Wednesday, January 16, 2013

«ሐራ» ነኝ ማለትህ ቅጥፈትይሆንብሃል!



የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ሆነውና ያሉበትን ሥፍራ ተተግነው እንደልዩ የመረጃ ምንጭ መስለው ቅጥፈት የሚዘሩ ብሎጎች ብቅ ብቅ ማለታቸውን ስናይ ቆይተናል። ከእነዚህም አንዱ «እኔ የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ» በማለት ራሱን ያስተዋወቀው አንድ ብሎግ ወታደርነቱን እጠብቃታለሁ ለሚለው ቤተክርስቲያን ዓላማ ብቻ ማዋል ሲገባው ሲፈልግ ለግለሰቦች ጋሻና መከታነቱን የሚያሳይ፤ ዛሩ ሲነሳበት ደግሞ ጋሻ የሆነላቸውን ሰዎች ቆሌ በመግፈፍ ካርታው እንደጠፋበት ወታደር እዚህም፤ እዚያም የሚዳክር ሆኖ ይስተዋላል።
በእጃችን ያሉ መረጃዎችን መሠረት አድርገን፤ ነገር ግን መረጃዎቹን ትተን ጥቅል ችግሮቹን ብቻ ከዚህ በፊት ስለዝዋይ ገዳም አስነዋሪ ተግባራት በዘገብን ጊዜ ይህ ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ ሽንጡን ገትሮ ለሊቀጳጳሱ በመከራከር እንባ ቀረሽ ልቅሶውን በጽሁፍ ባስነበበን ጊዜ ወታደር ነኝ የሚለው ዲስኩሩን ትተን «የዓይጥ ምስክር ድንቢጥ» በማለት አልፈነው ነበር።
ይኸው የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ ስለዝዋዩ ሊቀጳጳስ ጠበቃ መሆኑን በጽሁፉ ባሰፈረ ጊዜ በልማት፤ በማኅበራዊና በመንፈሳዊ  እድገት ትልቅ እመርታ ማሳየታቸውን ጠቅሶ ሊቀጳጳሱ ላይ የስም ማጥፋት እርምጃ ለመውሰድ የፈለጉ ወገኖች መነሻ ምክንያታቸው «የኦሮሞ ፓትርያርክ ለማሾም የሚራወጡ ቡድኖች ጠባብ አስተሳሰብ ያመጣው ችግር ነው»  በማለት ነጭ ውሸቱን በድጋፍ ዘመቻው በማከል ጠበቃነቱን ማሳየቱ አይዘነጋም። ጽሁፉን ያነበብን አንዳንድ ወገኖች  የኦሮሞ ፓትርያርክ ዝዋይ ላይ መሾም እንዴት እንደሚቻል አዲሱን ግኝት አያይዞ ባለማብራራቱ ግር ብንሰኝም እንደአስፈጋጊ ቀልድ እውነታውን ስለምናውቅ በወቅቱ አልፈነው ነበር። ይኼው ብሎግ ለሊቀጳጳሱ በወቅቱ ከሰጠው ምስክርነት ጥቂቱን ጠቅሰው ወደሌላው «በአንድ ራስ ሁለት ምላስ» ጽሁፉ እናመራለን።
«ሁለቱም አካላት በተለያዩ መንሥኤዎች የገዳሙንና የብፁዕነታቸውን ስም ለማጥፋት ይሞክሩ እንጂ በአንድ ጎራ ያሰለፋቸው ስጋት ተመሳሳይ እንደኾነ ምንጮቹ ጨምረው ያስረዳሉ፡፡ ይህም ስጋት ብፁዕነታቸው በቀድሞው ፓትርያሪክ እንደ እንደራሴም እንደ ተተኪም መታጨታቸውና ለዚህም ዓላማ ፓትርያሪኩ ከከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋራ እንዳስተዋወቋቸው የሚነገርላቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎሬዎስ ስድስተኛው ፓትርያሪክ  ለመኾን በመንግሥት ታጭተዋል በሚል የመነገሩ ወሬ ነው»
ይህ ከላይ በቀይ የተቀመጠው ጽሁፍ የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ የሊቀጳጳሱ ወታደር ሆኖ በወቅቱ የጽሁፍ ምስክርነቱን በመስጠት በብሎጉ ላይ ያሰፈረው ነበር። ይኼው ብሎግ  ከወራት በኋላ ማለትም ጥር 6/2005 ጀምሮ የተደረገውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ተከትሎ በሚወጡ ዘገባዎች ላይ የሊቀጳጳሱ ጫና እያየለና ተሰሚነታቸው እየተጠናከረ መምጣቱን ተከትሎ ወደ ፓትርያርክነት የሚያደርጉትን የእጩነት ጉዞ በማጥላላት ዘመቻ ውስጥ ገብቶ፤በመዘገብ ላይ መጠመዱ ነገሩን ሁሉ አስገራሚ ያደርገዋል። 

Saturday, January 12, 2013

ያቆመንና ሊያቆመን የሚቻለውን ትተን ማንን ስንይዝ መቆም ይቻለናል?

ብዙ መጠላላትና መነቃቀፍ ብዙ ቦታ ተሰጥቶት መገኘቱን በየእለት ውሎአችን እናያለን።  እውነት፤ እውነቱን መነጋገር ቢቻልም መነቃቀፍ በበዛበት ዓለም እውነቱን በእውነታ ለመቀበል የሚቸገርም ሞልቷል። የሚቀበል ቢኖርም፤ ባይኖርም እውነት ነው ብለን ያመንበትን መናገር እንዳለብን ስለምናምን መናገራችንን አናቋርጥም። ዛሬም በዚህ ጽሁፋችን የምናውቃቸውን እውነታዎች፤ አንዳንዱ እውነት ነው ብሎ እንደሚቀበልና የዚህ ተጻጻሪው ደግሞ ጥላሸት በመቀባት ልምዱ የቆመበትን ስፍራ በቃሉ እንደሚያሳየን በማሰብ ጥቂት ለመግለጽ  የምፈልጋቸው ነገሮች አሉን። ጽሁፋችንም በቤተክርስቲያናችን ዙሪያ ያጠነጥናል።

 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የእምነት ዓምድ /ዶግማ/ ማለትም ምሥጢረ ሥላሴን አብርታ፤ አምልታና አስፋፍታ በማስተማር፤ እንዲሁም ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ሥጋ የለበሰበትን ረቂቅ ምሥጢር ፤ ምሥጢረ ሥጋዌውን አብራርታ በመስበኳ የታነጸችበትን ሃይማኖታዊ አለት/ ኰክሕ/ ስንመለከት በእውነትም የእግዚአብሔር ደጅ ናት ብንላት ቢያንሳት እንጂ አይበዛባትም። በክርስቶስ መሠረት ላይ የታነጸች፤ በሐዋርያት ትምህርት ያደገችና በሊቃውንቱ በእነአትናቴዎስ፤ ባስልዮስ፤ ጎርጎርዮስ ወዘተ የምሁራን አስተምህሮ የበለጸገች መሆኗን ማንም ሊክደው የማይችል የታሪክ እውነት ነው።

ዳሩ ግን ይህንን መሠረቷን የሚንዱ፤ ወንጌሏን ወደጎን የሚገፉ፤ አጋንንታዊ ልምምዶችን በስመ ሥሉስ ቅዱስ የሚያስፋፉ፣ ተከታዮቿ ዓይናቸውን ከክርስቶስ ላይ ነቅለው በየምናምኑ ላይ  እንዲተክሉ የሚያበረታቱ ብዙ አሳዛኝ መጻሕፍት በተረት፤ በእንቆቅልሽ፤ በወግና በአስማት ተሸፍነው የቤተክርስቲያኒቱን የወንጌል አስተምህሮ ማእድ በመበከል መርዛቸውን ታቅፋ እንድትኖር መገደዷን አስተዋዩ በደንብ ሲረዳው፤ እልከኛውም  በአፉ ለመመስከር ያቅተው እንደሆን እንጂ ችግር እንዳለ ልቡናው እንደሚመሰክርበት እናስባለን። 

ልበ ጠማሞች ደግሞ «በድሮ በሬ ያረሰ የለም» የሚለውን ብሂለ አበውን ከአፋቸው ሳያወርዱ ፤ በዚያው መራር አፋቸው ደግሞ በድሮ ስር ለመደበቅ «የቀደመውን ድንበር አታፍርስ»  ከማለታቸውም በላይ ከእኔ ወዲያ ለአባቶቼ ርስት ቀናዒ የለም! በሚል የኩራት ካባ በመደረብ የቤተክርስቲያኒቱን የወንጌል ማእድ የመረዙትን ህጸጾች መነካት የለባቸውም በማለት የግብር አባታቸውን ሥራ ተረክበው ሳያስተጓጉሉ  ለማስጠበቅ ሲታገሉ ኖረዋል፤እየታገሉም ይገኛሉ ። ደግሞ እናንተ እነማን ናችሁ? በማለት ለጥያቄዎች መልስ የመስጠት ብቃቱ ሳይኖራቸውና መልስ ይሰጡ ዘንድ ማንም ሳያስቀምጣቸው ራሳቸውን ሰይመው መገኘታቸውም የሚገርም ነው።

Wednesday, January 9, 2013

እውነቱ የቱ ነው? (ከዚህ በፊት የቀረበ)

መነሻ ሃሳብ «ገመና 81» መጽሐፍ

  ሀተታ

በኦርቶዶክሳውያን  ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከታች ጀምሮ እስከላይኛው እርከን ድረስ ያለው ሰው ስህተት ይኖርብናል ወይም ልንሳሳት እንችላለን ብሎ የሚያስብ ማግኘት አዳጋች ነው። በክርስቶስ ደም የተመሰረተችው ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗን በመቀበል እንዳለ መሪውና ተመሪው ራሱንም በዚያው ዓይን እያየ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በሚል ከለላ ስር ራሱን በማስጠለል፤ ስህተትን አምኖ ለመቀበል አይፈልግም። የስህተት አስተምህሮ አለ፤ በእግዚአብሔር ቃል ሲመረመር አደጋው የከፋ ነው፤ የክፉ መንፈስ አሰራር ወደማወቅ እንዳንደርስ ቃሉን በክሏል ሲባል የሚሰጠው ምላሽ፤ 2000 ሺህ ዘመን የኖረችን ቤተክርስቲያን ዛሬ የተነሱ አፍቃሬ ተሐድሶ መናፍቃን ሊያርሟትና ሊበርዟት ይፈልጋሉ በማለት ታፔላ መለጠፍ ይቀናቸዋል። የስም ታፔላ መለጠፍ ብቻ ሳይሆን ሽልማት የሚያሰጥ ቢሆን ኖሮ የተመረጡና ለመስማት የሚዘገንኑ ስድቦችና ዛቻዎች ይዥጎደጎዳሉ።
በእርግጥ የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗ አያጠራጥርም። ምክንያቱም የመሠረታት በዓለቱ ላይ በፈሰሰው ደሙ ነውና። ይህ እውነት ቢሆንም በክርስቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ አባል ሆነው የሚኖሩት የአዳም ልጆች መሆናቸውንም በመዘንጋት የቤተክርስቲያኗን መንፈስና ባህርይ እንዳለ ወደሰዋዊ ማንነት በመውሰድ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በማለት ከስህተት አልባነት የቤተክርስቲያን ማንነት ጋር ራስን መቁጠር ትኩረት የሚያሻው መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል። በእርግጥም የተጠራነው ፍጽምት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹማን እንድንሆን ነው። ነገር ግን ሰው ከተፈጠረበት ማንነት የተነሳ በፍጽምቷ ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹም ሆኖ መኖር የሚችል ማንነት የለውም።
ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሊሆኑን የሚችሉት የገላትያ ሰዎች ማንነት ነው። የገላትያ ሰዎች በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ወደ ሕይወት መንገድ የተመለሱ ሕዝቦች ነበሩ። ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተጨምረው የቆዩ ሆነው ሳለ ሰብአዊ ማንነታቸው አሸንፎአቸው ወደስህተት መንገድ በመግባታቸው በሐዋርያው ጳውሎስ እጅግ የተወቀሱ ሕዝቦች ሆነዋል።
«የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነውገላ 31
ክርስቶስ ኢየሱስ በፊታቸው የተሰቀለ ሆኖ በእምነት ይታያቸው የነበሩት ሕዝቦች ከዚያ የቅድስና ማንነት ወርደውና እውነትን በመተው፤ የጠላት አዚም የወረደባቸው  ሕዝቦች እስከመሆን መድረሳቸውን ሲናገር እናያለን። ሥራቸውን ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የጀመሩ ሆነው ሳለ ቁልቁል ተመልሰው የሥጋን ሃሳብና እውቀት ወደማመን መመለሳቸው በእርግጥም አሳዛኝ የሰው ልጆች ማንነት ማሳያዎች እንደሆኑ የሚያስገነዝበን  ነገር ነው።
«እንዲህን የማታስተውሉ ናችሁ? በመንፈስ ጀምራችሁ አሁን በሥጋ ትፈጽማላችሁንገላ 33 ይላል።
እንግዲህ ክርስቲያኖች ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እምነታቸውን ሊጀምሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ይህንን ፍጽምና ወደአለማወቅ መመለስም ሊታይባቸው ይችላል። ምን ጊዜም ቢሆን የስህተት መንፈስ አገልግሎቱ፤ የእውነቱን መንፈስ ከሰው ልቡና ላይ በመውሰድ ወደስህተት መንገድ መምራት ስለሆነ በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ ሰዎች ውስጥ የስህተት አስተምህሮ እንደሚገባ እናረጋግጣለን።
ብዙዎች የአብያተ ክርስቲያናት አባላት በክርስቶስ ፍቅር ላይ ጸንተው ከመቆም ይልቅ ወደ ምድራውያንና ሰማያውያን ፍጥረቶች ፍቅራቸውን ስለለወጡ የሕይወት መንገድን ስተው መገኘታቸው እውነት ነው።
ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ልጁን ወደ ተሰሎንቄ የላከበት ዋናው ምክንያትም ተሰሎንቄዎች  ከእምነት ጽናታቸው ወደኋላ እንዳይመለሱ በመንፈስ ያበረታታቸው ዘንድ ነበር። ምክንያቱም ፈታኝ የምንጊዜም አዚሙን የሚያፈሰው  የአማኞችን ልቡና በማደንዘዝ ወደ አልሆነ አቅጣጫ መመለስ  ሥራው ስለሆነ ከዚህ ፈታኝ ይጠበቁ ዘንድ እንደላከላቸው ቅዱሱ ወንጌል ይነግረናል።
«ስለዚህ እኔ ደግሞ ወደ ፊት እታገሥ ዘንድ ባልተቻለኝ ጊዜ። ፈታኝ ምናልባት ፈትኖአቸዋል ድካማችንም ከንቱ ሆኖአል ብዬ እምነታችሁን ለማወቅ ላክሁ» 1 ተሰ 35