Monday, June 18, 2012

«ፍቅር ለይኩን ያቀረበው ትችት ውሃ የማይቋጥር ወንፊት ነው»

 
በአባ ሰላማ ድረ ገጽ ላይ «ፍቅር ለይኩን» የተባለ ሰው ስለየትኞቹ  ስም አጥፊ ብሎጎች ለመናገር እንደፈለገ ስማቸውን  ባይገልጽም እሱን ደስ ያላሰኘውን ነጥብ በማመልከት፤ የሰዎችንም ኃጢአት መዘርዘር ጥሩ እንዳልሆነ  መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥቅሶችን በማስረጃ አቅርቦ ምክርና ተግሳጽ ለመስጠት ሲሞክር ተመልክተናል።
ይህ በአባ ሰላማ ድረ ገጽ ላይ ጽሁፉን ያቀረበው «ፍቅር ለይኩን» የተባለው ሰው ፤ በፖለቲካው ዓለም ደከመን፤ ሰለቸን  ሳይሉ የኢሕአዴግን መንግሥት በማጥላላትና በመቃወም ሌሊትና ቀን በሚደክሙት ድረ ገጾች ላይ የተለያዩ ፖለቲካዊ መጣጥፎችንና አንዳንዴም መንፈሳዊ መሰል የነቀፋ ጽሁፎችን  የሚያቀርበው የደቡብ አፍሪካው «ፍቅር ለይኩን»  መሆኑን የምናውቀው ከስሙ ባሻገር «ሻሎም፤ ሰላም» በሚለው የጽሁፉ ማሰረጊያ  ቃል የተነሳ እሱነቱን ብንገምት ከእውታው የራቅን አይመስለንም።
ከዚህ ተነስተን ስለአቶ ፍቅር ለይኩን  ጽሁፍ ጥቂት ለማለት እንወዳለን።
 አቶ ፍቅር ስለአባቶች መዋረድና አለመከበር ተገቢ መሞገቻ ይሆነው ለመከራከሪያነት የተጠቀመበትን ዐውደ ጥቅስ  በማስቀደም እንጀምር።
‹‹ደፋሮችና ኩሩዎች ሆነው ሥልጣን ያላቸውን ሲሳደቡ አይንቀጠቀጡም፣ ዳሩ ግን መላእክት በኃይልና በብርታት ከእነርሱ ይልቅ ምንም ቢበልጡ በጌታ ፊት በእነርሱ ዘንድ የስድብን ፍርድ አያመጡም…፡፡›› ፪ጴጥ ፪፣፲፩፡፡
ይህን ጥቅስ አቶ ፍቅር ለይኩን ያቀረበው ምንም ይስሩ ምንም፤ ምንም ያድርጉ፤ የቱንም ያህል ይበድሉ፤  ስለ ጳጳሳት አትናገሩ፤ ምክንያቱም ወንጌል አትናገሩ ብሏልና ሲል የአፍ መዝጊያ ጥቅስ በማቅረብ ሊሞግተን ይፈልጋል። ጥቅሱ ስለማን እና ስለምን እየተናገረ እንደሆነ ግን አያብራራም። መቼም ምግባረ ብልሹና የጥፋት ኃይል ለሆኑ ሹመኞች ሁሉ እንድንገዛ የተነገረ ነው  እንደማይለን ተስፋ እናደርጋለን። እንደዚያማ ከሆነ አቶ ፍቅር የኢህአዴግ መንግሥት ክፉና መሰሪ ነው፤ የአባ ጳውሎስ አስተዳደር አጥፊና ከፋፋይ ነው እያሉ ለኢህአዴግ ውድቀት በሚሰሩ ድረ ገጾች ላይ ጽሁፎቹን ሲለቀልቅ ባልዋለም ነበር። ምክንያቱም ወንጌል እንደዚህ ሲል ያስጠነቅቀዋልና።
ስለ ጌታ ብላችሁ ለሰው ሥርዓት ሁሉ ተገዙ፤ ለንጉሥም ቢሆን፥ ከሁሉ በላይ ነውና፤
ለመኳንንትም ቢሆን፥ ክፉ የሚያደርጉትን ለመቅጣት በጎም የሚያደርጉትን ለማመስገን ከእርሱ ተልከዋልና ተገዙ። 1ኛ ጴጥ 2፤13-14
ኢህአዴግን መቃወምም ሆነ መደገፍ መብት በመሆኑ ጸረ ኢህአዴግ ድረ ገጾች አቋማቸውን ግልጽ አድርገዋል። የማያሻማ ሆኖ «ለንጉሥም ቢሆን ተገዙ፤ ክፉ የሚያደርጉም ቢሆኑ መኳንንቱ ከላይ ተልከዋልና» የሚለውን የወንጌል ቃል ጨቋኞች፤ አምባገነኖችንና አላውያን መሪዎችን ሁሉ አሜን ብለን እንድንሸከም የሚናገር ቃል አይደለም ከሚል ጽንሰ ሃሳብ የተነሳ እየታገሉ ይገኛሉ። አቶ ፍቅር ደግሞ በነዚያው ድረ ገጾች ስሜቱን በጽሁፍ እየገለጸ ሲያበቃ  ከወንጌል ቃል ጠቅሶ ለምግባረ ብልሹዎችና ለሥርዓት አፍራሾችም ቢሆን ተገዙ በማለት ሊያስተምረን ይፈልጋል። ምነው ጽሁፎቹን ለሚያቀርብባቸው ድረ ገጾች የእናንተ ተቃውሞ ቃለ እግዚአብሔርን የተጻረረና ሕገ እግዚአብሔርን ያፈረሰ ስለሆነ አርፋችሁ ተቀመጡ፤ ዝም ብላችሁም ለኢህአዴግ ተገዙ! የሚል ምክርና ጽሁፍ ያላቀረበላቸው? ብለን ስንጠይቅ የምናገኘው መልስ እኔና መሰሎቼ የምንጠላው ሲጻፍበት እንጂ የምናወዳቸው ሲነኩብን ያመናል የሚል ቃና ይሰጠናል።

አቶ ፍቅር ለይኩንም ይህንን የወንጌል ቃል እንደ ድረገጾቹ አምኖና ተቀብሎ  የጽሁፍ ዝንባሌውን በየድረ ገጾቹ እያቀረበ ሲገኝ  በተመሳሳይ መንገድ የወንጌልን ቃል በመጥቀስ የነውረኞች፤ የዘረኞችና የምግባረ ብልሹ ጳጳሳት ማንነት ሲገለጽ፤ የለም!  ለመሪዎች ዝም ብላችሁ ተገዙ፤ እንደዚያ የሚል ጽሁፍ ተጽፎ ይገኛልና በማለት ዝም ለማሰኘት ሲሞክር እጅግ ከማስገረም አልፎ ራስ ወዳድነቱ ግልጽ ሆኖ ይታየናል።
ምነው አቶ ፍቅር ለይኩን ወንጌል ለንጉሥ ተገዙ እንደሚለው ኢህአዴግ ከሰማይ የመጣ ነው መንግሥት ነው ብለህ በ«አሜን ወአሜን» ቃል የማትገዛው ለምን ይሆን? ለምንስ የአባ ጳውሎስን የቤተክህነት አስተዳደር ትቃወማለህ?
የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል እንዳለ ገልብጦ ከዐውደ ንባቡ ውጪ ለራስ ሃሳብ ማጠናከሪያ ማዋል አላዋቂነት ነው። ቃሉን ከእግረ ሊቃውንት ቁጭ ብሎ መማር ይቀድማል። ከዚያ ባሻገር የአቶ ፍቅር ለይኩን የሃይማኖት ቃል ማጠናከሪያ ጥቅስ ለአባቶች የጥብቅና ሥነ ሞገት እንዲያገልግል ተደርጎ እንደቀረበው ሁሉ ለመንግሥት አሜን ብሎ መገዛት እንደሚገባ ጥቅስ በማቅረብ መከራከር የሚቻል ቢሆንም ዐውዱን ላልተገባው መጠቀም እንዳይሆን  ጥቅሱን አለቦታው ከማቅረብ እንቆጠባለን።

አቶ ፍቅር ለይኩን  ምክሩን ሲቀጥል እንደዚህ  ሲል በርእሱ ይጀምራል።
«ይድረስ በአባቶቻችን ላይ የስደብና የማዋረድ ዘመቻ ለከፈታችሁ ብሎጎች፡- አባቶችን ማዋረድ የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር ማዋረድ ህልውናዋንስ መዳፈር እንደሆነ አታውቁምን…?!»
አዎ አባቶችን መሳደብና ማዋረድ ተገቢ አይደለም። የቤተክርስቲያኒቱንም ኅልውና መዳፈር ነው። በዚህ አባባልህ ላይ ምንም ጥያቄ የለንም። በአጭር ቃል እንስማማለን።
ይሁን እንጂ ችግሩ የሚመጣው እኔ «ፍቅር ለይኩን» የተባልኩት ሌሎች በሥጋ ድካም የሰሩትን ወይም ያደረሱትን በደልና ኃጢአት ስዘረዝር ትክክል ነኝ፤ ከኔ ውጪ ሲቀርብ ግን በፍጹም አያምርም የሚል የ«ዓይንህን ጨፍን ላሞኝህ» ፈሊጥ ሲቀርብን ግን ያሳፍራል። በወንፊት ጽሁፉ ውሃ ሊቋጥር የሚሞክርበትን  ይህን ጽሁፍ በዚህ ማስረጃ ውድቅ  ለማድረግ እንገደዳለን። በኢትዮ ሚዲያ ላይ ከወጣው ረጅም ጽሁፉ ውስጥ እንዲህ መዝዘናል።[ ሀ ]ሊንኩን ከግርጌ ይመልከቱ።
ፍቅር ለይኩን ለአንድ የእንጦጦ ራጉኤል ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በአንድ ወቅት የሙዚየም ጉብኝት ግብዣ ያቀርባል። መነኩሴው ለፍርሃት ማስታገሻ ይሁን ለጠላት መከላከያ ራሱ ብቻ በሚያውቀው ምክንያት ሽጉጥ ታጥቆ ይመጣል፤ ከሙዚየም መግቢያ ላይ ነገሩ ሊታወቅበት ስለሆነ መነኩሴው ለፍቅር ለይኩን መታጠቁን ያዋየዋል። እንደ ፍቅር ለይኩን ገለጻ ፈታሾቹም  እንደ መነኩሴው ትግሬዎች የነበሩ ሲሆን በቆቡ ምክንያት እምነት ተጥሎበት ሳይፈተሽ እስከነሽጉጡ ያልፋል። ከዚያ በኋላ ፍቅር ለይኩን እንዲህ ማለት የተሰማውን መተረክ ይጀምርልናል።
«መንፈሴ በእጅጉ ሐዘን ተሰማው። ለካ በወሬ ደረጃ የምሰማው ትክክል ነበር ማለት ነው? ታዲያ የእንጦጦ ጫካ ክፉ ክፉ አውሬዎችን ለመከላከል የተያዘች ሽጉጥ ምን ስትል መሃል አዲስ አበባ ድረስ ሽርሽር አማራት? ደግሞስ እስቲ ወገኖቼ ፍረዱ የእንጦጦ ጫካ ተመንጥሮ አልቆ ያፈጠጠ የቋጥኝ ድንጋይና የተራቆተ መሬት እንጂ ምን ጫካ አለው? የትኛውስ አስፈሪ አውሬ አሉበት?..............በማለት ይቀጥልና  በቅድስት ቤተክርስቲያናችን ስም የታጠቁና የተደራጁ የአባ ጳውሎስ ኃይሎች እንዳሉ በወሬ የሰማሁት አሁን በተግባር እውነታው ወለል ብሎ ታየኝ!»  ይላል ፍቅር በረጅሙ ትረካው።

ፍቅር ለይኩን አባቶችን ማዋረድ ወይም ገመናና ኃጢአት መጻፍ ትክክል አይደለም ሲል በአባ ሰላማ ድረ ገጽ ላይ ሊሞግት ሲፈልግ እራሱን ግን ከዚህ ውጪ ማድረጉ አስገራሚ ነው። መነኩሴው በሥጋ ድካም ይሁን በዓላማ ቢስነት የተነሳ ሽጉጥ ታጥቆ ሊሆን ይችላል። መነኩሴው አስተዳዳሪ ሆኖ ሲሾም በአባ ጳውሎስ የሽጉጥ ሽልማት ወይም የትጥቅ ስጦታ የተበረከተለት አስመስሎ በማቅረብ «በቅድስት ቤተክርስቲያናችን ስም የታጠቁና የተደራጁ የአባ ጳውሎስ ኃይሎች» በማለት በመነኩሴው ኃጢአት አባ ጳውሎስ በሌሉበት የሙዚየሙ የጉብኝት መድረክ ላይ አስቀምጦ ሲጨፈልቅ ትንሽ አይሰቀጥጠውም። መነኩሴውም ቢሆን በሥጋ ድካም ቢሸነፍና በእግዚአብሔር ላይ ያለው መታመን ቢሸረሸርና በምድራዊው ነገር ላይ ለመጣበቅ ከእምነቱ ቢወርድ  ይህንን ኃጢአትና በደል እንደትልቅ ዜናና ገድል ቆጥሮ የአንዱን ሰው ድካም ሁሉም እንዲያነበው በኢትዮ ሚዲያ ድረ ገጽ ላይ ማውጣትስ የቤተክርስቲያኒቱን ገመናና ጉድፍ አጋልጦ ለአጋላጭ መስጠት የማይሆነው እንዴት ነው? 

ሰዎች በመነኮሳትና በአባቶች ላይ የሚኖራቸውን እምነትና ፍቅርስ አይሸረሸርምን?  አቶ ፍቅር ለይኩን «ኢትዮ ሚዲያ» ድረ ገጽና በሌሎቹ ላይ የዚያን የደካማ መነኩሴ ኃጢአት ሲጽፍ ለአባቶች ዝናና ለቤተክርስቲያን ክብር  የጉድለት መግለጫ የማይሆነው  በምን ሎጂክ ይሆን? እሱ ስለደካማ መነኮሳትና ፓትርያርኩ ማንነት ሲጽፍ ትክክል ሲሆን ሌሎች ብሎጎች ግን ይህንን ዓይነት ለመጻፍ የወንጌሉ ጥቅስ ያግዳቸዋል፤ ይለናል መምህር ፍቅር ለይኩን!!
 እያለ ያለው «እኛ  በማይስማሙን ላይ ስንጽፍ እንጂ በተቀበልናቸውና ባከብራናቸው ሰዎች ላይ ሌሎች ሲጽፉ ማየት ያመናል፤ ማንበብም አንፈልግም፤ ምክንያቱም ይህ የቤተክርስቲያኒቱን ክብር ማዋረድ ይሆናልና» ነው የሚለው! 
አባ ጳውሎስ አስተዳዳሪ ለሚሆን ሰው ሥልጣንና ኃላፊነቱን የሚገልጽ ደብዳቤ እንጂ የሽጉጥ እንደማያስታጥቁ  አቶ ፍቅር ለይኩን አሳምሮ ቢያውቅም የአባ ጳውሎስን ኃጢአት ለማበራከትና ትግሬ መነኮሳትን ሁሉ ሽጉጥ ያስታጥቃሉ በሚል ጽንፍ  «የተደራጁ የአባ ጳውሎስ ኃይሎች» ለማለት ጥቂት አላንገራገረም። እንዲያውም «የአድዋ ሰዎች» በማለት ጎጥ እስከመጥራት ዘልቋል።

 አባ ጳውሎስና አስተዳደራቸው ችግር ቢኖርበት ይህንኑ መግለጽ ስህተት አለመሆኑን ብንቀበልም አቶ ፍቅር ለይኩን ይህንን መብቱን ለመጠቀም መቻሉን እንደአግባብነት ቆጥሮ ሌሎች ግን እሱ የማይቃወማቸውን ጳጳሳት ስህተትና ጉድለት መግለጽ ግን  የቤተክርስቲያንን ክብር ማዋረድ ስለሆነ  ዝም፤ ጭጭ በሉ ሲል ያስገርማል፤ ከመግረምም አልፎ ያሳዝናል።
በእውነትም ለሀገሪቱ ኪሳራና ጥፋት መስራት የሚገባቸውን ባለመስራታቸው ወይም መስራት የማይገባቸውን በማድረጋቸው የሃይማኖት መሪዎች እንደመሪነታቸው ለሚመሩት ሕዝብ ጉዳት ተጠያቂዎች ናቸው። ይሁን እንጂ የፈጠሩት ጉድለት፤ የፈጠሩት ሳንካ፤ በደልና ዐመጻ ካልተገለጸ ወይም ካልታወቀ እንዴት ማንነታቸው ሊታወቅ ይችላል? አቶ ፍቅር ለይኩን ሽጉጥ የታጠቀውን መነኩሴ እንደሃይማኖት አባትነቱ ማድረግ የማይገባውን በማድረጉ በዚያ ረጅም ጽሁፍ ጥፋተኛ አድርጎ የአባ ጳውሎስ ታጣቂ ሲያስመስለው በሌላ መልኩ «አባ ዲዮስቆሮስ የተባለ ጳጳስ ልጅ ወለደ» ሲባል ወይም እንደሙዳይ ተሸፋፍኖ ስንት የጥፋት ቅርስ በውስጡ እንደቋጠረ «ስለሙዳይ ጉዱ» ጳጳስ ሲገለጽ ግን የአባቶችን ክብር ማዋረድ ሆኖ ለቤተክርስቲያኒቱ የሚቆረቆር ሰው መምሰል በምንም መልኩ ከሚዛናዊ አስተሳሰብ የሚመነጭ ፍርድ አይደለም።
የሃይማኖት መሪዎች ያደረሱት ኪሳራና ጥፋት መግለጽ ካልተቻለ በምንም መንገድ ተጠያቂ ሊሆኑ ይችላሉ? «እናንተ ስለአባቶች ስትጽፉ ሳይሆን፤ እኔ ስጽፍ ብቻ ትክክል ይሆናል» የሚል የጉንጭ አልፋ ክርክር ውሃ አይቋጥርም።
አቶ ፍቅር ለይኩን  በዚያው ጽሁፉ ውስጥ የሃይማኖት ካባ ስለደረቡ አባቶች ድንቅ ሀተታ አቅርቦልን ነበር። እንዲህ ይነበባል።
ወደ ዋናው የጹሁፌ ጭብጥ ስመለስ ለዘመናት የሃይማኖት ካባን በደረቡ ፖለቲከኞችና ገንዘብ አምላኪ ይሁዳዎች፣ ሆዳቸው አምላካቸው ክብራቸው በነውራቸው በሆኑ ሰዎች ሲታመስና የኖረውና በሰይጣን ክፉ አሰራር የተተበተበው የቤተ ክህነቱ ተቋምና ቤተ ክርስቲያናችን፣ ለመታጠቅና ለማስታጠቅ፣ ለመግደልና ለማስገደል፣ ለዝርፊያና ምግባረ ብልሹነት፣ ለሴራና ለተንኮል ታሪክ አዲስ አይደሉም፤»
እዚህ ላይ ቆም ብለን ጥያቄ እናንሳ!  የሃይማኖት ካባ የደረቡ ማለት ምን ማለት ነው? በመንፈሳዊ ልብሳቸው የተደበቁ ፖለቲከኞችና ገንዘብ አምላኪ ይሁዳዎች እነማን ናቸው?  የት ነው ያሉት? ድርጊታቸውስ በምን በምን ይገለጣል?  ምን ምን አደረጉ? ሃሜት ሳይሆን እውነት የምታናገር ከሆነ ይህ ቢገለጽ ለእርማት አይጠቅም ብለህ ታስባለህ? እንደዚህ ስትል ማኅበረ ቅዱሳን እንዳይሰማህ! ምክንያቱም የማኅበሩ የስለላ መረብ የእያንዳንዱን ተጠርጣሪ የህይወት ታሪክ የሚያጠና የኤፍ-ቢ- አይ ዓይነት ክፍል ስላለው ማለቴ ነው፤ ዲ/ን ዳንኤል እንደተናዘዘው።
 መቼም ስለንፋስና ደመና ሳይሆን በሕይወት ስላሉና ይህ ተግባር እየታየባቸው ስለሚገኙ አባቶች እየተናገረ እንደሆነ እንገምታለን። ያንን መናገርና ማጋለጥ ካልተቻለ ማንነታቸው የሚታወቀው በምትሃት ነው ወይስ በጥንቆላ? አቶ ፍቅር ለይኩን የሚታወቅበትን ዘዴ ሊገልጽልን ይገባል። እስከሚገባን ድረስ ግን አቶ ፍቅር ለይኩን የአባ ጳውሎስን ወንጀልና ጥፋት በግልጽ እንደሚጽፍባቸው እናውቃለን።  ይሁን እንጂ ልጅ ስለወለዱ ወይም ስለዘራፊዎችና ዘረኞች ጳጳሳት ሲነገር ግን የቤተክርስቲያን ክብር ማዋረድ ይሆንበታል። 
በአንድ በኩል በመንፈሳዊ ልብስ ውስጥ የተደበቃችሁ ይሁዳዎችና ምግባረ ብልሹዎች በማለት ሁሉን ይጠቀልላል። በሌላ መልኩ ደግሞ እነዚህ ዓይነቶቹ አባቶች ሲገለጹ ደግሞ እኔ ከምለው ውጪ እነሱን አትነካኳቸው በማለት ከቤተክርስቲያን ክብር ጋር በማገናኘት ለመከራከር ይሞክራል።
ስለአባ ጳውሎስ አስገዳይነት፤ ዘረኝነት፤ ሃይማኖት የለሽነትና ምንፍቅና ስንናገር ትክክል ነው ካልን በአባ ጳውሎስ ፓትርያርክነት የተሾሙ ከ30 በላይ ጳጳሳት ሁሉ ፤ ሃይማኖትና ቅድስና በሌለው ፓትርያርክ ከተሾሙ  ጳጳስ ተብለው ሊጠሩ አይችሉም።  የአባ ጳውሎስን ግብር አጨልመን በቁራ ከመሰልናቸው የቁራ ልጆች ቁራዎች እንጂ ርግብ ሊሆኑ አይችሉምና ስለቁራ ስንናገር በዚያው ምሕዋር ውስጥ ያሉት ሁሉ ሊጠሩ የግድ ይሆናል። ስለአባ ጳውሎስ ቁራነት እንጂ ስለቁራ ልጆቻቸው አትናገሩ! ማለት ግን እብደት እንጂ ጤንነት አይደለም።
 ሳናበላልጥና ሳንከፋፍል ከየትኛውም ወገን ያለውን ስህተት፤ ምግባረ ብልሹነትና ዘረኝነት እንዲታረምና እንዲስተካከል  እንደተነገረው ቃል ብንናገር ምንም አያስነውርም።
«እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ፥ ወዮላችሁ።
እንዲሁ እናንተ ደግሞ በውጭ ለሰው እንደ ጻድቃን ትታያላችሁ፥ በውስጣችሁ ግን ግብዝነትና ዓመፀኝነት ሞልቶባችኋል» ማቴ 23«27-28 እንላቸዋለን።
አቶ ፍቅር ለይኩን በደቡብ አፍሪካ አባ ኃ/ማርያም ስለተባሉ መነኩሴ መቶ አለቅነትና ወንጀለኝነት በአንድ ወቅት የጻፈውን ጽሁፍ አስታውሳለሁ። እሱም ያስታውሰዋል። ዛሬ ግን ያንን ሁሉ ዘንግቶ ደርሶ ጻድቅ ለመምሰል ሲከጅል ያስገርማል።  ሃሳቡ ጥሩ ቢሆንም «እኔ ትክክል፤ ሌላው ስህተተኛ »  የሚል ሙግት፤ ጣፊ ለጣፊ ያሰኛል እንጂ ሀቀኛ አያደርግም።
በዚህ ጉዳይ የሚጠቀሱት ጥቂት ወሮበሎች እንጂ አብዛኛዎቹ አባቶች ሌላ ነገር ማድረግ ባይችሉ እንኳን፤ በዝምታ ወደፈጣሪያቸው የሚያነቡና የሚያለቅሱ ናቸው።  ፍየሎቹ ያስቸገሩት በየደረሱበት ሚያ! እያሉ ገበናቸውን ሰው ሁሉ እንዲሰማው ስለሚጮሁ ጥፋቱ የራሳቸው የጩኸት አፍ ነው።
ሌላው የአቶ ፍቅር ለይኩንን ጽሁፍ አስገራሚ የሚያደርገው አባ ፋኑኤልን፤ አባ ሠረቀ ብርሃንንና አባ ጳውሎስን  ሲሰድቡና ሲዘልፉ፤ /Axis of corruption & evil/ እያሉ የኖሩ ብሎጎች ሁለትና ሦስት ዓመት አልፏቸው ሳለ ምንም ሳይናገር ቆይቶ፤ ዛሬ እንደባህታዊ የሚቆጠሩ ግን ዘረኝነታቸውን በ 100 ማስረጃ ማረጋገጥ የሚቻልባቸው የአባ ቀውስጦስና የጉድ ሙዳዩ ጳጳስ ስም ሲነሳ ከእንቅልፉ መንቃቱ አስገራሚ ይሆናል።
ምነው ያኔ የቤተክርስቲያን ክብር ተዋረደ ለማለት ያልደፈረ? እንዲያውም በነዚያ ብሎጎች የአቶ ፍቅር ለይኩን ጽሁፎች ይስተናገዱ እንደነበር እናውቃለን። [ ለ ]
ከስሜት አባባሎቹ መካከል አቶ ፍቅር ለይኩን የአቡነ ሚካኤልና የአባ አብርሃም/ የጉድ ሙዳይ/ ስም መነሳት እንደከነከነው ለመናገር ሞክሯል። ጳጳስ ስለመሆን የቤተክርስቲያኒቱ ህግጋት ምን እንደሆነ ከመናገር ይልቅ ህጉን የጣሱ ሰዎች ስም ሲነሳ መንጫጫት ምን ይባላል? ወይ ሕጉ ተሽሯል በሉና ጵጵስናውን በማስታወቂያ ሁሉም የሚወዳደሩበት ክፍት የሥራ መደብ አድርጉ! አለበለዚያም እንደሕጉ ሳይኖሩ ስማቸው ለምን ይነሳል በማለት ማልቀስ ዋጋ የለውም።
ዮሐንስ ሚካኤል የተባለው ወጣት በመደበኛ ፍርድ ቤት ወላጅ አባቱ ጳጳስ መሆኑንና ህጋዊ ወራሽነቱን ካረጋገጠ ስለገመናቸው ኃላፊነቱ የራሳቸውን እንጂ የሌላ የማንም ሊሆን አይችልም።
ትልቁ አባት ብጹእ አቡነ መርሐ ክርስቶስ እነዚህንስ ብንድራቸው ይሻላል ያሉት ለቤተክርስቲያኒቱ ክብር ከማሰብ እንጂ የአባቶችን ገመና ከመዘክዘክ አንጻር አልነበረም። አሁንም ጋብቻ ክቡር ነው የምንለው ጋብቻቸውን ህጋዊ እንዲያደርጉ፤ በየሜዳው እየወለዱ በየፍርድ ቤቱ ክስ እንዳይጎትቱ፤ ዘረፋና ዘረኝቱን እንዲያቆሙ፤ ኃጢአታቸውን እያሰቡ እንዲኖሩ መናገር ተገቢ ነው። የታወቀ ኃጢአታቸው እንዲሸፈን ወደ አንድ ማኅበር ጉያ በመደበቅ ከንስሐ ይልቅ ለጩኸት የሚነቁ የጉድ ሙዳዮች  ቢገለጡ አያስነውርም።
የማርቆስ ወንጌል 4፥22
እንዲገለጥ ባይሆን የተሰወረ የለምና፤ ወደ ግልጥ እንዲመጣ እንጂ የተሸሸገ የለም።
ሥረ ነገሩ የሰውን ኃጢአትና ገመና መዘርዘር ተደርጎ መታየት የለበትም። ሊታይ የሚገባው እንደተጠሩበት አገልግሎት በመንጋው ጥበቃ ላይ መገኘት ባለመቻላቸውና ከፋፋይ፤ አድርባይና ዘረኛ ማንነታቸው እያደረሰ ካለው ጉዳት  አንጻር ነው።
ሲጠቃለል አቶ ፍቅር ለይኩን «እኔ ብቻ ስናገር ያምራል» የሚል ድምጸት ያለው የጽሁፍህ ትችት ውሃ እንደማይቋጥር ወንፊት ከመሆን የዘለለ አይደለም።