአቃቤ መንበሩ እና የጠቅላይ ሥራ አስኪያጁን ስራ ተረክቦ ሁሉቱንም ከጨዋታው ውጭ የማድረግ አላማ ይዞ ስለነበር አላማውን ለማስፈጸም አንድ እርምጃ ያደርሰኛል ይወስደኛል ብሎ ያሳበውን ሀሳብ ቢያቀርብም የኮሚቴው አባል የሆኑት አቡነ እስጢፋኖስ ጉዳዩን መቃወማቸው እነ አባ ሳሙኤልን አስደንግጧቸዋል። ይህ አካሄድ ከተሳከ በመዋቅሩ በኩል ያለውን የስራ አስኪያጁን እና የአቃቤ መንበሩን ግንኙነት ሙሉ በሙሉ በማጥፋት ሁሉቱንም ሥራ አና ግንኙነት አልባ አድርጎ ያስቀምጥ እንደነበር ታዛቢዎች ተናግረዋል። ሁለቱ ደግሞ ተገናኝተው የማይሰሩ ከሆነ ስራው በግል ኮሚቴዎች በትክክል ሊሄድ እንደማይችል የታወቀ ነው። ይህ ኮሚቴ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ሲቋቋምም የነበረው አላማ ቅዱስነታቸው በህይወት እያሉ አይነኩብን ሲሉዋቸው የነበሩትን ህጎች ለእነሱ በሚመቻቸው መልኩ አስተካክለው ከጨረሱ በኃላ የፓትርያርክ ምርጫ ለማድረግ ነው።

ከዛ ደግሞ እነዚሁ ጳጳሳት ስራ አስፈጻሚው ህግ ይውጣለት ብለው ሲጠይቁ አሁንም አቡነ እስጢፋኖስየምን ህግ ነው የሚወጣለት? ሲኖዶሱ የራሱ ሕግ አለው። ይሔ ድጋፍ ሰጪ ኮሚቴ አስከሆነ ድረስ ከፈለገ ከቋሚ ሲኖዶሱ ጋር ይሰብሰብ እንጂ ሌላ ህግ አይወጣለትም።ሲሉ ተቃውመዋል። ይህንን ሀሳብ አብዛኛዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ደግፈዋል።
የስብሰባው አካሄድ ግራ የጋባቸው እና የጭቅጭቁ መብዛት ያስመረራቸው አቡነ ናትናኤል እኔ ሽማግሌ ነኝ በስተርጅና መዋረድ አልፈልግም ይዘታችሁ ደስ አላለኝም ሲኖዶሱን የሚመራው መንፈስ ቅዱስ ነው እስካልን ለምን አንረጋጋም? በዚህ እድሜዮ ውርደት ከመቀበልና ሽምግልናዬን ከማበላሸት  ሚዲያ ጥሩና ሌላ ሹሙ እኔ ግን ስራውን እለቃለሁ። በማለት ተነስተው ሊወጡ ሲሉ  በእድሜ ገፋ ያሉት ጳጳሳት ሀሳቡን በመቃወማቸው እና በተለይም አቡነ ፊሊጶስአባታችን እንዲህ አይሁኑ እየተረዳዳን እንሰራለን በሆነ ባልሆነው ነገር እየተደናገጥን ቤተክርስቲያንን አሳልፈን መስጠት የለብንምበማለታቸው እንደገና ተመልሰው ተቀምጠዋል። እነ አባ ሳሙኤልም ከአቡነ ናትናኤል የእለቃለሁ ንግግር በኋላ ረገብ ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም ከጠቅላይ ሚኒስቴሩ ዕረፍት ጋር ተያይዞ የፓትሪያርክ ምርጫው ላይ ማኅበረ ቅዱሳን የያዘውን አቋም መቀየሩ ታውቋል። ጠቅላይ ሚኒስቴሩ በሕይወት እያሉ መንግስት ጣልቃ ሊገባ ስለሚችል አቡነ ሉቃስን ብናደርጋቸው ይሻላል የሚል አቋም የነበራቸው ሲሆን አሁን ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ካረፉ ባለስልጣናቱ ጊዜያቸውን በውስጥ ሽኩቻ ማጥፋታቸው አይቀርም በሚል በአንደኝነት ይዘዋቸው የነበሩትን አቡነ ሉቃስን ወደ ሶስተኛ ቦታ አውርደው አንደኛ እጩ አድርገው አቡነ ያሬድን ሲይዙ በሁለተኛነት ደግሞ አቡነ ማቴዎስን አስቀምጠዋል።
        ሲኖዶሱን መንፈስ ቅዱስ ይመራዋል ተብሎ ቢታመንም በአሁኑ ሰዓት ሲኖዶሱን እያመሱት ያሉት ማኅበረ ቅዱሳንን እና ዋነኛ ወኪላቸው ማንያዘዋል መሆናቸው ይታወቃል። ማንያዘዋል በቤተክህነት አካባቢ ይሔ ነው የሚባል ስራ ሳይኖረው ውሎውም አዳሩም እዛው ሆኗል። በሁሉም ነገር ውስጥ እየገባ ለማቡካት ይሯሯጣል። አባቶችን በተለያየ የሀሳብ ውዥንብር ውስጥ እየከተተ ግራ ያገባል። ይሁንና ለማኅበረ ቅዱሳንም ቢሆን ጳጳሳቱን በራሱ የሀሳብ አሰላለፍ ማስኬድ አቡነ ጳውሎስን ለመቃመም እንደማስተባበር የቀለለ ሆኖ እንዳላገኘው የሰሞኑ ሁኔታ ያስረዳል።