Monday, October 5, 2015

ስለአንዳንድ በኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ ላይ…ከአንዳንድ የኦሮሞ ጸሐፍት የተሰነዘሩ…ያስቀየሙኝ ክታቦች!!


በአማን ነጸረ ፣ መስከረም 10 ቀን 2008 ዓ.ም

የታላላቅ ኦሮሞ ወንድሞቼን ቅሬታ የተጫናቸው ጽሑፎች አንብቤ ቅር አለኝ፡፡መነሻ የሆናቸውን ታሪካዊ በደል ለመረዳት አልሰነፍኩም፡፡ያም ሆኖ መስመር ያለፈና ባንድ ቦይ ብቻ የፈሰሰ በመሰለኝ ቅሬታቸው ቅር አለኝ፡፡ቅሬታዬ ቆየ፡፡ፈራሁ፡፡ከዚህ በላይ በሆዴ ከቆየ ቂም ይሆንና ይጎዳኛል ብዬ ፈራሁ፡፡ስፈራ ቅሬታዬን በረጅሙ (በፌስቡክ ስሌት ነው ርዝማኔው መጉላቱ) ጻፍኩት፡፡ሆኖም ስጽፈው ከ3 ችግሮች እንደማልነጻ አምኜ ነው፡፡አንድም በሁለንተናዬ ስላደኩበትና አሁን ድረስ በዕለት ኑሮዬ ስለሚደጉመኝ እንዲሁም የማኅበራዊ መደብ ጀርባዬ ስለሚመዘዝበት ተቋም ስናገር ንግግሬ ከሚዛናዊነት ይልቅ ወደ ተከላካይነት (advocacy?) እንደሚያጋድል ይታወቀኛል፡፡ሲቀጥል አማተር ነኝና የአጻጻፍና የማስረጃ ስደራ ችግር አያጣኝም፡፡እንዲያም ሲል ከሃይማኖት-ፖለቲካ ተዛምዶ አንጻር ያለኝ አረዳድና ንባብ ድኩም መሆኑን አልስተውም፡፡በተረፈ ‹‹አንዳንድ›› ብዬ የምጠራቸውን የኦሮሞ ጸሐፍት በስም ጠቅሻለሁ፡፡ጉዳዬ ስለክታባቸው ያውም ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን (ከአሁን በኋላ የኢኦተቤክ) በማስመልከት ስለጻፉበት ነጥብ ብቻ ነው፡፡ከዚህ ውጭ እነሱም ሆነ ሌሎች ጸሐፍያን ስለሚያነሱዋቸው ተያያዥ ጉዳዮች መጻፍ የዚች ትሑት (ታናሽ) ጽሑፍ ዐላማ ስላልሆነ ተዛማጅ ጉዳዮችን አለመንሳቴን በአትሕቶ-ርእስ እገልጻለሁ፡፡
በዚች ጽሑፍ የማተኩርባቸው ቅሬታዎች፡- (1)የኢኦተቤክ ደባትር ‹‹ጋላ›› የሚለውን ቃል ሆን ብለው ኦሮሞን ለማሳነስ ፈልስፈዋል፣(2)የኢኦተቤክ ሥርዓት እኩልነትን አይቀበልም፣(3)አቶ አጽሜ እና አለቃ ታዬ የኢኦተቤክ ደባትር ናቸው፣(4) የኢኦተቤክ ለአፋን ኦሮሞ ጽዩፍ ናት፣(5)በኢኦተቤክ እልህ የተነሳ ወለጋ ፕሮቴስታንት ሆነ፤ጅማ፣ወሎ፣አርሲ እና ሐረር ሰለሙ፣(6)የኢኦተቤክ አስተምህሮ ከኦሮሞ ባሕል ጋር ተጻራሪ ነው፣(7)የኢኦተቤክ ካሕናት በሲሶ ገዥነት በኦሮሞ ምድር የመሬት ከበርቴች ነበሩ የሚሉ ናቸው፡፡አሁን ቀጥታ ወደታመቀው ክስና ሐተታዬ….

1-- ክስ አንድ፡- ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል የኢኦተቤክ ደባትር ፈጠራ ነው!!

‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል ‹‹የአቢሲኒያ ቤተክሕነት ፈጠራ ነው›› ይላሉ እነ አባስ ሐጂ(ዶ/ር)፡፡‹‹ጋላ›› = መጻተኛ (stranger/outsider) የሚለው አገላለጽ የአቢሲኒያ ቤተክሕነት ፖለቲካዊና ርዕዮተ-ዓለማዊ አመክንዮ ያለው ፈጠራ ነው-- “fabricated by an Abyssinian clergy for politico-ideological reasons” ይሉናል (Mekuria cited in Being and Becoming Oromo: Re-examining the Galla/Oromo Relationship,p.105)፡፡ይቺን አገላለጽ በክብር እቃወማታለሁ፡፡ምክንያቱም በበኩሌ ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል በዚያ መልኩ በኢኦተቤክ የሃይማኖታዊ ሥርዓት መከወኛ መጻሕፍት ተጽፎ እና ተተርጉሞ አላገኘሁትም፡፡አውቃለሁ፡፡ብዙ የኦሮሞ ጉዳይ ጸሐፍት በ1960ዎቹ በ‹‹ራዕየ-ማርያም›› የወጣውን ስርዋጽ (ሆን ተብሎ በእኩያን የተጨመረ--ስረ-ወጥ--ከስር ያልነበረ) ጽሑፍ ይጠቅሳሉ፡፡እንደማመጥ፡-
(1.1) እሱ ስርዋጽ በኢኦተቤክ ደረጃ በሊቃውንትና በቅ/ሲኖዶስ ተመክሮበት ወይም በማናቸውም ከኢኦተቤክ አስተዳደር ጋር ግንኙነት ባለው አካል ፈቃድ/ትእዛዝ/ የወጣ አይደለም፡፡
(1.2) ስርዋጹ የኦሮሞን ብቻ ሳይሆን የሙስሊም፣የፈላሻ (ቤተ-እስራኤል) እና የሻንቅላ (ቤንሻንጉል-ጉሙዝ) ሕዝቦች ክብርንም እየጠቃቀሰ ኢ-ክርስቲያናዊ በሆነ መንገድ ያጎድፋል፡፡ታዲያ ያስተዋለ ሰው በግእዝ ቋንቋ ‹‹ሸ›› የሚባል ፊደል የማይታወቅ ሆኖ ሳለ በስርዋጹ ‹‹ፈላሻ እና ሻንቅላ›› የሚሉ ‹‹ሸ›› የበዛባቸው ቃላት በመታየታቸው ብቻ ተራ የእኩያን ጭማሪ (ስርዋጽ) መሆኑን መረዳት ይችላል፡፡እንዲህ ዐይነት ስርዋጽ ጽሑፎች ከዚህ በፊትም ከአንዳንድ ገድላትና ዜናመዋዕሎች ጋር ጎጃምን እንደ አገርና ሕዝብ በተለየ መልኩ ለማነወር በኵሸት ሕዝቡን ‹‹በላዕተ-ሰብእ (ቡዶች)››፤ሀገሩን‹‹ሀገረ-በላእተ-ሰብእ (የቡዶች ሀገር)›› የሚል ተቀጽላ ለመስጠት ተሞክሮ ሊቃውንቱ ታግለው ስርዋጹን ከኅትመት ከልተውታል፡፡ግብጻውያን በፍትሐ-ነገሥቱ ላይ የጨመሩት ‹‹የኢትዮጵያ አዋቂዎች ከራሳቸው ሊቅ ጳጳስ አይሹሙ›› የሚለውና በስንክሳር እስከዛሬ ለታሪክ ተመዝግቦ የሚገኘው ‹‹ኢትዮጵያውያን ከራሳቸው ሰው ጳጳስ ለመሾም ስላሰቡ መቅሰፍት ወረደባቸው›› የሚል ስርዋጽ በገቢር ከ1920ዎቹ ጀምሮ ቢሻርም ስርዋጹ ዛሬም አልተፋቀም፡፡እንዲህ ሲያጋጥም ለፍረጃ ከመሽቀዳደም ስርዋጹን ለማስተካከል ከመጣር በተጓዳኝ ገቢራዊነቱንም መፈተሽ፡፡
(1.3) ገቢሩ ሲፈተሸ ብዙኃን ኦሮሞ-ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ይህ ‹‹ጋላ ጋር የተኛ…›› የሚል ስርዋጽ ከመውጣቱ በፊት፣በወጣበት ጊዜ እና ከወጣም በኋላ በኢኦተቤክ ከተራ ካሕን እስከ መዓርገ-ጵጵስና ሲያገለግሉ ነበር፡፡አሁንም ያገለግላሉ፡፡ይሕም ስርዋጹ በምንም ተአምር ከኢኦተቤክ እንደማዕከላዊ ተቋም ታዝዞና ኃላፊነት ተወስዶ እንዳልገባ ገቢራዊ ማሳያ ነው፡፡ለነገሩ በ1960ዎቹ ብልጭ ብሎ የጠፋው ባለስርዋጽ መጽሐፍ አሳታሚና ማ/ቤቱም የኢኦተቤክ ንብረት አልነበሩም፡፡
(1.4) በምዕመን ደረጃ የኢኦተቤክ ብሔር ለይታ ‹‹እከሌን አግቡ፣እከሌን አታግቡ›› አትልም፡፡የመጣው ሁሉ ክርስትና ይነሳል፡፡ክርስትና ተነስቶ አቅመ-አዳም/ሔዋን የደረሰው ሁሉ ጋብቻው በሥርዓተ-ተክሊል ይፈጸምለታል፡፡ይሕ ድርጊት ብሔር አይለይም፡፡በዚህ መንገድ ቁጥራቸው አያሌ የሆነ ኦሮሞ ኦርቶዶክሳውያን በቅድስት ቤ/ክ እርስ በርሳቸውና ከፈቀዷቸው ብሔረሰቦች ተወላጆች ጋር በሥጋ ወደሙ ተወስነው ጋብቻ ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡እየፈጸሙ ነው፡፡ስለሆነም ከ‹‹ጋላ ጋር የተኛ›› እያለ የኵነኔ ፍርድ የሚሰጠው ስርዋጽ የኢኦተቤክ ያላትን አሰራር በቃልም በተግባርም አይገልጽም፡፡ምክንያቱም ጽሑፉ--ስርዋጹ የእርሷ ስላልሆነ!!
(1.5) እስከማውቀው በኢኦተቤክ የኦሮሞ ሕዝብ እና ታሪክ ከሌሎች ተለይቶ በአሉታ አይታይም፡፡ምክንያቱ ግልጽ ነው፡፡በቅርብ ዓመታት በአንዳንድ የኦሮሚያ አካባቢዎች ኦርቶዶክሳውያንን በጫና የማስለምና የማጰንጠጥ ሙከራዎች ብቅ ማለት ቢጀምሩም በረጅሙ የኦሮሞ ሕዝብ ታሪክ ሕዝቡ እንደ ሕዝብም ሆነ የአስተዳደር ሥርዓቱ (ገዳ) በሌላው ሕዝብ ላይ የሃይማኖት ማንነትን በኃይል የመጫን ባሕል አልነበረውም፡፡የ16ኛው ክ/ዘ የኦሮሞ ጦርነቶችም ሃይማኖታዊ ገጽታቸው ጎልቶ ሲነገር አልሰማንም፡፡ሃይማኖት ጫና ካልተደረገበት ደግሞ ሃይማኖታዊ ሰማዕትነት የለም፡፡ስለዚህ የዮዲት፣የሱስንዮስ፣የግራኝ መሐመድ፣የደርቡሽ፣የጣሊያን፣የደርግ እና የ20ኛው ክ/ዘመን የአክራሪ እስልምና ጥቃቶች በኢኦተቤክ መዛግብት በ‹‹ዘመነ-ሰማዕታትነት›› ሲመዘገቡ የኦሮሞ ታሪክ እንደ ብሔር በዚያ መልኩ አልተካተተም፤ድሮም አሁንም፡፡ስለሆነም ያን ያህል ብሔሩን ለማሳደድና የተለየ ስም ለመስጠት የሚያበቃ ቅራኔ በኢኦተቤክ በኩል አልነበረም፤የለም፡፡
(1.6) ወደ ቤተ-መንግሥቱ ደባትር እንሂድ፡፡እውነት ነው፡፡የቀድሞ ነገሥታት ዜና-መዋዕል ጸሐፊዎች በኢኦተቤክ የተማሩ ሊቃውንት ናቸው፡፡ቅብዐ-መንግሥት ቀብተው የሚያነግሡ አንጋሾችም የኢኦተቤክ ጳጳሳት (በዜግነት ግብጻውያን ጳጳሳት) ነበሩ፡፡ነገሥታቱ ኦርቶዶክሳውያን የነበሩ መሆናቸው እውነት ነው፡፡ነገሥታቱ በአገዛዛቸው ዘይቤ ኦርቶዶክሳዊነት የተጫነው religious nationalism አዝማሚያ እንደሚያሳዩና ለኢኦተቤክ አበው የተለየ ውዴታና ከበሬታ እንደነበራቸውም አይታበልም፡፡ኦርቶዶክሳውያን አበው (ጳጳሳት) ንጉሡ በእነሱ እምነት ማደሩን እና እስከ ፍጻሜ ዘመኑም በእምነቱ እንደሚጸና ቃል አስገብተው ይቀቡት እንደነበር እሙን ነው፡፡ይሄ አሰራር ይብዛም ይነስም በሁሉም ቀደምት የነገሥታት ሥርዓት በሰፈነባቸው አህጉር ያለ ነው፡፡በኦሮሞ ጥንታዊ የገዳ ባህልም ተሞክሮው ያለ ይመስላል፡፡ለአባ ገዳነት ለመብቃት ቅብዐተ-ቃሉ (በቃሉ መቀባት) ስለማስፈለጉ ታቦር ዋሚ ብሩ ጸጋዬን ጠቅሶ ሲጽፍ ‹‹…ለአባ ገዳነት ለመብቃትም ዋነኛው መመዘኛ የዋቄፈና ሃይማኖትን አክብሮና የሕዝቡን ወግና ሥርዓቶች ተከትሎ መገኘት ሲሆን…የሉባዎች ስልጣን የሚጸድቀው በቃሉ (አባ ሙዳ) የቡራኬ፣የምርቃትና መቀባት ሥርዓት ነው›› ይላል (ታቦር ዋሚ፡ገ.248)፡፡እርግጥ የአባ ገዳ ሲመት በዘር ሳይሆን በምርጫ መሆኑ ተራማጅ ያሰኘዋል፡፡
(1.7) ወደ ሐተታዬ ስመለስ ነገሥታቱ ለኢኦተቤክ እንደሚባለው ‹‹ሲሶ መንግሥት›› ባይሆንም መጠነኛ እርዳታ ሲያደርጉ መኖራቸውም እውነት ነው፤ኦፌሴላዊ ቋንቋቸውም ለረጅም ጊዜ የኢኦተቤክ መገልገያ የሆነው ግእዝ እንደነበረም እናውቃለን፡፡ያ!ማለት ግን ዜና-መዋዕል ጸሐፊዎች በግእዝ የሚጽፉት ሁሉ የኢኦተቤክ ዶግማና ቀኖና ነው፤ወይም የኢኦተቤክ የውዳሴና ቅዳሴ ዶክመንት ነው ማለት አይደለም፡፡ግእዝ ቋንቋ ነው፡፡እምነት፣ፍልስፍና፣ኑፋቄ፣ታሪክ፣ጥንቆላ፣…ይጻፍበታል፡፡ስለዚህ ይሄን ሳያስተውሉ የኢኦተቤክ በግእዝ ቋንቋ ለተጻፈ ዶክመንት ሁሉ (በተለይ ለነገሥታ ዜና-መዋዕል) ኃላፊነት አለባት ማለት በላቲን ፊደልና ቋንቋ ለተጻፈ ሁሉ ካቶሊኮች ተጠያቂ ናቸው፤ወይም ደግሞ በዐረብኛ ለተጻፈ ሁሉ እስልምና ተጠያቂ ነው እንደማለት ይሆናል፡፡
(1.8) ‹‹ጋላ›› ወደሚለው ቃል አጠቃቀም ልምጣ፡፡ዛሬ አንዳንድ ኦሮሞ ወንድሞቻችን ሚሽነሪዎች ‹‹ጋላ›› የሚለውን ቃል ስለማይጠቀሙ ወደ ወለጋ ያቀኑ ሚሽነሪዎች ተቀባይነት አገኙ ይሉናል፡፡ሸጋ፡፡ሚሽኖችን እንስማቸው፡፡<<The Missinories referred to the Oromo as the Hamitic [non-semetic] GALLAS who spoke GALLINYA.They used this condescending term…as late as 1973, nearly ten years after working with Oromo…>>ይላሉ(GilchrristII:73) (አጽንኦቱ የኔ ነው)፡፡የሚያሳዝነው እነዚህ የፕሮቴስታንትና የካቶሊክ ሚሽኖች ከ10 ዓመትና ከዚያ በላይ (ለምሳሌ፡- የMissio-Galla ባለቤቱ ካቶሊኩ አባ ማስያስ ከ145-1880 ዓ.ም ለ35 ዓመታት እንዲሁም የVicariatus Apostolici apud Gallas Commentarium Historicum ab erectione Vicariatus usque hodie ባለቤቱ አባ ጃሮሶ ከ1882-1938 ዓ.ም ለ46 ዓመታት) በኦሮሞ ሕዝብ መካከል ቋንቋውን (አፋን ኦሮሞ) እየተናገሩ ኖረው በእንግሊዝኛና ጣሊያንኛ ተጠቃሽ መጻሕፍቶቻቸው ‹‹ጋላ›› የሚል ቃል የሚጠቀሙት ‹‹በአቢሲኒያ ቄሶች›› ተጽእኖ እንደሆነ ለማስመሰል ይሞከራል፡፡ያሳዝናል፡፡መቼም ‹‹የአቢሲኒያ ቄሶች›› ተጽእኖ አውሮፓና አሜሪካ ድረስ ተጓጉዞ ለሚታተም የሚሽነሪ መጽሐፍ እንዴት ተጽእኖ ፈጣሪ እንደሚሆን እነሱና ደቀ-መዛሙርቶቻቸው ብቻ ናቸው የሚያውቁት!!
(1.9) ወደ ቤ/ክ መጻሕፍት እንመለስ፡፡ቢያንስ ስለቅኔ ቤት እና ዜማ ቤት ምስክር መሆን እችላለሁ--ስላለፍኩባቸው፡፡በነዚህ ጉባኤያት ‹‹ጋላ›› የሚል የግእዝ ቃል አልሰማንም፡፡በሌላ በኩል በውዳሴ ማርያም የአንድምታ ትርጓሜ የ1990 እትም ላይ በገጽ-86 እንዲህ የሚል ቃል ይገኛል ‹‹…በግብፅ የሚገኙ መነኮሳት በአመት ሁለት ጊዜ ያበስላሉ፡፡…ከአኃው [መነኮሳት] አንዱ ቢታመም ትኩስ እንጀራ የሚያመጣልኝ ባገኘሁ በቀመስሁት ነበር አለ፡፡ከዚህ በኋላ አንዱ የማን ወንድም ትኩስ እንጀራ እያለ ይሞታል ብሎ በመካከሉ <በርበር የሚባል ጋላ> ያለበት ነው፤ያንን አልፎ ሄዶ አምጥቼልሀለሁ ቅመስ አለው…›› እያለ ‹‹ጋላ›› ማለትን ለሽፍታ በርበር ሰጥቶ ይተርክልናል፡፡ በቅ/ያሬድ የኅዳር 29 የተፍጻሜተ ሰማዕት ቅ/ጴጥሮስ ድጓና በእለቱ ስንክሳር ‹‹ጋላት›› (በግእዙ ‹‹ላ›› ላልቶ ነው የሚነበብ) የሚል ቃል ይገኛል፡፡ቅ/ያሬድ በዐረብ ምድር በ4ኛው ክ/ዘ ስለተሰዋው ተፍጻሜተ - ሰማዕት ጴጥሮስ ሲያዜም ‹‹…አባ ጴጥሮስ ተፍጻሜ-ሰማዕት፣መጠወ ርእሶ ለ‹ጋላት›….›› ይለናል፡፡ቅ/ያሬድና የውዳሴ ማርያም መተርጉማን ቃሉን ለሰሜን አፍሪካ ኢ-ክርስቲያን የ3ኛው መቶ ክ/ዘ በርበሮች ሰጥተው ነው የሚናገሩት፡፡ከዚህ ውጭ እኔ ባጭር ዘመኔ ባነበብኳቸው የኢኦተቤክ መንፈሳዊ መጻሕፍት ‹‹ጋላ›› ስለሚለው ቃልና ስለብያኔው አላገኘሁም፤አልተማርኩም፡፡በቅኔ ቤት ‹ደብተራ› ተብለን የተማርንበት የእጅ ጽሑፍ ግስ (መዝገበ-ቃላቱን ግስ እንለዋለን) ‹‹ጋላ›› የሚል ቃል በፍጹም የለውም፡፡የእጅ ጽሑፉ ዛሬም በመጽሐፍ መደርደሪያዬ ያለ ነው፡፡
(1.10) ስለሆነም ይሕን ቃል ‹‹የኢኦተቤክ ደባትር ፈጠራ ነው›› በሚል ድምዳሜ ቤተክርስቲያኒቱንና ሊቃውንቷን በምልዐት ከሥርዓታቱ ጋር አላጥቆ ፈርጆ በጭፍን ከማሳደደድ በፊት ግራቀኙን ማየት አይከፋም፡፡ቢያንስ በተጓዳኝ የዚህን ቃል ምንጭ ዐማራን ጨምሮ በከፋ፣ሐዲያ፣ሲዳማ፣ጋሞ፣ትግራይ፣ሶማሌ….ከመሳሰሉ ብሔረሰቦች ቋንቋ ውስጥ ማሰስ፣ወደ ጎረቤት ሶማሊያና ኬንያ የታሪክ ጽሑፎች ጎራ ብሎ መጠየቅና ሰነድ ማገላበጥ፣ከሩቅ ዘመን ጀምሮ በምድረ-ኦሮሚያ ኖረው በአውሮፓ መጻሕፍትን ያሳተሙ የሚሽነሪ ጽሑፎችን በጥንቃቄ ማገላበጥ የተሻለና ሚዛናዊ መደምደሚያ ላይ ለመድረስ የሚረዳ ይመስለኛል፡፡Thomas Zitelman የተባለው ጸሐፊ በBeing and Becoming Oromo የጥናት መጽሔት Re-Examining the Galla/Oromo Relationship የተሰኘ ጽሑፉ ዘመናዊውና የታደሰው የኦሮሞ ማንነት ቅርጽ የያዘው በስዊድን ሚሽነሪዎች ነው የሚል ምልከታውን ገልጹዋል፡፡እንጥቀሰው <<During the late 19th C the Swedish Protestant missionray activities at Monkullo [Eritrea] provided a contextual frame for a modern reformation of being Oromo, by mixing Protestant zeal,romantic European nationalism and elements of Oromo past>> >>ይላል(Being and Becoming Oromo:p.108)፡፡እንጠርጥር ካልን ይቺ ጽሑፍ የሚሽነሪዎች ተጽእኖ በጎላባቸው የኦሮሚያ አካባቢዎች ሰባክያኑ ከስብከታቸው ጋር ‹‹የአቢሲኒያዎች ቤ/ክ ለኦሮሞ ‹ጋላ› የሚል አዋራጅ ስም ስላወጣች አትሆናችሁምና አዲስ ማንነት በፕሮቴስታንታዊነት ተላበሱ የሚል ብሔር-ተኮር ቅስቀሳ በወለጋ አካባቢ ሳይካሄድ እንዳልቀረ ታመላክታለች›› ብለን መጥርጠር ይቻላል፡፡ይቺ-ይቺ ፀረ-ተዋሕዶ የሚሽኖች ስብከት ተጠራቅማ የኦሮሞ ማንነትን በአዲስ እይታ ለመቅረጽ የተጉ ምሁራነ-ኦሮሞ የሆኑ ጸሐፍት ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል--“fabricated by an Abyssinian clergy for politico-ideological reasons” እያሉ ለጥጠው እንዲጽፉ አበረታታች፡፡ጥርጣሬዬ ነው!!!የሚሽነሪዎቹ ተደጋጋሚ ጸረ-ተዋሕዶ ምዕራባዊ ጽሑፎች የወለዱት ጥርጣሬ!!

2-- ክስ-ሁለት፡-የኢኦተቤክ መዋቅር እኩልተኛ ስላልሆነ ኦሮሞዎች አይጋሩትም!!

የታሪከ-ኦርቶዶክስ ሊቅ ተደርጎ በነመሐመድ ሐሰን (ዶ/ር) እና በነአባስ ሐጂ (ዶ/ር) እዚህም እዚያም የሚጠቀሰው መኩሪያ ቡልቻ (ዶ/ር) <<Oromo Orthodox Christians, though they share religion with Abyssinians, do not share the political/ideological orientation of the Ethiopian Church whose main interest was the preservation [of] structural inequalities enshrined in myths and legends>>ይሉናል(Mekuria cited in Abbas Haji:106)::ታድለው!እዚህ መደምደሚያ ላይ ለመድረስ <የታለ ያደረጋችሁት የመስክ ጉብኝት፣የታለ ለኦሮሞ ኦርቶዶክሳውያን የተደረገው ቃለ-መጠይቅ፣የታለ በየሃማኖቶቹ መካከል ለንጽጽር የሰራችሁት የዳሰሳ ጥናት?> የሚላቸው የለም፡፡የፈለጉትን ቢጽፉ ቋንቋው እንግሊዝኛ እስከሆነ ድረስ ‹‹የደብተራ ተረት›› አይባልባቸውም፡፡ታድለው!ከዚህም ከዚያም እያገጣጠሙ ለያዙት ዐላማ እና ለታደሙበት ድርጅት የሚሆን ታሪክ በልክ ይሰፋሉ፡፡ወደ ሕዝቡ ወርደው አያጠኑም፡፡ብቻ መርጠው ይተነትናሉ፡፡ታሪክ ማለት ትንታኔ፤ትንታኔ ማለት ታሪክ ይሆናል፡፡
(2.1) እስኪ የኢኦተቤክ አደረጃጀት ይታይ፡፡ጥንት ‹‹የሊቃውንት ጉባኤ/ማኅበረ-መነኮሳት/ማኅበረ-ካሕናት›› የተሰኘ የውስጥ ሃይማኖታዊ አስተዳደሩን፣ዶግማና ቀኖናውን የሚበይን አካል ነበረ፡፡ከ1951 ዓ.ም ጀምሮ የኢኦተቤክ ከግብፅ መንፈሳዊ የሞግዚት አስተዳደር ነጻ ወጥታ የራሷን ቅ/ሲኖዶስ ሰይማለች፡፡ፓትርያርኩ ከፋም ለማም ላለፉት 56 ዓመታት የሚሾመው በምርጫ ነው፡፡በአጥቢያ ደረጃ ባለው አደረጃጀት ከምዕመናንና ካሕናት የተውጣጣ ‹‹ሰበካ-ጉባኤ›› የተሰኘ አካል ከ1960ዎቹ መጀመሪያ ዓመታት ጀምሮ እስካሁን ድረስ በ3ቱም ሥርዓታተ-መንግሥታት ያለማቋረጥ እየተመረጠ ቤ/ክ’ንን በማስተዳደር ላይ ይገኛል--ከፋም ለማም፡፡በደርግም አልተቋረጠም፡፡መራጩ ምዕመኑና ካሕኑ ነው፡፡እርግጥ <ዲሞክራሲ፣አሴምብሊ፣ካውንስል፣…> የሚሉ ቃላትን ባለመጠቀማችን ዲሞክራሲ ላይ በኋላቀርነታችን ለሰራነው በደል ዘመናዊ ዲሞክራት ጸሐፊዎቻችንን መጠየቅ ይኖርብናል!!
(2.2) እገምታለሁ፡፡ይሕ የ40 እና የ50 ዓመታት ተሞክሮ የሃይማኖቱን ብሉይ ታሪክ አይገልጽም ይባል ይሆናል፡፡ገዳማቱ ይመርመሯ!!!በስተሰሜኑ ማዕከላዊ ኦሮሚያ ያለውን ገዳም እንምረጥ--የሰላሌውን ደ/ሊባኖስ!!የገዳሙ መሪ ጥንት ‹እጨጌ› አሁን ‹ፀባቴ› ይባላል፡፡ብቻውን በገዳሙ ላይ የማዘዝ መብት የለውም፡፡<ምርፋቅ> በሚል ስም የሚጠራ 12 ተመራጭ መነኮሳት የሚሰየሙበት የመማክርት ጉባኤ አለ፡፡መራጮቹ የገዳሙ አባላት (መነኮሳት) ናቸው፡፡ተመራጮቹ አጠቃላዩን የገዳሙን ሕግ ከጸባቴው (አስተዳዳሪው) ጋር በመሆን ይደነግጋሉ፤ያጠፋውን ቀኖና ይሰጣሉ፤የአባላትን ቅሬታ ይፈታሉ፤ፀባቴውን ይቆጣጠራሉ፤በገዳሙ ወጣ ያለ ባሕርይ የሚያሳይ መነኮስ ካለ ጾምና ስግደት በመበየን በገዳሙ ማረሚያ ቤት እስከመላክ የሚያደርስ የውስጥ ሕግ ነበረ፡፡የገዳሙ አባል መነኮሳት በምርፋቅ አባላት ላይ ቅሬታ ካላቸው እንዲሁ ቅሬታቸውን አቅርበው ምርፋቁን አውርደው በሌላ ምርፋቅ ይተኩታል፡፡ይሕ ሥርዓት ትናንት ነበረ፤ዛሬም አለ፤ወደፊትም እስከ ምጽአተ-ክርስቶስ ይኖራል ብለን እናምናለን፤አምነን እንናገራለን!!
(2.3) ይሕን አሰራር እነ መኩሪያ ቡልቻ ከሚያወድሱት የአባ ሙዳ አሰራር ጋር እናነጻጽረው፡፡መኩሪያ ቡልቻ <<The Office of Aba Muuda was…open to the Oromo people as a whole and was visited by delegates from every ‘gosa’ and from different parts of Oromo-land, but non-Oromos were not allowed to participate in rituals>>ይላል(Being and Becoming Oromo:53)::በተጨማሪም አባ ሙዳ ወይም ቃሉ (መራሄ-ዋቄፈና) ለመሆን የሚቻለው በዘር ማለትም ከአባት ወደ ልጅ በሚተላለፍ የተወላጅነት ሰንሰለት ብቻ እና ሲመቱም እስከ እድሜ ልክ (እንደ የኢኦተቤክ የፕትርክና ቀኖና) መሆኑን ታቦር ዋሚን ጨምሮ ብዙ ጸሐፍተ-ኦሮሞ አረጋግጠዋል (ታቦር ዋሚ፡ገ.221)፡፡እንግዲህ እኩልተኛ ሥርዓት ማለት ሁሉም እንዳቅሙ እንዲወዳደር የውድድር እድል (equal opportunity) የሚከፍት ማለት ከሆነ እንደ ኦሪት ሌዋውያን ዘርና ብሔርን (ኦሮሞን ብቻ!) መሰረት አድርጎ የሃይማኖት መሪነትን የሚያወራርሰው ዋቄፈና እየተወደሰ በሌላ በኩል ላመነ፣ለተጠመቀና መንፈሳዊውን እውቀት ለጨበጠ ሁሉ እንኳንስ ብሔር ዜግነት ሳይመርጥ ለሰብዓዊ ፍጡር ሁሉ ክፍት ሆኖ የኖረው ቤተመቅደስ በpreservation [of] structural inequalities ሲከሰስ መስማት ግራ ያጋባል፡፡ብቻ ግን በዛሬው የUNDHR ዘመን ‹‹ዘእምነገደ-ይሑዳም ሆነ፤ዘእምነገ-ሙዳ ጊዜውን የዋጁ ሥርዓታት አይመስሉም›› ብለን እንለፍ!!

3-- ክስ-ሦስት፡- አለቃ ታዬ እና አቶ አጽሜ የኢኦተቤክ ደብተራዎች ናቸው!!

እነዚህን ሰዎች (አለቃ ታዬንና አቶ አጽሜን) መሐመድ ሀሰን፣አባስ ሐጂ፣መኩሪያ ቡልቻ፣ታቦር ዋሚ በስፋት ጠቅሰው ጽሑፋቸውን ሲመቻቸው ግብዐት አድርገውታል፡፡በጽሑፎቻቸው ‹‹የራሷ የኢኦተቤክ ጸሐፍት አለቃ ታዬና አቶ አጽሜ እንዲህ አሉ›› ለማለት ከሰዎቹ ስራ ሐሜት ሐሜቱን ነቃቅሰው እንደማጠናከሪያ ተጠቀመውበታል፡፡ሳይመቻቸው ቤተክርስቲያኗን ከነአለቃ ታዬ ጋር እየደረቡ ጭምር ጽሑፋቸውን በአያሌው አጣጥለውታል፡፡እሱ ችግር የለውም፡፡መብታቸው ነው፡፡ችግሩ ሰዎቹ የቤተክሕነት ወኪልና የኢኦተቤክ ደባትር እንደነበሩ ተደጋግሞ መጠቀሱ ነው--ያልሆኑትን!!እስኪ ባጭሩ ታሪካቸውን ከሃይማኖት አንጻር ብቻ በጨረፍታ እንይ…
(3.1) አቶ አጽመጊዮርጊስ (1825-1907 ዓ.ም) የሰሜን ሸዋ ተወላጅ (ዐማራ?) ናቸው፡፡ስለ ኦሮሞ በታሪክም በጸያፍም ሊታይ የሚችል ታሪክ ጽፈዋል፡፡እሱ የኔ ማጠንጠኛ አይደለም፡፡የኔ ማጠንጠኛ የእሳቸው ጽሑፍ የኢኦተቤክ አቋም ተደርጎ መወሰድ እንደሌለበት ማስረገጥ ነው፡፡ምክንያቱም እሳቸው የኦርቶዶክሳዊት ቤ/ክ አባል አልነበሩም፡፡እንዲያውም እድል ባገኙ ቁጥር ኦርቶዶክስን የሚያጥላሉና የካቶሊክ ሚሲዮናውያን በስፋት ሀገሪቱ ላይ አለመንሰራፋት የሚያንገበግባቸው፣የነአባ ማስያስ ሚኒልክን ካቶሊክ ማድረግ አለመቻል የሚቆጫቸው፣የሱስንዮስ ዘመን የሚናፍቃቸው ሰው የነበሩ ስለመሆናቸው አንዳንድ ቃላቶቻቸው ያሳብቃሉ፡፡ጭልጥ ያሉ ካቶሊክ ነበሩ፤ያውም የኢኦተቤክ እና የካሕናቷ ከሳሽ፡፡ማስረጃ እናምጣ፡፡ፕ/ር ታምራት አማኑኤል በጻፉት ‹‹ስለኢትዮጵያ ደራሲያን›› የተሰኘ ምጥን መጽሐፍ በገጽ-14 ይኸንኑ የአቶ አጽሜን ጸረ-ኦርቶዶክስ አቋም ሲገልጹ ‹‹በካቶሊክ ሃይማኖት ያዲሱ ትውልድ ዘመን ሰው ስለነበሩ ለሃይማኖታቸው የነበረባቸው ቅንኣት በኦርቶዶክሳውያን ወገን ላይ ምክንያት ባገኙ ቁጥር ከልክ ያለፈ የተግሳጽ ቃል አስጽፉዋቸዋል፡፡አንዳንድ ጊዜም ታሪኩ መንገድ ሳይሰጣቸው በኦርቶዶክሳውያን ላይ የኃይል ቃል ለመጻፍ ምክንያቱን በግድ ፈልገው ያመጡት ይመስላል›› በሚል አስፍረዋል፡፡አቶ አጽሜ ለኦሮሞ የተቆረቆሩ መስለው የሚሽኖችን አለመምጣት በቁጭት ያነሳሉ፡፡የጦሩን መሪ ንጉሥ ምኒልክ ትተው በዐማራነት የፈረጇቸውን የኢኦተቤክ ካሕናትን ክፉኛ ይወርፋሉ፡፡የእሳቸውን የአጻጻፍ መንፈስ፣የውስጣቸውን ካቶሊካዊ ቅናትና መነሳሻ (motive) ያላጤኑ እንደነመሐመድ ሐሰን አይነት ጸሐፍት የእሳቸውን የጥላቻ ቃል እንዳለ እየወሰዱ ያጮሁታል (JOS:vol-7:p119)፡፡እነመሐመድ እና ጓዶቻቸው የካቶሊኮችን፣የሙስሊሞችንና ፕሮቴስታንቶችን ጽሑፎች ብቻ እየጠቀሱ ኦርቶዶክሳውያን ዶክመንቶችንና አማንያኑን ሳያመሳክሩ ስለኢኦተቤክ መጻፍን እንደልማድ መያዛቸውን ገና ወደፊትም በዚህ አጭር የዳሰሳ ጽሑፍ እናገኘዋለን፡፡አሁን ወደሌላው የኢኦተቤክ ደብተራ ወደተባሉት ጸሐፊ እንለፍ--ወደ አለቃ ታዬ ገብረማርያም!
(3.2) አለቃ ታዬ በ1853 ዓ.ም በጌምድር (ጎንደር)ተወለዱ፡፡ከአድዋ ዘመቻ በፊት (በ1872 ዓ.ም አካባቢ) ወደ ሐማሴን (ኤርትራ) ምንኩሉ የተባለ የስዊድን ሚሲዮናውያን ማረፊያ ሄደው ፕሮቴስታንት ሆኑ፡፡እዚያ ሳሉ ከምዕራባዊው ትምህርት ይልቅ ወደ ምስራቁ አዘነበሉ፡፡የግእዝ መጻሕፍት መመርመር ጀመሩ፡፡ለዚሁ እንዲረዳቸው ወደ ጎንደር ተመልሰው በ1875 ዓ.ም ቅኔ-ቤት ገቡ፡፡በ1877 ዓ.ም ቅኔ ተቀኝተው (ቤት ሞልተው ነው የሚባለው በባሕሉ) ተመለሱ፡፡በምንኩሉ ሚሲዮን አስተማሪ ሆኑ (ደማቆቹ፡ገ.57-68)፡፡ጥሩ የንባብ ተሞክሮ በቤተ-ፕሮቴስታንት ስላዳበሩ በእነሱ እርዳታ በ1889 ዓ.ም የግእዝ ሰዋስው አሳተሙ፡፡በሚሲዮናውያኑ የተልእኮ-ድጋፍ (ስፖንሰርሺፕ) ጀርመንኛ እና ፈረንሳይኛ አጥንተው በጀርመን የግእዝ አስተማሪ እስከመሆን ደርሰዋል፡፡ከዚያ መልስ በጎንደር ያባታቸው (አቶ ገ/ማርያም) ርስት ተፈቅዶላቸው እስከ 1903 ዓ.ም ይኖሩ ነበር፡፡‹‹...ይሁን እንጂ በደብረ ታቦር ሳሉ ‹ጻድቃን አያማልዱም› በሚል ክርክር ከካሕናት ጋር ስለተጋጩ ብዙ ጭቅጭ አገኛቸው፡፡በመጨረሻም በዚሁ ክርክር ምክንያት ወደ አዲስአበባ ተላለፉና ከአቡነ ማቴዎስ [ግብጻዊው] ፊት ቀርበው ነገሩ ከታየ በኋላ ከኢኦተቤክ [በውግዘት] ተለይተው የሚሲዮን ማኅበር አባል ሆነው ተቀመጡ፡፡›› (መርስዔኀዘን ወልደቂርቆስ፡ገ.146)፡፡ከዚህ ጊዜ ጀምሮ አለቃ ታዬ ከኢኦተቤክ ተገልለው እስከ እለተ-ሞታቸው ነሐሴ 15 ቀን 1916 ዓ.ም በመንግሥት ሠራተኛነት ታሪክ ሲጽፉ የነበረ መሆኑ አይካድም፡፡ነገር ግን ምንም እንኳ ከ19 ዓመታቸው ጀምሮ በፕሮቴስታንት እምነት በድብቅ ገብተው የኖሩ ቢሆንም የኢኦተቤክ ልጅነታቸው የታሪክ መጽሐፉን ከመጻፋቸው ከ13 ዓመታት በፊት (በኅቡዕ ፕሮቴስታንት መሆናቸው ከታወቀ ከ31 ዓመታ በኋላ) በ1903 ዓ.ም በይፋ ተቋርጡዋል፡፡ይሄው የብላታ መርስዔኀዘን መጽሐፍ በገጽ-147 ኅዳግ እንደሚተርከው አለቃ ታዬ በተወለዱ በ63 ዓመታቸው (ፕሮቴስታንት በሆኑ በ44ኛው ዓመት) በሞት ሲለዩም በኢኦተቤክ ለመቀበር ተናዝዘው ስለነበር አስከሬናቸውን ለማሳረፍ የቅ/ሥላሴ ካቴድራል ካሕናት በንግሥት ዘውዲቱ ሳይቀር ቢለመኑ ‹‹ይሕ ጸረ-ማርያም በቤተክርስቲያናችን አይቀበርብንም›› ሲሉ ተቃውሞ በማንሳታቸው የአለቃ ታዬ አስከሬን ወደ ጉለሌ ተወስዶ በፕሮቴስታንት መካነ-መቃብር ተቀብሯል፡፡እንግዲህ የኢኦተቤክ በቁም አውግዛ የለየችው፣በሞቱም ‹ሃይማኖት የለያየንን መቃብር አንድ አያደርገንም› ብላ ባመነበት አዲስ እምነት ካረፉ አዳዲስ አማንያን ወገኖቹ መቃብር ጎን እንዲያርፍ የጥምቀት ልጅነቱን ገፍፋ ቅጽሯን የዘጋችበት እና አንድም ጽሑፉን ያልተቀበለችው ዐለቃ ታዬ ነው ‹‹የኢኦተቤክ ደብተራ›› እየተባለ በየቦታው ከላይ በጠቀስኳቸው የኦሮሞ ጸሐፍት ስሟ የሚብጠለጠለው፡፡በዚህ አያያዝ ዛሬ ከኦሮሞ ብሔርተኞች ጋር ጽንፍ ረግጠው የሚወራከቡት ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም እና ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌም ወደፊት ‹‹የኢኦተቤክ ደባትር›› ላለመባለቸው ዋስትና የለም!!

4-- ክስ-አራት፡- ኦርቶዶክስ ኦሮሚፋን ትጸየፋለች!

እውቁ የኦሮሞ ታሪክ ጸሐፊ መሐመድ ሀሰን በJOS (Journal of Oromo Studies.volume-7) ገጽ 118 ላይ በወጣ ጽሑፉ ጆቴ የተባለ ደራሲ ጠቅሶ <<The Amhara clergy failed to capture the hearts and minds of the Oromo by their total failure to use the Oromo language for their missionary work.Infact upto 1993, the Oromo language was considered too profane to be used by the Church>> ይለናል፡፡ሸጋ፡፡በምስማማበት ተስማምቼ ልጀምር፡፡የኢኦተቤክ ኦሮሚፋን ለስብከተ-ወንጌል ድሮም ሆነ አሁን (አሁን ላይ እጅግ መሻሻል ቢኖርም) በቅጡ ተጠቅማበታለች ብዬ አልዋሽም፡፡ነገር ግን ይሕ የሆነው መሐመድ እና ጆቴ እንደሚሉት ለኦሮሚፋ በተለየ መልክ ጽዩፍ (too profane) ሆና ነው ብየ አላምንም፡፡ላስረዳ፡-
(4.1) ዐማርኛ ራሱ በሊቃውንቱ ለቅዱሳት መጻሕፍት ትርጉም አገልግሎት መስጠት የጀመረው በጎንደር ዘመነ-መንግሥት ወቅት ያውም ካቶሊካውያንና ፕሮቴስታንቶች የሰሜኑን ሕዝብ በአካባቢው ቋንቋው እያስተማሩ ምዕመኑን ማስኮብለላቸው ባሳደረው ጫና ነው፡፡ዐማርኛ በተደራጀ መልኩ ለመጻሕፍት ትርጓሜ የዋለበትን (የወቅቱ የትርጓሜ መንገድ በራሱ የግእዝ ተጽእኖ እጅግ ቢበረታበትም) ትክክለኛውን ጊዜ ስናስቀምጠው በአጼ አድያም ሰገድ ኢያሱ ዘመን (ከ1674-1694) ስለመሆኑ በሚሊኒየሙ የታተመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ እስከ ፳፻ (2000ዓ.ም) መጽሐፍ በገጽ 187 አብራርቶ ያቀርብልናል፡፡ዐማርኛ በሥርዓተ-ቅዳሴ መካከል ለመነገር የበቃው ደግሞ ከ1913 ዓ.ም ወዲህ አባ ኪዳነማርያም በተባሉ የዋድላ (ወሎ) መነኩሴ አማካይነት ስለመሆኑ መርስዔኀዘን በገጽ 143 ተርከውልናል፡፡
(4.2) ከትርጉም ጋር በተያያዘ ጥቂት ግነት ያለበት ቢመስልም ሐቁን ያላጣውና ተስፋዬ ቶሎሳ በተባሉ አጥኚ የአፋን ኦሮሞን ጽሑፋዊ የታሪክ ሂደት የሚዳስስ የጥናት ወረቀት ገጽ-77 የተጠቀሰው የጀምስ ብሩስ አስተያየት ይታይ፡፡ብሩስ <<...there is an old law in this country (Ethiopia), handed down by tradition only, that whoever should attempt to translate the holy scripture into Amharic, or any other language his throat should be cut....>> በማለት ልማዳዊ ሕጉ ከግእዝ ውጪ ባሉ ቋንቋዎች ሁሉ ዐማርኛን ጨምሮ ይሰራ እንደነበር ይተርካል፡፡ልማዳዊ ሕጉ በአብዛኛው የሰሜን ኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊ አሁን ድረስ ሕያው ነው፡፡ጸሎትና ቅዳሴው ለግእዝ ያደላ ነው፡፡በትግራይ፣በጎጃም፣በጎንደር፣በወሎ እና በሸዋ ግእዝ ጠቅሶ የማይሰብክ ሰባኪ እንኳንስ በካሕናቱ በምዕመናኑም የሚሰጠው ክብር እምብዛም ነው፡፡ሕዝቡ ለግእዝ ያደላል፡፡እዚያ በአማርኛ/ትግርኛ ብቻ ብትንደቀደቅ ‹‹ስብከቱ ጥሩ ነበር፤ግና ‹ቦለቲካ› በዛው›› ይልሀል፡፡
(4.3) ተስፋዬ ቶሎሳ በጥናቱ የቀደሙ ነገሥታትን የኦሮሚፋ ቋንቋን ጨቋኝነት በስፋት ቢገልጽም እ.ኤ.አ በ1877 ዓ.ም አለቃ ዘነብ (እኒህ ሰው የአጼ ቴዎድሮስን ዜና-መዋዕል የጻፉ የሸዋ ተወላጅ ሲሆኑ የጉራጌ ሕዝብ ከምኒልክ ጋር በተዋጋ ጊዜ ተገድለዋል--አለቃ ዘነብ) ለአጼ ምኒልክ መጽሐፈ-ኢያሱን፣መጽሐፈ-መሳፍንትን፣መጽሐፈ-ሩትን እና መጽሐፈ-ሳሙኤልን ወደ ኦሮሚፋ ተርጉመውላቸው በአውሮፓ ሊያሳትሙ ሲሉ ለማሳተም ቃል የገባላቸው ሚሲዮናዊው Krapf ከዚህ ዓለም በሞት በመለየቱ ኅትመቱ እንዳልተከናወነ የፓንክረስትን የ1976 እትም መጽሐፍ ጠቅሶ አስቀምጦታል፡፡‹‹ደማቆቹ›› የተሰኘ በመፍቀርያነ-ፕሮቴስታንት ጸሐፍት የተዘጋጀ መጽሐፍም ስለ አናሲሞስ ነሲብ ሲተርክ ይህንኑ የአለቃ ዘነብን ውጥን አንስቶታል (ደማቆቹ፡ገ.29)፡፡አናሲሞስን ከአጼ ምኒልክ ያገናኙት አቡነ ማቴዎስ እንደሆኑ፣አናሲሞስም ለአጼ ምኒልክ የኦሮምኛውን መጽሐፍ ቅዱስ እንዳበረከተላቸው፣ንጉሡም አናሲሞስን አጃቢ ባልደረባ ሰጥተው ወደ ወለጋ እንደላኩት ይኸው መጽሐፍ (ደማቆቹ) ይገልጻል፡፡የኢኦተቤክ ያላትን አስተምህሮ ሳይቃረን እንዲያስተምር ጳጳሱ አቡነ ማቴዎስ (ግብጻዊ) ራሳቸው ለአናሲሞስ ነግረውት ነበር፡፡ጳጳሱ ለወለጋው የወቅቱ አስተዳዳሪ በጻፉት ደብዳቤም ይሕንኑ አሳውቀዋል፡፡እንጥቀሰው ‹‹...እጅግ ለተከበርከውና ለተወደድከው ደጃዝማች ገብረእግዚአብሔር እንዴት አለህ?እኔ የማርቆስ አምላክ ይመስገን ደህና ነኝ፡፡ይሕ ከወደብ (ኤርትራ) የመጣው ኦኔሲሞስ ወደ እኛ መጥቶ እንዲያስተምር ጠይቆናል፡፡ከቤተክርስቲያናችን ትምህርትና እምነት የተለየ ጕዳይ አስተምሮ እንደሆነ እንድናውቀው አድርግ፡፡ነገር ግን ከኛ ትምህርትና እምነት ያላፈነገጠ ትምህርት የሚሰጥ ከሆነ ይቀጥል፤ማንም አንዳች አይበለው›› (ደማቆቹ፡ገ.33)፡፡እርግጥ ነው በኋላ ዘመኑ አናሲሞስ ችግር አጋጥሞታል፡፡ነገር ግን ችግሩ የገጠመው ኦሮሚፋን ተጠቅሞ በመስበኩ ሳይሆን የተሰጠውን መመሪያ ጥሶ ከኢኦተቤክ ዶግማና ቀኖና የሚጋጭ ፕሮቴስታንታዊ ትምህርት በማስተማሩ ነው፡፡ ይሕ ደግሞ በእሱ ላይ ብቻ ሳይሆን ቀደም ሲል ፕሮቴስታንታዊ ትምህርት ባስተማሩት ጎንደሬው አለቃ ታዬ፣ካቶሊካዊ ትምህርት ባስተማሩት ጎጃሜው አባ ገብረሚካኤል (በአጼ ቴዎድሮስ ታስረው ሳለ ስላረፉ ቫቲካን እንደ ብፁዕ ሰማዕት ነው የምታያቸው)፣በልዩ ልዩ የጸጋ-ተዋሕዶ-ቅባት ክርክሮች ወቅት በዐማራና በትግራይ ሊቃውንትም ዘንድ የደረሰ ነው--መሳደዱ፡፡ስለሆነም ዛሬ ላይ ቆሜ አንድ ሰው በእምነቱ የተነሳ መሳደድ እንደሌለበት በሙሉ ልቤ ባምንም ገና ወለጋ ለምኒልክ ሳይገብር በአካባቢው በሰፈነው የባርነት ንግድ በ1854 ዓ.ም (ምኒልክ በዚህ ጊዜ በመቅደላ እስር ቤት የአጼ ቴዎድሮስ እስረኛ ነበሩ) ተሽጦ ኋላ በሚሲዮናውያን አርነት ከወጣ በኋላ ለኦሮሚፋ ቋንቋ ታላቅ ውለታን የሰራው አናሲሞስ የተሳደደው በኦሮሞነቱ እና በኦሮሚፋው ነው ብዬ አላምንም፡፡የወቅቱ የኢኦተቤክ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ቋንቋ ሳይለዩ አናሲሞስ ስለኦርቶደክስ እንዲሰብክ የበኩላቸውን ጥረዋል፡፡ስብከቱን ለፕሮቴስታንታዊ ተልእኮ ሲጠቀምበት ግን ወቅቱ በፈቀደው ሕግና ሥልጣን ስብከቱን ለማገድ ተንቀሳቅሰዋል፡፡ይህ እንቅስቃሴያቸው ከሃይማኖት ነጻነት ጋር እንጂ ከቋንቋ ነጻነት ጋር አይገናኝም ብዬ አምናለሁ፡፡ሌላ ዋቢ እንጥራ!
(4.4) ከሆሮ-ጉድሩ ተማርኮ ኋላ በምድረ-ጎጃም ታላቅ ካሕን፣ጸሐፊ እና የተመሰገነ ሠዐሊ የነበረው አለቃ ተክለኢየሱስ (ነገሮ) ዋቅጅራ በ1891 ዓ.ም በኦሮሞ-ቤት (ሆሮ-ጉድሩ) ስለተካሄው የጎጃሙ ንጉሥ ተክለሃይማኖት ጉዞ (ጦርነቱ በ1871 ዓ.ም ተጠናቋልና ይሄኛው ጉዞ ለጦርነት አይደለም፤ለቤ/ክ ግንባታ እንጂ) እንዲህ ይተርካል ‹‹...የዚህ ጊዜ ንጉሥ ተክለሃይማኖት...ኦሮሞ ቤት ዲለሎ ከሚባል ቦታ ሲደርስ ቤተክርስቲያን ሲሰራ ባጀ፡፡...ኦሮሞውን ሁሉ አሳምኖ ብዙ ታቦት ተከለ፡፡ተሠሪ ሠራበት፡፡...[በ1871 ዓ.ም ከሆሮ-ጉድሩ ማርኮ] ያሳደጋቸውን ኦሮሞዎች ሁሉ ከዘመድ እያስተዋወቀ ለነሻቃ ይርባ [ሂርጳ?]፣ለነሻቃ ጉደታ፣ለነበጅሮንድ ናደው ከየአባታቸው ርስት ጉልት አድርጎ ሰጥቶ ቤት አሠራቸው፡፡...ከዲለሎ ሲመለስ አለቃ ተክለኢየሱስን ጠርቶ ዘመዶችህ እነሻቃ ይርባ [ሻቃ ሂርጳ የንጉሥ ተክለሃይማኖት ሰይፍ ጃግሬ ነበር] አገራቸው ገብተው ከዘመድ ተገናኝተው ለጉልት ሲበቁ ምነው አብረኸኝ ሳትሄድ አለው፡፡...ከርሞ የቀዎ ጊዮርጊስ ጌታ አደርግሀለሁ፡፡...እዚያው [ሥዕል] እየሣልክ ታሳምንልኛለህ፡፡ነገርግን የኦሮምኛ ቋንቋ እንዳይጠፋህ ይኹን አለው፡፡›› (አለቃ ተክለኢየሱስ፡ገ.198)፡፡ይቺ የተክሌ ሐተታና ‹‹እዚያው [ሥዕል] እየሣልክ ታሳምንልኛለህ፤ነገር ግን የኦሮምኛ ቋንቋ እንዳይጠፋህ ይኹን አለው፡፡›› የምትለዋ የንጉሥ ተክለሃይማኖት አገላለጽ በወቅቱ ዛሬ እንደሚባለው በኢኦተቤክ አካባቢ ኦሮሚፋ ‹‹ጽዩፍ›› የሚባል ቋንቋ እንዳልነበረ ፍንጭ ትሰጠናለች፡፡የንጉሥ ተክለሃይማኖት ዐላማም ጎጃም ማርኮ ያቆያቸውን ኦሮሞዎች ተጠቅሞ ሆሮ-ጉድሩን እና አካባቢውን በኦሮሚፋ እያስሰበከ በኦርቶዶክሳዊነት አሳምኖ ለማጥመቅ መሆኑን ይጠቁመናል፡፡
(4.5) የኢኦተቤክ በሰሜን በኩል ባሉ ብሔረሰቦች ውስጥ ሴሜቲክ በሚባሉት ዐማራና ትግራውያን (ሐማሴኖችን ጨምሮ) ብቻ ሳይሆን ሰሜናዊ ኩሽቲክ በሚባሉት አገዎች ዘመናትን የቀደመ ተጽእኖ አላት፡፡‹‹ላል-ይበላ›› የሚለው ስም አገውኛ ስለመሆኑና አገዎች ቤተመንገሥቱን 300 ዓመታት ተቆጣጥረውት እንደነበር ተደጋግሞ ተነግሯል፡፡ወደ ደቡብ ስንሄድ የከፋን ሕዝቦች ታሪክ የጻፈው በቀለ ወ/ማሪያም አዴሎ እንደሚነግረን የኢኦተቤክ በአካባቢው ከ600 እስከ 700 ዓመታት የቆየና የተመዘገበ ታሪክ አላት፡፡ለአብነትም በቀለ ወ/ማሪያም በ1532 ዓ.ም የተተከለው ባሃ ጊዮርጊስን ይጠቅስልናል፡፡(በቀለ ወ/ማሪያም፡ገ.122 እና 123)፡፡በወላይታም የደብረ-መንክራት ተክለሃይማኖት ቤ/ክ እድሜ ከ800 መቶ ዓመታት በላይ ይቆጠራል፡፡በ14ኛው ክ/ዘ በምድረ-ጉራጌ እነ አቡነ ዜናማርቆስ ያቋቋሙት የምሑር-ኢየሱስ ገዳም ዛሬም ከነግርማው አለ፡፡በጋሞዎች ምድር ያለችው ብርብር ማርያም ከንጉሥ ገብረመስቀልና ከንጉሥ ዘርዓያዕቆብ ጋር የተገናኘ የሺህ ዓመት ታሪክ ትቆጥራለች፡፡በሸዋ የኦሮሞ ምድር ያሉት የወንጪ(አምቦ) ቂርቆስ፣የዝቋላ/ጩቃላ አቦ፣የዝዋይ/ባቱ ደሴት ገዳማት፣የደ/ሊባኖስና የዐዳዲ ማርያም ገዳማት፣...የሚቆጥሩት እድሜ በትንሹ ከ500 ዓመታት በላይ ነው፡፡ሃይማኖቱ ከ6 ሀገራት ጋር ዶግማ ቀኖና ስለሚጋራ ከነዚህ ሀገራት የመጡ ቅዱሳን በኃላፊነት ጭምር እየተቀመጡ እስከቅርብ ጊዜ አገልግለዋል፡፡የዐረብኛ፣የሱርስት፣የግሪክ እና የእብራይስጥ ቋንቋ ሳይቀር ሊቃውንቱ እያጠኑ ቅዱሳት መጻሕፍትን ተርጉመዋል፡፡ላመነና ለተጠመቀ ሁሉ መድረኩ ክፍት ነበር፡፡እነ መሐመድ ሐሰን ይሄን ሳያጣሩ፣ወይም እያወቁ ሳያካትቱና ጥቂት እንኳ ለሚዛናዊነት ሳይጨነቁ ‹‹The Amhara clergy›› እያሉ ሃይማኖቱን የአንድ ብሔር በማስመሰል መጻፋቸው እጅግ ቅር ያሰኛል፡፡ሃይማኖቱ ለዐማርኛ ቋንቋ የሚባለውን ያህል ታሪካዊ የሥነ-ጽሑፍ ቦታ እንዳልነበረው እስኪ ቀ.ኃ.ሥ ይንገሩን፡፡
(4.6) ቀ.ኃ.ሥ በ‹‹ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ›› የመጀመሪያ ክፍል መጽሐፋቸው ገጽ 136 በዘመናቸው ዐማርኛ የነበረበትን ዝቅተኛ የቤ/ክ አገልግሎት ሲገልጹ ‹‹...ቅዳሴው ሕዝቡ ሁሉ በማያውቀው በግእዝ ቋንቋ ስለነበር ብዙዎች የዜማውን ድምጽ ከመስማት በቀር ምስጢሩን የሚያስረዳ ቃል ሳይሰሙ በየቤታቸው ይመለሱ ነበር፡፡...›› ካሉ በኋላ በእሳቸው ዘመን ስለነበረው ጅማሮ ሲገልጹ ‹‹...አሁን ግን ጸሎተ-ቅዳሴው በአማርኛ ቋንቋ እንዲተረጎምና እንዲታተም አድርገን በየቤተክርስቲያኑ ስለታደለ ሕዝቡ መላውን እንኳ ባይሆን ዋና ዋናውን ቃል በቋንቋ ሲነበብ መስማት ጀምሯል፡፡ወንጌልና የሐዋርያት መልእክትም በአማርኛ ቋንቋ እንዲነበብላቸው ተደረገ፡፡›› ይሉናል፡፡በነገራችን ላይ መጽሐፈ-ቅዳሴ ከግእዝ ወደ አማርኛ በነጠላው የተተረጎመውና የታተመው በ1918 ዓ.ም ነበር፡፡ተርጓሚው መርስዔኀዘን ወልደቂርቆስ ነበሩ፡፡አማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ በነጠላ ትርጓሜ በ1832 ዓ.ም አባ አብርሃም (አባ ሮሜ) የታተመ ቢሆንም የተሟላና ሊቃውንተ-ቤተክርስቲያን የተሳተፉበት አማርኛ መጽሐፍቅዱስ የታተመው ግን በቅርቡ በ1953 ዓ.ም ነበር፡፡በዚህ ወቅት (ኧረ ቀደም ብሎ ነው!) መጽሐፍ ቅዱስን አናሲሞስ ነሲብ ወደ አፋን ኦሮሞ፤አለቃ ተወልደመድኅን ገብሩ ወደ ትግርኛ ተርጉመውት ነበር (የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ-ቃላት፡ገ.95)፡፡ድጋሚ ላስታውስ!የኢኦተቤክ በቀደመው ዘመን በስብከተ-ወንጌል ረገድ በየብሔረሰቡ ቋንቋ የመስበክ ብቃት ነበራት እያልኩ አይደለም፡፡አቋሜ የኢኦተቤክ የቋንቋ አጠቃቀም ውስንነት ልክ እስልምና ለዐረብኛ፤ካቶሊክ ለላቲን ቋንቋዎች እንደሚሳሱት (ኦሪጅናል ድርሰቶችና ዜማዎች በቋንቋዎቹ ስለተቀናበሩ) እሷም ለግእዝ ስሱ በመሆን እንጂ ኦሮሚፋን በተለየ ዐይን በማየት አይደለም የሚል ነው፡፡
(4.7) ይሕ በግእዝ ብቻ የመገልገል የኢኦተቤክ ልማድ መንበረ-መንግሥቱ በአክሱማውያን (ትግራውያን)፣በዛጉዌዎች (አገዎች) እጅ እና በየጁ ኦሮሞ ወረሴህ/ወራ-ሼክ እጅ በነበረበት ጊዜ (ለምሳሌ፡- ከየጁ ኦሮሞ የሚወለዱት ታላቁ ራስ ዓሊ ደብዳቤ ሲጽፉ ‹‹ጦማር ዘእምኀበ-ርእሰ-መኳንንት ዓሊ›› በማለት በግእዝ ነው አርእስታቸውን የሚጀምሩት)፤ኋላም ዙፋኑ በአጼ ዮሐንስ ተመልሶ ወደ ትግራይ ባመራበት ዘመን በኢኦተቤክ የግእዝ የበላይነት የጸና ነበር፡፡
(4.8) የቀደመው የግራኝና ደርቡሽ ሰቆቃ (አጼ ዮሐንስ በመተማ ተሰውተው ደርቡሽ ጎንደርን በወረራ ሲያጠፋ በሃይማኖቱ እውቀት ጫፍ የደረሱ ከ20 በላይ መምሕራንን አርዶ ነበርና) በወቅቱ ሀንጎቨሩ እንዳለ ሆኖ በተለይ ደግሞ የአጼ ሱስንዮስ ዘመን ካቶሊካዊ ፍልስፍና ኋላ ፊቱን ቀይሮ ጸጋ/ሦስት ልደት/-ቅብዐት-ተዋሕዶ/ካራ/ የሚል የውስጥ ክፍፍል በመፍጠር ሃይማኖቱ በውሳጣዊ ሽኩቻ ከመዳከሙም በላይ ከሊቃውንት ማዕከላቱ ትግራይ-ጎንደር-ጎጃም-ወሎ-ሸዋ ወጥቶ ወደሌሎች ብሔረሰቦች በስፋት በስብከተ-ወንጌል እንዳይደርስ ይሄው ሽኩቻ እስከ ዘመነ-መሳፍንት ፍጻሜ ዘልቆ ጎታች የነበረ መሆኑን ማስተዋል አይከፋም፡፡ እንጂ የኦሮሚፋ ስብከት ያልተስፋፋው መሐመድ ሐሰን እና ኦቦ ጆቴ እንደሚሉት ለኦሮሚፋ too profane በመሆን አይመስልም፡፡ጥያቄ ላንሳ፡፡ዶክቶር መሐመድ ወደ ኢኦተቤክ ከማለፉ በፊት እስልምና ለቁቤ እና አፋን ኦሮሞ ያበረከተውን ጸጋ ሊተነትንልን ይችል ይሆን?የአፋን ኦሮሞ ቁራን ነበረ?ቁራን በኦሮሚፋ ይቀራ ነበር?አዛንስ?ለንጽጽር እንዲመች ጥያቄዎቹ ቢብራሩ ሸጋ ነው!ስላደገበት እስልምና-እና-ኦሮሞነት ተዛምዶ ለመተንተን የተሻለ ግንዛቤ አለው ብዬ ነው!የእሱ የተጸውኦ(መጠሪያ) ስም ‹‹መሐመድ ሐሰን›› በኦሮሚፋ አይደል!!ይተርጉምልና!!
(4.9) እግረ-መንገድ እስኪ ከ100 ዓመት በፊት በኦሮሚፋ እና በዐማርኛ ቅልቅል (ፍርንዱስ) ሆኖ የግጥም ምጣኔው ‹ሥላሴ› የምንለው ከ3ኛው መስመር ጀምሮ ቤት እየመታ የሚሄድ ባለ 8 መስመርና ባለ 6 ቤት ቅኔ እንስማ፡፡የቅኔው ባለቤት አለቃ ዘወልዴ ይባላሉ፡፡ምናልባት በፕ/ር ታምራት ‹‹ፊተኛይቱና ኃለኛይቱ ኢትዮጵያ›› የሚል መጽሐፍ በተለየ አጻጻፍ ጽፈዋል የሚባሉትና መጽሐፋቸውን ያላገኘንላቸው ዘወልዴ ይሁኑ አይሁኑ አላወቅኩም፡፡ቅኔው የተደረገው በምኒልክ ጊዜ የነበረውን አስተዳደር በመተቸት ነው፡፡የተወሰደው በ1980 ዓ.ም በደርግ ጊዜ በአ/አ/ዩ አማካይነት ከታተመው ‹የግእዝ ቅኔያት የስነ-ጥበብ ቅርስ ክፍል-2› ከተሰኘ መጽሐፍ ገጽ-389 ነው፡፡የሊቁ ቅኔ እንዲህ ይነበባል..
አርካ-ኬቲ፡ሁንዱማ-ጨብሴ፤
ሌንጫ-ጎፍታኮ፡ኢጆሌ-ሌንጫ፤
አሁንም-የእውነት፡ግሩም፡አንበሳ፡የአንበሳ-ኮርማ፡የቢያ፣
በክንድህ-ሰበርኸው፡የሁሉን፡ሶማያ፣
ዱጉማ፡ጎፍታኮ፡ዱጉማ፡አሲ-መና-ኬቲ ገበያ፣
ሀሬ-ጉደቴ፡ፈርዳን-ፉለያ፣
ማሎ፡ማሎ፡ጎፍታ-ኪያ፣
መና-ፈርዳ፡ፉደቴ፡አህያ፡፡
ትርጉም፡- ‹‹አንበሳ የአንበሳ ልጅ፤ጌታየ ክንድህ ሁሉን ሰበረች፤አሁንም የእውነት አስፈሪ አንበሳ የአገር አንበሳ ኮርማ (አንተ)፤የሁሉን በትር በክንድህ ሰበርኸው፤እውነት ጌታዬ ከዚህ ገበያ ቤትህ እንደ አይጠ መጎጥ ፈረሶች ሲርቁ አህያ ከፍ ከፍ ተደረገች፤ምነው ምነው የእኔ ጌታ የፈረስን ቤት አህያ ወሰደች›› የሚል ነው፡፡
ምስጢሩ፡- ባለቅኔው የምኒልክን በባላባቶች ላይ የተገኘ አሸናፊነት አወድሰው ነገር ግን ‹‹በባህሉ ፈረስ እያለ አህያ ቀሚስ እንደማትለብስ እየታወቀ እስዎ ታላላቆችንና ምሁራኑን ትተው ለታናናሾች እና ላልተማሩት ቦታ (ስልጣን) እየሰጡ ነው›› በማለት የምኒልክን አስተዳደር በኦሮሚፋ የሚተች ነው፡፡በውዳሴ ጀምሮ በትችት መቋጨት ከቅኔ ባሕሪያት አንዱ ነዋ!

ይቀጥላል///////

Tuesday, September 15, 2015

ተከስተ ጌትነት ለተወራበት የወሲብ ቅሌት፤ ዋሽንግተን ዲሲ ለሚታተመው ዘኢትዮጵያ ጋዜጣ የሰጠው ምላሽ

እኔ ወ/ሮ ሆሳዕናን አስገድጄ አልደፈርኩም። በፍርድ ቤትም አልተከሰስኩም። ለዚህም ማስረጃ አለኝ።”
የወ/ሮ ሆሳዕና ባለቤት ባለፈው በቪ ኦ ኤ በቀረበው ፕሮግራም መግቢያ ላይ “በሚስቴ ላይ የጾታ ጥቃት ተፈጽሞባታል” ያለውና ወይዘሮ ሆሳዕናም በዚያው ፕሮግራም ላይ ቀርባ “ጉዳዩ በህግ የተያዘ ነገር ነው” ያለችው ነገር ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው። እኔ ማንንም ሰው አስገድጄ አልደፈርኩም ምንም አይነት ክስም አልቀረበብኝም። ከወንጀል ነፃ መሆኔን የሚያሳይ ህጋዊ ማስረጃ በአሜሪካን አገር ጉዳዩ ከሚመለከተው መስሪያ ቤት በጠበቃዬ አማካይነት ያገኘሁት እሷ በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ቀርባ ከስሸው ጉዳዩ በህግ ተይዟል ብላ በተናገረች በሚቀጥለው ቀን ነው።

 ይባስ ብሎ በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ፓስተር ተከሰተ ባለትዳር ሴት ደፍሮ ተከሰሰ የሚለውን ዜና ውሸት እና የፈጠራ ወሬ መሆኑን የሚያሳየው እኔ እነሱ ከሚኖሩበት ሚንያፖሊስ ከተማ እኔ ወደምኖርበት ወደ ዋሽንግተን ስመለስ ወደ አውሮፕላን ጣቢያ የሸኘችኝ እራስዋ ወይዘሮ ሆሳዕና ነች። በብዙ ጭቅጭቅ የ1000 (አንድ ሺህ) ዶላር የእጅ ሰዓት በራስዋ ክሬዲት ካርድ ገዝታልኛለች። ለዚህም ሌላ ህጋዊ ማሰረጃ አለኝ። በዚያን ሰአት እንኳን ልትከስኝ ቀርቶ ለወንድ ልጅ ሰዓት መስጠት እወዳለሁ ብላ እኔ ሰአት አልፈልግም እያልኳት እሷ ግን እኔ የወንድ ልጅ ሰዓት ስለሚስደስተኝ ልግዛልህ። አንተ ብትፈልግ ወደፊት በሌላ ነገር ቀይረው በማለት ከነደረሰኙ ሰጠችኝ።

አንተና ወይዘሮ ሆሳዕና እንዴት ተገናኛችሁ ጉዳዩስ እንዴት እዚህ ደረጃ ደረሰ? ብለን ላቀረብነው ጥያቄ የሰጠው ምላሽ፡ ወ/ሮ ሆሳዕናና የእኔ ባለቤት የአንድ ሰፈር ሰዎች ናቸው። ከዚያም በራስዋ በወይዘሮ ሆሳዕና ተደጋጋሚ ግፊትና ጥረት ተቀራረብን። የቤተሰባችን አካል ሆነችና አገልግሎትህን ስለምወድ እንድደግፍ ጌታ አሳሰበኝ በሚል መንፈሳዊ አካሄድ ለእኔና ለቤተሰቦቼ በተለያየ ጊዜ ስጦታ ሰጥታናለች። የቤተክርስቲያን አገልጋዮች በምዕመናን በጎ ፈቃድ የፍቅር ስጦታና የአገልግሎት ድጋፍ ማግኘት የተለመደ ስለሆነ እኔም በአገልግሎት ዘመኔ እኔንና አገልግሎቴን የሚደግፉ ብዙ ደጋግ ሰዎች ስላጋጠሙኝ ወይዘሮ ሆሳዕና ያለችውንም በቅንነት ተቀበልኩት። በመጨረሻም እኔ ባለቤትህና አንተ ለምን የጋራ ቢዝነስ አንጀምርም? እኔ ገንዘብ አለኝ፣ የቤተሰብ የቢዝነስ ልምዱም ስላለኝ አንተ ደግሞ ኢትዮጵያ ታዋቂ ስለሆንክ ሦስታችን አብረን ኢትዮጵያ ቢዝነስ ብንሰራ ሊሳካልን ይችላል ብላ ጠየቀችን። እኔም ማንኛውም ዘማሪ አንደሚመኘው ከቤተክርስቲያን ምንም ነገር ሳልጠብቅ ራሴን እና ቤተሰቤን በግሌ እየሠራሁ በማስተዳደር በነፃ የማገልገል ከፍተኛ ፍላጎት ስለነበረኝ እኔና ባለቤቴ በሀሳቡ ተስማማን። እኔ እነሱ ወደሚኖሩበት ከተማ የሄድኩት እና ሆቴል ያረፍኩት ራስዋ ወይዘሮ ሆሳዕና በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ቀርባ እንደተናገረችው በጋራ ስለምንጀምረው ቢዝነስ ለመነጋገር ነበር። ይህን ሀሳብ ያመጣችው እራሷ ወይዘሮ ሆሳዕና ነች።

በራሷ ገንዘብ የአውሮፕላን ትኬት ቆርጣ እራሱዋ ሆቴል ይዛ፣ (ለዚህም ማስረጃ አለኝ)። ከዚያ በኋላ አሁንም ራሷ በአሜሪካን ድምፅ ቀርባ እንደተናገረችው ያረፍኩበት ክፍል ውስጥ ገብታ ልብሷን አወለቀች። ብዙ ተፈታተነችኝ። የምሄድበት መንገድ ትክክል እንዳልሆነና ሆን ተብሎ የገባሁበት ወጥመድ እንዳለ ሲገባኝ ፍላጎቱ ባይኖረኝም እሷን ሳላሳዝን ሞራልዋን ሳልነካ በሰላምና በእርጋታ ለመውጣት “በቃ አሁን እኔ መረጋጋት አልቻልኩም ፍላጎቱ የለኝም ሌላ ጊዜ ተመልሼ ልምጣና ያንቺን ፍላጐት አሟላለሁ” ብዬ ቃል ገባሁ። እሷም ተመልሼ ወደእሷ ከመጣሁና መሻቷን ከፈጸምኩ አብረን ልንሠራ ከተነጋገርንበት ቢዝነስ በተጨማሪ ለግሌ ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንደምትሰጠኝ ነግራኝ ተለያየን። ካረፍኩበት ሆቴል ወደ አውሮፕላን ጣቢያ ስንሄድ ለወንድ ልጅ የሰዓት ስጦታ መስጠት ያስደስተኛል ብላ ከላይ እንደጠቀስኩት የአንድ ሺህ ዶላር ሰዓት መንገድ ላይ ወደሚገኝ ሞል ኦፍ አሜሪካ የገበያ ማዕከል ውስጥ ሜሲስ የሚባል ስቶር ወስዳ ገዛችልኝ።

አየር ማረፊያ አውርዳኝ ስንለያይ ለመጀመርያ ጊዜነጻነት ተሰማኝ። ዋሽንግተን ዲሲ ተመልሼ እቤቴ ስገባም የሆነውን ነገር ሁሉ ለባለቤቴ አንድም ነገር ሳልደብቅ ነገርኳት። ከዚያም እንደ አንድ ክርስቲያን እና እንደ አንድ አገልጋይ ከእኔ የማይጠበቅ ነገር አድርጌአለሁ ብዬ ያለማንም አስገዳጅነት በራሴ ፈቃድ ለቤተክርስቲያን ተናግሬ ወዲያውኑ ራሴ አገልግሎት አቆምኩ። በራሴ ቤተክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የአሜሪካን ክፍለግዛቶች በሚገኙ አብያተክርስቲያናት እንዳገለግል የተጋበዝኩባቸውን አገልግሎቶች በሙሉ በራሴ ፈቃድ ሰረዝኩ። እኔ ወደዋሽንግተን ከመጣሁ በኋላ ወይዘሮ ሆሳዕናም እኔን በስልክ ለማግኘት ተደጋጋሚ ሙከራ አደረገች ግን አልተሳካላትም። ከዚያ በኋላ የበቀል እርምጃው ግራ በሚያጋባ መልኩ መጣ።
መጀመሪያ ለእኔ ባለቤት ለወ/ሮ የምስራች ባለቤቱዋ አቶ መላኩ ደውሎ ሚስቴ ከአንቺ ባል ጋር አብራ ስለተኛች ይቅርታ ልትጠይቅሽ ነው ብሎ ስልኩን ለወይዘሮ ሆሳዕና ሰጣት። ወይዘሮ ሆሳዕናም እኔ ከባለቤትሽ ከተከስተ ጋር ተኝቻለሁ ይቅርታ አድርጊልኝ ብላ በስልክ ለእኔ ባለቤት የድምፅ መልእክት ተወችላት (ደውለው ለባለቤቴ የተውት የእሱም የእሷም የድምፅ መልዕክት ማስረጃው አለኝ)። ከዚያ ደጋግመው ደውለው ባለቤቴን አገኟትና ባልሽ ከሚስቴ ጋር ተኛ ብሎ ነገራት። ባለቤቴም በቃ ካጠፉ ይቅር እንበላቸው እና ነገሩ ይቁም አለችው።

ባለቤቴም ሁሉንም ነገር አልቀበል ስትል ወደ ቤተክርስቲያን ሄዱ። አቶ መላኩ ቤተክርስቲያን ሄዶ ፓስተር ተከስተ ከሚስቴ ጋር ተኝቷል አገልግሎት ማቆም አለበት ይቅርታ መጠየቅ አለበት አለ። እኔም የእግዚአብሔር ቃል እንደሚለው እና መንፈስ ቅዱስ እንደሚወቅሰኝ ከአንድ አገልጋይ የማይጠበቅ ጥፋት አጥፍቻለሁ። እግዚአብሔርንም በድያለሁ ለዛም እራሴን ከአገልግሎት አስቁሚያለሁ። እናንተንም ይቅርታ እጠይቃለሁ አልኩኝ። ሰዎቹ ዓላማቸው ክርስቲያናዊ ዕርቅ እንዳልሆነና አሳባቸውን በመቀየር ለሌላ ለተሻለ የበቀል እርምጃ ሊጠቀሙበት እንደሆነ አስቀድሜ ለሦስቱ ሽማግሌዎች ነግሬአቸው ነበር። ነገሩ በሰላም እንዲያልቅና ክርስቲያናዊ አካሄድ ነው ብዬ ስለማምን ሙሉ ኃላፊነት ወስጄ ይቅርታን ጠይቄአለሁ። አቶ መላኩ ግን የግብረሥጋ ግንኙነት ፈጽመሃልና እመን የሆነውንም ዝርዝር ነገር ንገረኝ ብሎ ጠየቀኝ። እኔም ሙሉ ኃላፊነት ወስጄ ይቅርታንም ጠይቄ የወይዘሮ ሆሳዕናን ስሜትና ስብእና የሚነካ ዝርዝር ነገር ውስጥ ግን እንደማልገባ አሳወቅሁኝ። ምክንያቱም እንደዚህ ዓይነት ነገር ያልተለመደ በመሆኑና አቶ መላኩ ማወቅ የሚፈልገውን መረጃ በሙሉ ከገዛ ሚስቱ ማግኘት ስለሚችል ነው። ቤተክርስቲያንም ፓሰተር ተከስተ ከአንድ አገልጋይ የማይጠበቅ ጥፋት አጥፍቻለሁ ብሎ በራሱ ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ገብቶአል አገልግሎትም አቁሞአል ፣አንተንም ይቅርታ ጠይቋል ነገሩ እዚህ ጋር ይለቅ ብለው ጠየቁት ። እነሱ ግን እኔን ለማጥፋት ቆርጠው ስለተነሱ ነገሩ እንዲቆም አልፈለጉም።

ቤተክርስቲያን መጥተው ያሰቡትን ያህል እኔን የጎዱኝ እና ያዋረዱኝ ስላልመሰላችው ቪ ኦ ኤ ሄደው ፓስተር ተከስተ አስገድዶ ደፍሮኛል ጉዳዩም በህግ ተይዞአል የሚል በሽምግልናው ወቅት በጭራሽ ያልተነሳ ሌላ ተጨማሪ የውሸት ታሪክ ፈጠሩ። ይህን አላማ እንዲያስፈጽም ጋዜጠኛ አዲሱ አበበን ይዘው መጡ። አቶ አዲሱ ጋር ስንነጋገር ሆን ብሎ እኔን ለማጥቃት እንዳሰበና እውነቱን ማወቅ እንደማይፈልግ ስለገመትኩ በጉዳዪ ለይ ምንም አይነት ኢንተርቪው ላንተ አልሰጥም፣ ጉዳዪም በቤተክርስቲያን ሽማግሌዎች ተይዟል አልኩት። የቤተክርስቲያን መሪዎች እና ጉዳዩን የያዙትም ሽማግሌዎችም አቶ አዲሱን ይሄ የቤተክርሰቲያን ነገር ነው በዚህ ነገር ላይ ምንም አይነት ፕሮግራም በሬዲዩ ላይ መሥራት የለብህም ብለው እየነገሩትና እየተለመነ በማን አለብኝነት ጉዳዩን አጣሞ ሁላችሁም እንደሰማችሁት እኔን በሚያዋርድ ፣ስሜን በሚያጠፋ፣ ሕይወቴንና አገልግሎቴን በሚያበላሽ መልኩ ፕሮግራሙን ሰርቶ በሬድዮ አቀረበው። አሁንም የምለው እኔ የበደሉኝን ሁሉ ይቅር ብያለሁ። እንደ ክርስቲያንና እንደ አገልጋይ አጉድዬ በተገኘሁባቸው ጉዳዮች ላይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምህረትን ከባለቤቴና ከቤተክርስቲያኔ ደግሞ ይቅርታን አግኝቻለሁ። ዛሬ ደግሞ በእኔ ምክንያት ያዘናችሁትን ሁሉ ይቅርታ እጠይቃለሁ ብሏል።
አሁን እያሳየኸኝ ያለውን ማስረጃ ይዘህ ለማስተባበልና በሕግ ለመፋረድ እስከዛሬ ለምን ሙከራ አላደረግህም? ለሚለው ጥያቄም መልስ ሰጥቷል።

ሥሜንና ክብሬን በተመለከተ እኔ ሥምና የሚዋረድ ክብር የለኝም። እኔን ከጎዳና ላይ አንስቶ ሰው ያደረገኝ እግዚአብሔር ነው። ከእርሱ ውጭ በሰው የሚዋረድም የሚከብርም ማንነት የለኝም። ፍትህን በተመለከተ ደግሞ የምንኖርበት አሜሪካ የፍትህ አገር መሆኑን አውቃለሁ። የትኛውም ድርጅት፣ ባለሥልጣንም ሆነ ግለሰብ ከሕግ በታች መሆኑንም አውቃለሁ። ወንጌል አምኖ እንደዳነ ክርስቲያን ግን እግዚአብሔር ሁሉንም በጽድቅ ስለሚፈርድ ፍትህን ከእግዚአብሔር እንጂ ከማንም ሰው አልጠብቅም። ባለቤቴም ቢሆን ሁሉም ነገር በሰላምና በይቅርታ እንዲያልቅ ስለምትፈልግ ወደ ፍርድ ቤትም አልሄድንም። በዚህ አጋጣሚ ሳሚ በማያውቀውና በሌለበት ነገር በኔ ምክንያት ስለተሰቃየ ና በውሽት ስሙ ስለጠፋ በጣም ያዘንኩ መሆኔን እገልጻለሁ።

Thursday, September 10, 2015

ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?

ክፍል ሁለት
በክፍል አንድ ያቆምንበትን ሃሳብ ይዘን ከመቀጠላችን በፊት አንዳንድ ተቺዎች ባነሱልን ሞገት ዙሪያ ለዛሬ ጥቂት ማለት እንደሚያስፈልግ ስላመንን በዚያ ዙሪያ እንቆያለን።
 ሞጋቾቹ የሚያቀርቡት ማስረጃ በመዝሙር 34፤7 ላይ ያለውን ጥቅስ ነው።

«የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል»

ይህንን ጥቅስ በመያዝ ቅዱሳኑ መላእክት ሁልጊዜ በሰዎች ዙሪያ ሰፍረው ስለሚገኙ ማዳን፤ ጸሎት መቀበልና መልስ መስጠት የዘወትር ሥራቸው ነው ይላሉ። በሌላ ደግሞ መላእክት የሚኖሩበት ከተማ ኢዮር፤ ራማና ኤረር እንደሆነም ይናገራሉ። መላእክት ዘወትር በዚህ ምድር ባሉ ሰዎች ዙሪያ ሰፍረው የሚገኙ ከሆነ በኢዮር፤ ራማና ኤረር የሚኖሩት መላእክት ምንድናቸው? ወይስ መላእክት በሰማይም በምድርም በአንድ ጊዜ ይገኛሉ ማለት ነው? ተብለው ሲጠየቁ የመላእክትን ውሱን ተፈጥሮ ለማመን ይዳዳሉ። ነገር ግን በተግባር ይህንን ይቃረናሉ። ለምሳሌ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በተፈጥሮ ሥፍራው በሰማይ እያመሰገነ ሳለ በማእዘነ ዓለሙ ሁሉ ስሙን የሚጠሩትን  ሰዎች ልመና ይሰማል? መልስም ይሰጣል ወይ? ተብለው ሲጠየቁ አዎ ይሰማል ለማለት አያፍሩም። እንዲያማ ከሆነ ቅዱስ ሚካኤል በአንድ ጊዜ በሁሉም ሥፍራ ይገኛል ማለት ነው። ይህ ደግሞ ትልቅ ስህተት ነው። ፍጡር በተፈጥሮው ውሱን የመሆኑን ማንነት ይንዳል።

  እርግጥ ነው፤ ቅዱሳኑ መላእክት ሰዎችን ይራዳሉ፤ ያግዛሉ። ይህንን ስንል መጋቤ ፍጥረታትየሆነውን  እግዚአብሔርን በሥራ ያግዙታል ማለት አይደለም።  ይህች ያለንባት ምድር ትሁን ዓለማት በሙሉ የሚተዳደሩት በእግዚአብሔር ብቃትና ሥልጣን እንጂ በመላእክት አጋዥነት አይደለም። እግዚአብሔር ብቻውን በቂ ነው። ሁሉን ተአምራት የሠራ እርሱ ብቻውን ነው።
«እርሱ ብቻውን ታላቅ ተኣምራትን ያደረገ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና» መዝ 136፤4
የተአምራትና የድንቅ ነገር ሁሉ ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ ነው። ስለሆነም መላእክቱ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ አንጻር ያደረጉትን እያየን መላእክቱን በውዳሴና በስባሔ የምናቀርብላቸው አምልኮ የለም። ደግሞም ቅዱሳኑ መላእክት የሚኖሩባቸውን ዓለመ መላእክት ትተው በዚህ ምድር የሚዞሩበትም ሁኔታ እንዳለ መጽሐፍ ቅዱስ አይነግረንም። ይልቁንም ይህችን ምድር ያለመታከት የሚዞርባት ሰይጣን ብቻ ነው።
 ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ የፈረጠጠ እሱ ብቻ ስለሆነ ተቆጣጣሪ አልቦ ሆኖ ይኖራል። በራሱ ፈቃድ የት፤ የት እንደሚዞር ለፈጣሪው እንዲህ ሲል እናገኘዋለን።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም፤ ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ምድርን ለመዞር፤ በእሷ ላይም ለመመላለስ ፈቃድ አይጠይቅም። «ከወዴት መጣህ?» የሚለው የእግዚአብሔር ጥያቄ የሚያስረዳን አፈንጋጭና በፈቃዱ ያለትእዛዝ የሚዞር መሆኑን ነው። ቅዱሳን መላእክቱ ግን እንደዚህ አይደሉም። በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሥራ አላቸው፤ ትእዛዝ ይቀበላሉ፤ ትእዛዝ ይተገብራሉ እንጂ እንደሰይጣን በሰዎች ስለተጠሩ ወይም ባይጠሩም ስለፈለጉ የትም አይዞሩም፤ ያለትእዛዝም አይንቀሳቀሱም። በሁሉም ሥፍራም በምልዓት አይገኙም።

  መጽሐፍ ቅዱስ በትንቢተ ዳንኤል ላይ የመላእክትን ውሱንነት፤ መውጣት፤ መውረድ በደንብ የሚያስረዳን ቃል እንዲህ ይላል።
«እነሆም፥ አንዲት እጅ ዳሰሰችኝ፥ በጕልበቴና በእጄም አቆመችኝ። እርሱም፦ እጅግ የተወደድህ ሰው ዳንኤል ሆይ፥ እኔ ዛሬ ወደ አንተ ተልኬአለሁና የምነግርህን ቃል አስተውል፥ ቀጥ ብለህም ቁም አለኝ። ይህንም ቃል ባለኝ ጊዜ እየተንቀጠቀጥሁ ቆምሁ። እርሱም እንዲህ አለኝ። ዳንኤል ሆይ፥ አትፍራ ልብህ ያስተውል ዘንድ፥ ሰውነትህም በአምላክህ ፊት ይዋረድ ዘንድ ካደረግህበት ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ቃልህ ተሰምቶአል እኔም ስለ ቃልህ መጥቻለሁ። የፋርስ መንግሥት አለቃ ግን ሀያ አንድ ቀን ተቋቋመኝ እነሆም፥ ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ እኔም ከፋርስ ነገሥታት ጋር በዚያ ተውሁት» ዳን 10፤10-13
ነቢዩ ዳንኤል ያከናወነው መንፈሳዊ ተጋድሎ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተወደደ ስሙ ያልተጠቀሰ አንድ መልአክ የተሰጠውን መልእክት ሊነግረው መጥቷል።   መልእክቱ ለዳንኤል ከመድረሱ በፊት የፋርስን መንግሥት የተቆጣጠረው የተቃዋሚ መንፈስ አለቃ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከውን መልአክ 21 ቀን መንገድ ላይ እየተዋጋ አዘግይቶታል። ያንንም የእግዚአብሔር መልአክ ሊያግዘው ቅዱስ ሚካኤል እንደመጣና ውጊያው ከቅዱስ ሚካኤል በዚያ እንደተወውና ወደእርሱ እንደወረደ መልአኩ ለቅዱስ ዳንኤል ሲነግረው እናነባለን።

ከዚህ ምንባብ የምንረዳው ፤
1/ መላእክት የሰዎች መልካም ሥራና ተጋድሎ በእግዚአብሔር ሲወደድ የማናውቀው መልአክ ሊረዳን፤ ሊያግዘን፤ ሊያድነን ከእግዚአብሔር ዘንድ ሊላክ እንደሚችል፤
2/ መላእክቱን ለእገዛና ለረድኤት የሚያመጣቸው የኛ ስራ በመላእክቱ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት በማትረፉ እንዳልሆነ፤
3/ አንድ መልአክ ወደተላከበት ስፍራ ሲሄድ የነበረበትን ሥፍራ እንደሚለቅ፤ በቦታ እንደሚወሰን፤ ባለጋራ ሊዋጋው እንደሚችል፤
4/ መላእክት እንደሚተጋገዙ፤ አንዱ ከአንዱ በኃይልና በሥልጣን እንደሚበልጥ፤
5/ መውጣትና መውረድ እንዳለባቸው፤ በሁሉም ስፍራ እንደማይገኙ ያስረዳናል።
ስለሆነም ቅዱሳን መላእክት ይራዱናል፤ ያግዙናል፤ ያድኑናል ሲባል ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ባላቸው ግንኙነት የተነሳ በተልእኮ ሲመጡልንና ሲደርሱልን ብቻ ነው። ከዚያ ባሻገር ሰዎች ስም እየመረጡ፤ የኃይል ሚዛን እያበላለጡ ስለጠሯቸው የሚመጡ አይደለም።
እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች የሚያስረዱን በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሚላኩ መሆናቸውን ነው።
«የሰማይ አምላክ እግዚአብሔር፥ እርሱ መልአኩን በፊትህ ይሰድዳል» ዘፍ 24፤7  «እግዚአብሔር መልአኩን ከአንተ ጋር ይልካል፥ መንገድህንም ያቀናል»ዘፍ 24፤40  «እግዚአብሔርም መልአኩን አዘዘው፥ ሰይፉንም በአፎቱ ከተተው» 1ኛ ዜና 21፤27  «እግዚአብሔርም ጽኑዓን ኃያላኑንና መሳፍንቱን አለቆቹንም ከአሦር ንጉሥ ሰፈር እንዲያጠፋ መልአኩን ሰደደ» 2ኛ  ዜና 32፤21  «መልአኩን የላከ፥ ከአምላካቸውም በቀር ማንም አምላክ እንዳያመልኩ» ዳን 3፤28  «አምላኬ መልአኩን ልኮ የአንበሶችን አፍ ዘጋ» ዳን 6፤22
አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የማልኮስን ጆሮ ለቆረጠው ጴጥሮስ እንዲህ ብሎት ነበር። «
«ወይስ አባቴን እንድለምን እርሱም አሁን ከአሥራ ሁለት ጭፍሮች የሚበዙ መላእክት እንዲሰድልኝ የማይቻል ይመስልሃልን?» ማቴ 26፤53
 ለኢየሱስ በስቅለቱ ሰሞን የመያዝ፤ የመገፋት፤ የመንገላታት የመገረፍ መከራ ሁሉ ከአብ ዘንድ ትእዛዝ ሳይወጣ የሚያግዙት መላእክት አይመጡም ነበር። ፈቃዱን ሳይሆን የአብን ፈቃድ ለመፈጸም የመጣውም ይህንን ሁሉ ሊቀበል ነውና። ከዚህ ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት የምንረዳው እውነታ ቅዱሳን መላእክቱ ከአብ ትእዛዝ ሳይሰጣቸው የትም መሄድ የማይችሉት ወልድ የመጣው የአብን ፈቃድ ሊፈጽም ስለሆነ ነው። ተገቢ ለሆነው የሰዎች ልመናና ጸሎት የሚያስፈልገውን የሚያደርገው ሁሉን አዋቂ በሆነው በእግዚአብሔር ትእዛዝ ሲላኩ ብቻ ነው።
የሰዎች ድርሻ ወደእግዚአብሔር መጮኽና መለመን ሲሆን ምላሹን ደግሞ የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው። «መላእክቱን በስማቸው ስንለምንና ስንማጸናቸው ይሆንልናል፤ ይደረግልናል»የሚሉ ሰዎች ቆንጽለው የሚያቀርቧት የመዝሙር 34፤7 ጥቅስ «የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል» የሚለውን ነጥለው በማውጣት ቢሆንም የዚህ አጋዥ መከራከሪያ ጥቅስ ሙሉ ማስረጃ ግን ከላይ ከፍ ባለው ቁጥርና ከታችም ዝቅ ብሎ በተጻፈው የምንረዳው፤ እግዚአብሔር ላይ ብቻ እንድንታመን የሚያደርጉ ናቸው። ሙሉ ጥቅሱ ይህንን ይመስላል።
«ይህ ችግረኛ ጮኸ፥ እግዚአብሔርም ሰማው፥ ከመከራውም ሁሉ አዳነው።
የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።
እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው።
የሚፈሩት አንዳችን አያጡምና ቅዱሳኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፍሩት» መዝ 34፤ 6-9

ነቢዩ ዳዊት በደረሰው ችግር ወደእግዚአብሔር ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤ ከመከራውም አዳነው። የእግዚአብሔርም መልአክ እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ በታዘዘም ጊዜ ያድናል። ምክንያቱም በእግዚአብሔር የሚታመኑና እሱንም የሚፈሩት አንዳች አያጡምና። ቁጥር 8 እና 9  በእግዚአብሔር መታመንና መፍራትን ገንዘብ ያደረጉ ሁሉ ምላሽ እንደሚያገኙ ያስረዳናልና።

«ቅዱሳን መላእክቱ በዚህ ምድር እየዞሩ ለሰዎች የሚራዱና የሚያግዙ በመሆናቸው በስማቸው የሚደረገውን የሰዎችን ልመናና ጸሎትም ይሰማሉ» የሚል ክርክር የሚያነሱ ሰዎች መላእክቱ በቀጥታ ታዘው ያደረጉትን መነሻ በማድረግና በማድነቅ እንጂ ቅዱሳኑ መላእክት ራሳቸው ምሥጋናንና ውዳሴን ተገቢያቸው እንደሆነ ሽተው እግዚአብሔርን ከሚያውቁ ሰዎች ሲቀበሉ አናይም። እንዲያውም በራእይ መጽሐፍ ላይ እንደምናነበው ቅዱስ ዮሐንስ፤ እግዚአብሔር በመልአኩ በኩል ስላደረገለት፤ ስለነገረውና ስላሳየው ነገር ሁሉ በፊቱ ወድቆ በሰገደ ጊዜ የተሰጠው ማስጠንቀቂያ እንዲህ የሚል ነበር።

«ልሰግድለትም በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እርሱም፦ እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና አለኝ»       ራእ 19፤10
ዛሬ ግን ሰዎች «ለእግዚአብሔር ስገድ» የሚለውን የመልአኩን የማስጠንቀቂያ መልእክት ወደጎን ትተው «ለመልአኩም ስገድ» እያሉ ሲሰብኩ ይገኛሉ። መልእክት አድራሹ መልአክ ከዮሐንስ በተሻለ ስለመልእክቱ ምንነት እውቀት እንዳለው እርግጥ ነው። ከዐውደ ንባቡ እንደምንገነዘበውም ስለመልአኩ ቢያንስ ሁለት ዐበይት ነገሮችን እንረዳለን። አንድ፤ መልእክቱን በቀጥታ ከእግዚአብሔር እየሰማ ለዮሐንስ የሚያደርስ መሆኑን። ሁለትም፤ መልአክቱ ከዮሐንስ ዘንድ ከመድረሱ በፊት በመልአኩ ዘንድ የተሰማና የታወቀ መሆኑን ነው። ስለሆነም ዮሐንስ ስግደትን ለመልአኩ መስጠት የፈለገው መልአኩ የፈጣሪ የቅርብ ባለሟል በመሆኑና የሚያየውን ግርማ በመፍራት እንዲሁም ይዞለት የሚመጣው መልእክቶቹ እጅግ ከባድና ከዚህ በፊት በሕይወቱ ሰምቶአቸው የማያውቅ ከባድ የሕይወት ልምምድን የሚያሳዩ በመሆናቸው የተነሳ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል።
ስለዚህ «ተጠንቀቅ» ያለውን ቃል መጠበቅ ብልህነት ነው።
ክፍል ሦስት ይቀጥላል …..

Saturday, September 5, 2015

ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው !!


ከዚህ በፊት ስለተከስተ ጌትነት የአሜሪካው አማርኛ ድምጽ አየር ላይ ካዋለው መረጃ ተነስተን ዐመጻውን በንስሐ እንዲተው የሚያሳስብ ዘገባ አውጥተን ነበር። በንስሐ ስለመመለሱ እየተናገረ ባለበት ሁኔታ የባለቤቱን ጽናትና ያላትን የይቅርታ ልብ ተመልክተን ወደፍቺና የግድያ ተግባር ላለመሄድ የተጓዘችበትን የክርስትና አርአያነት «አሌክስ አብርሃም» የዘገበውን ልናስነብባችሁ ወደድን።
 


ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው !!
 (አሌክስ አብርሃም )

ይቅርታ መቸም እንደሚወራው ቀላል ነገር አይደለም !! በተለይም በባልና በሚስት ማሃል በአንድኛው ወገን ለትዳር አለመታመን ሲከሰት የተበደለው አጋር ይቅር ለማለት ይቸገራል …እንዲህ አይነቱ ነገር ሲከሰት ሚስት ባሏን በመፍለጫ …በተኛበት አቅምሳው እጇን ለመንግስት የሰጠችበት ዜና ሰምተናል ….ባልም በገጀራ ሚስቱን አመሳቅሎ ዘብጥያ የወረደባቸውን በርካታ ዜናዎች በቲቪ ተመልክተን አማትበናል ! የራሱ ጉዳይ ያሉም ትዳራቸውን በትነዋል !
ይህን ነገረ ካለነገር አላነሳሁትም …. በዚያ ሰሞን ከወደአሜሪካ የሰማነው ዜና የሚታወስ ነው …..ዘማሪ ተከስተ ጌትነት ሚስቴን አማግጦብኛል ያለ አንድ ሰው በየሚዲያዎቹ ቀርቦ ፍረዱኝ ሲል ሁላችንም ሰምተን ጉድ ጉድ ብለናል ! ማገጠች የተባለችውም ሴት በየሚዲያው እንዴት ካንድ አይሉ ሁለት ሶስት ጊዜ ወዳረፈበት ክፍል ጎራ እያለች ‹‹ሳትፈልግ ›› አብረው እንደተኙ በዝርዝር መግለፅዋ ይታወሳል ….ፓስተር ተከስተ ጌትነትም ይህንኑ አምኖ ይቅርታ መጠየቁ እንደዛው ..ሚዲያውም እስኪበቃው አናፍሶታል !ዘማሪ /ፓስተር ተከስተ በሚያገለግልበት ቤተክርስቲያንም አገልግሎቱን እንዳቆመ ተዘግቦ ነበር !!
ታዲያ ያኔ አገር ይያዝ ያለው ሚዲያ ለዚችኛዋ ዜና ጭጭ ማለቱ ስለገረመኝ …ያው ችግሩን ካወራን መጨረሻውስ ምን ሆነ የሚለውን ዝም ማለቱ ተገቢ አይደለም በሚል ይችን ፅሁፍ እነሆ አልኩ ……. ትላንት ‹‹የእውነት ቃል ጎስፕል ሚዲያ›› ‹‹የእንደገና አምላክ›› በሚል ርእስ እንደዘገበው ከሆነ ዘማሪ ጌትነት ባለፈው ቅዳሜ በምእመኑ ፊት ቁሞ ስለሁኔታው ምስክርነቱን ሰጥቷል … ባለቤቱ የምስራችም የሆነውን ሁሉ ይቅር እንዳለች በሚገልፅ አጭር ቃል እንዲህ ብላለች ‹‹ ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው ›› ፓስተር ጌትነትም ወደአገልግሎቱ ተመልሷል !! መቸስ ይቅርታ ጥሩ ነው … መልካም የትዳርና የአገልግሎት ጊዜ ይሁን እያልኩ ….ምንም እንኳን የመጀመሪያ ተጎጅዋ እርሷ ብትሆንም እንዲህ በችግር ጊዜ የራሷን ብሶት ትታ ከባሏ ጎን የምትቆም ሚስት ማግኘት መታደል ነው የሚል የግል አስተያየቴን ጨምሬ ላብቃ !!

Wednesday, August 26, 2015

በአመልካች ጣትህ ሌላው ላይ ስትጠቁም፤ ሦስቱ ጣቶችህ ይመሰክሩብሃል!





  አንዳንድ ሰዎች የራሳቸውን ግፍ፤ ዐመጻና ኃጢአት ለመሸፈን የአቻቸውን በደልና ዐመጻ በማቅረብ ለመደበቅ ይሞክራሉ። ነገር ግን የሌላው ሰው ዐመጻና በደል መቁጠር የራስን የኃጢአት ደብዳቤ አይፍቀውም። በየትኛውም ማእዘን የሚገኙ ዐመጸኞች ከዐመጻቸው እስካልተመለሱ ድረስ ዐመጻቸው ሰላማዊውን ሊያጠፋ ይችላል።  ከኋላ ይሁኑ ከፊት ዐመጸኞች የቆሙበት ሥፍራ ብቻውን ንጹሐን አያደርጋቸውም። ይልቁንም ሰላማዊው ላይ በሽታቸው እንዳይጋባ ቢቻል ሸክማቸውን በንስሐ እንዲያራግፉ ሊነገራቸው፤ ሸክሙ ተስማምቶናል ካሉም ራሳቸው ተሸክመው ገለል እንዲሉ ሊደረግ ይገባል።  ተፈጥሮ የሰጣትን ሁለት መልክ በመጠቀም ለማሳሳት ሞክራለች ተብሎ በምሳሌ እንደሚነገርላት የሌሊት ወፍ ከአይጦች ዘንድ ሄዳ ጥርሷን በማሳየት «እኔ የእናንተ ወገን ነኝ» ካለች በኋላ ከወፎችም ማኅበር ተቀላቅላ ክንፏን እያራገበች «የተከበራችሁ ወገኖቼ እንደምን አላችሁ!» እንዳለችው እንስሳ በሁለት ገጽ ለማታለል የሚሞክሩ የዘመኑ ተለዋዋጮች ራሳቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሸክም ሆነው ሳሉ የችግሯ ደራሽ ለመምሰል መሞከራቸው በዚህ ዘመን እንደማይቻል በግልጽ ሊያውቁት ይገባል።

   ሰሞኑን የምንመለከተው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደአዞ ሐረግ በጎን በቅሎ በዋናው ግንድ ላይ የተጠመጠመው በቅዱሳን ስም የሚጠራው ማኅበር ተራራ የሚያክል የራሱን ኃጢአትና ዐመጻ ላይደበቅ ሸሽጎ የሙስና ተዋጊና የቤተ ክርስቲያኒቱ አዳኝ ለመሆን ሲታትር እያየን ሲሆን በሞት የሚፈላለጋቸውንም ፓትርያርክ በማወዳደስ ላይ መጠመዱ «ቁርበት አንጥፉልኝ» የተባለውን ብሂል እንድናስታውስ አድርጎናል።

  እኛም ነገሩ ቢገርመን «አመልካች ጣትህን ስትጠቁም፤ ሦስቱ ጣቶችህ በራስህ ላይ ይመሰክሩብሃል» ልንለው ወደድን። ሙሰኞቹም፤ ማኅበሩም የቤተ ክርስቲያኒቱ ጠንቅ ከመሆን ባለፈ አንዳቸው የአንዳቸው አጣሪ፤ ጠቋሚና አባራሪ ሊሆኑ በፍጹም አይችሉም። ከዚህ በፊት በማኅበሩም ላይ ሆነ በነፍሰ በላ ሙሰኞቹ ላይ ተከታታይ ጽሁፍ በማቅረብ ሁሉ አጥፊዎች  መሆናቸውን በግልጽ ተናግረናል። አሁንም የምንናገረው ያንኑ በመድገም ነው። የምናሰምርበትም እውነት «ከማኅበሩና ከሙሰኞቹ የትኛው በመወገድ ሊቀድም ይገባል? የሚለው ካልሆነ በስተቀር በሁለቱም አላስፈላጊነት ላይ አንዳችም ብዥታ የለንም»

   ስለሆነም በማኅበሩ ላይ ከዚህ በፊት በፓትርያርኩ የተያዙ አቋሞች በሙሰኞች ማጥራት ሽፋን የሚታለፍ ወይም የሚቀየር ከሆነ ከሁለት ጅቦች መካከል አንዱን ጅብ ምርጫ የመውሰድ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ቤተ ክርስቲያኒቱን ለመታደግ የሚደረግ እንቅስቃሴ አይደለም እንላለን። በመካከላቸው የመጠንና የዓይነት ካልሆነ በስተቀር ቤተ ክርስቲያኒቱን በሚግጡ ጅቦች መካከል የተግባር ልዩነት ስለሌለ ሁሉም ቦታቸውን ሊይዙ የሚገባቸው የጥፋት ኃይሎች መሆናቸው አያጠያይቅም። እንደምንመለከተው ያለው መገፋፋት በሦስት የሚከፈል ይመስለናል።

  1ኛው- ጫንቃው የደነደነ ማኅበር ከቦታው ሊወገድ የተገባው ቢሆንም  የተወሰኑ አስተዳዳሪዎችና ከታች ያሉ ዘራፊዎች፤ ቅዱስ ነኝ የሚለውን ማኅበር የሚጠሉት ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ስላደረሰው በደልና ግፍ በመቆርቆር ብቻ ሳይሆን በስለላ መረቡ ስለተጠለፉና እዳ በደላቸው ስለተጻፈባቸው፤ ከሚከተላቸው ፍርሃትና ድንጋጤ ለመገላገል ሲሉ በሐቅ ከሚታገሉት ጋር በኅብረት የሚጮኹ አንድ ቡድን ናቸው።

 2/ ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያኒቱን መስሎና አኅሎ በላይዋ ላይ ነግሶ በስሟ መነገዱ የታያቸው፤ በመንገድ ላይ ቆሞ እንቅፋት የሆናቸው፤ ለስውር ዓላማው የስለላ ቡድኑን ያወቁ፤ የቤተክርስቲያኒቱን ልጆች ለራሱ መመልመሉ የቆጫቸው፤የገቢ አቅሙን እያደለበ፤ ሀብቷን ለራሱ ዓላማ ሲጠቀም የተመለከቱ፤ የኃጢአት በደል ጸሐፊ፤ ለሲኖዶስ ክፍፍል ረጅም እጅ ያለው መሆኑን የተረዱ በትክክል አምነው የሚታገሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በሁለተኛ ረድፍ አሉ። ይህ ረድፍ ድምጹን የሚሰማና የሚያስተባብረው የበላይ አመራር ቢኖር ኖሮ ውጤታማ ሥራ ለመስራት የሚችልና በሙሰኛ አስተዳዳሪዎችም ይሁን በማኅበሩ ተግባር የመረረው ቡድን ነው ።

  3/ ራሱን ቅዱስ፤ ጻድቅና የቤተ ክርስቲያኒቱ መድኅን አድርጎ የተነሳ፤ በገንዘቡ፤ በኃይሉ፤ በአስተዳደሩ፤ በሴራ መዋቅሩና በእንቅስቃሴው አደገኛ የሆነ፤ የራሱን የሲኖዶስ አባላት ያደረጃ፤ ስለቤተክርስቲያኒቱ ሳይሆን ከጥቅሙ ጋር ለቆመ ሰይጣንም ቢሆን የሚተባበር፤ ሰዎችን በማጥመድ አገልጋይ ለማድረግ የሚተጋ፤ የሰዎች የእዳ በደል መዝጋቢ፤ ሰላይ፤ በዝሙት የረከሰ፤ ነጋዴ፤ አስመሳይና አታላይ ነገር ግን በሩቅ ሲያዩት ቆዳው ከእባብ የለሰለሰ ማኅበር፤ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባለው በሦስተኛ ረድፍ አለ።
በዚህ መካከል ከወዲህም ከወዲያም የሚዘምቱ፤ ነገር የሚያማቱ፤ የሚያወሻክቱ፤ የአስመሳዮች ቡድን እንደወቅቱ ሁኔታ፤ ኃይል ወዳጋደለበት የሚያጋድሉ የአስተሳሰብ ድሆች ከሲኖዶስ ጀምሮ በየደረጃው ቢኖሩም ተጽእኖ ፈጣሪ ሆነው ለእክል የሚበቃ አቅም የላቸውም።

 በሦስቱ ረድፎች ያለውን የኃይል አሰላለፍ ተመልክቶ ተገቢ ከሆነው ወገናዊ ኃይል ጋር በመቆም እንቅስቃሴ መውሰድ የተገባ ቢሆንም እስካሁን ከወሬ ባለፈ የሚታይ እርምጃ ብዙም ሲወሰድ አይታይም።
ወቅቱ በፈጠረው የቤተክርስቲያኒቱ ተግዳሮትና የችግር እሳት መካከል የተገኙትት ፓትርያርክ ማትያስ ምን ዓይነት እርምጃ፤ መቼና ከማን ጋር ሆነው መውሰድ ይችላሉ? የሚለው ጥያቄ ምላሽ የሚያሻው ወቅታዊ ጉዳይ ይመስለናል። አካሄዱን በሳተ፤ ውጤቱም ምን ሊሆን እንደሚችል ባልተጠና ውሳኔ የሚወሰድ እርምጃ ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል። ስለሆነም በገበያ ግርግር መካከል የሚዘለው ማኅበር የራሱን የቤት ሥራ ሳይጨርስ «ከፓትርያርኩ ጋር አለሁ፤ አለሁ» የሚለው ጉዳይ አሳሳቢ ነው።
ስለማኅበሩም ይሁን ማኅበሩን በሚደግፉ ነገር ግን ብዙ ችግር ባለባቸው ሰዎች ዙሪያ ትንፍሽ የማይለው «ሐራ» የተባለው ብሎግ የማኅበሩ ቀኝ እጅ ስለሆኑት አባ ማቴዎስ ለሙስና ውጊያ የመዘጋጀታቸውን ዜና መስራቱ እንዲሁም የፓትርያርኩን ፈቃደኝነት አደበላልቆ ማቅረቡ ችግሩን ለመቅረፍ ሳይሆን የማኅበሩን ጉዳይ ለመሸፈን አጋጣሚ ማግኘቱን የሚያመለክት ነው።
 ስለሆነም ለፓትርያርኩ የመፍትሄ ሃሳብ ሊሆኑ የሚችሉ ነጥቦችን ለመጠቆም እንወዳለን።

  1/ በቅድሚያ ፓትርያርኩ ብቻቸውን ተንቀሳቅሰው፤ ብቻቸውን ጮኸው፤ ብቻቸውን ታግለው የሚያመጡት ውጤት እንደሌለ በመረዳት የተሻለ ግንዛቤ፤ እውቀትና የአስተዳደር ክህሎት ያላቸውን የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ግድ የሚላቸውን ሰዎች በሥራ አጋርነት በዙሪያቸው ማሰባሰብ ያስፈልጋቸዋል። ከጳጳሳቱም ብዙዎቹ በማኅበሩ የተጠለፉ ወይም ከሙስናና ከዘረኝነት ጋር የተሳሰሩ ስለሆነ ከጳጳሳቱም ሆነ ከበታች ሹማምንት መካከል ጥንቃቄ የታከለበት ምርጫ መደረግ አለበት። የፓትርያርኩ ልዩ ፀሐፊ፤ የፕሮቶኮል ሹም፤ የውጪ ግንኙነት ክፍል፤ የፓትርያርኩ ቢሮ ኃላፊ እና ሌሎች ተጨማሪ ክፍሎችን ማደራጀት ያስፈልጋል። የፓርትያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት በሆነው አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውስጥ ሥራ አስኪያጅ፤ የሀገረ ስብከቱ ፀሐፊ፤ የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ወዘተ ክፍሎች ፓትርያርኩ ለሚያደርጓቸው ቀጣይ እርምጃዎች ወሳኝ ስለሆኑ ይህንን በተጠናና መልኩ እንደገና ማዋቀር የግድ ይላል። የፓትርያርኩ ጽ/ቤት የየዕለት የሥራ ውሎ ከበታች ክፍሎች ሪፖርት በመቀበልና ለፓትርያርኩ በማቅረብ ተከታታይ የሥራ መመሪያና ትእዛዝ በማስተላለፍ ያልተቋረጠ ክትትል ማድረግ ያስፈልጋል።

2/ እንደአጭር ጊዜ የማስተካከያ እርምጃ  ከላይ በተራ ቁጥር 1 በተመለከተው ነጥብ ውስጥ ያሉ አካሎችና ሌሎች አጋዦች ያሉበት አጣሪ ኮሚሽን በማዋቀር በሚያደርጉት ምርመራ በሙስና የከበሩ፤ ከሌላቸው ደመወዝና ልዩ ገቢ ውጪ ሃብት ያከማቹ፤ አላግባብ የበለለጸጉ፤ የገንዘብ ብክነትን ያስከተሉ አሰራሮች ሁሉ ዝርዝር መረጃቸውና ከነመፍትሄ ሃሳቦቻቸው በማቅረብ ማስተካከያና የሕግ እርምጃ በማስወሰድ በፍጥነት መግታት ተገቢ ወቅታዊ እንቅስቃሴ መሆን አለበት እንላለን። ነገር ግን እንደረጅም ግብ ሊታይ የሚገባው ጉዳይ በፓትርያርኩ የሚመራ የመዋቅር ጥናትና ማሻሻያ መምሪያ በማቋቋም ከዘመናዊ አስተዳደር ጋር ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማዘመን የመዋቅር ማሻሻያ ጥናት መደረግ ይገባል። 

ከዚያ ባሻገር በማኅበሩ ግፊት፤ በአስፈጻሚ ጳጳሳቱ በኩል ሙስናን እናጣራለን ማለቱ «በቆሻሻ መጥረጊያ ቤት መወልወል ይሆናል»

3/ ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በፊት እንደተወሰነው ሀብትና ንብረቱን እንዲያስመዘግብ፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሞዴላ ሞዴሎች እንዲጠቀም፤ ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ያለውን ሂሳብ በቤተ ክርስቲያኒቱ ኦዲት እንዲያስመረምር፤ ለወደፊትም በቤተ ክርስቲያኒቱ ተወስኖ በሚሰጠው ደንብ እንዲመራ የተላለፈውን ውሳኔ ያለምንም ማመንታት ተግባራዊ ማድረግ የግድ ይላል። በዚህ ዙሪያ ፓትርያርኩ የገቡትን ቃል በመጠበቅ ማስፈጸም እንዳለባቸው እናምናለን።
ስለሆነም ስለሙስናና ስለገንዘብ ብክነት ለመናገር በዘረኝነትና በእከከኝ ልከክህ የተሳሰሩ የጥቅም ተጋሪ ጳጳሳቱና ከኋላ በሚገፋቸው ማኅበር ሳይሆን እጃቸው ንጹህ የሆነ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን የጣሪያ ሳር ያልመዘዙ ልጆችዋ በኩል በመሆኑ ፓትርያርኩ ቆም ብለው በአስተውሎት እንዲመለከቱት ልናሳስብ እንወዳለን። እርግጥ ነው፤ ቤተ ክርስቲያን ችግር ላይ ነች። ነገር ግን ችግሯን ተተግነው ደረስንላት የሚሉ ሁሉ የየራሳቸውን ስውር ዓላማ ደብቀው የተነሱ ስለሆነ ጥንቃቄ መወሰድ ይገባዋል።

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ 

በቅንነት የምንገልጽልዎ ነገር የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር የሚያንገበግባቸው፤ በታማኝነት፤ በፈሪሃ እግዚአብሔር ለማገልገል መንፈሳዊነቱም ፈቃደኝነቱም ያላቸው የተማሩ ልጆች ስላሉአት በጥንቃቄ አጥንተው ለቀጣይ እርምጃ እንዲበራቱ እንጠይቃለን። ማኅበሩም አጋጣሚዎችን ለራሱ በሚመቸው መልኩ እየተጠቀመ፤ የተወሰነበትን ውሳኔዎች ለማስቀልበስ የሚሄድበትን መንገድ ሊዘነጉ አይገባም። ቁርጠነቱ ካለ ሙሰኞችንም፤ ማኅበሩንም ቦታ ቦታቸውን ለማስያዝ ሰውም፤ ጊዜም፤ ኃይልም አለ!!

Saturday, August 22, 2015

ዘማሪት ዘርፌ ከበደ በማኅበረ ቅዱሳን ከተጠመደባት ወጥመድ በእግዚአብሔር ርዳታ ዳነች!


ባለፈው እሁድ ማለትም 10/12/2007 ዓ/ም በአዳማ ከተማ፣ በሥላሴ ቤተክርስቲያን፣ በተካሄደው ታላቅ ጉባኤ ዘማሪት ዘርፌ ከበደን በሕዝብ ሁሉ ፊት ‹‹በድንጋይ ወግሮ ማስወገርን›› ዓላማ አድርጎ ወደ ጉባኤው በነጎደው ማህበር ቅዱሳን ወጥመድ፤ እግዚአብር በችሎቱ ያዳናት፡፡ ይህ የጥፋት ማኅበር በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ጠብንና ሁከትን በምዕመናኑ መካከል የመፍጠር አጀንዳ ከመሸከሙ የተነሳ እንዲህ ዓይነት የወረደ አህዛባዊ ወጥመድ አጥምዶ በእግዚአብሔር ጉባኤው ውስጥ መግባቱ ለብዙዎች ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳን ያነገበ ጽንፈኛ ማህበር መሆኑን ፍንትው አድርጎ ያሳየ ሆኖል፡፡

    ዘማሪት ዘርፌ ከበደ በቤተክርስቲያናችን ደንብና ስርዓት በመዘመር በሕዝብ ሁሉ ፊት በአንድ ልብ በአንድ መንፈስ እግዚአብሔርን እያከበረች ባለበት ወቅት ነው፤ ባለ-ጊዜ በሆነ አንድ የማህበሩን ራዕይ በሚያራምድ ግለሰብ፤ መድረክ ላይ በእጇ የጨበጠችውን ማይክ በመንጠቅ፣ በግብዝነት በነሆለለ አዕምሮ ቢስነት በጥፊ ለመምታት ሙከራ ያደረገው፡፡ በሰዓቱ በሺዎች የሚቆጠር ምእመናን በመንፈስ መቃኘት ተወስኖ፣ በቅድስት ቤተክርስቲያን ዐውደ ምህረት ተሰባስቦ፣ የአንድነት የምስጋና ድምጽ ወደ ክቡር ዙፋን፣ ወደ ጸባኦት እንዲህ ሲል ይዘምር ነበር፡-

‹‹የማልደራደርበት የማልቀብረው እውነት፣ አንገት የማያስደፋ የማላፍርበት፣ ኢየሱስ የሚለው ስም እስትንፋሴ ነው፣ እውነቱ ይሄ ነው››፡፡ አስከትሎም ደግሞ በዚሁ የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ኢየሱስን በሚያከበረው መንፈስ በመቀጣጠል ይሄው ሕዝብ፡- ‹‹የኔ ናርዶስ የኔ ቤዛ፣ በመዓዛው ልቤን ገዛ፣ ያንን መዳፍ ተመልክቼ፣ ተከተልኩት ሁሉን ትቼ"

 እያለ በአንድ ልብ እያመሰገነ ባለበት ቅጽበት ነው እግዚአብሔር ሲከብር በአንዳች ቁጣ የሚሞላው፣ በአንዳችም ሽንፈት ወራዳ ሥራን ሲሰራ የሚታወቀው፣ የጨለማው ዓለም ገዥ ዲያብሎስ በአደራጃቸው ጋሻ ጃግሬዎቹ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል በስጋ አካል መዋጋት የጀመረው፡፡ በዚህ ሽብር መሐል ነው መጋቢ ምስጢር ቀሲስ ገብረሚካኤል የማነ በመነሳት ከወጋሪዎቿ እጅ ባላቸው የቤተክርስቲያኒቱ ስልጣንና አክብሮት በመንጠቅ ሥራ ተጠምደው ሳሉ፤ የአዳማ ከተማ ፖሊስ በስፍራው ደርሶ ዘማሪት ዘርፌን ከጽንፈኛው ማህበር ወጥመድ ያያዳኗት፡፡ መጽሐፍ እንደሚል፡- ‹‹ነፍሳችን እንደ ወፍ ከአዳኞች ወጥመድ አመለጠች። ወጥመድ ተሰበረ እኛም አመለጥን።›› መዝ 124፡-7፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን የተመለከቱ፣ በዚህ አንካሳ ማኅበር ሽብር ክፉኛ ልባቸው የተሰበረ ምዕመናን ‹‹በጉባኤው ውስጥ በሐዘን እንባ ፊታቸው›› ሲታጠብ ተስተውሏል፡፡ ማህበረ ቅዱሳን የቤተክርስቲያን የወቅቱ ፈተናና መከፋፈል ምክንያት መሆኑ አሁን አሁን በግላጭ መታየት ጀምሯል፡፡

    እንዲህ ዓይነት የወረደ ግብር በማኅበረ ቅዱሳን ሁከት ፈጣሪነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናንና ብርቅዬ አገልጋዮቿ ላይ መፈጸሙ እንግዳ እንዳልሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ለዛም ነው ብዙዎች የደብር አለቆችና ካህናት በአንድ ድምጽ ማኅበሩ ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳውን በቤተክርስቲያኒቱ ስም እየፈጸመ እንዳለ የመሰከሩትን በማስረጃነት በመጥቀስ ሆነ ብሎ ‹‹ቤተክርስቲያኒቱን በሽብር ለማናጥ እየሰራ›› ነው ሲሉ የሚከሱት፡:

    ከዚህ በፊትም ይሄው ማህበር ባሰለፋቸው ጨካኝ ወንቤዴዎቹ በመታገዝ፤ ግንቦት 8 ቀን 2005 ዓ/ም በቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን፣ የቀሲስ ሊቀ መዘምራን ትዝታው ሳሙኤልን ደም ማፍሰሳቸውንና በአምቡላንስም ለፈጣን ህክምና ሆስፒታል ድረስ ለመሄድ ተገዶ እንደነበር የምናስታውሰው ነው፡፡ ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ቀሲስ ትዝታው ሳሙኤል በማኅበረ ቅዱሳን በኩል በቅድስት ቤተክርስቲናችን ላይ እየደረሰ ስላለው እኩይ ተግባር ለአባ ሰረቀ ብርሃን ያቀረበውን ግልጽ ጥያቄ  ማየት ይችላሉ፡-

    በቅርቡ አፍሪካ ሕብረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን፣ በሴኔ ወር 12 ቀን 2007 ዓ/ም እንዲሁ በደቀመዝሙር ዘማሪ ዲያቆን ከፍያለው ቱፋ ላይ ከፍተኛ ድብደባ መፈጸሙና ለቀናት ያክል በህክምና ሲረዳ መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡ ድብደባቸው ሳይሆን የሚገርመው ቅድስት ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ በማን አለብኝነት መፈንጨታቸና አገልጋዮችን እየደበደቡ ሞባይል ቀፎና ገንዘብ የመዝረፋቸው ነገር ነው የሚደንቀው፡፡

ለዚህ ማሳያ የሚሆነው ዲያቆን ከፍያለው ቱፋን ደብድበው ከጣሉት በኋላ የ4500 ብር ስማርት ፎንና ገንዘብ ሰርቀው ሲያበቁ ‹‹አንተ ተሐድሶ፣ አንተ ጴንጤ፣ ደበደብንህ፣ ምንትሆን እንግዲህ›› እያሉ መንፈሳዊ መስለው መቆማቸው ነው፡፡ እግዚአብሔር ከዚህ ዓይነቱ አዕምሮ ቢስነትና ድንዛዜ የቅድስት ቤተክርስቲያንን ምዕመን ይጠብቅልን!
ይህን መረጃ ያቀበላችሁኝ የአዳማ ሥላሴ ቤተክርስቲያን መዘምራንን እግዚአብሔር አምላክ ይባርካችሁ! የጨለማውን ሥራ እንዲህ በብርሃን ጸዳል መግለጡ ተገቢ ነውና!
ከውስጥ አዋቂ ምንጭ

Wednesday, August 19, 2015

ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?


1/ እንደመግቢያ፤

   መላእክትና ሰዎች በእግዚአብሔር ግብር የተፈጠሩ ፍጡራን ናቸው።  በኦሪት ዘፍጥረት የመጀመሪያዎች ሁለት ምዕራፎች እንደተመለከተው በላይ በሰማይ፤ ከታች በምድርና በጥልቅ ውሃማ አካሎች ሁሉ እግዚአብሔር በለይኩን ቃሉ (ከአዳም በስተቀር) የፈጠራቸውን ሥነ ፍጥረቶች እናገኛለን። በመሠረተ እምነት ደረጃ ፍጡር ስንል ፈጣሪ ወይም አስገኚ ያለው ነገር ማለታችን ነው። መፍጠር ወይም የሌለውን ነገር ማስገኘት ማለት አንድን ነገር መሥራት ወይም መፈብረክ ማለት አይደለም። የነገረ መለኮት ምሁራን መፍጠርን ወይም ማስገኘትን ሲገልጹ «from nothing to something» በማለት ይገልጹታል። «ከምንምነት ወደአንድ ነገርነት» ማምጣት ማለት ነው።  እግዚአብሔር ለመፍጠር መነሻ ሃሳብ ወይም ጥሬ ነገር /substance/ አያስፈልገውም።  

   ፍጡራን ግን ይህንን ማድረግ አይቻላቸውም። ለምሳሌ ወንበር የሠራ ሰው ፈበረከ ወይም ሠራ ቢባል እንጂ «ፈጠረ ወይም አስገኘ» ሊባል የተገባው አይደለም ይላሉ ምሁራኑ። ምክንያቱም «ወንበር» የተባለውን ቁስ ለመሥራት  አንዳንድ ነገሮች «something» የግድ ያስፈልጉታልና ነው። ይህም የሥራ ጉዞ «from something to something» በቅርጽ፤ በመጠንና በይዘት ይለውጠዋል እንጂ /from nothing to something/ ከምንም ነገር ሳይነሳ «ወንበር» የተባለውን ቁስ ማቅረብ አለመቻሉ የጉድለቱ አንድ አስረጂ እንደሆነ በአመክንዮ ያቀርባሉ።  ያንንም ወንበር እንኳን ለመሥራት ወይም ለመፈብረክ የግድ የሚያስፈልጉት ጥሬ ሀብቶች /raw materials/ የሠራተኛው የራሱ ግኝቶች አይደሉም። 

   ስለሆነም ፍጡራን በሙሉ ያላቸው ሁኔታ፤ ችሎታና ብቃት ያልተወሰነ፤ በአፈጣጠር ያልተገደበ አይደለም። በሥራቸው ሁሉ ምሉዕነት ያለው፤ ጉድለት አልቦነትም የማይጎበኘው አይደለም። መላእክትና ሰዎች መነሻም፤ መድረሻም አላቸው። መነሻና መድረሻ ያለው ፍጥረት ደግሞ በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት በሁሉ ሥፍራ መገኘት አይችልም። በሥራው ሁሉ በብቃትና በራሱ ኃይል የማከናውን ፍጹምነት የለውም።

 የእግዚአብሔር ባህርይ ግን ከዚህ የተለየ ነው። እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪና አስገኚ ስለሆነ መነሻም መድረሻም የለውም። ኋለኛ የሌለው ፊተኛ፤ ፊተኛም የሌለው ኋለኛ እሱ ብቻ በመሆኑ አልፋና ኦሜጋ እንለዋለን።
መጽሐፍ ቅዱስ « በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ» ዘፍ 1፤1 ሲል እግዚአብሔር ከምንም ነገር «from nothing to something»  ለመፍጠር ወይም ለማስገኘት ምንም ተጨማሪ ነገር እንዳላስፈለገውና እሱ ብቻ እንደተቻለው እንረዳለን። ሰማይና ምድርን ግን የፍጥረት መነሻ ሆነው ተከስተዋል። ሁለቱም በሥፍራ፤ በቦታና በሁኔታ ተወስነዋል። ምድር በውስጧ የተገኙት ፍጥረታትም ሁሉ መነሻና መድረሻ፤ መጠነ ውሱንነትና መጠነ አኽሎኝነት ይዘው መገኘታቸውን በእያንዳንዱ የሥነ ፍጥረታት ጠባይዓት ላይ እንመለከታለን። ከፍጥረታት አንዱ ክፍል የሆነው የሰው ልጅን ብንመለከት በፍጥረተ ጠባዩ  የአስተሳሰብ፤ የአፈጣጠርና የማንነት ብቃት በተሰጠው እሱነቱ ልክ ተወስኖ ይገኝበታል።

  እርግጥ ነው፤ ስለሃይማኖት ጥሩ ግንዛቤ ያለው ሰው ያለብዙ ምክንያታዊ ውጣ ውረድ «ፍጡራን በአንድ ጊዜ በሁሉ ሥፍራ መገኘት አይችሉም!» ብሎ መልስ ሊሰጥ ይችላል። ደግሞም የሚሠመርበት እውነት፤ በሁሉ ሥፍራ፤ በአንድ ጊዜ፤ በስፍሐትና በምልዐት  (በምሉዕ ኵለሄነት) የመገኘት ብቃት ከእግዚአብሔር በስተቀር ለፍጡር አይቻለውም የሚለውን እውነት አምኖ መቀበል ነው። ሁሉን ቻይነት/Omnipotence/ ከእግዚአብሔር በቀር ለማን ይቻለዋል? ለማንም!!

«ከማኅፀን የሠራህ፥ የሚቤዥህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ሁሉን የፈጠርሁ፥ ሰማያትን ለብቻዬ የዘረጋሁ ምድርንም ያጸናሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ ከእኔ ጋር ማን ነበረ?» ኢሳ 44፤24

በላይ በሰማይ፤ በታች በምድር በሁሉም ሥፍራ ያለና የሚኖር፤ የሚሰማም፤ መልስ የሚሰጥም እግዚአብሔር ብቻ ነው።
ቅዱሳን መላእክት ይሁኑ ቅዱሳን ሰዎች በሰማይ ሥፍራቸው ሳሉ በምድር የሚደረገውን ሁሉ ያውቃሉ? ያያሉ? ይሰማሉ? በፍጹም አያውቁም፤ አያዩም፤ አይሰሙም።  በሰማይ ሳሉ በምድር ያለውንም የሚያውቁ ከሆነ በስፍሐትና በምልዓት ይገኛሉ ማለት ነው። ይህ ደግሞ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ያለ ስህተት ነው። ከላይ ለመግለጥ እንደተሞከረው በአንድ ጊዜ በሁሉም ስፍራ የመገኘትን ብቃት የፈጣሪ እንጂ የፍጡራን እንዳልሆነ የገለጽነውን እውነታ የሚጻረር ይሆናል።  

2/ «እግዚአብሔር ብቻውን በሁሉ ሥፍራ አለ» የምንለው ለምንድነው?

መልሱ አጭር ነው። እግዚአብሔር በላይ በሰማይ፤ በታች በምድርም፤ በሁሉ ሥፍራ መገኘት የሚችለው በላይ በሰማይ ይሁን በታች በምድር ላለው ነገር ሁሉ ፈጣሪና አስገኚ ስለሆነ ነው።
 ከባዶነት ወደአንድ ነገርነት ማምጣት የቻለ ፈጣሪ፤ በፈጠረው ነገር ሊገደብ፤ ሊወሰን፤ ሊከለከል አይችልም። ፍጥረታት ግን በዚህ ብቃት ውስጥ ሊገቡ አይችሉም። ምክንያቱም ፍጥረታት በቦታ፤ በሁኔታና በአፈጣጠር ውሱን ስለሆኑና ከፈጣራቸው እግዚአብሔር ጋር ሊስተካከሉ ስለማይችሉ ነው። የቅዱሳን መላእክትና የቅዱሳን ሰዎች ብቃት እግዚአብሔር በሰጣቸው መጠንና ፈቃድ የተወሰነ ነው።  መላእክቱ ይሁኑ ሰዎች ፍጡር እንጂ ፈጣሪዎች ባለመሆናቸው ፍጥረተ ዓለም ይወስናቸዋል። እግዚአብሔር ግን እንዲህ አይደለም። በትንቢተ ዳንኤል ላይ እንዲህ እንደተመለከተው፤
«በምድርም የሚኖሩ ሁሉ እንደ ምናምን ይቈጠራሉ፤ በሰማይም ሠራዊት በምድርም ላይ በሚኖሩ መካከል እንደ ፈቃዱ ያደርጋል፤ እጁንም የሚከለክላት ወይም ምን ታደርጋለህ? የሚለው የለም» ዳን 4፤35

3/ የቅዱሳን መላእክት ውሱንነትና በስፍሐት አለመገኘት

እያየን በመጣነው ከእግዚአብሔር ስፉሕነትና ከፍጥረታት ውሱንነት የተነሳ መላእክት በምልዐት በሰማይም በምድርም ሊገኙ እንደማይችሉ  እናምናለን። ነገር ግን ከላይ የገለጽነውን ጉዳይ ዳግም ማንሳት ያስፈለገን ዐቢይ ምክንያት ብዙ ሰዎች የመላእክትን ውሱን መሆን፤ በሁሉ ሥፍራ በአንድ ጊዜ አለመገኘት አምነው ሲያበቁ  ከዚህ ተቃራኒ በሆነ አቋም  ቅዱሳን መላእክት በአንድ ጊዜ በሰማይና በምድር የመገኘት ብቃት እንዳላቸው የሚያስተምሩና አምነው የሚያሳምኑ  ሰዎች በመኖራቸው  ነው። 

   ሰው በአንድ ጊዜ አማኝም፤ ከሀዲም መሆን አይችልም። ምክንያቱም  ጣፋጭ ፍሬ የሚሰጥ ዛፍ ፤ በጭራሽ መራራና ጣፋጭ ፍሬ በአንድ ጊዜ ማፍራት እንደማይቻለው ሁሉ በእምነት የቅዱሳን መላእክትንም ሆነ የቅዱሳን ሰዎችን የውሱንነት ተፈጥሮ ካመንን በኋላ በምንም ዓይነት መንገድ ከዚህ በተጻራሪ መቆም ስለማይቻለን ነው።
ብዙ ጊዜ ሰዎች አምኛለሁ ባሉበት እምነት ውስጥ ክህደት መሰል ነገር የለም ብለው የሚከራከሩት ስላመኑት እምነት በቂ እውቀትና ግንዛቤ ስለሌላቸው ነው። ለዚህ ጥሩ አብነት የሚሆነን ነጥብ፤ በአንድ ወቅት ሰዱቃውያን ወደ ጌታችን፤ አምላካችንና መድኃኒታችን  ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርበው ትንሣኤ ሙታንን ለመቃወም «በምድር ሰባት ባል ያገባች ሴት በሰማይ ለማንኛቸው ትሆናለች?» ብለው በጠየቁት ጊዜ የሰጣቸው መልስ  በየትኛውም ዘመንና ጊዜ ለሚነሳ ጥያቄ እንደአስረጂ አቅርበን እዚህ ላይ ብንጠቅሰው ተገቢ ይመስለናል።
«ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ መጻሕፍትንና የእግዚአብሔርን ኃይል አታውቁምና ትስታላችሁ» ማቴ 22፤29 አላቸው።

  እግዚአብሔርን የሙታን ብቻ አምላክ አድርጎ መንሥኤ ኃይሉን መካድ ከባድ ስህተት ነው። መጻሕፍት የሕያዋን አምላክ ብለው ሲመሰክሩ ይህንንም አለማወቅ ስንፍና ነው። ለዚህ ሁሉ ምክንያቱ አንድ ነው።
  ሰዎች «እናምንበታለን» ባሉት ነገር ውስጥ የሚገቡ ስህተቶች ሁሉ ተቀባይነት አግኝተው ሃይማኖታዊ ካባን የሚላበሱት «መጻሕፍቱንና የእግዚአብሔርን ኃይል» በደንብ ካለመረዳታቸው በሚመጣ ጉድለት እንደሆነ ሁሉ፤ በዚህም ዘመን ያሉ ስህተቶችን እንዲሁ እንገነዘባቸዋለን።  ሰዱቃውያን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በእጃቸው ይዘው ሲያበቁ ስለትንሣኤ ሙታን አለመኖር አምነው መቀመጣቸው ላያስገርም ይችላል። ምክንያቱም ሰዎች የእግዚአብሔር ኃይል መገለጫ መንገዶችን ወደሚናገሩ ወደ ቅዱሳት መጻሕፍቱ ይሄዳሉ እንጂ መጻሕፍቱ ወደሰዎቹ ሊመጡ አይችሉም ነው።  በእጃቸው ያለው መጻሕፍትማ  የሚሉት እንደዚህ ነበር።

«ስለ ትንሣኤ ሙታን ግን እኔ የአብርሃም አምላክ፥ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ ነኝ የሚል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እናንተ የተባለውን አላነበባችሁምን? የሕያዋን አምላክ ነው እንጂ የሙታን አይደለም»  እያለ እውነቱን ቢናገርም እያየበቡ ስለማያስተውሉ የትንሣውን ኃይል ክደዋል (ማቴ 22-31-32 ፤  ዘጸ 3፤6 )

ሰዱቃውያኑ ከተቀበሏቸው መጻሕፍት ውስጥ የተጻፈውን አለማወቃቸው የሚያስረዳን ነገር መጻሕፍትን በመያዝ ወይም በማንበብ  እውነት ሁልጊዜ ይገለጣል ማለት አይደለም።  መረዳቱ ካላቸው ሰዎችም ዘንድ ለኛ ያልተገለጠን እውነት ስለሚኖር ሌሎችን በመጠየቅ ወይም የሚሉትን በማስተዋልና እንደእግዚአብሔር ቃል በመመርመር ወዳልደረስንበት እውነት ልንደርስ እንችላለን። እንደዚሁ ሁሉ በዚህ ዘመንም ያሉ ሰዎች የቅዱሳን መላእክትንንና የቅዱሳን ሰዎችን ውሱንነትና በምልዐት ያለመገኘት ተፈጥሮ አምነው ሲያበቁ በተግባር ግን ከዚህ አስተሳሰብ በተቃራኒ ቆመው የመገኘታቸው ነገር በመጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነታ ውስጥ ለመኖር ካለመቻል የመጣ እክል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። 

4/ በሰማይ ሥፍራ ያሉ ቅዱሳን በዓለመ ምልዓትይገኛሉን?

ፍጡራን ውሱንና በሁሉ ሥፍራ የመገኘት ብቃት እንደሌላቸው ከላይ በተደጋጋሚ ለማሳየት በሞከርነው ላይ ካመንን በዓለማት ሁሉ በምልዓት ሊገኙ አይችሉም ብለን ደፍረን መናገር እንችላለን። እንደመላእክቱ ሁሉ ቅዱሳን ሰዎች በተወሰነ ሥፍራ፤ በተወሰነ  መጠንና  በተፈቀደላቸው ዓለም የሚኖሩ እንጂ ምሉዕ በኵለኄ ስላይደሉ እንደፈጣሪ ሁሉን አዋቂነት የላቸውም ብንልም ስህተት አይደለም። ከዚህ በተለየ አስተሳሰብ ላይ ከሆንን ደግሞ ሊሆን የሚችለው ነገር ሁሉን ቻይ በሆነው በእግዚአብሔር ኃይልና ፍጡር በሆነው ፍጥረት መካከል ያለውን ልዩነት አለመረዳት ስለሚሆን እምነቱ በክህደት የተሞላ ይሆናል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የፈጣሪን ኃይል ለፍጡራን ከመስጠት የበለጠ ክህደት የለም። እግዚአብሔርን የሚመስል ምንም ነገር ሊኖር አይችልምና።

«አቤቱ የእስራኤል አምላክ ሆይ፥ በሰማይ ወይም በምድር አንተን የሚመስል አምላክ የለም፤ በፍጹም ልባቸው በፊትህ ለሚሄዱ ባሪያዎችህ ቃል ኪዳንንና ምሕረትን የምትጠብቅ» 2ኛ ዜና 6፤14

መላእክት ቅዱሳን በመሆናቸው ወይም ቅዱሳን ሰዎች አምላካቸው ስላከበራቸው እግዚአብሔርን የሚመስል ባህርይ እንዳላቸው አድርጎ ማሰብ  አስነዋሪ ነገር ነው። ቅዱሳን በዓለመ ሥጋ ሳሉ ወይም በዓለመ መላእክት የሚገኙ መላእክት የሚሠሩት ሥራ በእግዚአብሔር ፈቃድና በተሰጣቸው ጸጋ ይወሰናል። በዚህ ምድር የሚኖሩ ቅዱሳን ሙት ቢያስነሱ፤ ደዌ ቢፈውሱ ከተሰጣቸው ጸጋ አኳያ እንጂ በተፈጥሮ ካላቸው ብቃት የተነሳ አይደለም።  በዚያም ጸጋ ቢሆን የሚመሰገነውና ሊመሰገን የተገባው የጸጋው ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ ነው። ቅዱሳኑን ማክበር አንድ ነገር ነው፤ ነገር ግን በማክበር ሽፋን ወይም እግዚአብሔር በነሱ በኩል በሠራው አስደናቂ ነገር የተነሳ ለእነሱ ምሥጋናና ውዳሴ እንድንሰጥ የሚያደርገን አንዳችም መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ የለም። ጸጋ ማለት እግዚአብሔር በወደደው መንገድ የራሱን ሥራ የሚሠራበት ኃይል እንጂ ሠራተኞቹ ይመሰገኑበት ዘንድ የተሰጠ የውዳሴያቸው መሣሪያ አይደለም።

«አሁንም ጸጋን ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔርን ለምኑ፤ ይህ ከእጃችሁ የተሰጠ ሲሆን ከቶ ፊታችሁን ይቀበላልን? ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር» ሚል 1፤9

ጸጋ የሚሰጥ፤ የሚከለከል ኃይል ነው። ጸጋ ሰጪው በፈቀደው መጠን ለፈቀደው ጉዳይ የሚሰራበት መንገድ እንጂ ወሰን የሌለውና ሁሉን ለማድረግ ክበበ ተፈጥሮን አልፎ የሚሄድ ምሉዕ ኃይል ያለው ማለት አይደለም።

«እንደ ተሰጠንም ጸጋ ልዩ ልዩ ስጦታ አለን» ሮሜ 12፤6


«ሐዋርያትም የጌታን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በታላቅ ኃይል ይመሰክሩ ነበር፤ በሁሉም ላይ ታላቅ ጸጋ ነበረባቸው» የሐዋ 4፤33

በአንድ ወቅት ሐዋርያው ጳውሎስ ልስጥራን በሚባል ሀገር በገባ ጊዜ በልስጥራን የተባለ ከልጅነቱ ጀምሮ እግሩ ሽባ የሆነና የሰለለ ሰው አግኝቶ በኢየሱስ ስም ከፈወሰው በኋላ  አማልክት ከሰማይ ወርደዋል ብለው ሲያበቁ ሕዝቡና የድያ ካህን ኮርማ ሊሰዋላቸው ፈለገ። ጳውሎስና በርናባስ ግን ልብሳቸውን ቀደው እንዲህ አሉ።

«እንዲህም አሉ። እናንተ ሰዎች፥ ይህን ስለ ምን ታደርጋላችሁ? እኛ ደግሞ እንደ እናንተ የምንሰማ ሰዎች ነን፥ ከዚህም ከንቱ ነገር ሰማይንና ምድርን ባሕርንም በእነርሱም ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር ትሉ ዘንድ ወንጌልን እንሰብካለን» የሐዋ 14፤14-15

የቅዱሳን መላእክትም ይሁን የቅዱሳን ሰዎች ዋና የእምነታቸው ማእከል ራሳቸውን በምሥጋናውና በተሠራው ቦታ ማስቀመጥ ሳይሆን እግዚአብሔር በእነሱ በኩል እንዲከብር ማድረግ ነው።  ከጳውሎስ ተአምራት የተማርነው ነገር ተአምራቱን የሠራው ጳውሎስ ሳይሆን መክበር ያለበት የተአምራቱ ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ እንዲከብር ሰዎች ሁሉ ዓይናቸውን በእግዚአብሔር ላይ እንዲጥሉ በኃይለ ቃል ሲናገራቸው የምናነበውም ለዚህ ነው።

5/ በሰማያት ሥፍራ ያሉ ቅዱሳኑ መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች የሰዎችን ልመናና ጸሎት ሰምተው ምላሽ ሊሰጡ ይችላሉን?

የቅዱሳኑን ውሱንነትና በምልዓት ያለመገኘት ብቃት መመልከት ያስፈለገን ከዚህ በታች ለምናቀርባቸው ጭብጦች ገላጭ አስረጂ እንዲሆኑን ከመፈለግ የተነሳ ነው። ውሱንነትና በምልዓት አለመገኘት ማለት ከታች ለሚነሱት ነጥቦች መልስ ይሰጡናል።
እዚህ ላይ ሁለት የተለያዩ ነጥቦችን ልናነሳ እንገደዳለን። አንደኛው ቅዱሳን መላእክት በሰማያት ባለ የምሥጋና ዓለም እያሉ በምድር የሚደረገውን ነገር ሁሉ ያውቃሉ ወይ? የሚለውንና በገነት ያሉ ቅዱሳን በምድር የሚደረገውን ሁሉ ማየት ወይም መስማት ይችላሉ ወይ? የሚለውን ነጥብ ለይቶ መመልከት ተገቢ ነው።
 ከቅዱሳን መላእክትና ከቅዱሳን ሰዎች ተፈጥሮ የተነሳ በምልዐት ያለመገኘትን ጉድለት የተነሳ በገነት ወይም በዓለመ መላእክት ያሉ ቅዱሳን በዚህ ክበበ ዓለም ያለውን ነገር ሁሉ በአንዴ ሰምተው፤ በአንዴ አውቀው፤ ምላሽ ሊሰጡ አይችሉም። በወሰነ ነፍሳዊ አካል በገነት ሳሉ በዚህ ምድርም የመገኘት ብቃት የሌላቸው ከመሆኑም ባሻገር በተፈጥሮአቸውም  በገነት ሳሉ  በምድር ያሉ ሰዎችን ጸሎት በብቃት በመስማት ምላሽ ለመስጠት  ስላይደለ የሁሉን አዋቂነትና ሰሚነት ችሎታ የላቸውምና በምድር ላይ ሆነን በገነት ይሰሙናል ልንል የተገባ አይደለም። ይህን የማድረግ ባህርይ የእግዚአብሔር የብቻው ነው። 

   በዚህች ባለንባት ምድር በየትኛውም ማእዘነ ዓለም በስማቸው የሚደረገን ልመና በገነት ሳሉ ይሰማሉ ማለት ፈጣሪ ናቸው ብሎ በክህደት አዘቅት ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱሳን መላእክትን እግዚአብሔር ለፈለገው ዓላማ ሲልካቸው ወይም እንዲገኙ በተሰወነላቸው ሥፍራ ከመገኘት በስተቀር በፈቃዳቸው ወይም ሰዎች ስለጠሯቸው እንደፍላጎታቸው ሊሄዱ አይችሉም፤ ያልተወሰነ የመስማት ብቃትም የላቸውም።  በኢጣሊቄ ይኖር ለነበረ ጭፍራ፤ የመቶ አለቃ የሆነው ቆርኔሌዎስ ጸሎቱና ምጽዋቱ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተወደደ ስሙ ያልተገለጸ የእግዚአብሔር መልአክ በተልእኰ መጥቶ መልእክት ማድረሱንና ማድረግ ስለሚገባው ነገር ሲናገረው እናነባለን።

እዚህ ላይ ሊሠመርበት የሚገባቸው ነጥቦች ሦስት ናቸው።

ሀ/ የመልአኩ ድርሻ  ማንነቱን ማስተዋወቅ ወይም የራሱን ሃሳብ መግለጽ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላለፈውን መልእክት ማስረዳት ብቻ ነው። ከነበረበት ሰማያዊ ሥፍራም በተልእኰ ወደቆርኔሌዎስ ሲሄድ የነበረበትን ዓለመ መላእክት ለቆ ይወርዳል እንጂ በስፍሐት በነበረበት ቦታም በተመሳሳይ ሁኔታ ሊገኝ አይችልም። መውጣትና መውረድ ያስፈለገውም ለዚህ ነው።
ለ/ መልአኩ ከቆርኔሌዎስ ቤት የተገኘው መልአኩ በስሙ ስለተደረገው ጸሎትና ምጽዋት ምላሽ ሊከፍለው መምጣቱን ለመንገር ሳይሆን ቆርኔሌዎስ በአምላኩ ስም ያደረገው ነገር በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ማግኘቱን  በመግለጽ የእግዚአብሔር መልእክት ለማድረስ ብቻ ነው።
ሐ/ በዚህ ሥፍራ ስሙ ያልተገለጸውን የመልአክ ስም በምትሃት ጠቅሰን በመናገር መልእክት አድራሽነቱን እንደባለቤት ቆጥረን እንድናመሰግነው የሚያደርገን አንዳች ነገር የለም።

 ይሁን እንጂ በዘጸአተ እስራኤል ታሪክ ላይ ያልተገለጸው መልአክ፤ ሚካኤል እንደመራቸው ተደርጎ የተጠራውና በትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ውስጥ እንደተመለከተውም፤ ሠለስቱ ደቂቅን ከእቶን እሳት ያዳናቸው፤  እግዚአብሔር ባወቀ ያልገለጸውን የመልአክ ስም በመስጠት ሚካኤልና ገብርኤል ናቸው እያሉ የስህተት ትምህርቶች ምሥጋናውን ሁሉ  ከእግዚአብሔር ላይ ለመውሰድ የተደረገ ትግል ከመሆን አያልፍም። በእግዚአብሔር ሥፍራ ላልተገለጹ መላእክት ክብርና ምስጋናን በመስጠት እግዚአብሔርን ማስቀናት የጠላት ሴራ ውጤት ነው። በእርግጥም ይህንን የሚያደርገው ሰይጣን ነው።  ምክንያቱም በቅዱሳን መላእክት ስም ተሸሽጎ ሰዎችን ከእግዚአብሔር ፈቃድ ለማስወጣት የብርሃን መልአክ ነኝ ቢል ማስመሰል የቆየ ተግባሩ ነው።  በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ  ሳይገልጽ በዝምታ ያለፈውን ነገር እንዳለ ለሱ በመስጠት በዝምታ እንደመተው የመሰለ ማለፊያ እውቀት የለም።

   እንደዚሁ ሁሉ ወደቆርኔሌዎስ የተላከውን መልአከ ማንነት እግዚአብሔር ብቻ ባወቀው ሁኔታ ስላልተገለጸ ከዝምታ ባለፈ ወደስም ገላጭነት የሚያሸጋግረን ምክንያት የለም። «እንደአናንያ፤ እንደአዛርያ፤ እንደሚሳኤል፤ አድነን ገብርኤል» እንድንል የሚያደርገን ከመጽሐፉ ባለቤትም የተሻለ እውነት እኛ ዘንድ የለም።
ስለሆነም ቅዱሳን መላእክቱ ሰዎች ወደእግዚአብሔር በሚያቀርቡት ልመናና ጸሎት ወይም እግዚአብሔር እንዲራዱ፤ እንዲታደጉ ሲልካቸው በትእዛዝ ብቻ ተልእኰአቸውን ለመፈጸም ከሚመጡ በስተቀር ሰዎች ስማቸውን ስለጠሩ፤ በስማቸውም ስለተማጸኑ፤ ለዚያ የሚሆን ዋጋ ለመስጠት ደስ ተሰኝተው፤ ላደረጉትም ትድግና ምስጋና ለመቀበል ሽተው በጭራሽ አይመጡም። ምክንያታችንም ከላይ ስንገልጽ እንደመጣነው መላእክቱም ይሁኑ ቅዱሳኑ በሰማይ ሳሉ በምድር ላይ በስማቸው የተደረገውን የሰዎችን ሁሉ ልመና መስማት፤ መቀበልና ምላሽ የመስጠት ብቃት ስለሌላቸው ነው። በምልዓት ተገኝቶ የመስማትና ጸሎት የመቀበል ችሎታ የእግዚአብሔር ብቻ ስለሆነ!!

ክፍል ሁለት ይቀጥላል ….

Saturday, August 1, 2015

ኤሎሄ ኢየሱስ!

እንደምነህ ጌታ፤ ቸሩ ፈጣሪያችን፤
እኛማ አለነው፤ ከተባለ ኖርን።  
አልደላን፤ አልሞቀን በርዶን፤ አልተመቸን፤  
መግባትና መውጣት፤
ማልቀስና ማዘን ድሩን አድርቶብን፤                                                                                                                        
አንዱ ሲወጣብን፤ አንዱ ሲሄድብን።                                                                                                     
እነሆ አለነው፤ የሰው መንገድ ሆነን።

በናፍቆት ስንጠብቅ፤ ኑረትን የኖርነው
ሌሎች የገቡባት ሰማይ ቤት እንዴት ነው?
እመጣለሁ ብለህ ቆየህሳ  ምነው ?
እኛማ .....እኛማ
ለሹመኛ አለቃ፤ ማመልከቻ ፅፈን
ለወፈ ሰማይ ሕዝብ፣ መድረክ ላይ ለፍፈን
ጸሎት ቤታችንን፤ እኛው ላይ ቆልፈን
የምድር አተካራ፤ ህግጋቱን አልፈን                                                                                                                                    
ቢጨንቀን፤ቢጠበን
ሁለት ሽህ ዘመን፤ እነሆ አለፈን     
ስጋችንን ለብሰህ፤ ካየነው ዐይንህን።

የመምጣትህ ተስፋ ርቆ እየዳመነ                                                                                                       
እምነት ተስፋ ፍቅር እየመነመነ
ቢዘገይ ሰዓቱ ...እምነትን ዘንግተን                                                                                                                           
የልባችን ምኞት፤ ቢያይል መሻታችን                                                                                                       
የሰጠኸውን ትተን ያላልከውን ሆንን                                                                                                         
ችላ ብለን አደርን፤ ረሳንህ ጌታችን
ጠብቀን ጠብቀን ሁለት ሽህ ዘመን።

ሲሰግዱ ሰግዳለሁ፤ ሳይታጎል ጾሜ                                                                                                      
ሲበሉም በላለሁ፤ ልማዴን ደግሜ                                                                                                                                              
እልልታም፤ ዝማሬም ሲነቅፉም ቀድሜ                                                                                                                         
ምሰሶ ዐይኔ ውስጥ እኔም ተሸክሜ፤                                                                                                      
እነሆ አለሁኝ በዘልዛላ እድሜ።
የንስሐ ዘመን ቢኖረኝ ጥቂት                                                                                                                     
የቀረህ መሰለኝ ያንተ መዘግየት
ጥቂት ልጠይቅህ አቤቱ ጌታ ሆይ                                                                                                                              
ከነቅዱሳንህ አንተ ደህና ነህ ወይ?
ከምር እንደሚያሙት ምጽአት ቀረ እንዴ ?
በቶማስ ልቡና ጠረጠርኩ አንዳንዴ !                                                                                                                                  
ታውቀዋለህና ያለውን በሆዴ።
መጠርጠሬስ በእውነት ከእምነቴ ነው እንጅ፤                                                                                                 
አይደለም ከክዳት ለመውጣት ከደጅ፤                                                                                                       
ዘመኑን ከፋና እድሜን የሚፈጅ፤                                                                                                         
ኃጢአት ነገሰ፤ ለጠላትም ወዳጅ                                                                                                                    
ባየኸው ትውልዱን ሆኖልህ የማይበጅ።                                                                                                             
አንተ የሰጠኸው ረዳቱ ቀረና                                                                                                                
ራሱን አወቀ አሉ፤ ወንዱንመረጠና፤                                                                                                                                                                                                                       
ይሄ ሁሉ ሆነ ረዝሞ መዘግየትህ                                                                                                                
ኧረ መቼ ይሆን የመምጫ ዘመንህ?
የሆነስ ሆነና ሰማይ ቤት እንዴት ነው
አብረሃም ሰላም ነው ...
እዛስ ቤት ገነባ? ወይስ በድንኳን ነው ?
እኛማ ይሄውልህ ...
በቤት ኪራይ ችንካር እየተሰቀልን
‹‹ኤሎሄ›› እንላለን ጎጆ እንድጥልልን ....
ወደላይ ገነባን ወደጎን አሰፋን
ወደላይም ከላይ ወደጎንም ከጎን
እንደጉድ ተገፋን
ቤት ለእንግዳ ማለት ጭራሹኑ ጠፋን !!
አባታችን ሙሴ እንዴት ነው ለክብሩ
ውቅያኖስ መክፈያው ደህና ናት ብትሩ ?
እኛማ ይሄውልህ ....
እንጀራ ፍለጋ ባህር ስናቋርጥ
የተስፋዋን ምድር ቀን ሞልቶ ሳንረግጥ
የትም ውሃ በላን የትም አሳ ላሰን
ን ገ ር ል ን ና ብትሩን ያውሰን ....
በትር ያለው መሪ መቼም አላገኘን፤                                                                                                              
ዘመን የሚያሻግር እባክህ ላክልን።
እናልህ ጌታ ሆይ ....
ከተስፋዋ ምድር ወደሌላ ተስፋ አለን እየኳተን
መሄጃው ሲገርመን
መመለሻ መንገድ መቆሚያ ቦታ አጥተን ...!
ላባታችን ሙሴ እንደምትልልን ...
የመሄድ ዘመን ነው
ባህር የሚያሻግር
በትርህን ላክልን ...

ሰማይ ቤት እንዴት ነው ? ...                                                                                                                                                         
ዳዊትስ ደህና ነው ?
ዛሬም ይዘምራል ..መሰንቆበገና?                                                                                                                                            
ሃሌ፤ ሃሌ ሉያ የሰማይ ምስጋና፤                                                                                                         
ጎልያድስ የት ነው? በዚያ በቁመና።
እኛማ እኛማ
እልፍ አላፍ ጎልያድ ከቦን ሲደነፋ
ወንጭፉን ጠቅልሎ ምነው ዳዊት ጠፋ?
ብሎሃል በልልን
 ጌታ ሆይ ከሰማህ                                                                                                                                         
ከዘመን ጎልያድ ታደገን እባክህ                                                                                           
ሙተናል፤ ቆስለናል፤                                                                                                                            
ወንጭፍ እምነታችን ተጠቅልሎ ወድቋል።
ለረከሰ ጠጠር ለሞላ ወርዋሪ
‹‹ወንጭፍህን ስጠው ለዚህ ታሪክ አውሪ››

እንዴት ነህ ጌታ ሆይ ... ሰማይ ቤት እንዴት ነው ?
የሙሴ አልጋ  ወራሽ  ኢያሱ ሰላም ነው ....?
ያቆማትን ፀሐይ ግቢ ቢላት ምነው ...?
ያው እንደምታውቀው
ዐሥራ ሦስት ወር ፀሐይ                                                                                                                     
ወርኀ ክረምት ሸሸ፤ እየበዛ ሀጋይ                                                                                                            
ራሳችን ፈረሰ፤ምድሪቱ ደረቀች፤                                                                                                               
ወንዙ መነመነ፤ ባዶ እርቃን ቀረች።                                                                                                         
እባክህን ጌታ ሆይ ወይ ቶሎ ናልን፤                                                                                                   
ምትቆይ ከሆነም ኤልያስ ይምጣልን                                                                                                             
በጻድቅ ጸሎቱ ዝናም ያውርድልን፤                                                                                                           
በጎ ሰው ከጠፋ ዘመናት አለፈን።

ወራቱ በሙሉ ፀሐይ እያዘለ
የተሾመው ሁሉ ‹ፀሐይ ነኝ› እያለ
የሰው ጀምበር በዝቶ
ባቃጠላት ምድጃ አገር
ምን ታምር ይኖራል .... በዚህኛው ዘመን፤                                                                                                            
ታሪክ አውሪ ትውልድ፤ ኤልያስ የለውም፤                                                                                                              
ሹመቱ ምድራዊ፤መንፈሱም ሥጋውም።

ኧረ ጌታ ናልን  በናትህ ....በውድህ
በጭንቅ አላማጇ፤ ለአቅሌሲያ ብለህ
ወይ ዝናብ ላክልን ወይ ዝናብ ሁነህ ና
ማጣፊያው አጠረን፤ ሙቀት ገደለና !

ሔዋንስ ደህና ናት ?
ያው የልጅ ልጆቿ
በእግሯ ተተክተን፤
የፍሬው ሲገርምህ
ግንዱንም አንክተን፤
ፍጥረተአዳም                                                                                                                                                               
ገምጠነዋል ሥሩን።
                                                                                                                                             
የባሰ ሳይመጣ ቶሎ ድረስልን፤                                                                                                                        
አንድም ሰው አታገኝ የቆየህ እንደሆን                                                                                                        
ማራናታ እያልን ይኼው እንጮሃለን
አውራ እንደሌለው መንጋ ተበትነን
ቀበሮ ጨረሰን፤ ፈጀን፤ አቃጠለን                                                                                                                  
ኤሎሄ ኢየሱስ ቶሎ ድረስልን።

(ከጌታቸው ይመር ግጥሞች ለንባብ እንዲመች ተደርጎ በመካነ ጦማሩ የተስተካከለ)