Wednesday, January 16, 2013

ሰበር ዜና፤ ቅዱስ ሲኖዶስ ስድስተኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ ውሳኔ አሳለፈ

ጥር 8/2005 ዓ/ም  ምሽት ላይ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ባስተላለፈው ዜና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከጥር 6 ጀምሮ ባደረገው ስብሰባ ማጠቃለያ ላይ በሰጠው መግለጫ 6ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ ውሳኔ ማስተላለፉን ገልጿል።


ዜና ዘገባው አያይዞ እንደገለጸው በአሜሪካ ካሉ አባቶች ጋር ሲደረግ የቆየው ድርድር ሁሉ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ሲኖዶሱ በቀጥታ ወደምርጫ ለመግባት የተገደደ መሆኑን በመጠቆም፤ ነገር ግን የአሜሪካው ሲኖዶስ ወደእርቁ ተመልሶ አብሮ ለመሥራት ፈቃደኛ ከሆነ ለመቀበል ፈቃደኝነቱ እንዳለም አያይዞ አስረድቷል።
  ይህም ቀደም ሲል ሲነገር እንደቆየው አቡነ መርቆሬዎስ በፈለጉት ቦታ በጡረታ ከሚቀመጡ በቀር 5ኛ ፓትርያርክ ስንል ቆይተን፤ ቁልቁል ተመልሰን 4ኛ ፓትርያርክ በማለት የራሳችንን ሥራ የምናፈርስበት ምክንያት የለም የሚለውን ሃሳብ በደንብ ያንጸባረቀና ግልጽ ያደረገ መግለጫ ነበር። በሞት የተለዩትን ፓትርያርክ ሕገ ወጥ ናቸው በማለት የውጪው ሲኖዶስ ሲሞግት የቆየበትን ጥያቄ ተቀብሎ 4ኛውን ፓትርያርክ ወደመንበር መመለስ ማለት በ5ኛው ፓትርያርክ የተሰሩትና የተሾሙትን ጳጳሳትም በሕገ ወጥ ስልጣን የተገኘ ሹመት በማሰኘት ጥያቄ ውስጥ የሚከትና ወይም እንደገና ሊታደስ ይገባዋል የሚልን መንፈስ የሚያስነሳ ስለሆነ ከወዲሁ ስለአራተኛ ፓትርያርክ መመለስ ጉዳይ የሚነሳውን ፋይል ዘግተን ወደ 6ኛው ተሸጋግረናል በማለት እቅጩን የተናገረ ዘገባ ይመስላል። ይህም በፓትርያርኩ በራሳቸው አንደበት በቀጥታ  ባይሰማም በእነ አቡነ መልከ ጼዴቅ ይነሳ የነበረው የ4ኛው ፓትርያርክ ወደሥልጣን የመመለስ የእርቅ ክርክር እዚሁ ላይ ያቆማል ማለት ነው። 
የሀገር ቤቱን ሲኖዶስ እንደብቸኛ ሲኖዶስ በመቀበል፤ የውጪው ሲኖዶስ ከሀገር ቤቱ ጋር ለመቀላቀል ዝግጁ ይሆን? ያ ካልሆነ የእርቁ ፋይል እዚህ ላይ ይዘጋል!  ሁሉም ወገን ሥልጣን አይቅርብኝ የሚል ፈላጊ ስለነበር አንድ መሆን አልተቻለም። ሥልጣን የማያስጎመጅ አማራጭ ይኖር ይሆን?

«ሐራ» ነኝ ማለትህ ቅጥፈትይሆንብሃል!



የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ሆነውና ያሉበትን ሥፍራ ተተግነው እንደልዩ የመረጃ ምንጭ መስለው ቅጥፈት የሚዘሩ ብሎጎች ብቅ ብቅ ማለታቸውን ስናይ ቆይተናል። ከእነዚህም አንዱ «እኔ የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ» በማለት ራሱን ያስተዋወቀው አንድ ብሎግ ወታደርነቱን እጠብቃታለሁ ለሚለው ቤተክርስቲያን ዓላማ ብቻ ማዋል ሲገባው ሲፈልግ ለግለሰቦች ጋሻና መከታነቱን የሚያሳይ፤ ዛሩ ሲነሳበት ደግሞ ጋሻ የሆነላቸውን ሰዎች ቆሌ በመግፈፍ ካርታው እንደጠፋበት ወታደር እዚህም፤ እዚያም የሚዳክር ሆኖ ይስተዋላል።
በእጃችን ያሉ መረጃዎችን መሠረት አድርገን፤ ነገር ግን መረጃዎቹን ትተን ጥቅል ችግሮቹን ብቻ ከዚህ በፊት ስለዝዋይ ገዳም አስነዋሪ ተግባራት በዘገብን ጊዜ ይህ ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ ሽንጡን ገትሮ ለሊቀጳጳሱ በመከራከር እንባ ቀረሽ ልቅሶውን በጽሁፍ ባስነበበን ጊዜ ወታደር ነኝ የሚለው ዲስኩሩን ትተን «የዓይጥ ምስክር ድንቢጥ» በማለት አልፈነው ነበር።
ይኸው የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ ስለዝዋዩ ሊቀጳጳስ ጠበቃ መሆኑን በጽሁፉ ባሰፈረ ጊዜ በልማት፤ በማኅበራዊና በመንፈሳዊ  እድገት ትልቅ እመርታ ማሳየታቸውን ጠቅሶ ሊቀጳጳሱ ላይ የስም ማጥፋት እርምጃ ለመውሰድ የፈለጉ ወገኖች መነሻ ምክንያታቸው «የኦሮሞ ፓትርያርክ ለማሾም የሚራወጡ ቡድኖች ጠባብ አስተሳሰብ ያመጣው ችግር ነው»  በማለት ነጭ ውሸቱን በድጋፍ ዘመቻው በማከል ጠበቃነቱን ማሳየቱ አይዘነጋም። ጽሁፉን ያነበብን አንዳንድ ወገኖች  የኦሮሞ ፓትርያርክ ዝዋይ ላይ መሾም እንዴት እንደሚቻል አዲሱን ግኝት አያይዞ ባለማብራራቱ ግር ብንሰኝም እንደአስፈጋጊ ቀልድ እውነታውን ስለምናውቅ በወቅቱ አልፈነው ነበር። ይኼው ብሎግ ለሊቀጳጳሱ በወቅቱ ከሰጠው ምስክርነት ጥቂቱን ጠቅሰው ወደሌላው «በአንድ ራስ ሁለት ምላስ» ጽሁፉ እናመራለን።
«ሁለቱም አካላት በተለያዩ መንሥኤዎች የገዳሙንና የብፁዕነታቸውን ስም ለማጥፋት ይሞክሩ እንጂ በአንድ ጎራ ያሰለፋቸው ስጋት ተመሳሳይ እንደኾነ ምንጮቹ ጨምረው ያስረዳሉ፡፡ ይህም ስጋት ብፁዕነታቸው በቀድሞው ፓትርያሪክ እንደ እንደራሴም እንደ ተተኪም መታጨታቸውና ለዚህም ዓላማ ፓትርያሪኩ ከከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋራ እንዳስተዋወቋቸው የሚነገርላቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎሬዎስ ስድስተኛው ፓትርያሪክ  ለመኾን በመንግሥት ታጭተዋል በሚል የመነገሩ ወሬ ነው»
ይህ ከላይ በቀይ የተቀመጠው ጽሁፍ የቤተክርስቲያን ወታደር ነኝ ባዩ ብሎግ የሊቀጳጳሱ ወታደር ሆኖ በወቅቱ የጽሁፍ ምስክርነቱን በመስጠት በብሎጉ ላይ ያሰፈረው ነበር። ይኼው ብሎግ  ከወራት በኋላ ማለትም ጥር 6/2005 ጀምሮ የተደረገውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ተከትሎ በሚወጡ ዘገባዎች ላይ የሊቀጳጳሱ ጫና እያየለና ተሰሚነታቸው እየተጠናከረ መምጣቱን ተከትሎ ወደ ፓትርያርክነት የሚያደርጉትን የእጩነት ጉዞ በማጥላላት ዘመቻ ውስጥ ገብቶ፤በመዘገብ ላይ መጠመዱ ነገሩን ሁሉ አስገራሚ ያደርገዋል። 

Saturday, January 12, 2013

ያቆመንና ሊያቆመን የሚቻለውን ትተን ማንን ስንይዝ መቆም ይቻለናል?

ብዙ መጠላላትና መነቃቀፍ ብዙ ቦታ ተሰጥቶት መገኘቱን በየእለት ውሎአችን እናያለን።  እውነት፤ እውነቱን መነጋገር ቢቻልም መነቃቀፍ በበዛበት ዓለም እውነቱን በእውነታ ለመቀበል የሚቸገርም ሞልቷል። የሚቀበል ቢኖርም፤ ባይኖርም እውነት ነው ብለን ያመንበትን መናገር እንዳለብን ስለምናምን መናገራችንን አናቋርጥም። ዛሬም በዚህ ጽሁፋችን የምናውቃቸውን እውነታዎች፤ አንዳንዱ እውነት ነው ብሎ እንደሚቀበልና የዚህ ተጻጻሪው ደግሞ ጥላሸት በመቀባት ልምዱ የቆመበትን ስፍራ በቃሉ እንደሚያሳየን በማሰብ ጥቂት ለመግለጽ  የምፈልጋቸው ነገሮች አሉን። ጽሁፋችንም በቤተክርስቲያናችን ዙሪያ ያጠነጥናል።

 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የእምነት ዓምድ /ዶግማ/ ማለትም ምሥጢረ ሥላሴን አብርታ፤ አምልታና አስፋፍታ በማስተማር፤ እንዲሁም ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ሥጋ የለበሰበትን ረቂቅ ምሥጢር ፤ ምሥጢረ ሥጋዌውን አብራርታ በመስበኳ የታነጸችበትን ሃይማኖታዊ አለት/ ኰክሕ/ ስንመለከት በእውነትም የእግዚአብሔር ደጅ ናት ብንላት ቢያንሳት እንጂ አይበዛባትም። በክርስቶስ መሠረት ላይ የታነጸች፤ በሐዋርያት ትምህርት ያደገችና በሊቃውንቱ በእነአትናቴዎስ፤ ባስልዮስ፤ ጎርጎርዮስ ወዘተ የምሁራን አስተምህሮ የበለጸገች መሆኗን ማንም ሊክደው የማይችል የታሪክ እውነት ነው።

ዳሩ ግን ይህንን መሠረቷን የሚንዱ፤ ወንጌሏን ወደጎን የሚገፉ፤ አጋንንታዊ ልምምዶችን በስመ ሥሉስ ቅዱስ የሚያስፋፉ፣ ተከታዮቿ ዓይናቸውን ከክርስቶስ ላይ ነቅለው በየምናምኑ ላይ  እንዲተክሉ የሚያበረታቱ ብዙ አሳዛኝ መጻሕፍት በተረት፤ በእንቆቅልሽ፤ በወግና በአስማት ተሸፍነው የቤተክርስቲያኒቱን የወንጌል አስተምህሮ ማእድ በመበከል መርዛቸውን ታቅፋ እንድትኖር መገደዷን አስተዋዩ በደንብ ሲረዳው፤ እልከኛውም  በአፉ ለመመስከር ያቅተው እንደሆን እንጂ ችግር እንዳለ ልቡናው እንደሚመሰክርበት እናስባለን። 

ልበ ጠማሞች ደግሞ «በድሮ በሬ ያረሰ የለም» የሚለውን ብሂለ አበውን ከአፋቸው ሳያወርዱ ፤ በዚያው መራር አፋቸው ደግሞ በድሮ ስር ለመደበቅ «የቀደመውን ድንበር አታፍርስ»  ከማለታቸውም በላይ ከእኔ ወዲያ ለአባቶቼ ርስት ቀናዒ የለም! በሚል የኩራት ካባ በመደረብ የቤተክርስቲያኒቱን የወንጌል ማእድ የመረዙትን ህጸጾች መነካት የለባቸውም በማለት የግብር አባታቸውን ሥራ ተረክበው ሳያስተጓጉሉ  ለማስጠበቅ ሲታገሉ ኖረዋል፤እየታገሉም ይገኛሉ ። ደግሞ እናንተ እነማን ናችሁ? በማለት ለጥያቄዎች መልስ የመስጠት ብቃቱ ሳይኖራቸውና መልስ ይሰጡ ዘንድ ማንም ሳያስቀምጣቸው ራሳቸውን ሰይመው መገኘታቸውም የሚገርም ነው።