Friday, June 20, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነጽሁፍ ዘላለም መንግሥቱ)

ካለፈው የቀጠለ (ክፍል ሁለት)

4.  ይህ  ደራሲ  ማርያምን  መለኮታዊ  ክብርን  ለማቀዳጀት  የጣረ  ወይም እንዲያደርግ  ያነሣሱት  ሰው  ነው።

 ምናልባት  መጽሐፉ  ስለራሱ እንደሚናገረው  ከግብጽ  ተገኝቶና  በዐረብኛ  ተጽፎ  ከሆነ  ክርስቲያኖች ማርያምን  እንደ  አምላክ  ያዩአታል  የሚያሰኝ  ዐረባዊ  ጫና  ሊኖርበትም ይችላል። ለምሣሌ፥ በኢስላም ግምት ክርስቲያኖች አብ፥ ወልድ፥ መንፈስ ቅዱስ  አንድ  አምላክን  ሳይሆን  ማርያምንና  ኢየሱስን  ከአላህ  ጋር  እኩል አድርገው  እንደሚያመልኩ  ይነገራል፥  ተጽፎአልም።  “የመርየም  ልጅ  ዒሳ ሆይ  አንተ  ለሰዎቹ፥  እኔንና  እናቴን  ከአላህ  ሌላ  ሁለት  አምላኮች አድርጋችሁ  ያዙ  ብለሃልን?  በሚለው  ጊዜ  (አስታውስ) . . .”( ቁርአን አልማኢዳህ ቁጥር 116)

   በተአምረ ማርያም  ደግሞ  ማርያም  ያላት  ሥልጣንና  የምታደርጋቸው  ትንግርቶች መለኮት  ብቻ  እንጂ  ማንም  ፍጡር  ሊያደርጋቸው  የማይችላቸው  ነገሮች ናቸውና እውነትም  ከመለኮት  ያልተናነሰ  ኃይልና  ችሎታ፥  ሞገስና  ክብር፥ሥልጣንና ስግደት ተጎናጽፋ ትገኛለች። እርግጥ  ነው  ጌታን  ያመኑና  የሚከተሉ  ተአምራትን  እንደሚያደርጉ ተጽፎአልና  በክርስትና  ታሪክ  ተአምራት  አዲስ  መሆን  የለባቸውም። የማርያም  ግን  የተለየ  ነው።  የሞተን  ማስነሣት  አንድ  ነገር  ነው፤  ግን፥ ለምሳሌ፥  በምዕራፍ  18  እና  19  ውስጥ  እንደሚነበበው  በደብረ  ምጥማቅ ተገልጣ  በዚያ  የነበሩ  ዘመዶቻቸውን  ብቻ  ሳይሆን  ጥንት  የሞቱትን ሙታን፥ አዳምና ሔዋንም ሳይቀሩ እያስነሱ አምጥቶ ለተመልካች ማሳየት መለኮትን  መጋራት  አይባልም?  ምክንያቱም  ትንሣኤ  የሰው  ሳይሆን የእግዚአብሔር  ብቻ  ሥራ  ነው።  ማርያም  ይህንና  ሌሎችንም  ሁሉ የምታደርገው  ደግሞ  እንደ  ጌታ  ደቀ  መዝሙር  በሕይወት  ሳለች  ሳይሆንከሞት  በኋላ  እየተገለጠችና  በአካል  እየመጣች  ነው።

  በዚህ  በተጠቀሰው ክፍል  እንደታየው  ያለ  ከሞተ  በኋላ  ከሞት  እየተነሣ፥  እየታየ፥  እየዳሰሰ፥ እያቀፈ፥  እየሳመ  ገባሬ  ተአምራት  ሆኖ  ከሰው  ጋር  የተባበረ  ኖሮ አያውቅም።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  የተጻፈ፥  በትንሣኤ  አካል  ከሞት የተነሣ  ጌታ  ክርስቶስ  ብቻ  ነው።  ከእርገቱ  በኋላ  እርሱ  ራሱም የተገለጠው  ለሁለት  ሰዎች  ብቻ  ነው፤  ለጳውሎስና  ለዮሐንስ።  ሁለቱም ባዩት  ጊዜ  ምን  እንደሆኑ  ተጽፎልናል፤  ሐዋ.  9  እና  ራእ.  1።  በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ትንሣኤ ሙታን እንደ ቁርስና ምሳ ተራ ጉዳይ ነው። በተአምረ  ማርያም  ጌታ  ኢየሱስ  በተጠቀሰባቸው  ቦታዎች  በ97  ወይም 98%  ያህሉ  ልጇና  ወዳጇ  ነው።  ፈጣሪዋ፥  አምላኳ፥  ጌታዋ  ከመሆኑ ይልቅ  ማለት  ነው።  ይህ  ፈጽሞ  አልተጠቀሰም  ማለት  ሳይሆን የተጠቀሰው  1  ወይ  2%  ብቻ  ነው።  በመጽሐፉ  የቀረቡት፥  ልክ  እንደ ስዕሉ  ሁሉ፥  የተሳሉት  እንደ  እናትና  ሕጻን ልጅ  ነው።  እናትና  ሕጻን ልጅ ብቻ  ሲታዩ  ክብደትና  ክብር  የተገባት  እናት  እንደምትሆን  ሆኖ  ነው አቀራረቡ።  ወደ  መጽሐፉ  መደምደሚያ  አንድ  ጊዜ  የ5  ዓመት፥  አንዴ የ8፥  አንዴ  የ12  ዓመት  የተጠቀሰ  ሲሆን  መጽሐፉ  ሲደመደም በመጨረሻው  ምዕራፍ  ኢየሱስ  የ18  ዓመት  ልጅ  ሆኖ  ገና  አሁንም የተጠየቀውን  አድራጊ  ሆኖ  ማርያም  የግሪክን  አገር  መጎብኘት  መፈለጓን ነግራው  እዚያ  ወስዷት  ታሪኩ  እዚያ  ይፈጸማል።  ከነዚህ  የመጨረሻ  4  ምዕራፎች  በቀር  በመጽሐፉ  ውስጥ  ኢየሱስ  በእናቱ  እቅፍ  ያለ  ሕጻን ነው። ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ እንኳ ሲታይ እንደ ሕጻን ሆኖ ነው።

5.  ይህ  ደራሲ  ወይም  ይህን  የመጽሐፉን  ይዘት  የተቀበሉትና  ያስጻፉት ሰዎች  በሰይጣን  የተታለሉ  ሰዎች  ናቸው።

 ይህ  ሁሉ  በመጽሐፉ  ውስጥ የተጠቀሱት  ነገሮች  ታይተዋል፤  ማርያምም  ተገልጣ  ተናግራቸዋለች፤ የተጻፈውም  ነገር  በትክክል  የታያቸውና  የተገለጠላቸው  ነው  ተብሎ ቢወሰድ  እንኳ  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ትምህርት  አንጻር  ሰዎችን  እውነትና መንገድ  ሕይወትም  ከሆነው  ከክርስቶስ  የሚያርቅ  ነገር  ስላስተላለፉ በማርያም  እየተመሰለ  የተገለጠ  ሰይጣን  ያሳታቸው  ሰዎች  ናቸው  ብሎ መደምደም  ይቻላል።  በ2ቆሮ. 11፥14  ሰይጣን  ራሱን  የብርሃንን  መልአክ እንዲመስል  እንደሚለውጥ  ተጽፎአል።  ይህች  ተገለጠች  የተባለችው  ማርያም ሐዋርያት የሰበኩትን  እውነተኛ ወንጌል እንኳ ብትሰብክ ይህንም መቀበል ግዴታ  አይሆንም፤ ምክንያቱም እውነተኛው  ወንጌል  ቀድሞውኑ ተሰብኮ፥  ተጽፎ  ተላልፎአላ!  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  የሚተላለፈው ትምህርት  ደግሞ  ከእውነት  ፈቀቅ  የሚያደርግ  ነው።  ይህን  በተመለከተ ጳውሎስ  በገላ.  1፥8  ነገር  ግን  እኛ  ብንሆን  ወይም  ከሰማይ  መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ  ወንጌል  የሚለይ  ወንጌልን  ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ  ይሁን አለ።  አዲስና  ወንጌል  የሚመስል  ግን  ያልሆነ  ነገር  የሚሰብክና  ታይቶ የሚገልጥ የዚህ ውግዘት ተሸካሚ ነው።

6. የተአምረ ማርያም ደራሲ  ደኅንነትን  የማያውቅ ሰው  ነው።

 በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ፥  በተለይም  በአዲስ  ኪዳን  በግልጽ  ተጽፎልን  የምናየው ደህንነት  ወይም  ድነት  ውብ  ነው!  የእግዚአብሔር  ድንቅ  የሆነው አሠራሩ፥  ኃጢአተኛውን  ሊያጸድቅ  አንድያ  ልጁን  መላኩ፥  ጌታችን መድኃኒታችን  ኢየሱስ  ክርስቶስም  በፈንታችን  በመስቀል  መሞቱና  እኛን ከዘላለም  ሞትና  ከኃጢአት  ባርነት  ነፃ  ማውጣቱ፥  ይህ  ድንቅና  ክቡር የሆነ  ግን  ግልጥና  ቀላል  ሆኖ  የቀረበው  ሥራው  አስገራሚ  ነው።  አቤት ደኅንነት  ውበቱ!  አቤት  ደኅንነት  ግልጽነቱና  ቀላልነቱ!  አቤት  ውስብስብ ያለመሆኑ!  አቤት  እርግጠኝነቱ!  ደህንነት  የሂደት ሳይሆን  የቅጽበት ለውጥ ነው።  ደኅንነት  ይታወቃል፤ አንድ  ኃጢአተኛ  ሲድን  መዳኑን  ያውቀዋል። እንዲያውቅ የሚያደርጉት ዋና ዋና ምስክሮች አሉ። 1ኛው የማይዋሽ ቃሉ ነው፤  በዳንንባት  ቅጽበት  የእግዚአብሔር  ልጆች  ሆነናል፤  ዮሐ. 1፥11-12፤
ልጁ  ያለው  ሕይወት  አለው፤  ይህ  ደግሞ  የሚታወቅ  ነው፤  1ዮሐ. 5፥12-13።  2ኛ  በዳንንባት  ቅጽበት  በውስጣችን  መኖር  የጀመረው  መንፈስ ቅዱስ  የእግዚአብሔር  ልጆች  መሆናችንን  ይመሰክርልናል፤  ሮሜ  8፥14-17።  3ኛው  ምስክር  የተለወጠ  ሕይወታችን  ነው።  ቀድሞ  የነበርነውን አይደለንም፤  ያልነበርነውን  ደግሞ  ሆነናል።  ሰው  ሲድን  አቤት  እረፍት!  አቤት  እፎይታ፥  አቤት  ሰላም!  አቤት  ነፃነት!  በመስቀል  ላይ  ከተፈጸመው የጌታ  ሥራ  የተነሣ  ደኅንነት  በእምነት  ብቻ  ነውና  በሥራ  እግዚአብሔርን አስደስቶ  መዳንንና  ጽድቅን  ለመቀዳጀት  መፍጨርጨር  የለም።  ይህ ደኅንነት  ደግሞ  ይጠፋል  ተብሎ  በስጋትና  በሰቀቀን  ሳይሆን  በታማኙ ታምኖ የሚኖሩት ኑሮ ነው። ክርስትና ይህ ቀላል የሆነ መዳን ነው። መ/ር ምህረተአብ  ምላሽ  በሰጠበት  ስብከት  ፓስተር  ዳዊት  “አታክብዱብን” ያለው  ይህንን  ነው።  መዳን  ይህንን  ያህል  ቀላል  ሆኖ  ነው  በአዲስ  ኪዳን የቀረበው።  ቀላል  ነው  ማለት  ግን  ርካሽ  ነው  ማለት  አይደለም።  ክቡር ዋጋ የተከፈለበት ነውና ርካሽ አይደለም፤ ግን ነፃ ነው! ነፃ! በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ግን  ይህንን  ነፃ፥  ቀላል፥  የሚያሳርፍ  ደኅንነት አናይም።  የማናይበት  ምክንያት  ግልጽ  ነው።  አንድ  ደራሲ  የሚያሳየው ያየውን  ነው።  እነዚህ  ሰዎች  ይህንን በጸጋው ብቻ  መዳንን  አልቀመሱም።
የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ከቶም አይደለችም።  ይህች  ማርያም  የክርስቶስ  ማዳን  እንዳይታይ  መጋረጃ ተደርጋለች።  ስለዚህ  ኢየሱስን  እስከ  መስቀሉ  እንኳ  ሳይሆን  እስከ አገልግሎቱም  ጅማሬ  ሳያደርሱት  በእናቱ  ስር  ያለ  ታዛዥ  ወጣት አድርገው  በ18  ዓመቱ  መጽሐፋቸውን  ደመደሙ።  ደኅንነት  ያለው መስቀሉ  ላይ  ነዋ!  በውስጡ  የሚታዩ  ሰዎችም  መዳንን  ያልተለማመዱ በነፍሳቸውም  የተቅበዘበዙ  ሰዎች  ናቸው።  በመጽሐፉ  ጥላቻ፥  ቂምና በቀል፥ መግደል፥ ፍርሃት፥ የሥልጣን ጥም፥ ውሸት፥ ወዘተ ይታዩበታል።  በምዕ.  61  ማርያምም  ውሸታም  ተደርጋ  ቀርባለች።  በአንዲት  ባልቴት ተመስላ  ወደ  አንድ  ሹም  ዘንድ  ሄዳ  የዋዳ  አገር  ሴት  መሆኗን  ነግራው ነበር።  የተአምረ ማርያሟ ማርያም መዋሸትም ትችላለች።

7.  ይህ ደራሲ  ያልተዋጣለት ልብ ወለድ ደራሲ  ነው። 

የተዋጣለት  ቢሆን መጽሐፉ ልብ ወለድ መሆኑን ይገልጥ ነበር። ነገር ግን፥ መጽሐፉ እውነት ሳይሆን  እውነት  ተደርጎ  ቀርቦአል።  እውነት  ያለመሆኑን  የሚያረጋግጡ ማስረጃዎች በቀጣዩ  ንዑስ ርእስ  ይቀርባሉ። በመጽሐፉ  ውስጥ  ከእውነት ጋር የተጠጋጋው  ብቸኛ ክፍል በዘርዓ ያዕቆብ  ዘመን ለማርያምና ለስዕል፥ ለመስቀልም  ስግደት  የተገባ  አይደለም  ብለው  ስቃይ  የደረሰባቸው  ሰዎች  (ደቀ እስጢፋኖስ)  ጉዳይ  የተጻፈበት  ተአምር  24  ብቻ  ነው።  ለዚያውም ከተሰደዱቱ  አንጻር  ከተጻፈው  ጋር  ሲተያይ  በውስጡ  የተጠቀጠቁውሸቶችም  አሉበት።  በሌሎች  ምዕራፎች  የተጠቀሱ  ታሪካዊ  ሰዎችም እንኳ  በታሪክ  ማኅደር  ሲፈተሹ  በተአምረ  ማርያም  የሚታየው ማንነታቸው ከእውነተኛ ማንነታቸው ጋር አይገጥምም። ተረቶችና  የፈጠራ  ሥራዎች  የእውነት  መልክ  ሊይዙ  የሚችሉባቸው ዘመናት  ያኔ  ብቻ  አይደለም፤  ዛሬም  ያው  ነው።  ለምሳሌ፥  የዳቪንቺ  ኮድ ልብ  ወለድ  መጽሐፍ  ነው።  መጽሐፉ  ተናፍሶለት  ፊልምም  ሆኖ ለተመልካች  ሲበቃ  ያዩት  አላዋቂ  ሰዎች  ታሪኩ  እውነትና  ቤተ  ክርስቲያን እንዳይወጣ  ደብቃ  የያዘችው  ምስጢር  እንደሆነ  ሽንጣቸውን  ገትረው ተከራክረዋል።  በሕይወት  ያለው  ደራሲ  መጽሐፉ  ልብ  ወለድ  መሆኑን እየመሰከረም  እንኳ  ልብ  ወለዱን  እውነት  ነው  ብሎ  መከራከር  ጅልነት ሳይሆን  እብደት  ነው።  ተአምረ  ማርያምም  ሆን  ተብሎ  ባለበት  መልኩ ተጽፎ  ካልሆነ  ምናልባት  በመጀመሪያ  እንደ  አጫጭር  ተረቶች  መድብል ተጽፎ ኋላ ማርያማዊ  ቀለም የተቀባበት  ይመስላል፤ ሊሆንም ይችላል።
እነዚህ  ጥቂት  ነጥቦች  ከቁጥር  ሊገቡ  የተገባቸው  የደራሲዎቹ  ወይም የደራሲው  ባህርያት  ናቸው።  እንደ  ደራሲው  መጽሐፉ  ራሱ  ደግሞ ሲፈተሽ ይህ መጽሐፍ የራሱ ውስጣዊ ባህርያት አሉት።

የመጽሐፉ ባህርያት / ይዘት

ራሱን  በየጊዜው  ለማረምና  ለማስተካከል  ወይም  ከዘመኑ  ጋር ለመመሳሰል  ከሚጥር  በቀር  በየትኛውም  ሃይማኖትም  ይሁን  ፍልስፍና ዘንድ  አንድ  ዋና  መሠረታዊ  መጽሐፍ  ይኖራል።  ሌሎች  ጥቃቅን መጻሕፍትም  ደግሞ  ይኖራሉ።  ሁልጊዜ  ጥቃቅኖቹ  የዋናውን  አሳብና ፈለግ  እየተከተሉ  ያንን  ያጠነክሩታል፥  ያብራሩታል  እንጂ  አይጻረሩትም። ዋናው  መጽሐፍ  ስሕተት  ያለበትና  የሚስተካከል፥  ወይም  በየጊዜው የሚሻሻል  ሆኖ  ካልተገኘ  በስተቀር  በጥቃቅኖቹ  መጻሕፍት  ውስጥ የሚገኙት  አሳቦች  በሙሉ  ወይም  በከፊል  ስሕተት  የተገኘባቸው እንደሆነ፥  ወይም  ከዋናው  መጽሐፍ  ጋር  የተጋጩ  ሆነው  ቢገኙ  ዋናው ትክክል ጥቃቅኖቹ እንደ ስሕተተኛ ይቆጠራሉ። ወደ  ክርስትና  እምነት  ስንመጣ  ምንጩ  መንፈስ  ቅዱስ  የሆነ  አንድ  ዋና፥ የማይለወጥ፥  ትክክለኛ፥  ሙሉ  ሥልጣን  ያለው  መጽሐፍ  አለን።  ይህ መጽሐፍ  ማናቸውም  ሌላ  መጽሀፍ፥  ስብከት፥  እና  ትምህርት  ብቻ ሳይሆን  አኗኗርም፥  ልምምዶችም፥  የሚፈተሹበት  ነው።  ይህ  መጽሐፍ መጽሐፍ  ቅዱስ  ነው።  ማንም  ክርስቲያናዊ  ካባ  የደረበ  መጽሐፍ ከካባው በታች ያለው ሰውነቱ በዚህ መጽሐፍ መርማሪነት መፈተሽ አለበት።
ተአምረ  ማርያም  ምንጩ  ምንድርነው?  ትውፊት  ነው  ወይስ  አፈ  ታሪክ ወይስ  ተረት?  ለምን ምንጩ  መጽሐፍ  ቅዱስ አልሆነም? መጽሐፍ  ቅዱስ መጽሐፍ  ቅዱስ  የወጡ  ጥቂት  ምንባቦች  መጽሐፉን  ክርስትና  እንዲሸት ተብለው  ከዐውዳቸው  ተፈንቅለው  በውስጥ  ተስገዋል።  ይህን  የሚያህሉ ግዙፍ  ትምህርቶች  ሲሰጡ  በመጽሐፍ  ቅዱስ  መፈተሽ  አያስፈልግም ነበር? ሌሎችም መፈተሻዎች አሉ። መጽሐፉ እርስ በርሱ ይጋጫል ወይስ አይጋጭም?  ከሌሎች  መሰል  መጽሐፎች  ጋርስ  ይስማማል  ወይስ ይጣላል?  በአፈጣጠሩስ  ተዓማኒነትን  የጨበጠ  ነው?  ከታሪክና  ከተረት ወደ  የቱ  ይቀርባል?  ወደ  የቱስ  ያዘነብላል?  ታሪካዊ  ከሆነ  ታሪኩ  ከሌላ ምንጭ ጋር ሊስተያይ ይችላል?  ተአምረ  ማርያምን  አንብቤ  ከፈጸምኩ  በኋላ  በውስጡ  ካገኘኋቸው ሕጸጾች መካከል ዋና ዋና የምላቸው እነዚህ ናቸው፤
የደፈረሰ ምንጭ፥
የተቃለለ ክርስቶስ፥
የተጋነነች ማርያም፥
የተፈናቀለ ታሪክ፥
የተምታታ ሲዖልና መንግሥተ ሰማያት፥
የተጣረሰ ደኅንነትና የተቃወሰ ክርስትና፥
የተላቀቀ መልክዓ ምድር፥
የተዋረደ ጋብቻ፥
ያፈነገጠ ተፈጥሮ።

እነዚህን  ነጥቦች  በቀጣዮቹ  ገጾች  በነጥብ  አወሳቸዋለሁ።  እንዲህ የከፋፈልኩት  መጽሐፉን  በየምዕራፉ  ከመሄድ  ይልቅ  በነጥብ  መሄዱ የተሻለ  ሆኖ  ስላገኘሁት  ነው።  ከነጥቦቹ  አንድ  ሁለቱ  በቀደሙት  ገጾች የተነካኩ  ናቸውና  በነዚህ  እጀምራለሁ።  በየክፍሉ  ውስጥ  የተወሱት በአብዛኛው  ናሙና  ምሳሌዎች  ናቸው  እንጂ  ሕጸጾቹ  በሙሉ  ቢዘረዘሩ በትክክል ራሱን መጽሐፉን የሚያህል መጽሐፍ ይወጣዋል።

1.  የደፈረሰ  ምንጭ። 

ቀደም  ሲል  እንደተጠቀሰው  የእትሙ  አሳታሚው አይታወቅም።  መታወቁ  መልካም  የሚሆነው  ጥያቄንና  አጠያያቂ ጉዳዮችን  ለመነጋገር  እንዲያስችል  ነው።  አሳታሚውን  በተመለከተ መጽሐፉ  ከእትም  ወደ  እትም  የሚሸጋገረው  ከገቢ  ምንጭ  ጋር  በተያያዘ መልኩ  ሊሆን  ይችላል።  የደፈረሰው  ምንጭ  ግን  የመጀመሪያ  ደራሲውን የሚመለከት ነው።  የደፈረሰ  ሲባል  የጠራ  ነገር  ተቃራኒ  መሆኑን  ለማሳየት  ነው።  በዝርዝር እንደምናየው  መጽሐፉ  ከግብጽ  የመነጨ  ለመምሰል  ያልተሳካ  ሙከራ ያደርጋል።  በመምህር  ባዩ  ታደሰ  የተጻፈ  መጽሐፍ  ምንጩን  በተመለከተ፥ “በ1989  ዓ.ም.  የታተመው  ተአምረ  ማርያም  በዚህ  ጊዜ  ተጻፍሁ  ብሎ በግልጽ  ባይነግረንም  በውስጡ  ከያዛቸው  ዘመኑንን  ከሚያመላክቱ ታሪኮች  ተነስተን  ድምዳሜዎች  ላይ  መድረስ  የሚያስችሉንን  ፍንጮች ይዟል።”  ብሎ  ሦስት  ትልልቅ  ነጥቦችን፥  ማለትም፥  በዘመኑ  በርካታ መጻሕፍት  መደረሳቸውን፥  የተተረጎመበትን  የአባ  ሚካኤልንና  አባ ገብርኤልን  ዘመነ  ጵጵስና፥  በዘመኑ  የተደረገውን  የነአባ  እስጢፋ  ስደት ዘርዝሮ  ይህንኑ  አሳብ  ሲደመድም  እንዲህ  ይላል፥  “መጽሐፉን  ትኩረት ሰጥተን  ስንፈትሸው  ግን  በ15ኛው  ክፍለ  ዘመን  ጳጳሳቱ  ኢትዮጵያ  ውስጥ ከገቡ  በኋላ  አከናወኑት  የተባለውን  ኢትዮጵያዊ  ታሪክ  በውስጡ  ይዞ ስለሚገኝ  ከግብጽ  ነው  የመጣው  መባሉን  ለማመንና  ከዚያ  ክፍለ  ዘመን በፊት  የተጻፈ  ነው  ለማለት  የሚያስችለንን  ድፍረት  እንድናጣ ያደርገናል።"
ዲያቆን  ጽጌ  ሥጦታው  ባስተማራቸው  ትምህርቶች  ላይ  በኢኦተቤክ ቅዱስ  ሲኖዶስ  የሊቃውንት  ጉባኤ  በተደረገበት  ሃይማኖታዊ  ምርመራ ወይም  ክርክር  አንዱን  የክስ  ጥያቄ፥  “ተአምረ  ማርያም  የተጻፈው  አባ እስጢፋኖስን  ለመቃወም  ነው  ብለሃል  ተባልሁ”  በማለት  ያነሣና መጽሐፉ  በእርግጥ  የተሠራው  እዚሁ  አገር  ውስጥ  መሆኑን  በዝርዝር መልሶአል።  ይህንንና  ሌሎችንም  ተቀራራቢ  ጥያቄዎች  በጻፈው  መጽሐፍ ውስጥ አካትቶአል።
ተአምረ  ማርያም  በውስጡ  እንደተጻፈው  በእርግጥ  ከመንበረ  ማርቆስ ከተገኘ ከዚያ ወዲህ በመንበረ ማርቆስ ይህ መጽሐፍ መኖሩ የታወቀ ነው ይሆን?  ወደ  መንበረ  ማርቆስ  ከመግባቱ  በፊትስ  የት  ነበር?  ወይስ  እዚያ ነው  የመነጨው?  የግብጽ  ቤተ  ክርስቲያን  ይህ  መጽሐፍ  ኖሮአት ያውቃል? ወይም ይህን መጽሐፍ ንብረቴ ነው ብላ ታውቃለች? በዐረብኛ የተጻፈ  ብዙ  መቶዎች  ዓመታት  ያስቆጠረ  የምንጭ  መጽሐፍስ  አለ?

እንዲያው  በዐረብኛ  ተጽፎ  ከሆነ  ተብሎ  ከታሰበ  ለማለት  ነው  እንጂ የምንጩ  ጽሑፍ  በግብጽ  ስለመኖሩ  የሚናገር  ምንም  አመላካች  ነገር በመጽሐፉ  ውስጥ  የለም።  ከግብጽ  ውጪ  ስለመኖሩም  አመልካች  ነገር የለም። የምችለውን ያህል ውጪያዊ ምንጮችን ከመጻሕፍትም፥ ከመረጃ መረብም  በመፈለግ  ይህን  የአገራችንን  ተአምረ  ማርያም  የሚመስል ወይም  እንደ  ምንጭ  ሆኖ  ሊጠሩት  የሚቻል  ቀራቢ  ሰነድ  ላገኝ አልቻልኩም።  ተገልጠው  ከተሰደሩ  የግብጽ  ቤተ  ክርስቲያን  የሰነድ ስብስቦችም  ውስጥ  እንኳ  ይህ  ተአምር  የለም።  በዲያቆን  ጽጌ  መጽሐፍ በግብጽ  ውስጥ  ተአምረ  ማርያም  በግብጽ  አለመኖሩን  በተመለከተ  ብዙ ዓመታት (10 እና 13 ዓመታት) በዚያ ተቀምጠው የመጡ መነኮሳት ይህን መሳይ  ተአምር  [ተአምረ  ማርያም]  በግብጽ  ያለመኖሩን  ማረጋገጣቸውን ዘግቦአል። ምንጩ  ጠፍቶ  ቅጅው  ብቻ  ነው  አሁን  ያለው  ወይም  በዚህ ዘመን  የቀረው  ካልተባለ  ምንጩ  ካለበት  ተገኝቶ  ቢፈተሽ  ስለምንነቱ ከቅጅው ይልቅ እውነቱን የመግለጥ ጉልበት ይኖረዋል። ከሌለም፥ ‘ዋናው እነ  አባ  አብርሃም  የጻፉት  ከገጸ  ምድር  ጠፍቶ  አሁን  የሚገኘው  ይህ በእጃችን ያለው የኛ ቅጅ ብቻ ነው’ ተብሎም መገለጥ አለበት።  በሌላ  ገጽታው  ግን  ተአምረ  ማርያም  የተተረጎመ  ሳይሆን  በኢትዮጵያ ውስጥ  የተሠራ  አገር  በቀል  መጽሐፍ  መሆኑን  የሚገልጡ  እጅግ  በርካታ ማስረጃዎችን በውስጡ የታቀፈ ጽሑፍ ነው። ይህ ማለት የወዲያ ታሪኮች ከግብጽ  ከመጡት  የተሰሙ  ወይም  የተነገሩ  ሊኖሩ  መቻላቸው  ሳይዘነጋ ነው።  በግብጽ  ውስጥ  ያሉ  ገዳማትና  ግልጽና  የታወቁ  ያልሆኑ  ቦታዎችም ጭምር  ተጠቅሰዋል።  ግብጽና  ግብጻውያን  ግን  እየተደነቁ  ሳይሆን እየተወገዙ  የተነገረባቸው  ታሪኮች  ያይላሉ።  በአንጻሩ  ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን  እየተመሰገኑ  ተጽፈዋል።  ግብጻዊ  ምንጭ  ግብጽን ሲያኮስስና ሲያዋርድ፥ ኢትዮጵያን ሲያገንንና ሲያሞግስ ይነበባል። በግብጽ  ውስጥ  በዐረብኛ  ቋንቋ  ስለ  ማርያም  እየተጻፈ  የኢትዮጵያ ቦታዎች እጅግ ተዘርዝረው ተጽፈዋል። እነሽሬ፥ ተከዜ፥ ዋሊ (ዋልድባ?)፥ ሸዋ፥  ደዋሮ፥  ሙገር፥  ወግዳ፥  መርሐ  ቤቴ፥  ኢፋት፥  ትግራይ፥  የረር፥ አግዓዚ፥  ደብረ  ብርሃን፥  ዳሞት፥  ጎጃም፥  አክሱም፥  መጠራ፥  ጣና፥ ሀዘሎ፥ ደብረ ወገግ፥ ዝቋላ፥ ወዘተ፥ የኢትዮጵያ ሰዎች እነ ሠረቀ ብርሃን፥አስከናፍር፥  ዘሚካኤል፥  ዘርዑ፥  ያሬድ  (ባለ  መዝሙሩ  ያገራችን  ሰው)፥ ዘርዓ ያዕቆብ፥ ዘርዓ ክርስቶስ፥ ዘርዓ ሐዋርያት፥ ወዘተ፥ በኢትዮጵያ የሆነ ታሪካዊ  ክስተት  ለማርያምና  ለመስቀል መስገድ  የተገባ አይደለም ያሉ  የነ ደቀ  እስጢፋ  ዝርዝር  ታሪክ  ሁሉ  መጽሐፉ  ከውጭ  ሆኖ  ስለ  ኢትዮጵያ እየዘገበ  የነበረ  ሳይሆን  እውስጥ  ሆኖ  እየተናገረ  ያለ  መጽሐፍ  መሆኑን ይፋ ያደርገዋል።

የኢትዮጵያ  ግዛቶች  ስሞች  እነ  ማርያም  የኖሩባቸውና  ከሄሮድስ  ሸሽተው ወደ  ኢትዮጵያ  መጥተዋል  ተሰኝቶ  ነው።  ይህም  ራሱ  ራሱን  ማቆም እስከማይችል  ድረስ  የገዘፈ  ፈጠራ  ነው።  እውነተኛው  ታሪክ  የተጻፈው በማቴ. 2፥13-23  ብቻ  ሲሆን  በትንቢት  እንደተጻፈው  የሄዱትና  የቆዩት በግብጽ፥  የተመለሱትም  ከግብጽ  ነው።  ተአምረ  ማርያም  ኢትዮጵያ ውስጥ  በደብረ  መጠራ  ሳሉ  የሄሮድስ  ሞት  ተነገራቸው  የሚለው  ከአዲስ ኪዳን  ጋር  ይጋጫልና  ትልቅ  ውሸት  ነው።  ወደ  ኢትዮጵያ መጥተው  ኖሮ ቢሆን ማቴዎስ  ይህን ለምን አይነግረንም ነበር? ከሆነ ምንም አሳፋሪ ነገር የለበትም።  ይህ  የተሳገ  ትረካ  መጽሐፉ  እዚሁ  አገራችን  ተቦክቶ የተጋገረበት  አንድ  አመላካች  ነው።  መመለሳቸውን  በተመለከተ  ማቴዎስ ከግብጽ  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ከመጠራ  (ኢትዮጵያ)፥  ማቴዎስ  ለዮሴፍ ተነገረው  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ለማርያም፥  ማቴዎስ  መልአክ  በሕልም ነገረው  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ገብርኤል  ለዮሴፍ  ነግሮት  ያረጋገጠላት ደግሞ  ልጇ  ኢየሱስ  ነው  ይላል።  እነዚህ  ሁለት  ምንጮች  እንዲህ ከተጣሉ  ማን  ይደመጥ?  ከተረት  የሚያንሱ  ነገሮች  የታጨቁበት  ተአምረ ማርያም ወይስ መጽሐፍ ቅዱስ? እዚህ  ተደርሶ  ወደ  ዐረብኛ  ተተርጉሞ  እንደገና  ወደ  ግዕዝ  የተመለሰ የግብጽ  ደርሶ  መልስ  ቲኬት  ተቆርጦለት  ሄዶ  እንደመጣ  የተደረገ  ሥራ ካልሆነ  ወይም  የጥንት  ባላባቶች  የአገልግል  ምግብ  ሲያምራቸው  እቤት የተሠራ  የአገልግል  ምግብ  አገልጋይ  ተሸክማ  በፀሐይ  ስትዞር  ውላ  መልሳ ወደተሠራበት  ቤት  እንደምታመጣው  ዓይነት  ካልሆነ  በቀር  ተአምረ ማርያም  የአገር  ውስጥ  ሥራ  ነው።  ይህ  መጽሐፍ  የተፈጠረበት  ዘመን አምልኮተ  ማርያም  የገነነበት  መሆኑ  ይህን  አገር  በቀልነት  ግልጽ ያደርገዋል።  የአገሪቱ  ጳጳሳት  እየተሾሙ  ይመጡ  የነበረው  ከግብጽ በመሆኑ  ግብጻዊ  ተጋቦት  እንዳለው  አይካድም።  ግብጻዊ  ተጋቦትና ከውጪ  የተጫሩ  ‘ታሪኮች’  ይኑሩበት እንጂ ተተረጎመ  የተባለበት  [ወይም የተጻፈበት]  ዘመንና  ሁኔታ  ምንጩን  አገራዊ  ያደርገዋል።  ምንጩን አገራዊ  ከሚያደርጉት  ነገሮች  ሌላው፥  በሌሎች  አገሮችና  ሃይማኖቶች በአፍቅሮተ  ማርያምና  በአምልኮተ  ማርያም  በተጠመዱቱ  መካከል  እንኳ ይህ መጽሐፍ ያለመገኘቱ ነው።
የመጽሐፉ  ደራሲዎች  ሦስት  ሆኑና  ከዚህ  የተነሣ  መጽሐፉ  እርስ  በርስ የሚጋጩ  ብዙ  ነገሮች  ኖረውበታል።  ቅራኔዎቹና  ግጭቶቹ  ከመጽሐፍ ቅዱስ  ብቻ  ሳይሆን  እርስ  በርሱም  ከታሪክም  ጋር  ነው።  ምናልባት ሲጠናቀቅ  አንድ  ሰው  ነው  የደበለውና  ቅራኔዎቹን  ሳያስታርቅ፥ ግጭቶቹንም  ሳይከረክም  በእያንዳንዱ  ምዕራፍ  ጅማሬና  ድምዳሜ ተመሳሳይ አንቀጾችን መለጠፉ መጽሐፉ የአንድ ሰው እጅ እንጂ የማኅበር እንዳይመስል አድርጎታል።

 የተጻፈበት ዘመን የዘርዓ ያዕቆብ ዘመን ነው። ቀደም ሲል  እንደጠቀስኩት  ተአምረ  ማርያም  ተተረጎመ  የተባለበት  የነገሠበት  7ኛ ዓመቱ  1434 ዓ.  ም.  መሆኑ  ነው።  ይህ  ዘርዓ  ያዕቆብ  የማርያምና የመስቀል  ስግደትን  ተግባራዊ  ያደረገ  ሰው  ነው።  ይህ  አዲስና  ኋላ  መጥ  ከመጽሐፍ  ቅዱስም  ያፈነገጠ  ትምህርት  መሆኑን  የተረዱና  እንቢ  ያሉ እስጢፋኖስ  በሚባል  መነኩሴ  የተመሩ  ሰዎች  መኖራቸው  አበሳጭቶት  ዘለፋ እስጢፋ  የሚባል  መጽሐፍም  የጻፈ ንጉሥ  ነው።  እነ  እስጢፋኖስን  በመቃወም  ብቻ  ሳይሆን  ሕዝቡንም  በጠንካራ  ማስፈራራት  ለመጠፈር  የማርያም  አምልኮ  አዋጅ  ታወጀ። አዋጁ  ደቂቀ እስጢፋን  የተቀበለ በቤቱ  ያኖረ  ርስት  ያለው  ከርስቱ  ሊነቀል፥  ሹሙ  ከሹመቱ  ሊሻር፥  እነዚህ  ደቀ እስጢፋ  ለድንግል  ማርያምና  ለአንድ  ልጇ  መስቀል  እንቢ  ያሉ ናቸውና አይሁድ  እንደሆኑ  ቅጣታቸውም  ሞት  መሆን  እንዳለበት  ነው።
እውነትም  አዋጁ  ገዳይ  ብቻ  ሳይሆን  አሰቃይቶ  ገዳይ  ሆነ።  አፍንጫ  እየተፎነነ፥  ምላስ  እየተቆረጠ፥  በግርፋትና  የከብት  አጎዳ  በላያቸው እየተነዳ፥  በድንጋይ  እየተወገሩ  ብዙዎች  በስቃይ  ተሰዉ።  ሃይማኖታዊ  ጥያቄዎችን  ለመጠየቅ  በቂ  እውቀት  ከሌለ፥  ቃሉን  አንብበው  መንፈሳዊ  ዓይናቸው  በርቶ  እውቀቱን  ያገኙትም  ሲጠይቁ  ወይም  ሲቃወሙ በንጉሥ ሥልጣንና  አቀነባባሪነት  ይህ  ግድያ  ከተፈጸመባቸው  ሕዝቡ  በመንፈሳዊ  ጨለማ እየዳከረ ቢኖር ምን ያስገርማል?

ለእንዲህ  ያለው  አምልኮተ  ማርያም  ቀዳሚው  ሁኔታ  ምን  ነበር  የሚለው ጥያቄ  ጥናት  የሚፈልግና  ከዚህ  መጣጥፍ  አሳብ  ያለፈ  ጉዳይ  ነው። በአጭር  ቃል  ግን  ስለ  ማርያምና  ወላጆቿ፥  ስለ  ኢየሱስ  ሕጻንነትና  ከዚያ ጋር  ስለተያያዙት  ነገሮች  የተጻፉት  በታሪክ  የሚታወቁት  መጻሕፍት የተጻፉት  ማርያም  ካረፈች  ከ100 ዓመታት በኋላ ነው። ታሪኩን  የሚናገሩ  በሌሉበት  የተፈጠረ  ሥራ  ነው።  ተአምረ  ማርያምማ  ራሱም  ስለ  ራሱ እንደሚመሰክረው  ከዚያ  መደብ  የሚገባም  አይደለም።  ማርያም በሕልምና  በራእይም እየተገለጠች  ያስጻፈችው ነውና። በዐፄ  ዘርዓ  ያዕቆብ  ዘመን  ከዚያ  ዘመን  በፊት  ኖሮ  ያልታወቀ  እንዲህ የመሰለ  መጽሐፍ  ቢጻፍ  ወይም  ቢተረጎም  ግን  አይደንቅም።  የዐፄ  ዘርዓ ያዕቆብ  ዘመን  ከሚታወቅባቸው  መልኮች  አንዱ  የስነ  ጽሑፍ  ፍንዳታ ነው።  ራሱ  ንጉሡም  አስቀድሞ  በገዳም  የኖረ  መነኩሴ  ሲሆን  መንግሥት በአጭር  ጊዜ  ከአባቱ  ሞት  በኋላ  ወደ  ወንድሞቹ  እየተላለፈ  ኋላ ከወንድም  ወደ  ወንድም  ልጅ  ሲያልፍ  ቆቡን  ጥሎ  ዘውድ  ሊደፋ ከምንኩስና  ወደ  ንግሥና  የመጣ  ሰው  ነው።  እንደ  ክርስቲያን  የተቀደሰ ኑሮ  በመኖር  ምሳሌ  የሆነ  ሰው  ሳይሆን  ደርቦ  እያገባና  እንደወደደ  የኖረ፥ እንደ  ክርስቲያን  በእግዚአብሔር  በመታመን  ሳይሆን  ጥንቆላን በመፍራትና በመሳቀቅ የኖረ ሰው ነው። እንደ  ገዳም  ሰውም  እንደ  ንጉሥም  ራሱም  እየጻፈም  ሌሎችንም እያስጻፈና  ከሌሎች  ቋንቋዎች  እየተተረጎመም፥  ዜጋው  በግዴታ የሃይማኖትና  የኅሊና  ጫና  እየተደረገበትም  ብዙ  ሠርቶአል።  ከእርሱ ዘመን  ቀደም  ሲል  መጡ  የተባሉ  ስዕሎችና  ግማደ  መስቀልም  ገናና ሆነዋል።  በዚህ  ጊዜ  ነው  ለማርያም  ስዕል  መስገድ  የመንግሥት  ግዴታ የሆነው።  እነ  መጽሐፈ  ምዕላድ፥  አርጋኖነ  ድንግል፥  ይኸው  በዚህ መጣጥፍ  የምንመለከተው  ተአምረ  ማርያም፥  ይህን  አዲስ  ጫና ላለመቀበል  በቆረጡት  ላይ  የተጻፈ  ዘለፋ  እስጢፋ፥  መጽሐፈ  ብርሃን እና መጽሐፈ  ጽልመት  ሌሎችም  ብዙ  በዚህ  ዘመን  ተጽፈዋል።  ነገረ ማርያምን  በተመለከተ  እንዲህ  የበዙ  መጻሕፍት  በተደረሱበት  ዘመን  ላይ ይህም መጽሐፍ ተተረጎመ ሳይሆን ተደረሰ ቢባል ተገቢ ነው። ሃይማኖቱ የንጉሥ  ጫና  ያለበት  ሲሆንና  ንጉሡ  ራሱም  ደራሲ  ይህን  መሳይ  ጽሑፍ የሚያስሸልምና  ባለሟል  የሚያስደርግ  ከሆነ  ለመጽሐፉ ፈጣሪዎችም  ይህ ዘመን ምቹ ዘመን ነው።

ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,
ማሳሰቢያ፤
 በመልእክት ሳጥናችን ገንቢ ያልሆኑና ስህተት ካለ ለእርማት የማያመቹ አስተያየቶችና ስድቦች እየደረሱን ነው። ጸሐፊው የተሳሳተው ነገር ካለ ወይም ጽሁፉ በቀረበበት ርዕስ ላይ በቂ ምላሽ መስጠት የፈለገውን በቀጥታ ለጸሐፊው በማቅረብ ወይም በመካነ ጦማራችን ላይ በማውጣት ለማስተናገድ ዝግጁ መሆናችንን እየገለጽን ለጸያፍ ቃላት ከተዘጋጀ የስመ ክርስትና አንደበት በመራቅና  ከኔ ወዲያ እውነተኛ ጸዳቂ  የለም!  ከሚል ሌላውን የመኮነን ግብዝነት መለየት የተሻለ እንደሆነ እንመክራለን ። ከዚያ በተረፈ  ብንቀበለውም፤ ባንቀበለውም ያለው እውነት በወንጌል የተነገረላት የክርስቶስ ኢየሱስ እናት ቅ/ማርያምና በተአምረ ማርያም ያለችቱ ማርያም አንድ አይደሉም። የክርስቶስ እናት ድንግል ማርያም ሁሉን ነገር በትዕግስትና በትህትና ትጠብቅ የነበረች ፍጹም ትሁትና የመሀሪ እናት ስትሆን (ሉቃስ 2፤19) የተአምረ ማርያሟ ማርያም ግን ሲኦል የምታወርድ፤ የምትሰነጥቅ፤ እንደእንጨት የምታደርቅ፤ የሰባት ዓመት መንገድ ያህል የሰው ሬሳ እንዲገማ የምታደርግ፤ ሥሉስ ቅዱስን የሚክድ የምትወድ፤ ጥላዋን ጥላ ሚዛን የምትሸውድ፤ ስሟንና ሀገሯን ሳይቀር በመደበቅ የምትዋሽ፤ እሁድ እሁድ ተአምሯን ያልሰማውን የምታወግዝና በአጠቃላይ አንዳችም ክርስቲያናዊ ጠባይ የሌለባት፤ ከክርስቶስ ይልቅ እኔ ልግነን የምትል፤ ጭካኔ የሚታይባት ናት። ይህች ኢትዮጵያ ውስጥ በዘርዓ ያዕቆብ የተፈጠረችው ማርያም፤ በየትኛውም መንፈሳዊ መመዘኛ መንፈስ ቅዱስ ያነጻትና የቀደሳት ድንግል ማርያምን አትወክልም።

Tuesday, June 17, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

ተአምረ  ማርያም  የተባለው  መጽሐፍ  እንደ  ስያሜው  ሁሉ  ማርያም እንዳደረገቻቸው  የሚነገሩ  የብዙ  ተአምራት  መድብል  ነው።  ከተአምራቱ በጣም  ጥቂቱን  ሕጻኑ  ኢየሱስ  ያደረጋቸው  ሲሆኑ  ብዙዎቹን  ማርያምና የማርያም  የተለያዩ  ስዕሎች  ናቸው  ያደረጉት።  አንዳንዱ  ምዕራፍ  ምንም ተአምርነት  የሌለበት  የተደረጉ  ነገሮች  የተዘገቡበት  ዘገባ  ቢሆኑም በእያንዳንዱና  በሁሉም  ምዕራፎች  መግቢያ  ወይም  አናት  ላይ  ማርያም ያደረገቻቸው  ተአምራት  እንደሆኑ  በቀይ  ቀለም  እየተጻፈ  በአንቀጽ ተቀምጦአል።  ተአምር  ባልሆኑት  ላይ  በአናቱ  ላይ  የማርያም  ተአምር መሆኑን  መጻፉ  የግድ  መሆን  ስላለበት  የተደረገ  ይመስላል።  ለምሳሌ፥ ሁለተኛው  ተአምር  ወይም  ምዕራፍ  ማርያም  ስለ  መጸነሷና  ስለ  ልደቷ የተነገረ  ሲሆን  ያው  የግዴታ  ልማድ  ሆኖ  ክብርት  እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ተብሎ ተጽፎአል። ያለዚያ እንደ ምዕራፍ 2 መግቢያ ማርያም  ገና  ከመጸነሷና  ከመወለዷ  በፊትም  ተአምር  ታደርግ  ነበርና ከልደቷ  በፊትም  ቀዳሚ  ኅልውና  ነበራት  ማለት  ይሆን?  አጻጻፉ ይመስላል። ከሆነ ዘላለማዊት ናት ሊሰኝ ይመስላል።  የመጽሐፉ አሳታሚና ባለቤት ማን ነው? ይህኛውን  (እኔ  ያነበብኩትን)  እትም  ያተመው  ተስፋ  ገብረ  ሥላሴ ማተሚያ  ቤት  ሲሆን  አሳታሚው  አልተጻፈም።  ከመግቢያው እንደሚነበበው  ግን  አሳታሚው  ተስፋ  ገብረ  ሥላሴ  ዘብሔረ  ቡልጋ ነው።  ይህ  መጽሐፍ  በኢኦተቤክ  ሰፊ  ተቀባይነት  ያለው  የነገረ  ማርያም ሰነድ  መሆኑ  አጠያያቂ  ባይሆንም  በማን  ቡራኬ  መታተሙ  አልተጻፈም። በበርካታ የኢኦተቤክ መጽሐፎች እንደሚታየውም የሊቀ ጳጳስ ምስል እና መልእክትም  የለበትም።  ስለዚህም  አይቶ፥  መርምሮ  አጽድቆ  ለአንባቢ የተገባ  ነው  ብሎ  ያሳለፈ  ተጠያቂ  አካል  የለውም  ማለት  ነው።  በእውኑ የኢኦተቤክ  ይህን  መጽሐፍ  እንደ  ቅዱስ  መጽሐፍ  አድርጋ  ትቀበለዋለች?  መቼም  ከተቀበለችው  በቂ  የሆነ  ታሪካዊ  ምንጭ  ያለው  ሆኖ  መገኘት አለበት?  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋርም  መጋጨት  የለበትም።  ምክንያቱም ማንም  ክርስቲያናዊ  መጽሐፍ  አስተምህሮአዊ  ተደርጎ  ከተወሰደ  ምንጩ መጽሐፍ ቅዱስ መሆን አለበት። ታሪካዊ ከሆነ ደግሞ ታሪካዊ ብቻ ነውና ሥልጣን  ያለው  መጽሐፍ  መሆን  የለበትም።  ደግሞም  ከዋናው ክርስቲያናዊ  መጽሐፍ  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ተያይቶ  ሊቀበሉት  ወይም ሊጥሉት የተፈቀደ መሆን የተገባው ነው። የኢኦተቤክ ይህን መጽሐፍ የኔ ብላ ትቀበለው ወይም አትቀበለው እንደሆነም  ግልጽ  አይደለም። በአንድ ድረ  ገጽ  ላይ  በቅርብ  ያነበብኩት  ሁለቱ  ሲኖዶሶች  ከሚነጋገሩባቸው ነጥቦች አንዱ ይህ መጽሐፍ እንደሆነም ነው። መጽሐፉ  አሁን  በታተመበት  ቅርጹ  አማርኛው  ከግዕዙ  ጋር  ጎን  ለጎን በመሆን  ተጽፎአል።  አንዳንዱ  የአማርኛ  ቃላት  ሆን  ተብለው  የተለሳለሱ ሲመስሉ  አንዳንዱን  አማርኛ  ለመረዳት  ደግሞ  ራሱ  ግዕዙ  ለዘመናችን አማርኛ  የቀረበ  የሚመስልባቸው  ቦታዎችም  አሉ።  አንዳንዱ  ጥቅስ ከትርጉም  ይልቅ  ማብራሪያ  የሚመስልባቸው  ቦታዎችም  ብዙ  ናቸው። የተአምራቱ  ቁጥራቸውም  ከአንዱ  እትም  ወደ  ሌላው  ይለያያል  ይባላል። እኔ  ባነበብኩት  መጽሐፍ  (የŦ ŹƃƂƆ  ዓመተ  ምሕረት  እትም)  ተአምራቱ ወይም  ምዕራፎቹ  123  ናቸው።  አንዳንድ  ተአምራት  ወይም  ምዕራፎች በአንዱ  የመጽሐፉ  እትም  ይገኙና  በሌላው  እትም  የማይገኙ  ከሆኑ መጠኑና ይዘቱ ከእትም እትም ይለያያል ማለት ነው። በመምህር  ባዩ  ታደሰ  መጽሐፍ ውስጥ  ከተቀነሱት  ተአምራት  አንዱን ‘ተአምር  97’  የተባለውን  በመጥቀስ  ከቀድሞዎቹ  እትሞች  በአንዱ (ለምሳሌ፥  ከ1924ቱ  እትም)  ተጽፎ  ከኋለኞቹ  እትሞች  (ለምሳሌ፥ ከ1989ኙ እትም) እንደቀረ በማውሳት ይህ የሆነው ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በግልጽ  በመጋጨቱ  ምክንያት  እንደሆነ  ታትቶ  ቀርቦአል።  ለውጥ የሌለበት  ለማስመሰል  ግን  ‘በድጋሚ  የታተመ’  እየተባለ  መቅረቡተወስቶአል። በሌላ  አንድ  መጽሐፍ  ውስጥ  የተጠቀሰ  ተአምረ  ማርያም ደግሞ  ተአምራቱ  አንድ  መቶ  አሥራ  አንድ  መሆናቸውን  ይጠቅሳል። ቁጥሩ  ወጣ  ገባ  ነው።  በአንድ  ድረ  ገጽ  ስለ  ተአምረ  ማርያም  በተጻፈ አጭር  መልእክት  ላይ  ምላሽ  ከሰጡት  ሰዎች  አንዱ  ተአምር  19  ላይ  ስለ መሐመድ  የተጻፈ  ነገር  እንዳለበት  ጠቅሶአል። እኔ  ባነበብኩት  ምዕ. 19ማርያም  ሙታንን  እያስነሳች  ለሰዎች  ስታሳይ  ነው  የተጻፈው  እንጂ  ይህ ስለሌለ  በድረ  ገጹ  የተጻፈው  ትክክል  ከሆነ  ምዕራፎቹ  ተሸጋሽገው፥ ታጥፈው፥ ወይ ተሰርዘው ይሆናል? ምናልባት አንዳንዱ እትም ምዕራፎቹ እየተመረጡና  የሚያጠያይቁት  እየተነቀሱ  የታተመ  ሊሆን  ይችላል፤  ግን ከላይ  እንደተጠቀሰው  ‘በድጋሚ  የታተመ’  እየተባለ  ከውስጡ  እየተገመሰ ከቀረ ይህ ስነ ጽሑፋዊ እብለትና አንባቢን መደለል ነው።

 የመጽሐፉ ምንጭ / ደራሲው ማን ነው?

ተአምረ ማርያም በመጀመሪያ በግብጽ አገር ከመዓልቃ ከመንበረ ማርቆስ (መንበረ  ማርቆስ  በእስክንድርያ  ነው  የሚገኘው)  የተገኘ  በዐረብኛ  ቋንቋ የተጻፈና  በኋላ  ወደ  ግዕዝ  ተተረጎመ  የተባለ  መጽሐፍ  ነው።  የጻፉት  አባ አብርሃም፥  አባ  ማርቆስና  አባ  ማቴዎስ  የተባሉ  [መነኮሳት]  ሲሆኑ የጻፉትም  ማርያም  አንዳንዴ  ራሷ  እየተገለጠች፥  ሌላ  ጊዜ  በሕልም፥  ሌላ ጊዜ  በራእይ  እየታየች  እየተነጋገረቻቸው  እንደሆነም  በመቅድሙ ተጽፎአል።  እነዚህ  ሦስት  መነኮሳት  እነማን  ስለመሆናቸው፥  መቼ ስለመኖራቸው፥  የት  ስለመኖራቸው፥  የምን  አገር  ወይም  የየትኛው ዐረብኛ  ተናጋሪ  አገር  ሰዎች ስለመሆናቸው የሚናገርም ምንም  ማብራሪያ በመጽሐፉ  የለም።  እነዚህ  ጸሐፊዎች  እነማን  ናቸው  ቢባል መታወቂያቸው  ቢያንስ  በመጽሐፉ  ውስጥ  የሚገኝ  መሆን  ነበረበት፤  ግን የለም። በምዕ.  1  ደቅስዮስ  የተባለ  ሰው  ታሪኳን  ሲሰበስብ  እንደተገለጠችለትና ስለጻፈላት  እንዳመሰገነችውም  ተጠቅሶአል።  ይህ  ደቅስዮስ  ሰብሳቢም ጸሐፊም  ተብሎአልና  እንደ  ሰብሳቢ  ብቻ  ሳይሆን  ከነአባ  አብርሃም  ጋር እንደ  ጸሐፊም  የሚቆጠር  ነው።  በምዕ.  6  ደግሞ  አንድ  ሰው  ሌላ መጽሐፍ፥ የፍልሰት መጽሐፍ እንዳገኘ ይናገራል። ቁ. 23 ላይ ይህን የጻፈ ዮሐንስ ነውም  ይላል።  ቁ. 18  ላይ እርሱ ራሱ  የጻፈውን ነገረኝም ይላል። ስለዚህ  ከነአባ  አብርሃም  በፊት  የተጻፈ  ያውም  በሐዋርያው  ዮሐንስ የተጻፈ  የፍልሰት  መጽሐፍም  የነበረ  ይመስላል።  በምዕ.  7  ደግሞ ስንክሳርን  በመጥቀስ  ያንንም  እንደ  ምንጭ  በመጥቀስ  የማርያምን  ዕርገት ይተርካል።  ስለ  ደራሲዎቹ  ከስማቸው  ውጪ  ከመጽሐፉ  ውስጥ  የምናገኝላቸው  ነገር የለም።  ስምና  ማዕረግ  ብቻ  ‘አባ  እገሌ’  ተብሎ  ከመጠቀሱ  በቀር  ሌላ ያለመኖሩ  ምንጩን  ሆን  ተብሎ  የተድበሰበሰ  ያደርገዋል።  ‘አባ  እገሌ’ ደግሞ  የመነኩሴ  ሁሉ  መጠሪያ  ነው።  በማን  ዘመን  መንግሥት  ወይም በማን  ዘመነ  ጵጵስና  ነበሩ?  የት  ነበሩ?  እነዚህ  ሴዎች  ሌላ  ምን  ጻፉ?  ቢባል  አጥጋቢ  ቀርቶ  የማያጠግብም  ማስረጃ  አይገኝም።  ምናልባት  ኖሮ ቢሆን  ከዚያ  በመንደርደር  የዘመኑን  ታሪካዊ  ስነ  መለኮት  በመቃኘት ነባራዊ  እውነታ  መጨበጥ  ይቻል  ነበር፤  ወይም  ሌላ  የጻፏቸው  ሥራዎች ቢኖሩ  የሰዎቹን  ስነ  መለኮታዊ  አቋም  በንጽጽር  መገምገም  ይቻል  ነበር። ግን እነዚህ ነገሮች የሉም። የዐረብኛው  የምንጭ  ጽሑፍም  መቼ  እንደተጻፈ  የሚያረጋግጥ  ውጪያዊ ምስክር  ወይም  ውስጣዊ  ማስረጃ  አይገኝለትም።  ከመጽሐፉ  መግቢያ እንደሚገመተው  የመጀመሪያውን  የጻፉት  በዐረብኛ  ሳይሆን  አይቀርም። እንደሚገመተው  ያልኩት  ግዕዙ  ተተረጎመ  የተባለው  ከዐረብኛ  መሆኑ እንጂ  የምንጭ  ቋንቋው  ዐረብኛ  ይሁን  ወይም  ራሱ  ዐረብኛው  ከሌላ ቋንቋ  የተተረጎመ  መሆኑን  ስለማይናገር  ነው።  ከሆነ  ዐረብኛ  የግብጽ ቋንቋ የሆነውና ቅብጥ ወደ ኋላ ተገፍቶ ከመነጋገሪያ ቋንቋነት የተወገደው ከእስልምናና  የዐረቦች  ወረራና  መስፋፋት  በኋላ  ስለሆነ  ከ8ኛው  ምዕት  ዓመት  በኋላ  ይሆናል  ማለት  ነው።  እንግዲህ  በዐረብኛ  መጻፋቸውና የተገኘው  ከግብጽ  መሆኑ  የኢትዮጵያና  የግብጽ  አብያተ  ክርስቲያናትን ቁርኝት  ተንተርሶ  አገሩን  ግብጽ፥  ዘመኑንም  ከእስልምና  ወረራ  በኋላ ጀምሮ እስከ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን ባለው ጊዜ ነው ብሎ ሰፊ ግምት መቸር ይቻላል።  በመቅድሙ  ይህ  የተተረጎመው  መጽሐፍ  የተገኘው  ከመንበረ ማርቆስ መሆኑ ተነግሮአል።  ተአምረ  ማርያም  ተተረጎመ  የተባለበት  ዘመኑም  ተጽፎአል።  ግን  ዋናው ከተጻፈ  ከስንት  ዘመናት  በኋላ  ስለመተርጎሙ  ግምትም  እንኳ  መገመት አይቻልም።  ተርጓሚዎቹ  አባ  ሚካኤልና  አባ  ገብርኤል  የተባሉ  ናቸው። አሁንም  ከስማቸው  ውጪ  ስለሰዎቹ  ከመጽሐፉ  ውስጥ  የምናገኘው ማንነታቸውን  ገልጦ  የሚያስረዳ  ነገር  የለም።  ተረጎሙት  የተባለበት  ጊዜ “ቆስጠንጢኖስ  የተባለ  ንጉሣችን  በዘርዓ  ያዕቆብ  ዘመን  በነገሠም  በ፯ ዓመት”  ተብሎ  ተጠቅሶአል።  ቆስጠንጢኖስ  ወይም  ዐፄ  ዘርዓ  ያዕቆብ የነገሠው በኛ አቆጣጠር ከ 1427-1461 ዓመተ ምሕረት ነው። የነገሠ 7ኛ  ዓመቱ  1434  ዓ.  ም.  ነው  ማለት  ነው።  በኋላ  ላይ  የምንጩን ድፍርስነት  በተመለከተ  አወዛጋቢና  አጠያያቂ  ነጥቦች  አነሣለሁ።  በአጭሩ ግን  በመጽሐፉ  ውስጥ  ከተጻፈው  የሚገኘው  የተአምረ  ማርያም  ምንጭ፥ መነሻና ዘመን ይህ ነው።

የጸሐፊው / የጸሐፊዎቹ ባህርያት

በአንዳንድ  መጽሐፎች  አንዳንዴ  እውስጡ፥  አንዳንዴ  በሽፋኑ  ስለ ደራሲው የተጻፈ አጭር ወይም ረጅም ታሪክ ወይም ግለ ታሪክ ይገኛል። ከመጽሐፉም  ከሌላ  ስፍራም  ካልተገኘ  በመጽሐፉ  ውስጥ  ከተነገሩት ነገሮች  በመነሣት  አንባቢው  የደራሲውን  የተለያዩ  የእምነትና  ማኅበራዊ አቋሞች እንዲሁም ስነ ልቡናዊ ከባቢና ስፍራ ማወቅ ይችላል።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ስለመጽሐፉ  ደራሲዎችም  ሆነ  ተርጓሚዎች ማንነት፥  አገልግሎት፥  እምነት፥  ዘመን፥  ገጠመኝ፥  ቦታ፥  ቤተ  ሰብ  ወዘተ የተጻፈ  ነገር  የለም።  ከመጽሐፉ  በመነሣት  ግን  ተአምረ  ማርያምን  የጻፉት ደራሲዎች  ወይም  ደራሲ  እምነቱ፥  የመጽሐፍ  ቅዱስ  መረዳቱ፥  የታሪክ እውቀቱ፥  ከክርስቶስ  ቁርኝቱ፥  ወዘተ፥  ምን  እንዲመስል  መገንዘብ ይቻላል። ጥቂቶቹ እነዚህ ናቸው።

 1.  የተአምረ  ማርያም  ደራሲ  እግዚአብሔርን  የሚንቅ  ሰው  ነው።

እግዚአብሔር  በነቢዩ  ኢሳይያስ  አድርጎ፥  እኔ  እግዚአብሔር  ነኝ ስሜ  ይህ ነው  ክብሬን  ለሌላ፥  ምስጋናዬንም ለተቀረጹ  ምስሎች  አልሰጥም  ብሏል፤ ኢሳ.  42፥8።  ክብሩን  ለሌላና  ለተቀረጹ  ምስሎች  አሳልፎ  አለመስጠት ብቻ ሳይሆን የተቀረጹ ምስሎች መደረግም የለባቸውም። ከ10ቱ ትእዛዛት 2ኛው  ይህ  ነው፤  በላይ  በሰማይ  ካለው፥  በታችም  በምድር  ካለው፥ ከምድርም  በታች  በውኃ  ካለው  ነገር  የማናቸውንም  ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም  ምስል  ለአንተ  አታድርግ፥  አትስገድላቸው፥ አታምልካቸውምም።  ዘጸ.  20፥4።  የዚህ  መጽሐፍ  ጸሐፊ  ግን  በግልጽ ይህንን  አምላካዊ  ትእዛዝ  በመተላለፍ  የእግዚአብሔርን  ክብር  ለሌላ፥ ማለትም፥  በፈጣሪ  ለተፈጠረች  ለማርያም  እና  በሰዎች  እጅ  ለተሳሉ የማርያም ስዕሎች ሸንሽኖ አሳልፎ ይሰጣል። በመጽሐፉ  ውስጥ  እግዚአብሔር  የተገለጠበትን  ክብር  እና  ማርያምየተገለጠችበትን  ክብር  ስናነጻጽር  በጉልህ  እግዚአብሔር የማርያም ፈቃድ ፈጻሚ  ነው።  ወሳኟ፥  አድራጊዋ፥  ቀጪዋ፥  ሸላሚዋ፥  ተበቃይዋ፥  ወደ ሲዖል  አውራጇ፥  ከሲዖል  ነጣቂዋ  እርሷ  ናት።  አዳምና  ሔዋን  እና  ሰው ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብር ሳይሆን ለእርሷ ክብር እንደተፈጠሩ ይናገራል መጽሐፉ።  በመጽሐፉ  ውስጥ  የሚታዩት  የማርያም  ስዕሎች  እጅ  ዘርግተው የመሥራትና  የማድረግ፥  አፍ  ከፍቶ  ድምጽ  አውጥቶ  የመናገር፥  ብያኔ የመስጠት፥  ሲወጉት  የመድማት፥  ተመልሰው  ሲለጠፉ  ጠባሳ  ሆኖ የመቅረት  ባህርይ  ያላቸው  ምስሎች  ናቸው።  ተአምራት  ማድረግ የእግዚአብሔር  ሀብት  ቢሆንም  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  እግዚአብሔር ሳይሆን  ማርያም  እና  ምስሎቿ  ናቸው  ተአምር  አድራጊዎቹ።  ከእግዚአብሔር  ኃይል  እና ከጌታ  ከኢየሱስ ስም  ሥልጣን ውጪ  ተአምር ከተደረገ  የዚያ  ተአምርና  ምልክት  ምንጭ  እግዚአብሔር  ሳይሆን  ሰይጣን መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል።

2.  ይህ  ደራሲ  መጽሐፍ  ቅዱስን  የማያውቅ  ሰው  ነው። 

በጣም  በጥቂት ቦታዎች  አልፎ  አልፎ  የተጠቀሱ  የመጽሐፍ  ቅዱስ  ክፍሎች  አሉ።  እነዚህ የተጠቀሱ  ጥቂት  ጥቅሶች  የተጠቀሱት  ያለቦታቸው  በመሆኑ  ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጋጩና የሚጣሉ ነገሮች ናቸው። መጽሐፉ የተደመደመው ኢየሱስ  18  ዓመቱ  ሆኖ  በግሪክ  ሳለ  ሲሆን  በወንጌል  ውስጥ  ያደረጋቸው አንዳንድ  ነገሮች  ገና  አገልግሎቱን  ሳይጀምርም  እንደተፈጸመ  ሆነው ተጠቅሰዋል።  የደራሲው  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ያለው  ግንኙነት  እነዚህን ጥቅሶች ለመውሰድ ብቻ ይመስላል። የመጽሐፍ ቅዱስ ዋና መልእክት ሰው ንጹሕ ሆኖ ተፈጥሮ ሳለ ኃጢአተኛ መሆኑና  እግዚአብሔር  ይህን  የወደቀ  ሰው  ለማዳን  በብሉይና  በአዲስ ኪዳን ያደረገው  ነገር  ነው።  ይህ ደግሞ በጣም  ግልጽ  ተደርጎ  ተጽፎአል። በብሉይ  ዘመን  ከሲና  ኪዳን  በፊት  በልቡና  ሕግ፥  ከሕገ  ልቡና  ዘመን በኋላ ደግሞ  ሕግ  ተሰጥቶ  ሰዎች  የመዳንን መንገድ  የሚሄዱበት  ያን  ሕግ በመፈጸም ሆነ። ሕጉም ራሱ ሊመጣ ያለው ነገር ምሳሌና ጥላ ነው እንጂ በዘላቂነት  ተጠብቆ  የሚዳንበት  አልነበረም።  ያ  ሁሉ  መስዋዕት  ጥላ  ሆኖ የሚያመለክተው  አካል  ነበረ፤  ያም  በመስቀል  ላይ  የሞተው  የክርስቶስ መስዋዕትነት  ነው።  ወንጌል  በአንድ  ጥቅስ  ቢጠቀስ  በዮሐ.  3፥16  የተጻፈው፥  በእርሱ  የሚያምን  ሁሉ  የዘላለም  ሕይወት  እንዲኖረው  እንጂ እንዳይጠፋ  እግዚአብሔር  አንድያ  ልጁን  እስኪሰጥ  ድረስ  ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና የሚል ነው።  የተአምረ  ማርያም  ደራሲ  የሸፈነው  ትልቅ  እውነት  ይህ  አንጡራው ወንጌል  ነው።  ተአምረ  ማርያም  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  እንደተጻፈው የሰውን  ልጆች  ለማዳን  እግዚአብሔር  ያደረገውን  እውነት  የጋረደ መጽሐፍ  ነው።  በዮሐ.  14፥6  ጌታ፥  እኔ  መንገድና  እውነት  ሕይወትም ነኝ፤  በእኔ  በቀር  ወደ  አብ  የሚመጣ  የለም  ያለውን  የተጻረረ  መጽሐፍ ነው።  በሮሜ  10፥13፥  የጌታን  ስም  የሚጠራ  ሁሉ  ይድናልና  የሚለው የምሥራች  በሌላ  ጫና  ተተካ።  መንገዱ  ኢየሱስ  ሳይሆን  ማርያም፥ መጠራት  ያለበት የጌታ  ሳይሆን የማርያም ስም  ተደረገና  ተለወጠ።  ለዚህ ነው  ይህ  ደራሲ  ደኅንነት  የሚገኝበትን  መንገድ  ያልተገነዘበ፥  መጽሐፍ ቅዱስን  የማያውቅ  ሰው  ነው  ያልሁት።  ካወቀ  ደግሞ  ሳያውቅ  የዘላበደ ሳይሆን አውቆ ያሳተ አሳች ነውና የባሰ አጥፊ ነው።  ይህ  መጽሐፍ  የተጻፈበት  ዘመን  ምእመናን  መጽሐፍ  ቅዱስን  እንደልብ የማያገኙበትና  የማያስተያዩበት  ዘመን  ነውና  የተነገረውን  ሁሉ  እንደ እውነት  ለመቀበል  ሃይማኖታዊና  ስነ  ልቡናዊ  ጫና  የሚደረግባቸው ስለሆነ  እውን  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ይጋጫል  ወይስ  አይጋጭም የሚለውን  የሚጠይቅ  አይኖርም።  የተማሩት  የሚባሉት  አለማሳወቃቸው ግን  የአዋቂ  አጥፊ  ያደርጋቸዋል።  ባለፉት  300  ዓመታት  ተራው  ሕዝብ ሊገባው  በሚችለው  ቋንቋ  መጽሐፍ  ቅዱስን  እንዲያገኝ  በመርዳትና  በማስተርጎም ፈንታ  ሌሎች  ጥረው  የተረጎሙት እንኳ  እንዳይደርስ  ታላቅ ተጋድሎ  ታደርግ  የነበረችው  ቤተ  ክህነት  መሆኗም  አስተዛዛቢ  ጉዳይ ነው።  ይህ  ራሱን  የቻለ  ሌላ  ጉዳይ  ቢሆንም  እዚህ  ያነሣሁት  ከሕዝብ መጽሐፍ  ቅዱስን  አለማወቅና  የተጻፈውን  ሳያስተያዩ  ከመቀበል  ጋር መነሣት  ስለተገባው  ነው።  እስከ  ቅርብ  ዓመታት  ድረስ  በኢኦተቤክ ስብከትና  ትምህርት  ለተራው  ምእመናን  በሚገባቸው  ቋንቋ  አይሰበክም ነበር።  ያኔ  ይህ  መጽሐፍ  በተጻፈበት  ዘመንማ  ሰው  በተስኪያን  ገብቶ ግድግዳ  ላይ  የተሳሉ  ስዕሎችን  ‘አንብቦ’  ነበር  የሚመለሰው  እንጂ  ሮሜ 10፥17  እንግዲያስ  እምነት  ከመስማት  ነው  መስማትም  በእግዚአብሔር ቃል  ነው  የሚለውን  አምኖ  እንዲድን  ሊሰማ  አልተደረገም።  የምእመናኑ አለማወቅ  ብቻ  ሳይሆን  ያውቃሉ  ተብለው  ሊያሳውቁ  የሚጠበቁትም ከቃሉ  ጋር  ጀርባና  ጀርባ  የሆነ  እንደዚህ  ያለ  መጽሐፍ  ሲያቀርቡ  አሳዛኝ ታሪክ  ነው።  ምን  ይደረግ!  ቃሉን  አያውቁትም።  ቢያውቁት  ኖሮ አይቃረኑትም ነበር።

3.  ይህ  ደራሲ  ክርስቲያንና  የክርስቶስ  ምስክር  ያልሆነ  ሰው  ነው።

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ክርስቲያናዊ  ባህርያት፥  ቃሉን  ማንበብ፥ እግዚአብሔርን  በመንፈስና  በእውነት  ማምለክ፥  ወንጌልን  ላልዳኑት ማሳወቅ፥  ክርስቶስን  መምሰል፥  የደቀ  መዝሙርነት  ኑሮ፥  የመንፈስ  ፍሬ፥ ጠላትን  መውደድ፥  የቅዱሳን  በቅድስና  መኖርና  በእምነት  መጽናት፥ ወዘተ፥  አይታዩበትም።  ይልቁን  በቀል  ይታይበታል።  የማያምኑትን መበቀል፥  በወንጌል  እውነት ተመርተው ሊኖሩ የሚወድዱትንም  መበቀል ይታዩበታል።  ክርስቲያን  ክርስቲያን  የተባለው  የክርስቶስ  ስለሆነ  ነው። አዳኙ፥  መሪው፥  ጌታው  ክርስቶስ  ነው።  በዚህ  መጽሐፍ  ግን  ማርያም አዳኝ፥  ኮናኝ፥  አጽዳቂ፥  ወደ  ሲዖል  አውራጅ፥  ወደ  መንግሥተ  ሰማያት አስገቢ፥  እየተገለጠች  መመሪያ  የምትሰጥ  ናት።  ይህ  እርሷን  ያለምንም ጥያቄ የሚከተል ሰው ክርስቲያን ነው መባል ያለበት ወይስ  ‘ማርያን’? ክርስቶስን  የሚያውቅ  ክርስቲያን  ያለ  ልክ  ከፍ  ያለውን  ጌታ  ስላወቀ በፊል. 2፥11  መላስም  ሁሉ  ለእግዚአብሔር  አብ  ክብር  ኢየሱስ  ክርስቶስ ጌታ እንደ ሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው እንደተባለ እርሱን የሚመሰክር ነው። ደግሞም  ጌታ  ከማረጉ  በፊት  በመጨረሻ  የተናገረው  ቃል፥  ምስክሮቼ ትሆናላችሁ  የሚል  ነው፤  ሐዋ. 1፥8።  ክርስቲያን  የክርስቶስ  ምስክር  ነው እንጂ  የሌላ  የማንም  ምስክር  አይደለም፤  ሊሆንም  የተገባ  አይደለም። እንዲህ  ያለ  መጽሐፍን  የጻፉና  ያስጻፉ፥  ከተጻፈ  በኋላም  የሚያሳትሙና የሚያሰራጩ  ክፉኛ  የሳቱት  ክርስቲያን  የማን  ምስክር  የመሆኑን  እውነት ባለመረዳት  ነው።  ይህ  ብቻ  ሳይሆን  የክርስቶስ  ሳይሆን  የሌላ  ምስክር መሆን  የሐሰት  ምስክር  ሆኖ  መገኘት  መሆኑን  ባለመረዳት  ወይም  አውቆ ከሐሰት ጋር ለመቆም ነው።  ምስክር  ያየውንና  የሰማውን  የሚናገር  እንጂ  ያዩና  የሰሙት  የጻፉትን የተነገረውን  እውነት  የሚሸፍን  አይደለም።  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  ግን ጌታ  ክርስቶስ  ተለጣፊ  ሆኖ ነው  የሚታየው። ጌታ ከራሱ  ጋር  ሌላ  ደባል የሚያቆምና  የሚጋራ  አምላክና  አዳኝ  አይደለም።  በነዚህ  ጥቂት  ጥቅሶች ውስጥ  “ብቻውን”  የሚሉትን  ቃላት  እናጢን፤  ብቻውን  አምላክ  ለሚሆን ለማይጠፋው  ለማይታየውም  ለዘመናት  ንጉሥ  ምስጋናና  ክብር  እስከ ዘላለም ድረስ ይሁን፤ አሜን። 1ጢሞ. 1፥17። ያንም መገለጡን በራሱ ጊዜ ብፁዕና  ብቻውን  የሆነ  ገዥ፥  የነገሥታት  ንጉሥና  የጌቶች  ጌታ፥  ያሳያል። 1ጢሞ. 6፥15።   ከብዙ  ጊዜ  በፊት  ለዚህ ፍርድ የተጻፉ  አንዳንዶች  ሰዎች ሾልከው  ገብተዋልና፤  ኃጢአተኞች  ሆነው  የአምላካችንን  ጸጋ  በሴሰኝነት ይለውጣሉ ንጉሣችንንና ጌታችንንም ብቻውን ያለውን ኢየሱስ ክርስቶስን ይክዳሉ።  .  .  .  ብቻውን  ለሆነ  አምላክና  መድኃኒታችን  ከዘመን  ሁሉ በፊት  አሁንም  እስከ  ዘላለምም  ድረስ  በጌታችን  በኢየሱስ  ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤  አሜን።  ይሁ. 1፥4፥25።  ይህ ብቻውን  የሚል  ቃል  (movnoß)  የሚጋራው፥  የሚዳበለው፥  አብሮት የሆነ  የሌለ  መሆኑን  ገላጭ  ቃል  ነው።  ለደኅንነት  ኢየሱስን  ከማርያምም ሆነ ከሌላ ከማንም ማዳበል ፍትሕ ሳይሆን ክህደት ነው።

ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,

Wednesday, June 11, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን በፓትርያርኩ ላይ የመጨረሻ የስም ማጥፋት መርዙን መርጨት ጀመረ!!

ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ስንል እንደቆየነው ከማኅበረ ቅዱሳን ስውር መሰሪ ተግባር ውስጥ አንዱ ጉዳይ የሊቃነ ጳጳሳቱን የሕይወት ታሪክ ባለው የገንዘብና የስለላ አቅም አስቀድሞ በመሰብሰብ ለችግር ቀን ሊጠቀምበት ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ የማስቀመጥ ጥበቡ ነው። ሊቃነ ጳጳሳቱ ማኅበሩ ለሚፈልገው አገልግሎት የጎበጠ ጀርባ ለማቅረብ ፈቃደኝነት ሲጎድላቸው ወይም ሲያገለግሉት ቆይተው የጎበጠ ጀርባቸውን ቀና በማድረግ የነጻነት አየር ለመተንፈስ ሲፈልጉ ያንን ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ ያስቀመጠውንና ስም ለማጥፋት ይጠቅመኛል ብሎ ያሰበበትን የቆሸሸ ሥራ እንደአዲስ ግኝት ብቅ በማድረግ በሕዝብ ዘንድ እንዲጠሉ የክፋት መርዙን በልዩ ልዩ አቅጣጫ መርጨት ይጨምራል።
እነሆ « የለውጥ አባት፤ ሙስናን ለመዋጋት ቃል የገቡ ፓትርያርክ» በማለት በማሞካሸት ጉሮሮው እስኪነቃ ውዳሴ ከንቱ ማብዛቱ ሳያንስ  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለማስረግ ሞክሮ ያልተሳካለትን «የሕግና የለውጥ አተገባበር መመሪያ» በማለት ያንቆለጳጰሰውን የቅጥፈት ስርዋጹን ሰነድ፤ ፓትርያርኩ «በመላ ሀገሪቱ ሊተገበር የሚገባው» በማለት አድናቆት እንደቸሩት ሲደሰኩር እንዳልነበር ሁሉ ፓትርያርኩ የማኅበሩን አካሄድ አይተው ፊታቸውን ሲያዞሩበት  በመረቀበት አፉ እርግማኑን ለማውረድ የተፋው ምራቅ ገና አልደረቀም ነበር።
የማኅበሩ የክፋት ጥግ ርኅራኄ የለሽ መሆኑን የሚያሳየን ሲያገለግሉት የቆዩት ሰለቸን ማለት ከጀመሩ ወይም ፊት ሰጥተው ሲያሳስቁት የነበሩት አባቶች ቅጭም ያለ ገጽታ ወደማሳየት ከተሸጋገሩ ስማቸውን በማጥፋት የነበራቸውን ስም ከአፈር በመደባለቅ እንዳይነሱ አድርጎ የመምታት ልኬታው ከባድ ነው።
ሰሞኑን በፓትርያርክ ማትያስ ላይ በግል ጋዜጦች፤ በአፍቃሬ እንዲሁም ስውር ብሎጎቹና በመንግስት ተቃዋሚ ድረ ገጾች ሳይቀር እየተቀባበሉ «ፓትርያርኩ የደርግ አገልጋይ ናቸው» ወደሚል የጋራ የስም ማጥፋት ዘመቻ ወርደዋል። «አንድ ሰሞን ማመስገን፤ አንድ ሰሞን መራገም» የማኅበረ ቅዱሳን «ሲመች በእጅህ፤  በማንኪያ ሲፈጅህ» መፈክር መገለጫ መሆኑ ነው።
አይሆንም እንጂ ቢሆንለት ፓትርያርኩ ነገ አዲስ ሀሳብ ይዘው ብቅ ቢሉና »ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያናችን የዓይን ብሌን ነው» የሚል መግለጫ ቢሰጡ  «12 ክንፍ ያላቸው ቅዱስ ፓትርያርኩ የክፍለ ዘመኑን አዲስ መግለጫ ሰጡ» በማለት እንደ ደብረ ብርሃኑ መብረቅ በብርሃን ወረደልን የፈጠራ ዜና ይለውጠውና ለፓትርያርኩ ገድል ይጽፍላቸው ነበር።
ይሁን እንጂ ይህ እንዳይሆን ለማኅበረ ቅዱሳን ህልም በመሰለ የእውነታ ውጥረት በፓትርያርኩ ስለተያዘ እርግማኑንና ስም ማጥፋቱን ስራዬ ብሎ ገፍቶበታል። ነገሩ ሲታይ «የማያድግ ጥጃ እንትን ይበዛበታል» እንዲሉ የስም ማጥፋት ዘመቻው የእስትንፋሱ የመጨረሻ ምዕራፍ እንደሆነ አመላካች ይመስለናል።
ፓትርያርክ ማትያስ«የደርግ ተላላኪ ነበሩ፤ አሁን ደግሞ የኢህአዴግ ተላላኪ ሆነው ተገልብጠዋል» በማለት ማጣጣሉ የሚያሳየን ነገር  የማኅበረ ቅዱሳን ተላላኪ ለመሆን በጭራሽ ፈቃደኝነት ቀርቶ ሃሳብ እንደሌላቸው ስላየ እንጂ ማኅበሩን እያሞጋገሱና ከወንበራቸውም ትንሽ ከፍለው ቢሰጡት ኖሮ ይህንን ወደመሰለ የብስጭት ማሳያ ነቀፋ ባልወረደም ነበር። እውነትን ለሕዝብ ለመግለጽ ፈልጎ ቢሆንማ ኖሮ አባ ገብርኤልን የመሰሉ የማኅበሩ ደጋፊ ጳጳስ በአንድ ወቅት አቶ ኢያሱ የመባላቸውን ዜና፤ አቡነ ጳውሎስን አውግዘው ወደአሜሪካ መፈርጠጣቸውን፤ እዚያም ሄደው የኢህአዴግ የተቃውሞ ሰልፍ አስተባባሪ ሆነው በአደባባይ መጮሃቸውንና 360 ዲግሪ ተሽከርክረው ወደጠሉት ሀገር መመለሳቸውን ዜና አድርጎ ለምን አይሰራም ነበር? ይህንንማ እንዳያደርግ አባ ገብርኤል የማኅበሩ ቀኝ እጅ ሆነው ስለሚያገለግሉ  ብቻ ነው።  ነገ ተነስተው «በዚህ ማኅበር ታምሰን የምንሞተው፤ እስከመቼ ነው?» የሚል ጥያቄ አቡኑ ቢያነሱ የታወቀና ያልታወቀ ኃጢአታቸውን እንደሸረሪት ድር ይዘከዝክላቸው ነበር።
በዘንድሮውም የሲኖዶስ ጉባዔ ላይ እንዳገኘው መረጃ ከሆነ የማኅበሩ ደጋፊ መሆናቸው በደንብ የሚታሙት ጳጳሳት ሳይቀሩ የድጋፍ ቀንዳቸውን አቁመው ሊከራከሩለት አለመድፈራቸው አንድም የማኅበሩ የእድሜ ዘመን ማጠሩን ከመገመት አንጻር አለያም በማኅበሩ ጥፋት የተነሳ ከኑግ እንደተገኘች ሰሊጥ እንዳይወቀጡ ከመስጋት የተነሳ ይመስለናል። ጥቅም ዓይናቸውን ካሳወራቸው መካከል ጥቂቶች ለመንጫጫት ከመሞከራቸው በስተቀር ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው ማኅበሩ አጀንዳ አስረቅቆ፤ ሲያስጸድቅ የነበረውን ጉልበት ዘንድሮ ሳያገኝ መክኖ ቀርቷል። አቡነ ጳውሎስን ተባብረው በአድማ ሲያዳክሙና ለራስ ምታት ሲዳርጓቸው የነበረው የሴራ አቅም በፓትርያርክ ማትያስ ተቀልብሶ በተገላቢጦች የማኅበሩና የደጋፊዎቹ ራስ ምታት ሆኖ የጫወታው ሜዳ ተጠናቋል።
ከዚህ በፊት ስንል እንደቆየነው አሁንም ደግመን የምንለው «የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን መብት ሲሆን ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ወደማኅበር አባልነት ወይም ደጋፊነት ከወረደ ያለበትን መንፈሳዊ ሥልጣን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስረክቦ በተራ አባልነቱ እንዲቀጥል የማስድረጉ ነገር መዘንጋት የለበትም» እንላለን። ሊቀ ጳጳስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ መንፈሳዊ ሥልጣን ላይ ተቀምጦ ከመንጋው ውስጥ በተለየ መልኩ የሚወደው ወይም የሚንከባከበው ወይም በጥብቅና የሚከራከርለት የተወሰነ የቤት ልጅ እና የእንጀራ ልጅ የሚባል ሊኖረው አይችልም። በሀዋሳ ታይቶ የነበረው ሁከት መነሻው በአባ ገብርኤል በኩል ማኅበረ ቅዱሳንን የቤት ልጅ አድርጎ የማየትና ማኅበሩን የሚቃወሙትን ደግሞ የእንጀራ ልጅ አድርጎ በማቅረብ መንጋውን በእኩል ለማገልገል ያለመቻል የጳጳሳት አባል የመሆን ልክፍት የተነሳ ነው። ይህ ችግር በቦረና፤ በሐረር፤  በመንፈሳዊ ኮሌጆችና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ሳይቀር በተግባር ታይቷል። ማኅበሩ «ከኛ ጋር ያልቆመ ጠላታችን ነው» በሚል ፈሊጥ በአባልነት የያዛቸውን ጳጳሳት እንደዱላ በክርስቶስ መንጋ ላይ እየወረወረ ይጠቀምባቸዋል።
ስለዚህ ፓትርያርክ ማትያስ በስም አጥፊው ማኅበርና ለማኅበሩ በተለየ አድረው መንጋውን በእኩል ዓይን ማየት በተሳናቸው ላይ ፍትሃዊና የተጨበጠ እርምጃ ለመውሰድ ማቅማማት እንደሌለባቸው ለማስገንዘብ እንወዳለን።
የስም ማጥፋት ዘመቻው የማኅበሩን ማንነት ገላጭ ሲሆን በንስሐ ተመልሶ ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው ልክ ከመንቀሳቀስ ይልቅ ክፋቱን ለመተው ያለመፈለጉ ማሳያ መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።

Sunday, June 8, 2014

«የዓላማ ሰው ከመሆን የሚከለክል ማንነትና መፍትሄው»

[«ከዓላማ መር መጽሐፍ» ለንባብ እንዲመች ተደርጎ የተወሰደ]

ማንኛውም ሰው ሕይወት በአንድ ነገር ግፊት ይመራል። ብዙ መዝገበ ቃላት «አንቀሳቀሰ» ለሚለው ግሥ፦ መራ፤ ተቆጣጠረ ወይም አቅጣጫን ወሰነ» የሚል ፍቺ ይሰጡታል። መኪናም ነዳህ፤ ሚስማር በመዶሻ መታህ ወይም ኳስ አንከባለልህ፤ በዚያን ወቅት ያንን ነገር እየመራህ፤ እየተቆጣጠርክና አቅጣጫውን እየወሰንክ ነው። ታዲያ ልክ እንዲሁ ሕይወትህን የሚመራው ኃይል ምንድነው?
   በአሁኑ ጊዜ በአንድ በሆነ ችግር በሆነ ጫና፤ ወይም ማለቅ ያለበትን ሥራ ለመጨረስ በጥድፊያ በመራመድና በመንቀሳቀስ ላይ ትገኝ ይሆናል። በክፉ ትዝታ፤ በአስበርጋጊ ፍርሃት ወይም በቅጡ ባልገባህ አንድ ኅሊናዊ እምነት ትመራ ይሆናል። ሕይወትህን ሊያንቀሳቅሱና ሊመሩ የሚችሉ ብዙ ሁኔታዎች፤ የሕይወት ፋይዳዎችና ስሜቶች አሉ። ቀጥሎ የተዘረዘሩት አምስቱ /5/ በጣም የተለመዱና የታወቁ ናቸው።

1/ ብዙ ሰዎች በበደለኛነት ስሜት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ዘመናቸውን ሁሉ ጸጸትና ቁጭት ከወለደው ሃፍረታቸው ለመሸሸግ ሲሸሹ ይኖራሉ። ቁጭትና ጸጸት የሚመራቸው ሰዎች የትዝታ ተጠቂዎች ናቸው። ያለፈው ሕይወታቸው መጪውን ህይወታቸውን እንዲቆጣጠረው ይፈቅዱለታል። ብዙውን ጊዜ ሳያውቁት የሕይወት ስኬታቸውን እያበላሹ እራሳቸውን ይቀጣሉ። ቃየል ኃጢአትን በሠራ ጊዜ በደሉ ከእግዚአብሔር ህልውና ለየው፤ እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፦ «በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ» ዘፍ 4፤12። ይህ ቃል በዘመናችን ያለ ዓላማ በሕይወት ጎዳና የሚንከራተቱ ብዙ ሰዎችን ይገልጣል።
  ምንም እንኳን የዛሬ ኑሯችን የትናንት ውጤት ቢሆንም፤ የትናንት ኑሯችን ግን የዛሬ እስረኞች ሊያደርገን አይገባም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓላማ ባለፈው ሕይወትህ የሚወሰን አይደለም። እግዚአብሔር ሙሴ የተባለውን ሰው ገዳይ የነበረ ወደ ሕዝብ መሪነት፤ ጌዴዎን የተባለው ፈሪ ደግሞ ወደ ደፋር ጀግና ለውጧቸዋል። በአንተ ቀሪ ሕይወትም እንዲሁ አስደናቂ ነገሮችን ሊያደርግ ይችላል። እግዚአብሔር ለሰዎች አዲስ የሕይወት ጅማሬ በመስጠት የተካነ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል። «መተላለፉ የተከደነለት፤ ኃጢአቱም የተሸነፈችለት እንዴት ብሩክ ነው» መዝ 32፤1

2/ ብዙ ሰዎች በቂምና በቁጣ ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ደረሰብን የሚሉትን ጉዳት ከማስወገድ ይልቅ አቅፈውት ይኖራሉ። የጉዳታቸውን ስቃይ በይቅርታ ከማስወገድ ይልቅ በመደጋገም ያብሰለስሉታል። አንዳንዶቹ ደግሞ ዝም በማለት ንዴታቸውን ውስጣቸውን  «አምቀው» ይይዙታል። የቀሩት ደግሞ የታመቀ ቁጣቸውን «በማፈንዳት» በሌሎች ላይ ያምባርቃሉ። እነዚህ ሁሉ አጸፋዎች ጤናማ ያልሆኑ የማይጠቅሙ ናቸው።
  የአንተ ቂም መያዝ፤ ቂም በያዝክበት ሰው ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ይበልጥ የሚጎዳው አንተን ነው። የጎዳህ ወይም ያስቀየመህ ሰው ድርጊቱን ረስቶ የራሱን ኑሮ እየመራ ይሆናል፤ አንተ ግን ያለፈውን ቂም አምቀህ በመያዝ በብስጭት ትብሰለሰላለህ።
 ልብ በል! ከዚህ በፊት የጎዱህ ሰዎች አልጥል ባልከው የገዛ ቂምህ ካልሆነ በቀር እየጎዱህ ሊኖሩ አይችሉም። ያለፈው ነገርህ አልፏል። ማንም ሊቀይረው አይችልም። በመራርነትህ ራስህን ብቻ ነው የምትጎዳው። በቃ ለራስህ ስትል ካለፈው ተማርና ተወው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ «ሞኙን ሰው ብስጭት ይገድለዋል፤ ቂሉንም ቅናት ያጠፋዋል» ኢዮብ 5፤2

3/ ብዙ ሰዎች በፍርሃት ይመራሉ።

   እንዲህ ላሉ ሰዎች የሥጋታቸው ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉት ነገሮች በሕይወታቸው ያሳለፉት አስፈሪ ጉዳት በእውነት ላይ ያልተመሠረተ ምኞትና ጉጉት፤ ቁጥጥር ባለበት ቤተሰብ ውስጥ ማደግ፤ ወይም በተፈጥሮ የመጣ ፍርሃት ያለባቸው ይሆኑ ይሆናል። ምክንያቱም ምንም ሆነ ምን በፍርሃት የሚኖሩ ሰዎች ድፍረት ከማጣታቸው የተነሳ ሁኔታዎችን ስለማይጋፈጡ ብዙ እድሎች ያመልጧቸዋል። ፍርሃትን በድፍረት ከማሸነፍ ይልቅ ችግር ካለበት ሁኔታ መሸሽንና ባሉበት ሁኔታ ውስጥ መቆየትን ይመርጣሉ።
ፍርሃት እግዚአብሔር ያቀደልህን እንዳትሆን የሚያደርግህና እራስህን ያስገባህበት እስር ቤት ነው። በፍቅርና በእምነት መሣሪያነት ልትጋፈጠው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «በፍቅር ፍርሃት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሃት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።

4/ ብዙ ሰዎች ለመበልጸግ ባላቸው ምኞት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉት ሰዎች የሕይወታቸው ዋና ግብ ሀብት ማግኘት ነው። እንዲህ ያለው ሁልጊዜ ሀብት የመፈለግ ግፊት የሚመነጨው ብዙ ሀብት ሲኖረኝ ይበልጥ ደስተኛ፤ ይበልጥ ታዋቂና ዋስትና ያለኝ እሆናለሁ ከሚል የተሳሳተ አመለካከት ነው። እነዚህ ሦስቱም አስተሳሰቦች ስህተት ናቸው። ሀብት ሊያስገኝ የሚችለው ጊዜያዊ ደስታን ነው። ምክንያቱም ቁሳዊ ነገሮች ስለማይለወጡ ያሰለቹናል። በመሆኑም አዳዲስ ትልልቅና የተሻሉ ነገሮችን እንደገና እንፈልጋለን።
   ብዙ ሀብት ካለኝ ይበልጥ የተከበርኩና ተፈላጊ ሰው እሆናለሁ የሚልና የማይጨበጥ እምነትም አለ። እኛ እራሳችንን የተመንበት ዋጋ ከትክክለኛ ዋጋችን ጋር ተመሳሳይ አይደሉም። ዋጋህ አንተ አሉኝ ከምትላቸው ውድ ነገሮች አይወሰንም። በሕይወት እጅግ ዋጋ ያላቸው ቁሳዊ ነገሮች እንዳልሆኑ እግዚአብሔርም ይነግረናል።
  ስለ ገንዘብ በጣም የተለመደው የማይጨበጥ እምነት ብዙ ገንዘብ ካለኝ በሁሉ ነገር ዋስትናዬ በጣም የተጠበቀ ይሆናል የሚለው ነው። አይሆንም! በተለያዩና ከአቅም በላይ በሆኑ ምክንያቶች ሀብት ወይም ገንዘብ በቅጽበት ይጠፋል። እውነተኛ ድነት ወይም ዋስትና የምታገኘው ፈጽሞ ማንም ሊወስድብህ ከማይቻለው ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ካለህ ግንኙነት ነው።

5/ ብዙ ሰዎች በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት በመፈለግ ማንነት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ወላጆቻቸው ወይ ልጆቻቸው  ወይ ደግሞ አስተማሪዎቻቸው አለዚያም ሌሎች ወዳጆቻቸው ከእነርሱ የሚጠብቁትን ነገር ለማሟላት የሚያደርጉት ጥረት ሕይወታቸውን እንዲቆጣጠር ይፈቅዳሉ። አንዳንድ ሰዎች ከጎለመሱ በኋላም እንኳን ለማስደሰት አስቸጋሪ በሆኑ ወላጆቻቸው ተቀባይነትን ለማግኘት ይፈልጋሉ። ሌሎች ደግሞ ሰዎች ስለ እነርሱ የሚያስቡት ነገር እያስጨነቃቸው በእኩዮቻቸው ተጽእኖ ይመራሉ። የሚያሳዝነው  ግን ብዙዎችን ለማስደሰት የሚሞክሩ ሰዎች በሂደቱ ራሳቸውን ያጣሉ።
ለስኬት የሚያበቁ ቁልፍ ነገሮችን በሙሉ ባላውቅም ለውድቀት የሚያበቃው ዋነኛ፤ ነገር ግን ሁሉን ለማስደሰት መሞከር ነው። በሌሎች አስተሳሰብ መመራት እግዚአብሔር ለሕይወትህ ያለውን ዓላማ እንድትስት የሚያደርግህ መንገድ ነው። አላስፈላጊ ጭንቀት፤ እርካታ ያጣ ሕይወት ጥቅም ላይ ያላዋልከው ችሎታና ሌሎች ብዙ ነገሮች ሕይወትህን ሊያሸከረክሩት ይችላሉ። ሁሉም ግን የትም የማያደርሱ ናቸው።

ማጠቃለያ፤

ከላይ የተዘረዘሩትን አስወግደህ በዚህ ምድር ላይ የምትኖርበትን ዓላማ ያወቅህ ከሆንህ፤
1/ ኑሮህን እያጨናነቅህ አትመራውም።
2/ ትኩረት ማድረግ የሚገባህን ለይተህ ታውቃለህ።
3/ ለዓላማህ ትጋት ትቆማለህ።
4/ ለዘላለም ሕይወት ዋጋ ትሰጣለህ።
5/ የዚህ ዓለም መሪህ፤ አሳብህ ወይም የሌሎች ጫና ሳይሆን እግዚአብሔር ብቻ እንዲሆን ትፈቅዳለህ።


ስለሆነም በዚህ ምድር ላይ የምትኖረው ለምን እንደሆነ አስቀድመህ እወቅ! የምትኖረው እንደሰው በልተህና ጠጥተህ ቀንና ሌሊትን በማንነትህ ላይ እያፈራረቅህ ለመኖር አይደለም። ይህንንማ ሌሎች እንስሳትም ያደርጉታል። አንተ ግን በእግዚአብሔር ዓላማ የተፈጠርክ፤ ለእግዚአብሔር ዓላማ የተሰራህ ነህና በዚህ ዓላማ ላይ ቆመህ መገኘት አለብህ!

በዚህ ምድር ላይ የተፈጠረከው ለየትኛው ዓላማ እንደሆነ ታውቃለህ? እርምጃህን እየወሰንክ ያለኸውስ እንዴት ነው?

Wednesday, June 4, 2014

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ችግር፤ የአንድ ጤናማ ሰው የጤንነት መስተጓጎልን ይመስላል!


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚገጥሟት ፈተናዎች ሁሉ ከውስጧ እንደሚነሳው ፈተና የሚከፋ የለም። ቤተ ክርስቲያኒቱ የኢኮኖሚ አቅሟ እያደገና ውጫዊው ተግዳሮቶቿ እየገዘፉ በመጡ ቁጥር የውስጥ ፈተናዎቿ መቀነስ ሲገባቸው በተቃራኒው እንደአዲስ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ መከራዋ ገዝፎ መልህቅ መጣያ ወደብ እንዳጣች መርከብ በእስራ ምእቱ የአስተዳደር እክል የባህር ማእበል እየተናጠች ትገኛለች። ይህንን ውስጣዊ ፈተና በቅድሚያ አትኩሮ የሚመለከት ዓይን የሌለው ማንም ቢሆን ውጫዊ ተግዳሮቶቿን ለመመከት የሚያስችል አቅም በምንም ተአምር ሊኖረው አይችልም። ስለሆነም ውስጣዊ ፈተናዎቿን ለይቶ በማስቀመጥ ለመፍትሄውም መንገድ ማስቀመጥ ተገቢ ይሆናል። በዚሁ መሠረት ተለይተው መቀመጥ የሚገባቸውን አንኳር ችግሮች እንደታየን መጠን ለማስቀመጥ ወደድን።

ዋና ዋና ችግሮቿ፤

1/ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ፤

2/ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ፤


3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤


በዋናነት የሚቀመጡ ናቸው ብለን እንገምታለን። ይህ ማለት አጠቃላይ ችግሮች እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት ሳይሆን ዘርፈ ብዙ ችግሮቿ መነሻ የሚያደርጉት እነዚህ ሦስት ዐበይት የአንድ ሰው የሕይወት እስትንፋስን የማግኘት ያህል ህልውና ያላቸው ነጥቦች ናቸው የሚል እምነት አለን።
አንድ ሰው ሕልውና አለው የሚያሰኘው ነፍስና ሥጋው ሲዋሃድ ነው። ሥጋውም ሕይወት አለው የሚባለው አእምሮው፤ አጥንትና ጅማት ከውስጥ ሕዋሱ ጋር ተገቢ ሥራውን ማከናወን ሲችል መሆኑ ይታወቃል። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሕይወት እንዳለው ሰው ለመቁጠር የሚያስችለን የቁመና መለኪያችን ዋና ዋና ችግሮች ከላይ በሦስት ልየታ ያስቀመጥናቸው ነጥቦች ናቸው። እንዴት? የሚለውን ቀጥለን እንመልከት።

1/ «ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በመንፈስ፤ በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ» የሚለው የጉድለት ነጥብ የአንድን ሰው የአእምሮ አስተሳሰብ ይወክላል። ሰውን ከሌላው እንስሳ የሚለየው ይህ አእምሮና ከአእምሮው የተያያዘው የጀርባው አጥንት በሚያስተላልፉት ኅብለ ሰረሰራዊ መዋቅር የተነሳ ነው። አእምሮ ካልሰራ ሰው ሊያሰኝ የሚችለውን የማንነት መገለጫዎችን ለመሥራት አይችልም። ስለዚህ በዚህ ደረጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአእምሮ ማዕርግ የተቀመጠው «ቅዱስ ሲኖዶስ» የሚባለው ክፍል ነው። ይህ ላዕላይ መዋቅር ህልውና እንዳለውና ምሉዕ ሰው ሊሰራ እንደሚገባው እንደባለ አእምሮ መስራት ካልቻለ ሌላው የሰውነት ክፍል በተገቢው መንገድ ሊሰራ አይችልም። ይህ የአንድ ጤናማ ሰው ዋና ማዕከል የሆነው አእምሮ በዚህ ሰዓት በተገቢው መንገድ እየሰራ አይደለም። ስለዚህ አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን እክል ገጥሟታል ማለት ነው። እክሎቹ በምን በምን ይገለጻሉ? የሚለውን ጥያቄ በሌላ ጽሁፍ እንመለስበታለን። በጥቅሉ ግን እዚህ ላይ ማስገንዘብ የምንፈልገው ነገር አንድ ጤናማ ሰው እንዳለው አእምሮ መስራት ያለመቻል ችግሮች ነጸብራቅ የሚመሰለው «ቅዱስ ሲኖዶስ» ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ አለመቻሉና የመንፈሳዊነት ብቃት፤ የእውቀት፤ የልምድና የችሎታ ጉድለት ስለሚታይበት የቤተ ክርስቲያኒቱ አእምሮ ችግር ላይ መሆኑን እንረዳለን ማለት ነው። አእምሮ ካልሰራ፤ ሰው ጤናማ ሊሆን አይችልም። ይህ አእምሮና የኅብለ ሰረሰር መዋቅሩ የሚታከመው እንዴት ነው? ጤናማ ካልሆነ ቤተ ክርስቲያን ታማለች ማለት ነው።

2/  «የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ» የሚለው ነጥብ ምሳሌነቱን ወስደን ለአንድ እንደ ባለአእምሮ ጤናማ ሰው ግዘፈ አካል ብንወስድና ብንተረጉመው የሰውየውን ሥጋ የውስጥ አካሎቹን ያሳየናል። ሕግ፤ ደንብ፤ መመሪያና ሌሎች የማስፈጸሚያ ስልቶች ማለት «ልብ፤ ኩላሊት፤ ጉበት ወዘተ» ውስጣዊ የዝውውር ሕዋሳትን ይወክላል። ጤናማ አእምሮ የሌለው ሰው ካለበት ችግር በተጨማሪ ከእነዚህ ውስጣዊ አካላቱ ውስጥ በአንዱ ላይ ሌላ እክል ካለበት የሕመሙን መጠን የከፋ ያደርገዋል። ስለዚህ ሲኖዶሱ እንደባለ አእምሮ ፤ አእምሮውን ማሠራት አለመቻሉ እንዳለ ሆኖ በላይ የሰው ልጅ የሕልውና ክፍሎቹ እንደሆኑት የውስጥ አካላቱ ተጨማሪ እክል ዓይነት የሕግ፤ የደንብ፤ የመመሪያ ወይም የማስፈጸሚያ ስልቶች ዓይነትና መጠን ተገቢ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚያስችል ካልሆነ በሽታው አደገኛ ሁኔታ ውስጥ መሆኑን ለመረዳት አይከብድም። ከአእምሮው ላይ በተጨማሪ ከውስጥ ክፍሎቹ ባንዱ ላይ ችግር የገጠመውን አንድ ሰው እስኪ በዓይነ ልቡናዎ ይሳሉና ይመልከቱ! እጅግ አሳዛኝና አስጊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝ ለመረዳት የሚከብድዎ አይመስለንም። ቤተ ክርስቲያን አእምሮውን በታመመ አመራር ስር መሆኗ ሳያንስ ስራዋን በተገቢውን መንገድ የሚያስኬድላት የውስጥ አካላቷን መጠበቂያ ማዕቀፍ አለመኖሩ የችግሯን ውስብስብነት የሚያሳይ ይሆናል።

3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤ የሚለውን ደግሞ የአንድ ምሉዕ ሰው ወሳኝ የክፍል እንቅስቃሴ ምሳሌያዊ መገለጫ አድርገን ብንወስደው  ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳን ይወክልልናል። ሰውየው ግዘፍ እንዲነሳ የሚያደርጉት፤ እንቅስቃሴውን የሚወስኑትና የዑደት ዝውውሩን የሚያገናኙት እነዚህ ዋና የሰውነት ክፍሎቹ ናቸው። ቤተ ክርስቲያን ስንል የክርስቶስ ጉባዔ ምዕመናን ማለታችን እንደመሆኑ መጠን ለቤተ ክርስቲያን ኅልውና ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳ ሆኖ ያስተሳሰረው ይህ የመዘወሪያ አካል ንጹህ፤ ያልተበከለ፤ ያልተጣመመና ጤናማ የህንጻ ክፍል ካልሆነ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ጤናማ ልትሆን በጭራሽ አትችልም። በነዚህ መሠረቶች ላይ የቆመው አካላዊ ህልውና የዝውውር ዑደቱ ከፈጣሪው በተቸረውና እፍ በተባለበት የሕይወት እስትንፋሱ በኩል አምላኩን በተገቢው ሊያመሰግን አለመቻሉ ጉባዔው የሚታወክ፤ የሚታመስ፤ በወሬ በሽታ የተጠመደ ይሆናል። በእድሜው መኖር በመቻሉና ነፍስያው አለመለየቷ ብቻውን አንድን ሰው ሕያው ሰው አያሰኘውም። በመንፈሱ የሞተ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ የለውም።
«በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና» ሮሜ 8፤14
በዚህም የተነሳ ጉባዔ አክሌሲያ እንደሆነ የሚታሰበው ትውልድ በልምድ፤ በባህል፤ በትውፊት ገመድ ተጠፍንጎ ከወንጌል እውነት ሳይታረቅና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በልቡናው ሰሌዳ ላይ ሳይጽፍ ነገር ግን አንገቱ ላይ የመስቀልና ምስል አንጠልጥሎ የሚሳደብ፤ የሚዋሽ፤ የሚሰክር፤ የሚያጨስ፤የሚያመነዝር፤ የሚሰርቅ፤ እምነት የማይጣልበት የባህል እምነት ተከታይ ሆኖ የሚታየው የእውነትን ወንጌል በመጋት አሳድጎ የቃሉን አጥንት መጋጥ ወደሚያስችል ሰውነት ማድረስ ስላልተቻለ ነው። በእምነት ሳይሆን በሃይማኖት የኖረውም በልምድ እንጂ እውነት ስለገባው አይደለም።  «እውነት ባለበት በዚያ አርነት አለ» የተባለው አንገት ላይ መስቀል አንጠልጥሎ ነገር ግን ነጻ እንዳልወጣ ሰው የሥጋ ሥራ የሚሰራ ሰው ማለት አይደለም። ስለዚህ ትውልዱ በወንጌል ነጻ የመሆን የእውነት ቃል ተኮትኩቶና በቀደምት አባቶቹ አስተምህሮ ታንጾ ባለመኖሩ አርነት ያልወጣ ሰው የሚያደርገውን የሥጋ ሥራ እየፈጸመ  በስም ክርስቲያን እየተሰኘ የባህልና የልምድ ተከታይ ሆኖ እንዲኖር ተፈርዶበታል።  ከልምድና ከባህል መንፈስ ነጻ መውጣት አለበት።
2ኛ ቆሮንቶስ 3፥17  «ጌታ ግን መንፈስ ነው፤ የጌታም መንፈስ ባለበት በዚያ አርነት አለ»

ማጠቃለያ፤

አንድ ሰው ጤናማ የሚባለው አእምሮው፤ ኅብለ ሰረሰሩ፤ የውስጥ አካላቶቹ፤ ደም፤ ስጋ፤ አጥንትና ጅማቱ ተዋሕደው በጤንነት ሲገኙ ነው። ምሉዕ ሰው ሆኖ ሕይወት ያለው መንፈሳዊ ጤንነቱ የሚጠበቀው ደግሞ የነፍስያው ራስ የሆነው ፈጣሪውን ሲያውቅና በተገቢው መንገድ ሲያመልክ ብቻ ነው። ከእነዚህ ባንዱ ጉድለት ቢገኝ አደጋ ውስጥ መሆኑ እርግጥ ነው። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንን የሕይወት ኅልውና ስንመለከት ጤናማ ሁኔታ ውስጥ እንዳይደለች ከላይ ያነሳናቸው ነጥቦች ያስረዱናል። የተከታዮቿ ቁጥር ወደታች የማሽቆልቆሉ ምክንያት የበሽታውን ደረጃ ያሳየናል። የአስተዳደር ሰላም አለመኖር፤ የነበራት ክብርና ተደማጭነት ማነሱም የገጠማት የህመም ደረጃ አደገኛ መሆኑን ያስረዳናል። የመከፈፋሏ መነሻ፤ የመከባበር ድቀት፤ የነውር ገመና ማደግ፤ ዋልጌነት፤ የብክነትና የዝርፊያው የትየሌለነት የበሽታዋ ደረጃ ምን ያህል እንደገዘፈ ለማወቅ ምርምር አይጠይቀንም። ቤተ ክርስቲያኒቱ ያልጠፋችውም ከእግዚአብሔር ታጋሽነትና ለንስሐ የሚሆን እድሜ ከመስጠት አምላካዊ ባሕርይው የተነሳ ይመስለናል። እንደሚገባን ሆነን መልካም ፍሬ ካላፈራን ግን መቆረጣችን አይቀርም።
የፈለገውን ያህል ተኩራርተን የቀደመችቱ መንገድ እያልን ብንደሰኩር ከእግዚአብሔር አስቀድሞ የተቀበልነውንና የሰማውን ዛሬ ይዘን በተግባር ካልተገኘን ከያዝነው የቁልቁለት መንገድ አያድነንም።  በአንድ ወቅት በትንሹ እስያ ለነበረችውና በተመሳሳይ የቁልቁሊት መንገድ ላይ ለነበረችው ለሰርዴስ ቤተ ክርስቲያን በዮሐንስ በኩል መልእክት ደርሷት ነበር።  ነገር ግን መስማት ስላልቻለች እየወረደች ካለበት የቁልቁሊት መንገድ ወጥታ፤ ስህተቶቿን አርማ፤ በእውነት የጌታዋ መንገድ ላይ ለመጓዝ የሚያስችላትን የንስሐ እድሜ ባለመጠቀሟ ከ500 ዓመት በኋላ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመጥፋት በቅታለች። በፍርስራሾቿ ላይም የእስልምና አዛን የሚያስተጋባባት የታሪክ ቤተ ክርስቲያን ሆናለች። ከመሆኗ በፊት የተነገራት ቃል ይህ ነበር።
«እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም» ዮሐ 3፤3
( በቀጣይ ጽሁፋችን  ዝርዝር ነገሮችን ለማየት እንሞክራለን)

Thursday, May 29, 2014

በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነ ጳጳሳቱ አድማና የማኅበረ ቅዱሳን ጣልቃ ገብነት በአቡነ ማትያስ ላይም ቀጥሏል!

ከሊቃነ ጳጳሳቱ ግማሾቹ የራሳቸውን የጉባዔ ላይ የድምጽ ጡንቻ በማፈርጠም ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ከሚመስሏቸው ጋር የመቀናጀት ጠባያቸው ከምንኩስና ጀምሮ የተዋረሳቸው እንጂ ድንገት የተከሰተባቸው ዐመል አይደለም። ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ደግሞ ከዚህ ፈርጣማና  ጠንካራ የቡድን  አቅም መፍጠር ከቻሉት ጋር መለጠፍ የሚፈልጉት አንድም ብቻቸውን መዝለቅ እንደማይችሉ ስለሚያውቁ፤ በሌላ መልኩም ሊመጣ ይችላል ከሚሉት ጥቃት ራሳቸውን ለመከላከል ከመፈለግ ራስን የማዳን ዘዴ የተነሳ ነው። ጥቂቶች ቢሆኑም አንዳንዶቹ ደግሞ ያልሆነ ንትርክና ጭቅጭቅ እንዲነሳ የማይፈልጉ፤ ዝም ብለው በመመልከት ታዛቢ የሚመስሉ በእድሜ የገፉ ሲሆኑ በጣት የሚቆጠሩት ደግሞ ስለቤተክርስቲያን የሚገዳቸው ነገር ግን ድምጻቸው ብዙም የማይሰማላቸው ናቸው።
 የቡድን ኃይል መፍጠር የቻሉት አብዛኛዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት የወጣትነት ዐመል ብዙም ያልራቃቸው፤ በቂ ኃብት ማከማቸት የቻሉ፤ ለተሸከሙት ማዕርግ ሳይሆን ለስምና ለዝና የሚጨነቁ በተለይም ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ንክኪ ያላቸው ናቸው። እነዚህኞቹ ለቤተ ክርስቲያን የሚታይ፤ የሚጨበጥ፤ ለትውልድ የሚተላለፍ ቋሚ ቅርስና ሀብት መፍጠር ያልቻሉ ነገር ግን በምላስ የሰለጠኑ፤ እምቢተኝነትና ቡድንተኝነት እውቀት የሚመስላቸው ናቸው። ቤተክርስቲያን መታመስ የጀመረችው እነዚህኞቹ ቅዱስ ወደተባለው ሲኖዶስ የመቀላቀል እድል ካጋጠማቸው በኋላ ነው። ማኅበረ ቅዱሳንም ከሀገር ቤት እስከ ውጪ ሀገር ድረስ በቤተ ክርስቲያኒቱ መልክና ቁመና ስሩን የሰደደው በእነዚህኞቹ ጀርባ ታዝሎና ተንጠላጥሎ ነው።
የቀድሞውን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እግር ተወርች አስረው አላሰራ ሲሉ የነበሩት እነዚህ ቡድንተኞች ዛሬም አንድ ግንባር ፈጥረው እድሜ ካላስተማራቸው አረጋውኑ መካከል ጥቂቶቹን አሰልፈው ማኅበረ ቅዱሳንን ከጀርባቸው አቁመው ፓትርያርክ ማትያስንም በተመሳሳይ መልኩ አላሰራ፤ አላንቀሳቅስ፤ አላላውስ እያሏቸው ይገኛል። በዚህ መልኩ የት ድረስ መጓዝ እንደሚቻል ለመገመት አይከብድም። ነገር ግን «ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም» እንዲሉ አበው መላ መፈለግ ፓትርያርክ ማለት «ርእሰ አበው» ማለት እንደመሆኑ መጠን የተሰጠውን ሥልጣን ለቡድንተኞች አስረክቦ የተነገረውን የሚቀበል ተላላኪ ማለት ባለመሆኑ ሥልጣኑ ሙሉዕ መሆኑን ማመን የግድ ይሆናል። ስለዚህ በአድመኝነት፤ ለማኅበሩ ወግነው አላሰራ ለሚሉ ምን መደረግ አለበት?  ነገሮች እየጠሩ፤ የችግሩም ገፈት ከላይ ካልተወገደ በስተቀር ተለባብሶ የትም አይደረስም። ቤተ ክርስቲያንም አትድንም፤ ባለማዕርጎቹም በዘመናቸው ንስሐ አይገቡም። ስለዚህ የማያወላዳ እርምጃና ውሳኔ ያለምንም ማቅማማት መውሰድ የግድ ይላል። ጥቂት ነጥቦችን እናንሳ።
1/ ከአድመኞቹ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብዙዎቹ ቃል የገቡበትን መሃላ አፍርሰው የቤተ ክርስቲያኒቱ ተጠሪ ነን ካሉ በኋላ ደመወዝተኛ፤ አበልተኛና የጥቅሟ ተከፋይ ሲያበቁ መንፈሳዊነቱን ክደው፤ ሀብት ንብረት አፍርተው ፤ እንደዓለማውያኑ የሚሊዮን ብር ቤቶችን የገነቡ፤ በባንክ ያከማቹ ስለመሆናቸው መረጃና ማስረጃ የሚቀርብባቸው ስለሆነ በሊቀ ጳጳስነት ማዕርግ የእግዚአብሔርን መንግሥት ብቻ ለማገልገል  ብቃት የሚጎድላቸውና «ለሁለት ጌቶች መገዛት አትችሉም» ያለውን የወንጌል ቃል ያፈረሱ ስለሆነ ከያዙት ማዕርግ ተሰናብተው ወደዓለማዊ ሀብታቸው እንዲሄዱ ሊሸኙ ይገባል።
2/ ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ቃለ መሃላ ከፈጸሙበት «ኩሎ ኀደግነ» ሁሉን ትተን ተከተልንህ ካሉ በኋላ በቀጥታ ያለሰማንያ ጋብቻ በትዳር ወልደው ከብደው የሚኖሩ፤ ገሚሱም በአዲሱ የቤተሰብ ህግ እንደተመለከተው « ትዳር በሚመስል ሁኔታ አብሮ መኖር ራሱ ጋብቻ እንደተፈጸመ ይገመታል» በሚል የህግ መንፈስ መሰረት አግብተው ዓለሙም፤ ሊቀጵጵስናውም ሁሉም ሳይቀርባቸው አጣምረው የያዙ ስለሆነ በእነዚህኞቹ «ጸሊማን አርጋብ»  ላይ በቂ ማስረጃ መቅረብ ስለሚችል በማያወላዳ ውሳኔ ለሌሎች ትምህርት ሊሆን በሚችል መልኩ ለትዳራቸው ታማኝ ሆነው እንዲኖሩ በክብር መሸኘት አለባቸው።
3/ ለዚህ ጥሩ አብነትና ምሳሌ ሊሆን የሚችለው በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከዚህዓለም በሞት የተለዩት የአቡነ ሺኖዳ አስተዳደር ተጠቃሽ ነው። ሊቃነ ጳጳሳት የራሳቸውን ሀብት ማፍራት አይችሉም። መነኮሳት ከመነኮሱበት ገዳም ውጪ ሌላ ገዳም በፍጹም አይቀበላቸውም። ከገዳሙ ከወጣ ምንኩስናውን እንደተወ ይቆጠራል። በሴት የተጠረጠረ መነኩሴ በቀጥታ ተጠርቶ ይጠየቃል እንጂ እንደኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተሸፋፍኖ ያሻውን እንዲፈጽም እድል አይሰጠውም። መረጃና ማስረጃ ከቀረበበት ቀሚሱን ከታች አንስቶ፤ እስከ አንገቱ ድረስ መሃል ለመሃል በመቀስ ቀደው መቋቋሚያ ገንዘብ ሰጥተው ሕዝባዊ እንዲሆን ያሰናብቱታል። ይህ ለሌላው ትምህርት፤ ለቤተ ክርስቲያንም ክብር ይሆናል። ነገር ግን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለው ነገር በዚህ ዘመን አሳፋሪ ሆኗል። ከሊቃነ ጳጳሳቱ ትዳር የመሰረቱ ሞልተዋል። የመነኮሳት ነጋዴ መሆናቸው ሳይታወቅ ሚሊየነር ሆነዋል። ዝሙትና ስርቆት ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደነቀዝ እየበላት ነው። በዚህ መልኩ ከቀጠለች የቤተ ክርስቲያኒቱ ኅልውና አስጊ ነው። እዚህ ላይ ከነጋ ድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ መጽሐፍ ጥቂት ቃል እንዋስ። «እግዚአብሔር መንግሥታችንን፤ ቤተክርስቲያናችንን ለባዕድ አሳልፎ አይሰጣትም እያለ ሕዝባችን በስንፍና ያለሥራ ይኖራል» እውነትም ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር ከጥፋት ተከላከለን፤ ነገር ግን እኛ ለቸርነቱ የተገባውን ሥራ ሠርተን በተግባር አላሳየንም» ብለዋል ነጋድራስ በጽሁፋቸው ከዛሬ ሰማንያ ዓመት በፊት።  ይሁን እንጂ ዛሬም ከስንፍናችን ፈቀቅ አላልንም። እግዚአብሔር ራሱ ይጠብቅ ብለን እኛው ያጠፋናትን ቤተ ክርስቲያን እንደባለእዳ ትተንለታል።
4/ ማኅበረ ቅዱሳን ማነው? የማነው? ምንድነው? ብዙ የሚያጠያይቅ ጉዳይ ነው። የጠራና የማያሻማ መልስ ያስፈልገዋል። ተለባብሶ በበግ ለምድ ተሸሽጎ አይዘለቅም። ስለማኅበረ ቅዱሳን ጥብቅና የሚቆም ማንም ቢኖር የማኅበሩ አባል የመሆን መብቱ የተከበረ ነው። ነገር ግን ሊቀጳጳስ ከሆነ በኋላ ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን የሲኖዶስ አባልነት ሥልጣን ይዞ የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን አይችልም። መሆን ከፈለገ ጵጵስናውን ማስረከብ አለበት።  አንድ ሚኒስትር የኢህአዴግ ምክርቤት አባልና የሰማያዊ ፓርቲ አባል በአንድ ጊዜ መሆን አይችልም። አንዱን ይተዋል፤ ወደአንዱ ይጠጋል እንጂ። ይህንን ለማስተካከል የፓትርያርኩ ሥልጣን ምሉዕ ነው። እነዚህ በሁለት ልብ ሲኖዶሱን የሚያውኩ ጳጳሳት በህግ አግባብ ካልተወገዱ የሲኖዶስ ሕውከት ማብቂያ አይኖረውም። ስለማኅበረ ቅዱሳን የሚከራከር ሊቀጳጳስ ከሲኖዶስ አባልነቱ ወደታች ወርዶ የተራ ማኅበር ደጋፊ ከሆነ ማዕርጉን ተገፎ  በማኅበር አባልነቱ እንዲቀጥል ከሲኖዶስ ሊባረር ይገባዋል።
5/ ፓትርያርክ ማትያስ ቆምጨጭ ያለና እርምት የሚሰጥ እርምጃ ከመውሰድ ውጪ በእንደዚህ ዓይነት የአድማና የቡድን ጭቅጭቅ እየተሰላቹ የትም አይደርሱም። ሊቀጳጳስ የሚባለው ማዕርግ ሊከበር የሚችለው ራሱ ማዕርጉን የተሸከው ሰው አክብሮ፤ የሚያስከብር ሥራ ሲሰራበት ብቻ ነው። ሹመትማ ይሁዳም ከሐዋርያት አንዱ ነበር። ነገር ግን ጥፋት እንጂ ልማት አልሰራበትምና ሐዋርያ መባሉ ቀርቶ «ሰያጤ እግዚኡ» ከመባል አልዳነም። ስለዚህም ቤተ ክርስቲያንን ከመሸጥ የማይመለሱ እነዚህ አድመኞች ሊቃነ ጳጳሳት ሻጮች ቢባሉ ምንም አያስነውርም። ስም መጥቀስ አያስፈልግም እንጂ እነማን ማናቸው? ምን አደረጉ? ምንሰሩ? በደንብ ይታወቃል።
6/ ቤተ ክርስቲያንን ከውድቀት ለማዳን፤ ማዕርጋት ዋጋና ክብር እንዲኖራቸው ለማድረግ ሲባል ያልተፈለገ ነገር ግን አስገዳጅ እርምጃ እስከመውሰድ የሚዘልቅ ክስተት መፈጠሩ አይቀርም።  ፓትርያርክ ከሆኑ በኋላ ከሚቆጠቁጠው የመንፈሳዊ ኅሊና ቁጭትና ከታሪክ ወቀሳ ለመዳን መስራት የሚገባውን ሁሉ ካልሰሩበት ማዕርጉን ተሸክሞ መቀመጥ በቤተክርስቲያን ውድቀት ላይ መተባበር በመሆኑ ሹመቱን አስረክቦ የራስን ነጻነት ማወጅ የተሻለ ነው።
በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነጳጳሳቱ አድማና የማኅበሩ ሴራ በአቡነ ማትያስም ላይ የሚቀጥለው  እስከመቼ ነው?
 አቡነ ማትያስ አርፈው የማኅበሩ አባል ሊቀ ጳጳስ ሌላ ፓትርያርክ እስኪሆን ድረስ ይህ ውጊያ አያቆምም።

Thursday, May 22, 2014

ግዝት(ውግዘት)…ኑፋቄ….መናፍቅነት…ግዝት-ዘበከንቱ… እና ወፈ-ገዝት መሆን!


 ( በአማን ነጸረ )
1. ግዝት(ውግዘት)፡ ማለት አንድ ምዕመን(አማኝ) በአፉ ክርስቲያን ነኝ ቢልም በተግባር ከሃይማኖት ወጥቶ ከበጎ ምግባር አድጦ(ተዛንፎ) ሲገኝ ከማኅበረ ምዕመናን እንዲለይ በስልጣነ-ክህነት የሚፈጸም መንፈሳዊ ቅጣት ነው፡፡
2. የውግዘት ዓላማ፡(ሀ)ቤ/ክ እንዳትረክስ፣(ለ)ኑፋቄው ወደ ሌሎች እንዳይዛመት፣(ሐ)ተወጋዡ በንስሐ እንዲመለስ እድል ለመስጠት ነው፡፡
3. የውግዘት ቅድመ-ሁኔታዎች፡(ሀ)ተጠርጣሪው ከሃይማኖት እና/ወይም ከበጎ ምግባር መውጣቱን ማረጋገጥ፣(ለ)ከጥፋቱ/ከክህደቱ እንዲመለስ ደጋግሞ መገሰጽና መምከር፣(ሐ)ተመክሮ ካልተመለሰ በስልጣነ-ክህነት አውግዞ መለየት፣(4)ውግዘቱ እንደጥሰቱ ዓይነት ከማዕረግ ዝቅ ማድረግ ወይም ስመ-ክርስትናን ነጥቆ መለየት ሊሆን ይችላል፡፡ከዚህ በኋላ ድርጊቱ-ኑፋቄ ተወጋዡም-መናፍቅ ይባላሉ፡፡በነገራችን ላይ ምንፍቅና የሚል ቃል በየመጻህፍቱ አላየንም፡፡በግእዙ ኑፋቄ ነው የሚባለው፡፡በአማርኛ መናፍቅነት፡፡
4. ግዝት-ዘበከንቱ እና ወፈ-ገዝት መሆን፡ ከላይ ያሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ያላሟላ ግዝት ግዝት-ዘበከንቱ ሲባል ገዛቹም ወፈ-ገዝት ይባላል፡፡ነገር ግን ተጠርጣሪው በግልጽ የተወገዘ ሃይማኖትንና ምግባርን ሲያራምድ ያገኘነው እንደሆነ መናፍቅ ብንለው ፍርድ የለብንም፡፡
5. ከንቱ እና ከንቱ አንድ ወገን ብለን ስለመርገም ዘበከንቱም እንናገር፡ ሀቅ ላይ ያልተመሰረተና የሚረገመውን ሰው ህሊና የመውቀስ አቅም የሌለው ከንቱ እርግማን በመጽሐፈ ምሳሌ 26 ቁ 2 እንደተገለጸው….እንደሚተላለፍ ድንቢጥ፣ወዲያና ወዲህም እንደሚበር ጨረባ እንዲሁም ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም፡፡ፍትሐ ነገስቱም በአንቀጽ 11 እንዲህ አይነቱን ረጋሚ “ወኩሎ ዘይረግም ይረግም ነፍሶ” ይለዋል::
ምንጭ፡ (1) መርሐጽድቅ ባህለ ሃይማኖት በ1988 ዓ.ም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የታተመ ገጽ 157 እስከ 161 ፣ (2)የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ-237፣ (3) ጥቅሶች፡ ማቴ 18 ቁ 15-18፣2ተሰ 3ቁ14፣ቲቶ 3 ቁ 11፣1ጢሞ 1ቁ 19፣2ጢሞ 2 ቁ 17፣1ቆሮ 5 ቁ 5፣2ቆሮ 2 ቁ 6
መነሻ፡ በ40 ቀን ያገኘነውን ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ባልተሰጠ ስልጣነ-ክህነት ሊነጥቁ የሚሞክሩ ወፈ-ገዝት ወንድሞቻችን!!

Sunday, May 18, 2014

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል የጉባዔ ተግዳሮት እንደሚገጥማቸው ይጠበቃል!





የዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ከመቼውም ጊዜ የተሻለ ምስጢራዊነቱን የጠበቀ እንዲሆን ተሞክሯል። ይህ ማለት ግን ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰወረ የአጀንዳ፤ የውይይት ሂደትና የውሳኔ እልባት ነበረ ማለት አይደለም። ምስጢራዊነቱ  የቤት ልጅ ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ለአብዛኛዎቻችን እንዲጠበቅ ያስፈለገበት ዋና ምክንያት በቅዱስ ፓትርያርኩ በተሰጠ የቅድመ ጉባዔ መመሪያ ቢሆንም በአንጻሩ ማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱም ምስጢራዊነቱ ቢጠበቅ የኅልውና ጉዳይ የባቄላ ወፍጮ እንዳይሆን ከመፈለግ የተነሳ እንደሆነ ውስጥ አዋቂ ምንጮች ግምታቸውን ያስቀምጣሉ። ምክንያቱም የዘንድሮው የጉባዔ ሂደት የማኅበሩን የሁለት ዐሥርተ ዓመታት ጉዞ ወሳኝ በሆነ መልኩ የሚመለከት ጉዳይ ከመኖሩ የተነሳ ምስጢራዊነቱ እንዲጠበቅ አስፈልጓልም በማለት ያክላሉ።
ቅዱስ ፓትርያርኩን ከገጠሟቸው ተግዳሮቶች አንዱ «ማኅበረ ቅዱሳን በምን ሕግና መንገድ ሊተዳደር ይገባዋል» በሚለው አንገብጋቢ ጉዳይ ላይና አዳዲስ ሊሾሙ በሚችሉ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ላይ የተያዘው የሁለት ወገን ሰልፍ ምክንያት እንደሆነ ይነገራል።
አንዱ ሰልፍ  በቅዱስ ፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል የሚነሳው ሃሳብ የማኅበሩ እንቅስቃሴ ከሰላምና ከፍቅር ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ የምትታወክበትና ያልተፈለገ እሰጥ አገባ ውስጥ የምትዘፈቅበት ምክንያት ስለበዛ እንደማኅበር መቆየት አለበት የሚያሰኝ አመክንዮ ባይኖርም እንኳን እንዲኖር ካስፈለገ አቅሙንና ደረጃውን አውቆ፤ እንቅስቃሴው ከአቅሙ ጋር ተገናዝቦ በተወሰነ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ ኅልው እንዲሆን የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣለት ጥብቅ ፍላጎት ያላቸው መሆኑ ነው።
ሁለተኛው ሰልፍ ደግሞ የማኅበሩ አባላት በሆኑ ሊቃነ ጳጳሳትና ማኅበሩ ራሱ በስለላ መዋቅሩ በኩል በሚያካሂደው የሩጫ ዘመቻ የተነሳ ያለው ሰልፍ ሲሆን ይህም ሲከናወን የቆየውን ስልት ማስቀጠል የሚያችል ልዩ መብት በራሱ ሰዎች በኩል አርቅቆ ለማስጸደቅ መቻል ነው። ይኼውም ማኅበሩ እስካሁን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር በተመሳሳይ የዘመቻ ስልት አፈንግጦ የወጣበትና በሥራ አስኪያጁ ስር እንዲቆይና የራሱን ኅልውና ለማቆየት አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣ የተሰጠውን የቆይታ ጊዜ ባለመጠቀሙ በዚህ ጉባዔ ላይ በሚፈልገው የጊዜ መግዢያ መንገድ የመቋጨት ዓላማ እንዳለው ከውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን ለማወቅ ተችሏል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ጉዳይ የአዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሲሆን ማኅበሩና ታዛዥ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት በሁለት መንገድ እየተሰናሰለ ለማስኬድ እየተሞከረ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ። ይኼውም በእነሱ ምርጫና አጽዳቂነት ተመልምለው ለሲኖዶስ መቅረብ የሚገባቸውን የመለየት ስራ ያከናወኑ ሲሆን በፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል ሊቀርቡ የሚችሉ ነገር ግን ለማኅበሩ ኅልውና ስጋት ሊሆኑ እንደሚችሉ ቅድመ ግንዛቤ የተያዘባቸውን አስቀድሞ ውድቅ የማድረግ ስልት መያዙም ሌላኛው እቅድ ስለመሆኑም ይነገራል። በተለይም እንደአባ ሠረቀ ብርሃን ወልደሳሙኤልና መሰል ተቃናቃኞች በምንም ዓይነት መንገድ ቢሆን ከእጩዎች ዝርዝር ውስጥ መግባት እንደሌለባቸው በማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል በጥቁር መዝገብ ውስጥ የሰፈሩ ናቸው። በሌላ መልኩም ንቡረ እድ አባ ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ በሥራ ችሎታና ሙስናን በመዋጋት ጠንካራ ስለመሆናቸው ጥያቄ ባያስነሳም በማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ የማያጎበድዱ፤ ለሹመት ደጅ የማይጠኑና እጅ መንሻ  የማያቀርቡ በመሆናቸው ለእጩነት ችላ ከተባሉት መካከል ናቸው።  
በፓትርያርኩ በኩል ሊቀርቡ የሚችሉና ማኅበረ ቅዱሳን ዓይናቸውን ማየት የማይፈልጋቸው እጩዎችን ላለመቀበል በደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በኩል በሁለተኛነት የተያዘው ዘዴ  ደግሞ «እኛ ምን ሠርተን ነው፤ የአዳዲስ እጩዎች ምርጫ ለማጽደቅ እንዲህ የሚያጣድፈን ምክንያት የለም!»  የሚል ሲሆን ጊዜውን በማዘግየትና የምርጫውን በር በመዝጋት ያልፈለጓቸውን ሰዎችን ለማስቀረት እንደስልት መያዙ ነው።
በሌላ መልኩም ከፓትርያርኩ ስር የማይጠፉ ለዓመታት የጵጵስና ስካር እያንገዳገደ ያቆያቸው አንዳንድ መነኮሳት ሰርገው ለመግባት የሚያደርጉት ሩጫ ሳይጠቀስ መታለፍ የሌለበት ሆኖ ተገኝቷል። ለዚህ ማዕርግ ብቁ ስለመሆናቸው የምዕመናንና ምዕመናት ምስክርነት የሌላቸው እንዲሁም ያለደረጃቸው ካቴድራል የተሰጣቸው ጠልፎ በላዎችና ተሸክመው የመጡትን ዶላር መመንዘር የማይሰለቻቸው ደግሞ ጺማቸውን እየላጉ ጳጳስ ለመሆን ማስፈሰፋቸው ትኩረት የሚያሻው ነገር ነው።  ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በአንድ በኩል ሠርተው ማሰራት የሚችሉትን ወደእጩነት እንዳይቀርቡ በር በመዝጋት ላይ ሲተጉ በሌላ በኩል ደግሞ በጓሮ በር መግባት የሚፈልጉ እንደቅድስት ሥላሴው ጎረምሳ አስተዳዳሪና መሰል የሹመት ስካር የሚያንገዳግዳቸው የችሎታ ባዶዎች አሰፍስፈው መገኘታቸው ጉዳዩን አስቸጋሪም፤ አሳዛኝም፤ አሳፋሪም ያደርገዋል።

ስለዚህ ፓትርያርኩ ተግዳሮት ገጥሟቸዋል ስንል በእነዚህ ውስብስብ እንቅስቃሴዎች የተነሳ ሲሆን መወሰድ የሚገባው ርምጃም ትኩረት የሚያሻው፤ ካለፈ በኋላ የማይቆጭ መሆን ስለሚገባው አበክረን ማሳሰብ እንወዳለን።

አጭር ነገር ግን የትኩረት አቅጣጫን የሚለውጡ ግንዛቤዎች፤

1/ ማኅበሩ እንደፈለገና እንዳሻው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚናኝ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ማኅበሩ ማኅበር እንጂ የቅዱስ ሲኖዶስ ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤት ወይም የቤተ ክህነቱ የመምሪያ አካል አይደለም። ሲኖዶስ ስለአንድ ማኅበር ከዓመት ዓመት በአጀንዳ የሚነጋገርበት ምክንያት የለም። ስለዚህ፤
  ሀ/ ቢቻል ራሱን ችሎ ሥልጣን ባለው አካል ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ እንደማኅበር በሀገሪቱ ሕግ እንዲንቀሳቀስ  በነጻ መተው አለበት እንጂ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶለት በራሱ እጅ እየተለበለበ መቀጠል የለበትም።  «ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ» ያቃተው ለምንድነው? ስለዚህ በዚህ ጉባዔ ፓትርያርኩ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እልባት እንዲያገኝ ማድረግ አለባቸው። በቀጠሮ የነፍስ መግዢያ ጊዜ የሚጠይቁ አፍራሾችን መዋጋት አለባቸው።
 ለ/ ማኅበሩ በኛው ስር ሆኖ ቢሰራ ውጤታማ መሆን ይችላል የሚል ግምት ካለ ( ከታየው ተሞክሮ የተነሳ የተሳሳተ ግምት እንደሆነ ቢታወቅም) የማኅበሩን ያለፈ ታሪክ ገምግሞ ወደፊት ምን ሊሰራ ይችላል በሚል ግንዛቤ ስር ሰፊ ጥናት ተወስዶ በተገደበና በተወሰነ የመተዳደሪያ ደንብ  ተቀርጾ አቅሙን ለክቶ በመስጠት የማያዳግም መቋቻ ሊደረግበት ይገባል።
2/ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫ በተመለከተ፤ ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት የራሳቸውን የሲኖዶስ አባላት ቁጥር ከፍ የማድረግና የትኛውንም ውሳኔ በአብላጫ ድምጽ ሙሉ በሙሉ የመቆጣጠር ፖለቲካዊ ስልት ለማስፈጸም የፈለጓቸውን በጥቆማ የማቅረብ ሲሆን በዚሁ ተቃራኒ ደጋፊ ያልሆኑና ለኅልውናቸው ስጋት እንደሆኑ የሚታሰቡትን እጩዎች ደግሞ በልዩ ልዩ መንገድ የመከላከል ሁኔታ አለ። ስለዚህ ይህንን ማጤን አስፈላጊ ነው እንላለን።
3/  በሌላ መልኩም የማኅበሩንና የደጋፊዎቹን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ብቻ ሳይሆን በእጩ ምርጫው ዝርዝር ውስጥ ያልተፈለጉ ሰዎች እንዳይገቡ ማድረግ በፓትርያርኩ በኩል እጅግ ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ ነው። ስነ ምግባራቸው፤ እውቀታቸው፤ ችሎታቸው፤ የአስተዳደር ብቃታቸው፤ ተሞክሮአቸውና መንፈሳዊ ብስለታቸው ሳይታይ በብልጣብልጥ ዘዴና በገንዘብ አቀባባዮች የተጋነነ መረጃ የተነሳ ኤጲስ ቆጶስነትን ለማሸከም መሞከር ነገ ለሿሚው ኀፍረት፤ ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሸክምና ውርደትን ሊያስከትል ስለሚችል የሹመት ስካር ያጠቃቸውን የጥቅምትና የግንቦት ተስፈኞች መከላከል ትኩረት ያሻዋል።

በመጨረሻም ቅዱስ ፓትርያርኩ በማኅበሩ ዙሪያ እየያዙ የመጡት ግንዛቤና ስጋት የመሆኑን ደረጃ የመገንዘብ አቋም የሚደገፍና የሚበረታታ ነው። ቤተ ክርስቲያኒቱ ከማኅበሩ ያለኪሳራ አንዳች አላተረፈችም፤ አታተርፍምም። ማኅበሩ ግን ያለቤተክርስቲያኒቱ ከባህር የወጣ ዓሳ ነው። ስለዚህ የፓትርያርኩ ስልጣን አንድን ማኅበር ጥግ ለማስያዝ የሚያንስ አይደለም። በቤተክርስቲያኒቱ ከፍተኛው የስልጣን እርከን ላይ የተቀመጠ ፓትርያርክ ከሀገሪቱ ሕግ ጋር ተቀናጅቶ የሚያስቸግረውንና ለአስተዳደር እንቅፋት የሆነውን ክፍል በህግ አደብ ለማስያዝ የማንም ጳጳስ የጩኸት እርዳታ አስፈላጊው አይደለም።  
ያለበለዚያ በማኅበሩ ተግዳሮት እየቆሰሉ እስከሞት መቀጠል አለያም አሜን ብሎ እጅ በመስጠት ታማኝ ሆኖ የማገልገል ምርጫ ብቻ ነው ከፊት ለፊት ያለው። አቡነ ጳውሎስን እያታለለ እስከኅልፈታቸው የተዋጋቸው ማኅበር ዛሬም ውጊያውን አላቋረጠም። ግን እስከመቼ?

Tuesday, May 13, 2014

በውስጡ ቀና መንፈሳዊ አባላት መኖራቸው ብቻ የሃይማኖት ማህበር አያሰኘውም!


(ከወልደገብርኤል ስሁል)
 
የየትኛውም እምነት ተከታዮች መንፈሳዊ ህይወትና የሃይማኖት ቀኖና በሚመለከቱ ጉዳዮች ያሻቸው ማመንና መከተል ይችላሉ፤ የቄሳርን ለቄሳር የእግዚአብሄርን ለእግዚአብሄር የሚለውን መርህ አክብረው ሁለቱን ሳያደበላልቁ እስከተጓዙ ድረስ። መጋቢት 1983 “በአቡነ ደርግ” ብላቴ ላይ የተቋቋመው ማ.ቅ. ዋና ዓላማው ጠመንጃ የታጠቀ የቅዱሳን ብርጌድ ሁኖ በማርክሲዝም የተከዳውን አምባገነን መንግስት የማዳን ተልእኮ ይዞ ሲሆን፤ ይህ ካልተቻለም “የብሄራዊ እርቅ መንግስት ይመስረት” በማለት ባቋራጭ የመንግስት ስልጣን ሊጨብጡ ይቋምጡ ለነበሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህራን (ማርክሲዝም ባዶ ሜዳ ላይ ጥሏቸው በመሄዱ የቆጫቸውና የደርግ ለሞት መቃረብ “ንስሃ” ለመግባት የተገደዱ የደርግ ቀኝ እጆች) በድህረደርግ ኢትዮጵያ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ ይሆናቸው ዘንድ ተጠፍጥፎ የተሰራ ማህበር ነው። መስራቾቹም የደርግ ደህንነት ያሰባሰባቸው አንዳንድ “ምሁራን”ና “መንፈሳዊ አባቶች” ሲሆኑ በህቡእ እንዲመሩት የተሰየሙትም ከነሱ የተውጣጡ “ታላላቅ ወንድሞች” ናቸው(ለማንም ግልጽ በሆነ ምክኒያት ስማቸውን እዚህ ላይ መጥቀስ ሳያስፈልግ)። ስለዚህ መስራቾቹና ህቡእ መሪዎቹ ፖለቲከኞች ናቸው፤ የተመሰረተበት ዓላማ ደግሞ መንፈሳዊም ሃይማኖታዊም አልነበረም፤ አሁንም አይደለም። በውስጡ ቀና መንፈሳዊ አባላት መኖራቸው ብቻ የሃይማኖት ማህበር አያሰኘውም።