Wednesday, September 26, 2012

"....ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን?

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ስለ ራሳቸው፣ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን…?

ይህ መጣጥፍ በሪፖርተር ጋዜጣ የእሁድ እትም በፍቅር ለይኩን የተባሉ ጸሐፊ ካስነበቡት ጹሑፍ ለጦማራችን በሚመስማማ መልኩ መጠነኛ ማሰተካከያ ተደርጎበት የተወሰደ ነው፡፡

 ‹‹እግዚአብሔር ሆይ ሁሉንም ነገር ለአንተ እተዋለሁ. . . አሜን!›› (በቅርቡ የሞቱት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ ከመሞታቸው በፊት ከተናገሩት የተወሰደ፡፡)
ሞት የሰው ልጆች ሁሉ አይቀሬ የሆነ የሕይወት ዕጣ ፈንታ ነው፡፡ ትልቁ ቁም ነገር በምድር ላይ በኖርንበት ወይም እንድንኖርበት በተሰጠን ዘመን የሠራነው ደግ/መልካምም ሆነ ክፉ ሥራችን ግን ሁሌም ከመቃብር በላይ ቋሚ ሀውልታችን ወይም ቅርሳችን ሆኖ እንድንታወስ ሊያደርገን እንደሚችል በቅጡ ማሰብ ይመስለኛል፡፡
ሰዎች ስለ ሞት የተለያየ አመለካከት አላቸው፡፡ ለአንዶንዶች ሞት ትርጉም የለሽ ጸጥታ ነው፡፡ ለሌሎች ደግሞ ሞት ዘላለማዊ እረፍት ነው፡፡ ለአንዳንዶች ሞት ምስጢራዊ እና ረቂቅ ነገር ነው፡፡ በክርስትናው ዓለም ውስጥ ላለን በርካቶች ደግሞ ሞት ወደ ዘላለማዊው፣ ፍፁም ሰላም እና እረፍትን ወደ ተሞላው ሰማያዊ ዓለም እንደ መሸጋገሪያ ድልድይ የሚቆጠር ነው፡፡
ስለ ሞት ያለን ግንዛቤ፣ ትንታኔ እና ፍልስፍና እንዳለንበት እና እዳደግንበት ማኅበረሰብ የኑሮ ልማድ፣ ባሕል እና እምነት/ሃይማኖት የተለያየ ፍቺ ይሰጠዋል፡፡ ሞት የቅርባችን እና የዕለት ተዕለት ክስተት የመሆኑን ያህል በአንፃሩ ደግሞ መቼም የማይለመድ እንግዳ ክስተት ሆኖ መቀጠሉ ለብዙዎቻችን እንቆቅልሽ ነው፡፡ ምነው በአዲሱ ዘመን፣ በወርኻ አደይ፣ ምድር፣ ተራሮች እና ሜዳዎች፣ ጋራ እና ሸንተረሩ በአበቦች አምረውና ተውበው በሚያጌጡበት፣ ሰዎች ሁሉ በአዲስ ራእይ ሕይወትን ውብ እና ፍቅርን የተሞላች ለማድረግ ብሩህ ተስፋን ሰንቀው ‹‹ጉልበቴ በርታ በርታ!›› በሚሉበት ውብ እና ተወዳጅ በሆነችው በወርኻ መስከረም ምን ነክቶህ ነው እንዲህ ሞት ሞት የሚሸት ጹሑፍ ምነው!? እረ…! ደግም አይደል የሚሉኝ ሰዎች አይጠፉም ብዬ እገምታለሁ፡፡
ግና ወደድንም ጠላንም መራሩ እውነታ ሞት ለሁላችንም የማይቀር ዕዳ መሆኑ ነው፡፡ ሞት የሁላችንም ዕጣ ፈንታ መሆኑ ማንኛችንም ብንሆን ለአፍታም ያህል ቢሆን እንዘነገዋለን ብዬ ለመናገር አልደፍርም፡፡ ስለዚህም ሞት ሲመጣ አማክሮ፣ ጊዜ እና ወቅትን ተከትሎ አይደለምና ስለ ሞት ለማውራት ምቹ ጊዜ፣ የተመረጠ ሰዓት ሊኖር ይችላል ብዬ አላስብም፡፡ ሞት አዲስ ዘመን፣ ወርኻ ክረምት፣ በጋ ወይም ጸደይ፣ ትንሽ፣ ትልቅ፣ መሪ ተመሪ፣ ንጉሥ፣ አገልጋይ፣ ሕጻን፣ አዛውንት… ወዘተ አይልምና፤ ለዚህም ነው በለመለመ ብሩህ ተስፋ እና ራእይ ሕይወትን ውብ እና ጣፋጭ ለማድረግ መልካም ምኞታችንን በምንገልጽበት በአዲሱ ዘመን መባቻ ስለ ሞት ለማውራት መጨከኔ፡፡
    የዕብራውያን ጸሐፊ የሆነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱም በኋላ ፍርድ ተመደቦባቸዋል፡፡›› (ዕብ ፱፣፳፯) በማለት የሞትን አይቀሬነት ያስገነዝበናል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገናም በሮሜ መልእክቱ፡- ‹‹በአዳም ኃጢአት ምክንያት ሞት በሰው ልጆች ሁሉ ላይ መንገሱን እና የዚህ የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ ሞት ድል መነሳቱን እና በክርስቶስ ሞት ምእመናን የዘላለም ሕይወትን እንደታደሉ›› እንዲህ ይተርካል፡- ‹‹በአንዱም (በአዳም) በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፣ ይልቁን የጸጋን ብዛት እና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ፡፡›› (ሮሜ ፭፣፲፯) ይለናል፡፡

   ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በወንድሟ በአልዓዛር ሞት እጅጉን ልቧ ተሰብሮ እና ሁለንተናዋ በሀዘን ደቆ በእግሩ ሥር ተደፍታ እያነባች፡- ‹‹ጌታ ሆይ አንተ በዚህ ኖረህ ቢሆን ኖሮ ወንድሜ ባለሞተ ነበር!›› ላለችው ለማርታ፡- ኢየሱስም፡- ‹‹ትንሣኤ እና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳን ሕያው ይሆናል፡፡›› በማለት በእርሱ (በሕያው እግዚአብሔር ልጅ) የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዳላቸው በቃሉ አረጋገጦላታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በቅዳሴው ‹‹ሞትን ይሽረው ዘንድ ሞተ!›› በማለት የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሞት ለዘላለም መሻሩን ይመሰክራል፡፡
ሞት በክርስቶስ ላመኑ በፍፁም የሚያስፈራ እና የሚያስጨንቅ ነገር አይደለም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለእኔስ ወደ ጌታዬ መሄድ ይሻለኛል ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡›› ሲል ሞቱን ወደ ጌታው እና አምላኩ የሚሻገርበት ድልድይ እንደሆነ ለፊሊጵስዩስ ክርስቶሳውያን የወንጌል ልጆቹ በላከላቸው መልእክቱ በግልፅ ነግሯቸዋል፡፡ እናም ሞት በክርስቲያኖች ዘንድ አስፈሪ እና አሳፋሪ አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፣ ሆኖም አያውቅም፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን የወንጌል አርበኞች፣ ጻድቃን እና ሰማዕታት ሞታቸውን እግዚአብሔር አምላካቸውን በዝማሬ እያመሰገኑ፣ እያመለኩ፣ በታላቅ ደስታ እና በጸጋ ነው የተቀበሉት፡፡
ወደ ተነሳሁበት ወደ ርዕሰ ጉዳይ ስመለስ 2004 ዓ.ም በሀገራችን በሃይማኖት፣ በሥነ ጥበብ እና በፖለቲካው መስክ አንቱ የተባሉ ሰዎችን ያጣንበት ዘመን ነው፡፡ በተለይም ደግሞ ወርኻ ነሀሴ ከሕይወት ጋር ግብ ግብ የገጠመ በሚመስል አስገራሚ ጥድፊያ፣ ዓመቱ ከማለቁ በፊት ሳልቀደም ልቅደም ያለ ይመስል በዓመቱ መጨረሻ በወርኻ ነሀሴ ሁለት ታላላቅ መሪዎችን በሳምንት ልዩነት ውስጥ ያጣንበት እንደ አየሩ ጠባይ ሁሉ ጨፍጋጋ እና አስደንጋጭ ወር ሆኖ አልፏል፡፡    
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን አባት እና መሪ የሆኑት ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እና የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚ/ር አቶ መለስ ዜናዊ የተከታተሉበት የሞት መርዶ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን ከዳር እስከ ዳር ያነጋገረ እና የሀዘን ከል ያለበሰ ክስተት ሆኖ አልፏል፡፡
በዚህ የሞት ክፉ ዜና የተነሳ በሀገራችን ያረበበው የሀዘኑ ድባብ እንደ ሰማዩ ደመና ገና ሙሉ በሙሉ የተገፈፈ አይመስልም፡፡ አሁንም ድረስ የእነዚህ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ መራኅያን ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ለብዙዎቻችን ባሰብነው ቁጥር እንቆቅልሽ እንደሆነብን ዘልቋል፡፡ ለአንዳንዶች በተመሳሳይ ወቅት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ የተከሰተው ይህ ያልተጠበቅ የሞት ጥሪ ‹‹የእግዚአብሔር ቁጣ ነው›› እኛም ንስሀ እንግባ ዘንድ ያስፈልገናል በማለት የእግዚአብሔርን ታላቅነት እና ኃያልነት ዳግም እንዲያስቡ እና እንዲያስተውሉ እንዳደረጋቸው ሲናገሩ በአደባባይ ተደምጠዋል፡፡
ለሌሎች ወገኖቻችን ደግሞ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ የሞት መርዶ ያው እንደተለመደው ተራ የፖለቲካ ጉንጭ አልፋ ወሬ ከመሆን አላለፈም፡፡ እናም አንዳንዶች ለሰሞኑ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ያልተገባ የስንፍ እና የፍርድ አስተያየት ከመሰጠት ባለፈ ሌላ አንድምታ እንዳልሰጡት በሰሞኑ ከሚነገሩ ወሬዎች፣ በማኅበረሰብ ድረ ገጾች እና በየብሎጉ ከሚጻፉ በርካታ ፍርድ አዘል ጹሑፎች እና አስተያየቶች ታዝበናል፡፡ እንዲያም ሲል ደግሞ እሰይ ስለቴ ሰመረ በሚል የሚያዜሙ እና ፍፁም ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እና ባሕል በጎደለው ሁኔታ በእነዚህ መሪዎች ሞት ጮቤ እየረገጡ ያሉ ወገኖችንም እረ ምን ጉድ ነው እያልን ለመታዘብም በቅተናል፡፡ 
እንዲሁ እንደ ዋዛ ለህክምና በሚል ሰበብ እንደ ወጡ እስከ ወዲያኛው የተለዩንና ከአሁን ከአሁን ጤንነታቸው ተመልሶ ይመጣሉ በሚል ተስፋ የጠበቅናቸው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በስተመጨረሻ ለብዙዎቻችን ጆሮ የማይታመን የሆነውን የሞታቸውን መርዶ ዜና ለማመን እየቸገረንም ቢሆን ለመስማት ነበር የተገደድነው፡፡ ደህና ናቸው፣ ከህመማቸው እያገገሙ ነው፣ በአዲሱ ዓመት ሥራቸውን ይጀምራሉ የተባለላቸው ጠቅላይ ሚ/ር በድንገት በተከሰተ ኢንፌክሽን ምክንያት በድንገት ሞቱ መባላቸው አሁንም ድረስ ለብዙዎቻችን ኢትዮጵያውያን የጠቅላይ ሚ/ሩ ህመማቸው እና አሟሟታቸው ምስጢር ነው፡፡
በዚህ ጽሑፌ ለመዳሰስ የፈለግኩት የቤተ ክህነቱ እና የቤ መንግሥቱ መሪዎች በሕይወታቸው እስትንፋስ መጨረሻ ምን እንደተናገሩ በመጠየቅ የተነሳው የመጣጥፌ ርዕሰ ጉዳይ እንደ አለመታደል ሆኖ አትኩሮቱን ያደረገው በውጩ ዓለም ባሉ መሪዎች እና ታላላቅ ሰዎች ላይ ነው፡፡ የዚህ ዐቢይ ምክንያት ደግሞ በቅርብ በሞት የተለዩን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስም ሆነ ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ ምን እንዳሉ፣ ምን እንደተናገሩ እና ለሕዝባቸው ምን ዓይነት የመጨረሻ መልእክት እንዳስተላለፉ የነገረን ሰው ወይም እኔ ምስክር አለሁ የሚለን ሰው እሰካሁን አለመገኘቱ ነው፡፡
ፍቅርን፣ ይቅር ባይነትን/እርቅን፣ ግልፅነትን፣ ታማኝነትን… ወዘተ በቃላቸውም ሆነ በተግባራቸው የሚሰብኩ መሪዎች ድርቅ ክፉኛ የመታት እናት ኢትዮጵያ መሪዎቿ እና ሕዝቦቿ በቅጡ ሳይተዋወቁ እና በፍቅር ሳይቀራረቡ ማዶ ለማዶ እንደተያዩ በሞት እስከ ወዲያኛው የሚሸኙባት ምድር የመሆኗ ምስጢር ማብቂያው መቼ እንደሆነ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡
በምስኪኗ ኢትዮጵያ መሪዎቻችን ብዙ ነገራቸው ለሕዝባቸው ምስጢር ነውና እነዚህ ለሁለት አሥርት ዓመታት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ መሪዎች ሆነው ያስተዳደሩ ፓትርያርክ አባ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ምን እንዳሉ ምን መልእክት እንዳስተላለፉ ለማወቅ አልታደልንምና ሳንወድ በግድ ቁጭት እና እልህ እየተፈታተነንም ቢሆን በጀመርኩት ርዕስ ስለ ባሕር ማዶዎቹ መሪዎችና ታላላቅ ሰዎች የመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ መልእታቸው ላምራ፡፡
ከጠቅላይ ሚ/ር መለስ ከጥቂት ሣምንታት በፊት በሞት የተለዩት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ በጉሮሮ ካንሰር በሽታ ምክንያት በአሜሪካ አገር ህክምና ያደረጉ ቢሆንም በቅርቡ ህመማቸው አገርሽቶ ወደ ሀገራቸው የጦር ኃይሎች ሆስፒታል ገብተው ሕክምና በመከታተል ላይ እያሉ ነበር ያረፉት፡፡ Web Ghana የተባለው ድረ-ገጽ ‹‹Mills’ Last Words Before He Died/የፕሬዝዳንት ሚልስ እልፈት እና ከመሞታቸው በፊት የተናገሩት የመጨረሻ ቃላቸው›› በሚል ርዕስ ባስነበበው ጹሑፍ ፕ/ር ሚልስ ከሞታቸው በፊት ካጠገባቸው የነበሩትን ወንድማቸውን ዶ/ር ካድማን ሚልስን በመጥቀስ የሚከተለውን ዘገባ አስነብቦ ነበር፡-
"Before my brother (Mills) died, the last words that he said that I clearly remember is that, he raised his hands in the air and he said ‘God, I leave it all to you, Amen’. I’ve no doubt that God heard his call. I’ve no doubt that he is now in the bosom of the Lord. I’ve no doubt that he’ll find eternal peace. Pray for him, and May God be with you, Fiifi," Dr Cadman Mills said.


የጋናው ፕሬዝዳንት ፕ/ር ሚልስ ወንድም እንደ ዶ/ር ካድማን ገለጻ ፕሬዝዳንት ሚልስ ከመሞታቸው በፊት ያሉት ነገር ቢኖር እጆቻቸውን ከዓይናቸው ጋር ወደ ሰማይ በማንሳት ‹‹እግዚአብሔር ሆይ ሁሉንም ነገር ለአንተ እተዋለሁ. . . አሜን!›› በማለት ነበር የወንድማቸውን የመጨረሻ ቃላቸውን እና ኑዛዜያቸውን ለጋናውያን በሲቃ በንባብ ያሰሙት፡፡ ዶ/ር ካድማን፡- ‹‹እግዚአብሔር የወንድሜን ጸሎት እንደሰማ እርግጠኛ ነኝ፣ ወንድሜ በአሁኗ ሰዓት በአባቱ በጌታ እቅፍ እንዳለም በጭራሽ አልጠራጠርም፣ ጌታ ኢየሱስም ዘላለማዊ እረፍትን እንደሰጠውም እርግጠኛ ነኝ፡፡ እባካችሁ የምትወዱት የጋና ሕዝቦች ሆይ ለመሪያችሁ ጸልዩለት፡፡›› በማለት ነበር ለጋናውያን መልእክታቸውን ያስተላለፉት፡፡
በዓለማችን ሰዎች በሞታቸው ሰዓት የሚናገሩት ቃላት ወይም ኑዛዜ እጅግ ትልቅ ግምት የሚሰጠው ነው፡፡ ማንኛውም ሰው በእስትንፋሱ መጨረሻ የሚናገራቸው ቃላት በተለያዩ ምክንያቶች ትልቅ ከበሬታ እና ሥፍራ ይሰጠዋል፡፡ ይህ ደግሞ በአብዛኛው ለሞት እና ከሞት በኋላ ላለው ዓለም ከሚሰጠው የተለየ ግምት እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ በጥንት ዘመን ከተለያዩ ሃይማኖቶች አንፃርም ሟች በመጨረሻ እስትንፋሱ ከመንፈሳዊው ዓለም ሕይወት ጋር በተያያዘ የሚናገረው አንዳች ምስጢራዊ ነገር ይኖራል በሚል እምነት በትልቅ ጉጉት ይጠበቃል፡፡
Encyclopedia of Death and Dying እንደሚያትተው በዓለማችን ከተነሱ ፈላስፎች መካከል እጅግ የከበረ ስም እና ዝና የነበረው ጆርጅ ሄግል (1770-1831) በሞቱ ወቅት አንዳች በሕይወት ዘመኑ ከተናገራቸው ድንቅ እና ጥልቅ ፍልስፍናዎቹ ባሻገር እጅግ ምስጢራዊ እና አዲስ የሆነ ልዩ ነገር ይናገራል በሚል አድናቂዎቹ ከበው ሲጠብቁት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በተቃራኒው ጆርጅ ሄግል በሞት እና በሕይወት መካከል ሆኖ ያለው ነገር፡- ‹‹በሕይወት ዘመኔ ከጻፍኳቸው የፍልስፍና መጻሕፍቶቼ እጅግ ጥቂት ሰዎች ብቻ ናቸው አሳቤንም ሆነ እኔነቴን የተረዱት›› የሚለውን ቃል ብቻ በቁጭት ስሜት ውስጥ ተናግሮ ነበር አይቀሬውን የሞትን ጽዋ የተጎነጨው፡፡
በክርስትናው ዓለም አንድ ሰው ሲሞት እስከ ዕድሜ ዘመኑ የሸሸገውን፣ ለማንም ያልገለጸውን ምስጢር፣ እውነት ወይም የደበቀውን በደሉን ይናገራል ተብሎ ስለሚታሰብ ነው የሟች ቃል ክብር እና ልዩ ሥፍራ የሚሰጠው፡፡ ስለዚህም በአብዛኛው ክርስቲያን ዓለም በሟች አጠገብ የሟችን የመጨረሻ ቃል ወይም ኑዛዜ የሚቀበል የሃይማኖት አባት/ካህን አብሮ እንዲሆን ይደረጋል፡፡ ይህ የእምነት አባት/ካህንም የሟችን ቃል እና የመጨረሻ ኑዛዜ ያለ ምንም ማጉደል እና መጨመር በሕይወት ላሉ ቤተሰቡና ዘመዶቹ ያሳውቃል ተብሎም ይታመናል፡፡
ኢንሳክሎፒዲያ ኦፍ ዴዝ በ18ኛው መቶ ክ/ዘመን በፈረንሳይ ውስጥ ማንኛውም ሀኪም በሞት እና በሕይወት መካከል ያለን በሽተኛ አንድ ቄስ/አናዛዥ ካህን የመጨረሻ ቃሉን እንዲቀበለው ሁኔታዎችን ማመቻቸት እንዳለበት በሕግ ተደንግጎ እንደነበር ያብራራል፡፡
በዓለማችን ታላላቅ እና ታዋቂ ሰዎች በእስትንፋሳቸው መጨረሻ የሚናገሩት ቃላት ልዩ ሥፍራ ይሰጠዋል፡፡ ከግሪክ ፈላስፎች መካከል እጅግ የተወደደው እና የተከበረው ፈላስፋው ሶቅራጥስ ‹‹ነፍስ ዘላለማዊ ናት!›› በሚል ፍልስፍናው ይታወቃል፡፡ በዚሁ ‹‹Soul is Immortal›› በሚለው ፍልስፍናው እና እንግዳ በሆነ አስተምህሮው ግሪካውያንን ታዳጊዎች እና ወጣቶችን አበላሽቷል፣ ሕዝባችንን መናፍቅ እንዲሆኑ አድርጓል በሚል ክስ የሞት ፍርድ እንዲፈረድበት ተደርጎ ነበር፡፡ ተማሪዎቹና ጓደኞቹ ሶቅራጥስን ከተፈረደበት የሞት ፍርድ እንዲያመልጥ ለማድረግ መላ የዘየዱለት ቢሆንም ሶቅራጥስ ግን ሞቴን በደስታ እና በጸጋ እቀበለዋለሁ በማለት ራሱን ለከሳሾቹ የሞት ፍርድ አሳልፎ ነበር የሰጠው፡፡
እናም ሶቅራጥስ የሞት ቅጣቱ የሚፈጸምበት መርዝ የተሞላ ኩባያ በፊቱ ቀርቦለት ሳለ ለቅርብ ጓደኛው ከመሞቱ በፊት የተናገረው የመጨረሻ ቃሉ እንዲህ የሚል ነበር፡- "Crito, I owe a cock to Asclepius; will you remember to pay the debt ?"  ወዳጄ ክሪቶ ከአስችሌፒየስ የተበደርኩት አንድ አውራ ዶሮ አለና እባክህ አደራህን መለሰስልኝ በማለት ይህችን ቃል ብቻ ተናግሮ ነበር ሞቱን ጽዋ የተጎነጨው፡፡ በፍልስፍናው እና በጥልቅ አስተሳሰቡ መላውን ግሪክ እና ዓለምን ጉድ ያሰኘ ይህ ሰው በሕይወቱ መጨረሻ የተናገረው ቃል አንድ የአውራ ዶሮ ዕዳ ጉዳይ መሆኑ አያስገርምም ትላላችሁ!? ግና አዎ ታላቁ ሶቅራጥስ በሕይወቱ መጨረሻ የማንም ባለዕዳ ሆኖ ላለመሞት ነበር የወሰነው፡፡
አውሮፓን እና መላውን ዓለም በወረራ የተቆጣጠረው ከሜቅዶኒያ እስከ ፓኪስታን ከግሪክ እስከ አፍሪካዊቷ ግብጽ በጦርነት ያስገበረው እና ገና በ33 ዓመቱ የሞተው ታላቁ እስክንድርም በሕይወቱ መጨረሻ እያነባ፡- "There are no more other worlds to conquer!" ወረራ ልይዘው ሚገባ ሌላ የቀረ ዓለም ይኖረኝ ይሆን በማለት እየጠየቀ ነበር ያንቀላፋው ጦረኛው ታላቁ እስክንድር፡፡
በሌላ በኩል የታላቁ እስክንድርን ታሪክ የጻፉ ጸሐፍት እንደሚናገሩት ደግሞ አሌክሳንደር ገና በሕይወት ሳለ ለቅርብ ጠባቂዎቹ ስሞት እጆቼን ከመቃብሩ ሳጥን አውጥታቸሁ ቅበሩኝ፤ ምክንያቱም ሁሉም ሲኖረኝ፣ ሁሉም የእኔ የሆነ የታደልኩ ባለጸጋ ስሆን በሞቴ ጊዜ ግን ምንም ነገር ይዤ አለመሄዴን ዓለም ሁሉ ያውቅ ዘንድ ብሎ በኑዛዜ መልክ እንዳስጠነቀቃቸው ጽፈዋል፡፡
የመቼውም የእንግሊዝ ምርጥ ጠቅላይ ሚ/ር እና በሳል ፖለቲከኛ የነበሩት ዊንስተን ቸርቸል በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁበትን "I could have prevented the war!" (W.W.II) ድንቅ የሆነ መጽሐፍ የጻፉት ቸርችል በሕይወታቸው መጨረሻ ያሉት ነገር፡- "What a fool I have been!" ምን ያለሁት ሞኝ ወይም ቂላ ቂል ሰው ነኝ ሲሉ ነው በራሳቸው ላይ በምጸት ተናግረው የሞቱት፡፡
በዓለማችን የተለያዩ ታዋቂ ሰዎች፣ ፈላስፎች፣ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ ደራሲያን፣ ፖለቲከኞች ወዘተ በሕይወት ዘመናቸው ይልቅ በሞታቸው የተናገሩት የመጨረሻ ቃላቸው ወይም ኑዛዜያቸው ታላቅ ክብር እና ሥፍራ ተሠጥቶት የዘላለም መታወሻ ሆኖ በብዙዎች ዘንድ ይታወሳል፣ ይነገራል፡፡
በተቃራኒው ደግሞ  በሕይወት መጨረሻ ስለሚነገሩ ቃላቶች እና ኑዛዜዎች በተመለከተ ከክርስቲያን ጁዊሽ ቤተሰብ የተወለደው እና የኮሚኒዝም ፍልስፍና አመንጪ እና አራማጅ  የሆነው ካርል ማርክስ አልጋው ላይ ተጋድሞ ሞቱን በሚጠባበቅበት በመጨረሻዋ ሰዓት አስታማሚው የነበሩት ነርሶች በመጨረሻ የሚናገረው ነገር እንዳለ በጠየቁት ሰዓት በቁጣ ሆኖ እንዲህ በማለት ነበር የጮኸባቸው፡-
"Go on, get out! Last words are for fools who haven't said enough." ቀጥሉ… ውጡ ብያለሁ የሚናገሩት የመጨረሻ ቃል እንዳላቸው ሊጠየቁ የሚገባቸው ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው የሚገባቸውን እና አስፈላጊውን ቁም ነገር ለማስተላለፍ ላልቻሉ ቂሎች እንጂ ለእኔ አይደለም በማለት ነው እንደ ብራቅ በመጮኽ አስታማሚ ነርሶቹን ክፍሉን ለቀው እንዲወጡለት ያዘዛቸው፡፡
በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ ሰፊ ድርሻ እና ስም ያላቸው እንደው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም ሆነ አቶ መለስ ዜናዊ ለሁለት አስርተ ዓመታት ያስተዳደሯቸውን ኢትዮጵያን እና ሕዝቦቿን ለዝንተ ዓለም ሲሰናበቷቸው በሕይወታቸው መጨረሻ ምን ተናግረው፣ ምን ብለው የማይቀረውን የሞት ጽዋ እንደተጎነጨ ለማወቅ አለመታደላችን ትንሽ ትንሽ አያስቆጭም ትላላችሁ፡፡
በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እና በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ መንገድ ደማቅ የሆነ አሻራቸውን ጥለው ያለፉ የእነዚህ መሪዎች የጀመሯቸውን ውጥኖች እና ራእዮች ከግባቸው ሳያደርሷቸው በሞት ሸለቆ ጥላ ውስጥ ያለፉ ዘንድ ግድ የሆነባቸው ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እና አቶ መለስ በስተመጨረሻ ተራቸው ደርሶ ሞት እጃችሁን ስጡ ሲላቸው በሕይወታቸው ፍፃሜ ምን ይሆን ያሉት…!? ምንስ ይሆን የተናገሩት…!?
  መጣጥፌን ሳይንሲስቱ ላፕላስ የመጨረሻ የሕይወቱ እስትንፋስ ቃል ላጠቃልል፡፡ ሳይንቲስቱ ላፕላስ በሕይወቱ መጨረሻ ሞቱን በመጠባበቅ በነበረበት ሰዓት በአልጋው ዙሪያ የከበቡት ጓደኞቹ በአንድ ድምፅ ሆነው፡- ‹‹ላፕላስ አይዞህ ትላልቅ የሆኑ ግኝቶችህ እና ሥራዎችህ በዓለም ዙሪያ ሁሉ እንድትታወስ ያደረጉሃልና ተጽናና…፡፡›› ባሉት ጊዜ ላፕላስ፡- ‹‹እነዚህ የምትሉኝ ነገሮች ሁሉ ምንም ዋጋ የላቸውም፣ ከንቱ የከንቱ ናቸው፡፡ በእነዚህ እናንተ በምትሉት ሳይንሳዊ ግኝቶቼ እና መጻሕፍቶቼ መታሰቤ ለእኔ ምኔ ነው!? በማለት ጠየቃቸው፡፡ ጓደኞቹም በመደንቅ ሆነው፡- ‹‹ላፕላስ ታዲያ የአተነትህ ሕያው ማስታወሻ፣ ሀውልት እና ቅርስ ምን እንዲሆን ትፈልጋለህ?›› በማለት በጉጉት ሆነው ጠየቁት፡፡
ሽማግሌው ሳይንሲስት ላፕላስም በተቆራረጠ ድምፅ በለሆሳስ ሆኖ ‹‹መታወሻዬ የሕያውነቴ ምስጢርም ፍ-ቅ-ር ብቻ እንዲሆን ነው የምፈልገው!›› ነበር በማለት የተሰናበታቸው፡፡ ፍ-ቅ-ር የሕያውነት ምስጢር፣ ለዘላለም ከመቃብር በላይ መታሰቢያችን፣ ሞትን ማሸነፊያው እውነተኛ መንገዱ አዎን ፍ-ቅ-ር እና ፍ-ቅ-ር ብቻ ነው፡፡ ኃያል ወልድን ከመንበሩ ስቦ ሰው እንዲሆን ያደረገው እና ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ ተፈትኖ፣ በምድር ላይ ተመላልሶ ሞታችንን በሞቱ ቀይሮ ሕይወትን የሰጠን ከወደድን ከታላቅ ፍቅሩ የተነሳ ነው፡፡ እናም በፍቅር የሞት መውጊያ ለዘላለም ተሰብሯል፣ ሲኦልም ድል ተነስቷል!
በፍቅር እና በበጎ ሥራችን ዘላለማዊ የሆነ የሕያውነት ሀውልት ለትውልድ እና ለሀገር ማቆም ይቻለን ዘንድ በመመኘት ልሰናበት፡፡ 2005 ዓ.ም ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ የፍቅር፣ የሰላም እና የሕይወት ዘመን ይሁንልን!
ሰላም! ሻሎም!