Saturday, August 18, 2012

ከኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ ምርጫ ምን እንማራለን?


የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ የምርጫ ሂደት በ1957 ዓ/ም ተሻሽሎ የወጣ ነው። ምርጫው የቤተክርስቲያኒቱ አባል የሆነው በሙሉ ያካተተ እንዲሆን የተሞከረበት ህገ ደንብ አለው። በእርግጥም ምርጫው በሲኖዶስ ፈቃድና እጣ የሚያበቃ  ሳይሆን ከየትኛውም ዘርፍ ያለውን አባሏን የሚያሳትፍ በመሆኑ እውነተኛ አባት ለመምረጥ አስቸጋሪ አልሆነባቸውም። ቢያንስ ቢያንስ አሁን ባለው የፖፕ ሺኖዳ ምትክ ምርጫ ላይ እንኳን ወደ 14 ሰዎች በግልና በጥቆማ ከቀረቡት የፓትርያርክ እጩዎች ውስጥ የማይፈለጉ ሰዎች ወደዚያ መንፈሳዊ ወንበር ሾልከው እንዳይወጡ ማስቀረት የሚችልበት የምርጫ ወንፊት ስላለው እስኪጣራ ድረስ ሂደቱን ሊያዘገይ አስችሎታል። መዘግየቱ ለመንበረ ሥልጣኑ ክፍት ሆኖ መቆየት አስቸጋሪ መሆኑ ባይካድም ክፍት እንዳይቆይ ተብሎ በሆይ ሆይ ቢሾም ደግሞ  የማይፈለጉ ሰዎች በቡድንና በድጋፍ ተጠግተው ሥልጣኑ ላይ ከወጡ በኋላ ሳያስለቅሱ ማውረድ እንዳይቸግር ከወዲሁ በወንፊት የማበጠሩ ጉዳይ መኖሩ ኮፕቶችን ቢጠቅማቸው እንጂ አይጎዳቸውም። ከዚያው ያገኘናቸው መረጃዎች የሚጠቁሙት ያንን ነው። እኛም የበሰለ ነገር ቢበሉት ሆድ አይጎረብጥምና ነገሩን አብስላችሁ ማቅረባችሁ ይበል የሚያሰኝ ነው እንላለን።
ወደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስንመጣ የራሷን ፓትርያርክ ስትሾም እድሜው እንደጥንታዊነቷ አይደለም። የዚያን እንዴትነት እስከነ ሰፊ ታሪኩ ትተን ፓትርያርክ መሾም ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ያለውን ሁኔታ በግብጽ አጽዳቂነት የተከናወኑትን ስንመለከት የድክመቶቻችን ውጤት እንጂ ስኬታችን ትልቅነት አድርጎ መመልከቱ ሚዛን አይደፋም። ራሳችን መሾም ጀምረናል ካልንበት ጊዜም ጀምሮ ቢሆን የመንግሥት እጅ በጓሮ በር ሳይገባበት የተከናወኑ ምርጫዎችን ለማግኘት ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ስለሚሆን አልፈነዋል። እንደዚያም ሆኖ በመገዳደል፤ በመከፋፈልና በመሰነጣጠቅ፤ በመወጋገዝ  የተሞላ መሆኑ የአሳዛኝ ገጽታው አንዱ ፈርጅ ሆኖ ዘልቋል። ዛሬም ከዚያ አዙሪት ስለመውጣታችን እርግጠኞች አይደለንም። ቤተክርስቲያኒቱን በማስቀደም ሳይሆን የሥልጣን ጥምን ለመወጣትና የመንፈሳዊ ማንነት ጉድለቱ ግዝፎ በመታየቱ ችግሮቻችን በአጭሩ የፕትርክና ታሪካችን ውስጥ የሺህ ዓመት ጥላሸትን አኑሯል።
ለመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ አሿሿም ልምዷ ከጥንታዊነቷ ጋር የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ ቢሆንም  እንኳን ፓትርያርኳን ለመሾም የግድ የ1000 ዓመት ልምምድ ያስፈልጋታል ወይ? ብለን እንጠይቃለን።
« ሞኝ ሰው ከራሱ ስህተት ይማራል፤ ብልህ ሰው ግን ከሞኝ ሰው ስህተት ይማራል» እንዲሉ  የሌሎችን ልምድ ቀምረን እኛ የተሻለ ሥራ ለመስራት እንደብልሁ ሰው መሆን ባንችል እንኳን እንደሞኝ ሰው ከስህተቶቻችን መማር ለምን እንደከበደን ሳስብ ግራ ይገባኛል።
በ21ኛው ክ/ዘመን ዲሞክራሲን ለመማር እንደአሜሪካ 200 ዓመት እስኪሞላ የምንጠብቅ ከሆነ ከሉላዊነት አስተሳሰብ ውጪ ነን ማለት ነው። አሜሪካ ውስጥ የተመረተ ሸቀጥ ኢትዮጵያ እስኪደርስ 200 ዓመት ይፈጅበታል ብሎ እንደማሰብ ይሆናል። እንደዚሁ ሁሉ ከኮፒቲክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ አሿሿም ሕገ ደንብ ለመማር የግድ የግብጽ ጳጳሳት እንደገዙን 1600 ዓመት ልንጠብቅ አይገባም።  የፓትርያርክነት የምርጫ አዙሪት  በመገምገም መፍትሄው በቅርቡ ሊሆን ይችል ይሆን? ለሚለው ጥያቄ መልሱ ሩቅ ይሆንብኛል።
አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ሲሆኑ በምርጫው ላይ የነበሩ ጳጳሳት ዛሬም አሉ። አቡነ መርቆሬዎስ ሲባረሩም፤ የመባረራቸውን ተገቢነት የደገፉ  አሁንም አሉ። አቡነ ጳውሎስ በተባረሩት ምትክ ሲሾሙ የመረጡ አሉ። አቡነ ጳውሎስን የመረጡ ተመልሰው የጠሏቸው፤ አሁን ሲሞቱ ደግሞ ተመልሰው ለመመረጥ ወይም ለመምረጥ ያሰፈሰፉ አሉ። እንግዲህ አቋሟቸው ለመገለባበጥ እንጂ ሊኖር በሚገባ ሃይማኖታዊ ጽናት ለመቆም በማይችሉ ሰዎች በሞላበት ሲኖዶስ ተስፋ የሚጣልበትና እግዚአብሔር የወደደውን ምርጫ ለማካሄድ ገና መቶ ዓመታትን ሊፈጅ ይችላል። ለዚያውም ሰማይና ምድር ሳያልፉ ከጠበቀን ነው። ዛሬ እንኳን ለምርጫው በውስጠ ምስጢር በመንግሥት በኩል የታለሙትና አውሬው ደግሞ በከተማይቱ እያስተጋባ የሚገኘውን ድምጽ ስናዳምጥ ነገም ልቅሶአችን ቀጣይ መሆኑን አመላካች ነው። በዚህ ዓይነት መልኩ ከሄድን ደግሜ እላለሁ፤ ነገንም ከእንባ አንላቀቅም።
የኛ ጉዳይ እንደዚህ ነው። የሚሆነውንና የሚመጣውን ከማያልቅበት እድሜ አይንፈገንና ሁሉን እናይ ይሆናል። እስከዚያው እስኪ ከኮፕቶች የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ ጥቂት እንመልከት።
1/ ፓትርያርኩ ባረፉ በ7ኛው ቀን  የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና የጠቅላይ ምክር ቤት አባላት ባሉበት በጵጵስና ቀዳሚ የሆነው ሊቀጳጳስ ዐቃቤ መንበር ሆኖ ይሰየማል። የዐቃቤ መንበሩ ምርጫ እንዳበቃ  የፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴ ይዋቀራል። አስመራጭ ኮሚቴው 18 አባላት ያሉት ሆኖ 9 ጳጳሳት ከሲኖዶሱ፤ 9 አባላት ደግሞ ከጠቅላይ ምክር ቤቱ ይመረጣሉ።
 ጠቅላይ ምክር ቤት ማለት በፓትርያርኩ ሊቀመንበርነት የሚመራ በመንበረ ፓትርያርኩ ስር የተዋቀረ ሲሆን  የሲኖዶስ አባላት፤ ቤተክርስቲያኒቱን በገንዘብ፤ በጉልበትና በእውቀት የሚደግፉ ምእመናን፤ አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት፤ የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ ያሉበት የ24 አባላት ምክር ቤት ነው።

Friday, August 17, 2012

በአቡነ ጳውሎስ እረፍት የማኅበሩ ምኞት ሰፋ ወይስ ጠበበ?



ፓትርያርክ ጳውሎስን እስከህይወታቸው ኅልፈት ድረስ ሲራገማቸው፤ ሲያዝንባቸው፤ ሲዘልፋቸው፤ ሲያሽሟጥጣቸውና በታመሙ ቁጥር አሁንስ የሚተርፉ አይመስልም እያለ ሲዘግብባቸው የቆየው ማኅበር አሁን እፎይ፤ ግልግል እንደሚል የደረሰበት የጥላቻው ጥግ ጽሁፎቹ ያረጋግጡልናል።
ደጀ ሰላም፤August 14, 2012
 እግራቸው ከጉልበታቸው በታች በከፍተኛ ደረጃ መጎዳቱንና የጤናቸው ኹኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ የሚነገርላቸው ፓትርያርኩ÷ ጤናቸውን ለመከታተል የሚያደርጉት ሳምንታዊ ወጪ ከስድሳ ሺሕ ብር በላይ ማሻቀቡን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
የደጀሰላም ወዳጅ አስተያየት ሰጪ- August 16, 2012 2:06 PM
Anonymous said...ግልግል ለተዋህዶ የተስፋ ጮራ ነው!ፈርኦን ሆይ ህዝቤን ልቀቅ ሲባል ካልሰማ የእግዚአብሔር እጅ ትዘረጋለች። ከቁጣው እሳት ማምለጥ የሚቻለው ማን ይሆን?
የፓትርያርኩ ሕመም ሳይሆን ፓትርያርክ ሆነው ለህክምና 60 ሺህ ብር ማውጣቱ ያስቆጨውን ማኅበር ምን ይሉታል? ገንዘቡ ከወጪ እንዲድን ቶሎ ይሙቱልን ማለቱ አይደለምን? በሳምንት ይህንን ያህል እየወጣ ነው የሚለውን ገንዘቡን ወጪ ከህመማቸው ጋር ማነጻጸር ቆይታቸው ከወጪ በስተቀር ምንም ትርፍ የለውም ማለቱ ነው እስከሚገባን ድረስ።
ማኅበሩ ፓትርያርኩን እንደሚጠላ ይታወቃል፤ ግን አሳዛኙ ነገር እሳቸውን በሚያይበት ዓይን ወዳጆቻቸውንም እንደዚያው መመልከቱ አስገራሚ ነው።
ማኅበሩ እነ እገሌ ጳጳሳት ነደ እሳት ናቸው፤ እነ አቶ እገሌም መኪና ሸለሙኝ እያለ የራሱን ወዳጆች ከፍ፤ ከፍ እያደረገ ስማቸውን ለአፍታም ከአፉ እንደማያሳርፈው ሁሉ በተነጻጻሪው አቡነ ጳውሎስ ደግሞ ከወዳጆቻቸው መካከል አንዳንድ ሰዎችን ቢያቀራርቡና ቤተኛ ቢያደርጉ ይህ የሰው ባህርያዊ ፍላጎት መሆኑን በመካድ ማኅበሩ ፓትርያርኩን ሲያወግዝና ሲራገም፤ ወዳጆቻቸው ሲያጣጥል መገኘቱ ያሳዝናል።  ማኅበሩ የራሱን ወዳጆች እንደሚቀርባቸው ሁሉ አቡነ ጳውሎስ የልብ ወዳጆቻቸውን ማቅረባቸው ምን ክፋት አለው? ማኅበሩ የራሱ ስራ ሌላ፤ የሰዎቹ መወዳጀት ሌላ ! በየትኛው ርስቱ ላይ ነው፤ ይህ ማኅበር እንደዚህ አድርጎ የሚነጫቸው?
ከእነዚህ ተረጋሚ ሰዎች ከማኅበሩ ድረ ገጾች ስማቸው እስካሁን እረፍት ያላገኘውና ወደፊትም እንደ አቡነ ጳውሎስ በሞት ከሄዱም በኋላ የማኅበሩ እርግማን ይለያቸዋል ተብሎ የማይታሰበው ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ፤ አባ ሠረቀ ብርሃን ወ/ሳሙኤል፤ መጋቤ ሐዲስ በጋሻው ደሳለኝ፤መምህር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል፤ ሊቀ ስዩማን ኃ/ጊዮርጊስ ጥላሁን፤ መምህር አእመረ አሸብር፤ ንቡረ እድ ኤልያስ እና ሌሎች  ስማቸው ከማኅበሩ አገልጋይ ድረ ገጾች ላይ ለእረፍት አይወርዱም።
ማኅበሩ እነዚህን ሰዎች የሚረግማቸው ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ባላቸው ቅርበት እንጂ ማኅበሩ እንደማኅበር የሚንቀሳቀስበትና የሚሄድበት መንገድ ከእነዚህ ሰዎች ጋር የሚገናኝ ስለሆነ አይደለም። አንዳንዶቹም ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ገጥመዋል ብሎ ከሚጨነቅበት ባሻገር በምርኮኝነት እጃቸውን ሰጥተው የማኅበሩ አገልጋይ መሆን ስላልፈለጉ ቅናት እየሸነቆጠ ስላስቸገረው ነው። ለምሳሌም ያህል በጋሻውን፤ ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤልንና ኃ/ጊዮርጊስ ጥላሁንን ማንሳት ይቻላል። ጥፋታቸው አንፈልግህም ማለታቸው ብቻ ነው።
ከደጀ ሰላም ስድብና እርግማን መካከል አንዱን እንመልከት።
ቅዱስ ሲኖዶስ በታሪክ እጅግ ሊያስመሰግነው በሚችል መልኩ በተሐድሶ ድርጅቶች እና አራማጆች ላይ የውግዘት ቃሉን ባስተላለፈ ማግሥት ቅዱስነታቸው ቀንደኛውን ተሐድሶ በአሜሪካ የሾሙበት ምክንያት የንፁሐን ኦርቶዶክሳውያንን ቅስም ለመስበር እንዲሁም ወደ ውጪ አገር ሰው በመላክ ሰበብ የሚያጋብሱትን ገንዘብ በታማኛቸው አማካኝነት ለማካሔድ በማሰብ መሆኑን ምንጮች አብራርተዋል። (ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 24/2004 ዓ.ም፤ ጁን 1/ 2012/
ቡነ ጳውሎስ ገንዘብ ለመዝረፍ ኃ/ጊዮርጊስን ወደ አሜሪካ ለመሾም የሚገደዱት በምን ስሌት ነው? የተሾሙ ሁሉ ገንዘብ ዘራፊዎች ናቸው? ኃ/ጊዮርጊስስ የማንን ገንዘብ ይዘርፋል? የማኅበሩ የጥላቻ ጥግ ጥቂት እንኳን ወደ እውነቱ አይቀራረብም።
ኃ/ጊዮርጊስ ቀድሞ የማኅበሩ ወዳጅ ነበር። ኃ/ጊዮርጊስ የጋብቻ ወረቀታችንን ቀደናል ባለ ማግስት ጀምሮ ማኅበሩ የዘመቻ ሰይፉን አንስቶበታል። ማኅበሩ ከእሱ የተለየ ሃሳብና መንገድ ያለውን ማንኛውንም ሰው እንደ ሰው የሚቀበልበት ተፈጥሮ የለውም። አሜን ብሎ የመገዛት ግዴታ፤ አለበለዚያም ከምድረ ገጽ እስኪጠፋ ድረስ የመዝመት ተልእኮ ያለው ማኅበር መሆኑን ስራዎቹ ራሳቸው ይመሰክራሉ።
ይህ ማኅበር በእሱ እርግማን ይሁን በእግዚአብሔር ፈቃድ የአቡነ ጳውሎስ ህልፈተ ህይወት የሆነበትም ምክንያት ለራሱ እንደመሰለው ቢያስብም፤  ነጋ ጠባ የሚጨቀጭቃቸው አባትከእንግዲህ በፊቱ የሉም።  በቀጣይ ወዳጆቻቸውን እስኪያጠፋ ድረስ ለጊዜው  ቤቱን ዘግቶ  የደስታ ከበሮ የመደለቅ መብቱ የተከበረ ነው። ይሁን እንጂ በአቡነ ጳውሎስ ሞት የተሰማውን ደስታ አጣጥሞ ሳይጨርስ፤ የፓትርያርኩ ወዳጆች ናቸው ብሎ የሚገምታቸውን ገና ካሁኑ ስማቸውን እየጠራ ዘመቻውን ጀምሯል።
(ደጀ ሰላም፤ ነሐሴ 10/2004 ዓ.ም፤ ኦገስት 16/ 2012
ፋውንዴሽኑ› መቋቋም ያስፈልጋል የተባለውን ገንዘብም እንደተለመደው ከስፖንሰርሽፕ፣ ከአድባራትና ገዳማት እንዲሁም ከተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ኢኮኖሚያዊ ምንጮች ለመሰብሰብ ሲዘጋጁ መቆየታቸውን የገለጸው የመረጃ ምንጩ÷ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነን፣ መልአከ ፀሐይ በቀለ ተሰማን (ቤቴል ቅዱስ ሚካኤል)፣ ሰሎሞን በቀለን (ቦሌ መድኃኔዓለም)፣ ቀሲስ ግሩም መልአክ ታዬን (ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት፣ ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤልን (ጠቅላይ ቤተ ክህነት) በዋና አደራጅነት ጠቅሰዋል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት በጉዳዩ ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኀይሎች በመታገዝ ጠንካራ ክትትል በማድረግ የወይዘሮዋንና ሌሎች አካላትን ችግር ፈጣሪነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማቆም እየሠራ እንደሚገኝ ተዘግቧል፡፡

Thursday, August 16, 2012

ሰበር ዜና፤ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አረፉ።



ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ያገኘነው ዘገባ አረጋግጧል። በሳምንቱ መጀመሪያ ገደማ ለሕክምና ዳጃች ባልቻ ከገቡ በኋላ አንዳንዶች ህመማቸውን እንደህመማቸው ቆጥረው ሳይሆን መታመማቸው ይፋዊ ዜና እንዲሆንላቸውና መጨረሻቸውም በሚፈልጉት መንገድ ሲያበቃ ለማየት የቋመጡ  ያህል ሲዘግቡ የሰነበቱበት እውን ሆኖ   በ9/12/ 2004  ዓ/ም ንጋት ላይ  አርፈዋል።
የቅዱስ ፓትርያርኩን ሞት ለረጅም ዘመን ሲጠብቁ የቆዩ ደስ ሲላቸው እስከ ሰውኛ ድክመታቸው ፓትርያርኩ ለዚህች ቤተክርስቲያን የሚችሉትን ያህል ሰርተዋል የሚሉ ደግሞ ማዘናቸው አይቀርም። ደጀ ብርሃን ብሎግ አቡነ ጳውሎስ ከስህተትና ከሰውኛ የድካም ጠባይዓት ፍጹም ነጻ ነበሩ ብላ ባታምንም  ቤተክርስቲያኒቱን ደከመኝ፤ ሰለቸኝ ሳይሉ በማገልገል፤ የተወረሱባትን ሃብትና ንብረት በማስመለስ ረገድ ትልቅ ስራ መስራታቸውን፤ በቅዳሴ አገልግሎት በህመም ውስጥ እንኳን እያሉ ማገልገላቸውን ትመሰክራለች።
አቡነ ጳውሎስን በአስተዳደር፤ በገንዘብ ጉዳይ፤ በዘረኝነት የሚወቅሱ ወገኖች አሁን በሞት ሁሉን ነገር ትተውላቸው ሲሄዱ ፍላጎታቸውን ሊያሟላ የሚችል ጳጳስ በመፈለግ «ትሻልን ሰድጄ ትብስን አመጣሁ» እንዳይሆን ከወዲሁ ትልቅ ፍርሃት አለን።
 በቀጣይ ጽሁፋችን ሙሉ ታሪካቸውን ይዘን የምንቀርብ ሲሆን እግዚአብሔር የወደደውን እንዲያደርግ ከማሰብ ባሻገር በጥላቻም ይሁን መጠን ባለፈ ምስጋና ውስጥ እንዳንሆን አንባቢዎቻችንን ለማሳሰብ እንወዳለን።
እግዚአብሔር በዐጸደ ቅዱሳን እረፍቱን ይስጥልን!