Monday, September 3, 2012

በጉጂ ቦረና ሀገረ ስብከት ጉዳይ የመንግሥትና የቤተክርስቲያን አደራ ተበላ!


የምዕመናንና የቤተክርስቲያን መብት ተጨፍልቆ ለሕገወጡ ግለሰብ የ"ይጽና" ደብዳቤ እየተረቀቀለት ነው።
source;http://dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com
ለዓመታት የዘለቀው የጉጂ ቦረና ዞን ሀገረ ስብከት ችግር አሁንም የሚፈታው አጥቶ፣ ምዕመናኑ በከፍተኛ ችግር ላይ መውደቃቸውን በዚያ ያሉ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ በነጌሌ ቦረና፣ በክብረ መንግሥት (አዶላ ወዩ) ከተማ፣ በሀገረ ማርያም እና በሌሎችም ከተሞች የሚገኙ ምዕመናንን ችግሮች አስመልክቶ ከዚህ በፊት በተከታታይ እንደዘገብንላችሁ የሚታወስ ሲሆን፣ በተለይም በክብረ መንግሥት ከተማ የ"ማኅበረ ቅዱሳን"ና የጥቂት ጥቅመኛ ግለሰቦች ጥምረት ባሳደረው ተፅዕኖ በዓመታዊው የቅድስት ኪዳነ ምሕረት በዓለ ንግሥ እንኳን ታቦት ሳይወጣ ምዕመናን በደረሰባቸው ሁከት አዝነው ወደየቤታቸው መመለሳቸውን መግለጻችን ይታወሳል፡፡
ችግሩን ለማባባስ የግል ፍላጎታቸውን በቤተክርስቲያን ላይ በመጫን ከክብረ መንግሥት ከተማ እንደ እነ ዘውዴ አበሩ ያሉ ግለሰቦች ለ25 ዓመታት ከሰበካ ጉባዔ አንወርድም በማለት ቤተክርስቲያንን ለግል ገቢያቸው ተጣብተዋት ያሉ ሲሆን፣ ሲያምር ተክለ ማርያም የተባለ ግለሰብም ነጌሌ ቦረና ላይ ቁጭ ብሎ በሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ስም ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" ጋር በመመሳጠር በማመስ ላይ መሆኑን
በወቅቱ በዝርዝር ገልጸናል፡፡ በተለይም ሲያምር ተክለ ማርያም በፈጸመው የዲስፕሊን ጥፋት ከሥራ አስኪያጅነቱ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ ትንሣኤ ዘጉባዔ ማተሚያ ቤት የተዛወረ ሲሆን፣ ይህንኑ ውሳኔ የሚያስፈጽም ጠፍቶ በእምቢ ባይነት አሻፈረኝ በማለት ይኸው ከአንድ ዓመት በላይ መቆየቱን በተጨማሪ ዘግበናል፡፡ ይኸው ግለሰብ በሕገ ወጥነት በመፋነን የሀገረ ስብከቱን መኪና እና ማኅተም ጭምር ይዞ በመሰወር ምዕመናንን ሲያንገላታ፣ ከጠቅላይ ቤተክህነትም ሆነ ከኦሮሚያ ክልል መንግሥት አቅም በላይ እየሆነ መምጣቱን አብራርተናል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ምዕመናን ያለ መታከት በተከታታይ አዲስ አበባ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት ድረስ በመመላለስ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ሰባት አባላት ያሉት አጣሪ ቡድን በነሐሴ ወር 2004 ዓ.ም መጀመሪያ ሳምንት ወደ ሥፍራው ተልኮ ነበር፡፡ እነርሱም:-
  1. አቶ ተስፋዬ ውብሸት የጠቅላይ ቤተክህነት ምክ/ሥራ አስኪያጅ
  2. አቶ ፍስሐ ከጠቅላይ ቤተክህነት ቁጥጥር ክፍል
  3. አቶ እስክንድር ከጠቅላይ ቤተክህነት ሕዝብ ግንኙነት
  4. ሊቀ ስዩማን ፋንታሁን ሙጬ ከጠቅላይ ቤተክህነት ሰበካ ጉባዔ
  5. አቶ ሰሎሞን ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር
  6. አቶ ጣሰው ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር
  7. አቶ ፈቃዱ ከኦሮሚያ ክልል ፍትሕና ፀጥታ ናቸው፡፡
ቡድኑም ሥራውን ነጌሌ ቦረና ላይ ሆኖ መሥራት በመጀመር ከአካባቢው የወረዳዎች ቤተክህነትና አጥቢያ ቤተክርስቲያን የምዕመናን ተወካዮች ቀርበው ጉዳያቸውን እንዲያስረዱ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ ጥሪው የተላለፈላቸው የምዕመናን ተወካዮችና የወረዳዎች ቤተክህነት ተጠሪዎች ከክብረ መንግሥት፣ ከሞያሌ፣ ከሻኪሶ፣ ከሀገረ ማርያም፣ ከገርባ፣ ከቀርጫ፣ ከሶለሞ፣ ከቦሬና ከሌሎችም አካባቢዎች ወደ ነጌሌ ቦረና በመጓዝ ላይ ሳሉ ነሐሴ 10/2004 ዓ.ም የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዜና ዕረፍት ተሰማ፡፡ ቡድኑም ምዕመናንን ሳያነጋግር ወደየመጡበት ከመንገድ እንዲመለሱ መልዕክት አስተላልፎ፣ ሥራውን አቋርጦ ወደ አዲስ አበባ ተመለሰ፡፡
ለቅዱስነታቸው የሐዘንና የሥርዓተ ቀብር ወቅት ካለፈ በኋላ ቡድኑ እንደገና ተገናኝቶ ሳይመክር እና ሳይወስን የጠቅላይ ቤተክህነት ምክ/ሥራ አስኪያጁ አቶ ተስፋዬ ውብሸት በግላቸው ሲያምር ተክለ ማርያም በራሱ ስለራሱ በሚያመቸው መልኩ ምንም ዓይነት ጥፋት እንደሌለበትና በምድብ ሥራው ላይ ጸንቶ እንዲቆይ የሚያዝ ደብዳቤ አርቅቆ እንዲያመጣ በማድረግ ሊፈርሙለት መሆኑን ውስጥ ዐዋቂ ምንጮቻችን ከወደ ጠቅላይ ቤተክህነት ገልጸውልናል፡፡
ሲያምር ተክለ ማርያም ቀደም ሲል በፈጠረው ችግር ከዞኑ አልፎ ጠቅላይ ቤተክህነት በሕገወጥነቱ ክስ መስርቶበትና ከምድብ ሥራው ላይ አንስቶት ሳለ እንደገና አጣሪ ቡድን መሰየሙ እና አጣሪ ቡድኑም ምንም ዓይነት የውሳኔ ሃሳብ ሳያቀርብ አቶ ተስፋዬ ውብሸት በተናጠል በግላቸው ይህንን ችግር ፈጣሪ ግለሰብ በቤተክርስቲያን ጫንቃ ላይ እንዲቆይ ማድረጋቸው፣ ለምዕመናን እና ለቤተክርስቲያን ያላቸው ግምት ዝቅተኛ መሆኑን ያሳያል ተብሏል፡፡
የጉጂ ቦረና ሀገረ ስብከት ከረጅም ጊዜያት ጀምሮ የአስተዳደር በደል ሲፈጸምበት የኖረና በጠቅላይ ቤተክህነትም በኩል ተገቢው ትኩረት ያልተሰጠው፣ ሕገ ወጥ ግለሰቦችና "ማኅበረ ቅዱሳን" እንዳሻቸው በቤተክርስቲያን ጉዳይ እጃቸውን ከተው የሚያጨማልቁበት ነው ተብሏል፡፡ ሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ቢመደብለትም እነዚሁ ሕገ ወጦች ባደረሱት ጫና ሊቀጳጳሱ አቡነ ሳዊሮስ ዝውውር ጠይቀው አካባቢውን ለመልቀቅ ተገደዋል ተብሏል፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላም እስካሁን ለሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ያልተመደበለት ሲሆን፣ በቅርቡ ደግሞ ሀገረ ስብከታቸውን እንኳን በቅጡ ማስተዳደር ላቃታቸው ለአቡነ ገብርኤል በተደራቢነት የተሰጣቸው መሆኑ ታውቋል፡፡
እርሙን ደግሞ ችግሩን ለመፍታት አጣሪ ቡድን ወደ ስፍራው ቢላክም ቡድኑ ከመንበረ ፓትርያርክ ጽ/ቤት በተለይም ከቅዱስነታቸው፣ ከጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤትና ከመንግሥት የተሰጠውን አደራ ወደ ጎን በመተው ችግሩ እንዲባባስ ባለበት መተውን ብዙዎች በቅሬታ ይገልጻሉ፡፡ ቡድኑንም "አደራ በላ" ብለውታል፡፡