Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts
Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts

Wednesday, August 19, 2015

ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?


1/ እንደመግቢያ፤

   መላእክትና ሰዎች በእግዚአብሔር ግብር የተፈጠሩ ፍጡራን ናቸው።  በኦሪት ዘፍጥረት የመጀመሪያዎች ሁለት ምዕራፎች እንደተመለከተው በላይ በሰማይ፤ ከታች በምድርና በጥልቅ ውሃማ አካሎች ሁሉ እግዚአብሔር በለይኩን ቃሉ (ከአዳም በስተቀር) የፈጠራቸውን ሥነ ፍጥረቶች እናገኛለን። በመሠረተ እምነት ደረጃ ፍጡር ስንል ፈጣሪ ወይም አስገኚ ያለው ነገር ማለታችን ነው። መፍጠር ወይም የሌለውን ነገር ማስገኘት ማለት አንድን ነገር መሥራት ወይም መፈብረክ ማለት አይደለም። የነገረ መለኮት ምሁራን መፍጠርን ወይም ማስገኘትን ሲገልጹ «from nothing to something» በማለት ይገልጹታል። «ከምንምነት ወደአንድ ነገርነት» ማምጣት ማለት ነው።  እግዚአብሔር ለመፍጠር መነሻ ሃሳብ ወይም ጥሬ ነገር /substance/ አያስፈልገውም።  

   ፍጡራን ግን ይህንን ማድረግ አይቻላቸውም። ለምሳሌ ወንበር የሠራ ሰው ፈበረከ ወይም ሠራ ቢባል እንጂ «ፈጠረ ወይም አስገኘ» ሊባል የተገባው አይደለም ይላሉ ምሁራኑ። ምክንያቱም «ወንበር» የተባለውን ቁስ ለመሥራት  አንዳንድ ነገሮች «something» የግድ ያስፈልጉታልና ነው። ይህም የሥራ ጉዞ «from something to something» በቅርጽ፤ በመጠንና በይዘት ይለውጠዋል እንጂ /from nothing to something/ ከምንም ነገር ሳይነሳ «ወንበር» የተባለውን ቁስ ማቅረብ አለመቻሉ የጉድለቱ አንድ አስረጂ እንደሆነ በአመክንዮ ያቀርባሉ።  ያንንም ወንበር እንኳን ለመሥራት ወይም ለመፈብረክ የግድ የሚያስፈልጉት ጥሬ ሀብቶች /raw materials/ የሠራተኛው የራሱ ግኝቶች አይደሉም። 

   ስለሆነም ፍጡራን በሙሉ ያላቸው ሁኔታ፤ ችሎታና ብቃት ያልተወሰነ፤ በአፈጣጠር ያልተገደበ አይደለም። በሥራቸው ሁሉ ምሉዕነት ያለው፤ ጉድለት አልቦነትም የማይጎበኘው አይደለም። መላእክትና ሰዎች መነሻም፤ መድረሻም አላቸው። መነሻና መድረሻ ያለው ፍጥረት ደግሞ በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት በሁሉ ሥፍራ መገኘት አይችልም። በሥራው ሁሉ በብቃትና በራሱ ኃይል የማከናውን ፍጹምነት የለውም።

 የእግዚአብሔር ባህርይ ግን ከዚህ የተለየ ነው። እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪና አስገኚ ስለሆነ መነሻም መድረሻም የለውም። ኋለኛ የሌለው ፊተኛ፤ ፊተኛም የሌለው ኋለኛ እሱ ብቻ በመሆኑ አልፋና ኦሜጋ እንለዋለን።
መጽሐፍ ቅዱስ « በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ» ዘፍ 1፤1 ሲል እግዚአብሔር ከምንም ነገር «from nothing to something»  ለመፍጠር ወይም ለማስገኘት ምንም ተጨማሪ ነገር እንዳላስፈለገውና እሱ ብቻ እንደተቻለው እንረዳለን። ሰማይና ምድርን ግን የፍጥረት መነሻ ሆነው ተከስተዋል። ሁለቱም በሥፍራ፤ በቦታና በሁኔታ ተወስነዋል። ምድር በውስጧ የተገኙት ፍጥረታትም ሁሉ መነሻና መድረሻ፤ መጠነ ውሱንነትና መጠነ አኽሎኝነት ይዘው መገኘታቸውን በእያንዳንዱ የሥነ ፍጥረታት ጠባይዓት ላይ እንመለከታለን። ከፍጥረታት አንዱ ክፍል የሆነው የሰው ልጅን ብንመለከት በፍጥረተ ጠባዩ  የአስተሳሰብ፤ የአፈጣጠርና የማንነት ብቃት በተሰጠው እሱነቱ ልክ ተወስኖ ይገኝበታል።

  እርግጥ ነው፤ ስለሃይማኖት ጥሩ ግንዛቤ ያለው ሰው ያለብዙ ምክንያታዊ ውጣ ውረድ «ፍጡራን በአንድ ጊዜ በሁሉ ሥፍራ መገኘት አይችሉም!» ብሎ መልስ ሊሰጥ ይችላል። ደግሞም የሚሠመርበት እውነት፤ በሁሉ ሥፍራ፤ በአንድ ጊዜ፤ በስፍሐትና በምልዐት  (በምሉዕ ኵለሄነት) የመገኘት ብቃት ከእግዚአብሔር በስተቀር ለፍጡር አይቻለውም የሚለውን እውነት አምኖ መቀበል ነው። ሁሉን ቻይነት/Omnipotence/ ከእግዚአብሔር በቀር ለማን ይቻለዋል? ለማንም!!

«ከማኅፀን የሠራህ፥ የሚቤዥህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ሁሉን የፈጠርሁ፥ ሰማያትን ለብቻዬ የዘረጋሁ ምድርንም ያጸናሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ ከእኔ ጋር ማን ነበረ?» ኢሳ 44፤24

በላይ በሰማይ፤ በታች በምድር በሁሉም ሥፍራ ያለና የሚኖር፤ የሚሰማም፤ መልስ የሚሰጥም እግዚአብሔር ብቻ ነው።
ቅዱሳን መላእክት ይሁኑ ቅዱሳን ሰዎች በሰማይ ሥፍራቸው ሳሉ በምድር የሚደረገውን ሁሉ ያውቃሉ? ያያሉ? ይሰማሉ? በፍጹም አያውቁም፤ አያዩም፤ አይሰሙም።  በሰማይ ሳሉ በምድር ያለውንም የሚያውቁ ከሆነ በስፍሐትና በምልዓት ይገኛሉ ማለት ነው። ይህ ደግሞ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ያለ ስህተት ነው። ከላይ ለመግለጥ እንደተሞከረው በአንድ ጊዜ በሁሉም ስፍራ የመገኘትን ብቃት የፈጣሪ እንጂ የፍጡራን እንዳልሆነ የገለጽነውን እውነታ የሚጻረር ይሆናል።  

2/ «እግዚአብሔር ብቻውን በሁሉ ሥፍራ አለ» የምንለው ለምንድነው?

መልሱ አጭር ነው። እግዚአብሔር በላይ በሰማይ፤ በታች በምድርም፤ በሁሉ ሥፍራ መገኘት የሚችለው በላይ በሰማይ ይሁን በታች በምድር ላለው ነገር ሁሉ ፈጣሪና አስገኚ ስለሆነ ነው።
 ከባዶነት ወደአንድ ነገርነት ማምጣት የቻለ ፈጣሪ፤ በፈጠረው ነገር ሊገደብ፤ ሊወሰን፤ ሊከለከል አይችልም። ፍጥረታት ግን በዚህ ብቃት ውስጥ ሊገቡ አይችሉም። ምክንያቱም ፍጥረታት በቦታ፤ በሁኔታና በአፈጣጠር ውሱን ስለሆኑና ከፈጣራቸው እግዚአብሔር ጋር ሊስተካከሉ ስለማይችሉ ነው። የቅዱሳን መላእክትና የቅዱሳን ሰዎች ብቃት እግዚአብሔር በሰጣቸው መጠንና ፈቃድ የተወሰነ ነው።  መላእክቱ ይሁኑ ሰዎች ፍጡር እንጂ ፈጣሪዎች ባለመሆናቸው ፍጥረተ ዓለም ይወስናቸዋል። እግዚአብሔር ግን እንዲህ አይደለም። በትንቢተ ዳንኤል ላይ እንዲህ እንደተመለከተው፤
«በምድርም የሚኖሩ ሁሉ እንደ ምናምን ይቈጠራሉ፤ በሰማይም ሠራዊት በምድርም ላይ በሚኖሩ መካከል እንደ ፈቃዱ ያደርጋል፤ እጁንም የሚከለክላት ወይም ምን ታደርጋለህ? የሚለው የለም» ዳን 4፤35

3/ የቅዱሳን መላእክት ውሱንነትና በስፍሐት አለመገኘት

እያየን በመጣነው ከእግዚአብሔር ስፉሕነትና ከፍጥረታት ውሱንነት የተነሳ መላእክት በምልዐት በሰማይም በምድርም ሊገኙ እንደማይችሉ  እናምናለን። ነገር ግን ከላይ የገለጽነውን ጉዳይ ዳግም ማንሳት ያስፈለገን ዐቢይ ምክንያት ብዙ ሰዎች የመላእክትን ውሱን መሆን፤ በሁሉ ሥፍራ በአንድ ጊዜ አለመገኘት አምነው ሲያበቁ  ከዚህ ተቃራኒ በሆነ አቋም  ቅዱሳን መላእክት በአንድ ጊዜ በሰማይና በምድር የመገኘት ብቃት እንዳላቸው የሚያስተምሩና አምነው የሚያሳምኑ  ሰዎች በመኖራቸው  ነው። 

   ሰው በአንድ ጊዜ አማኝም፤ ከሀዲም መሆን አይችልም። ምክንያቱም  ጣፋጭ ፍሬ የሚሰጥ ዛፍ ፤ በጭራሽ መራራና ጣፋጭ ፍሬ በአንድ ጊዜ ማፍራት እንደማይቻለው ሁሉ በእምነት የቅዱሳን መላእክትንም ሆነ የቅዱሳን ሰዎችን የውሱንነት ተፈጥሮ ካመንን በኋላ በምንም ዓይነት መንገድ ከዚህ በተጻራሪ መቆም ስለማይቻለን ነው።
ብዙ ጊዜ ሰዎች አምኛለሁ ባሉበት እምነት ውስጥ ክህደት መሰል ነገር የለም ብለው የሚከራከሩት ስላመኑት እምነት በቂ እውቀትና ግንዛቤ ስለሌላቸው ነው። ለዚህ ጥሩ አብነት የሚሆነን ነጥብ፤ በአንድ ወቅት ሰዱቃውያን ወደ ጌታችን፤ አምላካችንና መድኃኒታችን  ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርበው ትንሣኤ ሙታንን ለመቃወም «በምድር ሰባት ባል ያገባች ሴት በሰማይ ለማንኛቸው ትሆናለች?» ብለው በጠየቁት ጊዜ የሰጣቸው መልስ  በየትኛውም ዘመንና ጊዜ ለሚነሳ ጥያቄ እንደአስረጂ አቅርበን እዚህ ላይ ብንጠቅሰው ተገቢ ይመስለናል።
«ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ መጻሕፍትንና የእግዚአብሔርን ኃይል አታውቁምና ትስታላችሁ» ማቴ 22፤29 አላቸው።

  እግዚአብሔርን የሙታን ብቻ አምላክ አድርጎ መንሥኤ ኃይሉን መካድ ከባድ ስህተት ነው። መጻሕፍት የሕያዋን አምላክ ብለው ሲመሰክሩ ይህንንም አለማወቅ ስንፍና ነው። ለዚህ ሁሉ ምክንያቱ አንድ ነው።
  ሰዎች «እናምንበታለን» ባሉት ነገር ውስጥ የሚገቡ ስህተቶች ሁሉ ተቀባይነት አግኝተው ሃይማኖታዊ ካባን የሚላበሱት «መጻሕፍቱንና የእግዚአብሔርን ኃይል» በደንብ ካለመረዳታቸው በሚመጣ ጉድለት እንደሆነ ሁሉ፤ በዚህም ዘመን ያሉ ስህተቶችን እንዲሁ እንገነዘባቸዋለን።  ሰዱቃውያን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በእጃቸው ይዘው ሲያበቁ ስለትንሣኤ ሙታን አለመኖር አምነው መቀመጣቸው ላያስገርም ይችላል። ምክንያቱም ሰዎች የእግዚአብሔር ኃይል መገለጫ መንገዶችን ወደሚናገሩ ወደ ቅዱሳት መጻሕፍቱ ይሄዳሉ እንጂ መጻሕፍቱ ወደሰዎቹ ሊመጡ አይችሉም ነው።  በእጃቸው ያለው መጻሕፍትማ  የሚሉት እንደዚህ ነበር።

«ስለ ትንሣኤ ሙታን ግን እኔ የአብርሃም አምላክ፥ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ ነኝ የሚል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እናንተ የተባለውን አላነበባችሁምን? የሕያዋን አምላክ ነው እንጂ የሙታን አይደለም»  እያለ እውነቱን ቢናገርም እያየበቡ ስለማያስተውሉ የትንሣውን ኃይል ክደዋል (ማቴ 22-31-32 ፤  ዘጸ 3፤6 )

ሰዱቃውያኑ ከተቀበሏቸው መጻሕፍት ውስጥ የተጻፈውን አለማወቃቸው የሚያስረዳን ነገር መጻሕፍትን በመያዝ ወይም በማንበብ  እውነት ሁልጊዜ ይገለጣል ማለት አይደለም።  መረዳቱ ካላቸው ሰዎችም ዘንድ ለኛ ያልተገለጠን እውነት ስለሚኖር ሌሎችን በመጠየቅ ወይም የሚሉትን በማስተዋልና እንደእግዚአብሔር ቃል በመመርመር ወዳልደረስንበት እውነት ልንደርስ እንችላለን። እንደዚሁ ሁሉ በዚህ ዘመንም ያሉ ሰዎች የቅዱሳን መላእክትንንና የቅዱሳን ሰዎችን ውሱንነትና በምልዐት ያለመገኘት ተፈጥሮ አምነው ሲያበቁ በተግባር ግን ከዚህ አስተሳሰብ በተቃራኒ ቆመው የመገኘታቸው ነገር በመጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነታ ውስጥ ለመኖር ካለመቻል የመጣ እክል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። 

4/ በሰማይ ሥፍራ ያሉ ቅዱሳን በዓለመ ምልዓትይገኛሉን?

ፍጡራን ውሱንና በሁሉ ሥፍራ የመገኘት ብቃት እንደሌላቸው ከላይ በተደጋጋሚ ለማሳየት በሞከርነው ላይ ካመንን በዓለማት ሁሉ በምልዓት ሊገኙ አይችሉም ብለን ደፍረን መናገር እንችላለን። እንደመላእክቱ ሁሉ ቅዱሳን ሰዎች በተወሰነ ሥፍራ፤ በተወሰነ  መጠንና  በተፈቀደላቸው ዓለም የሚኖሩ እንጂ ምሉዕ በኵለኄ ስላይደሉ እንደፈጣሪ ሁሉን አዋቂነት የላቸውም ብንልም ስህተት አይደለም። ከዚህ በተለየ አስተሳሰብ ላይ ከሆንን ደግሞ ሊሆን የሚችለው ነገር ሁሉን ቻይ በሆነው በእግዚአብሔር ኃይልና ፍጡር በሆነው ፍጥረት መካከል ያለውን ልዩነት አለመረዳት ስለሚሆን እምነቱ በክህደት የተሞላ ይሆናል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የፈጣሪን ኃይል ለፍጡራን ከመስጠት የበለጠ ክህደት የለም። እግዚአብሔርን የሚመስል ምንም ነገር ሊኖር አይችልምና።

«አቤቱ የእስራኤል አምላክ ሆይ፥ በሰማይ ወይም በምድር አንተን የሚመስል አምላክ የለም፤ በፍጹም ልባቸው በፊትህ ለሚሄዱ ባሪያዎችህ ቃል ኪዳንንና ምሕረትን የምትጠብቅ» 2ኛ ዜና 6፤14

መላእክት ቅዱሳን በመሆናቸው ወይም ቅዱሳን ሰዎች አምላካቸው ስላከበራቸው እግዚአብሔርን የሚመስል ባህርይ እንዳላቸው አድርጎ ማሰብ  አስነዋሪ ነገር ነው። ቅዱሳን በዓለመ ሥጋ ሳሉ ወይም በዓለመ መላእክት የሚገኙ መላእክት የሚሠሩት ሥራ በእግዚአብሔር ፈቃድና በተሰጣቸው ጸጋ ይወሰናል። በዚህ ምድር የሚኖሩ ቅዱሳን ሙት ቢያስነሱ፤ ደዌ ቢፈውሱ ከተሰጣቸው ጸጋ አኳያ እንጂ በተፈጥሮ ካላቸው ብቃት የተነሳ አይደለም።  በዚያም ጸጋ ቢሆን የሚመሰገነውና ሊመሰገን የተገባው የጸጋው ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ ነው። ቅዱሳኑን ማክበር አንድ ነገር ነው፤ ነገር ግን በማክበር ሽፋን ወይም እግዚአብሔር በነሱ በኩል በሠራው አስደናቂ ነገር የተነሳ ለእነሱ ምሥጋናና ውዳሴ እንድንሰጥ የሚያደርገን አንዳችም መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ የለም። ጸጋ ማለት እግዚአብሔር በወደደው መንገድ የራሱን ሥራ የሚሠራበት ኃይል እንጂ ሠራተኞቹ ይመሰገኑበት ዘንድ የተሰጠ የውዳሴያቸው መሣሪያ አይደለም።

«አሁንም ጸጋን ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔርን ለምኑ፤ ይህ ከእጃችሁ የተሰጠ ሲሆን ከቶ ፊታችሁን ይቀበላልን? ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር» ሚል 1፤9

ጸጋ የሚሰጥ፤ የሚከለከል ኃይል ነው። ጸጋ ሰጪው በፈቀደው መጠን ለፈቀደው ጉዳይ የሚሰራበት መንገድ እንጂ ወሰን የሌለውና ሁሉን ለማድረግ ክበበ ተፈጥሮን አልፎ የሚሄድ ምሉዕ ኃይል ያለው ማለት አይደለም።

«እንደ ተሰጠንም ጸጋ ልዩ ልዩ ስጦታ አለን» ሮሜ 12፤6


«ሐዋርያትም የጌታን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በታላቅ ኃይል ይመሰክሩ ነበር፤ በሁሉም ላይ ታላቅ ጸጋ ነበረባቸው» የሐዋ 4፤33

በአንድ ወቅት ሐዋርያው ጳውሎስ ልስጥራን በሚባል ሀገር በገባ ጊዜ በልስጥራን የተባለ ከልጅነቱ ጀምሮ እግሩ ሽባ የሆነና የሰለለ ሰው አግኝቶ በኢየሱስ ስም ከፈወሰው በኋላ  አማልክት ከሰማይ ወርደዋል ብለው ሲያበቁ ሕዝቡና የድያ ካህን ኮርማ ሊሰዋላቸው ፈለገ። ጳውሎስና በርናባስ ግን ልብሳቸውን ቀደው እንዲህ አሉ።

«እንዲህም አሉ። እናንተ ሰዎች፥ ይህን ስለ ምን ታደርጋላችሁ? እኛ ደግሞ እንደ እናንተ የምንሰማ ሰዎች ነን፥ ከዚህም ከንቱ ነገር ሰማይንና ምድርን ባሕርንም በእነርሱም ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር ትሉ ዘንድ ወንጌልን እንሰብካለን» የሐዋ 14፤14-15

የቅዱሳን መላእክትም ይሁን የቅዱሳን ሰዎች ዋና የእምነታቸው ማእከል ራሳቸውን በምሥጋናውና በተሠራው ቦታ ማስቀመጥ ሳይሆን እግዚአብሔር በእነሱ በኩል እንዲከብር ማድረግ ነው።  ከጳውሎስ ተአምራት የተማርነው ነገር ተአምራቱን የሠራው ጳውሎስ ሳይሆን መክበር ያለበት የተአምራቱ ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ እንዲከብር ሰዎች ሁሉ ዓይናቸውን በእግዚአብሔር ላይ እንዲጥሉ በኃይለ ቃል ሲናገራቸው የምናነበውም ለዚህ ነው።

5/ በሰማያት ሥፍራ ያሉ ቅዱሳኑ መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች የሰዎችን ልመናና ጸሎት ሰምተው ምላሽ ሊሰጡ ይችላሉን?

የቅዱሳኑን ውሱንነትና በምልዓት ያለመገኘት ብቃት መመልከት ያስፈለገን ከዚህ በታች ለምናቀርባቸው ጭብጦች ገላጭ አስረጂ እንዲሆኑን ከመፈለግ የተነሳ ነው። ውሱንነትና በምልዓት አለመገኘት ማለት ከታች ለሚነሱት ነጥቦች መልስ ይሰጡናል።
እዚህ ላይ ሁለት የተለያዩ ነጥቦችን ልናነሳ እንገደዳለን። አንደኛው ቅዱሳን መላእክት በሰማያት ባለ የምሥጋና ዓለም እያሉ በምድር የሚደረገውን ነገር ሁሉ ያውቃሉ ወይ? የሚለውንና በገነት ያሉ ቅዱሳን በምድር የሚደረገውን ሁሉ ማየት ወይም መስማት ይችላሉ ወይ? የሚለውን ነጥብ ለይቶ መመልከት ተገቢ ነው።
 ከቅዱሳን መላእክትና ከቅዱሳን ሰዎች ተፈጥሮ የተነሳ በምልዐት ያለመገኘትን ጉድለት የተነሳ በገነት ወይም በዓለመ መላእክት ያሉ ቅዱሳን በዚህ ክበበ ዓለም ያለውን ነገር ሁሉ በአንዴ ሰምተው፤ በአንዴ አውቀው፤ ምላሽ ሊሰጡ አይችሉም። በወሰነ ነፍሳዊ አካል በገነት ሳሉ በዚህ ምድርም የመገኘት ብቃት የሌላቸው ከመሆኑም ባሻገር በተፈጥሮአቸውም  በገነት ሳሉ  በምድር ያሉ ሰዎችን ጸሎት በብቃት በመስማት ምላሽ ለመስጠት  ስላይደለ የሁሉን አዋቂነትና ሰሚነት ችሎታ የላቸውምና በምድር ላይ ሆነን በገነት ይሰሙናል ልንል የተገባ አይደለም። ይህን የማድረግ ባህርይ የእግዚአብሔር የብቻው ነው። 

   በዚህች ባለንባት ምድር በየትኛውም ማእዘነ ዓለም በስማቸው የሚደረገን ልመና በገነት ሳሉ ይሰማሉ ማለት ፈጣሪ ናቸው ብሎ በክህደት አዘቅት ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱሳን መላእክትን እግዚአብሔር ለፈለገው ዓላማ ሲልካቸው ወይም እንዲገኙ በተሰወነላቸው ሥፍራ ከመገኘት በስተቀር በፈቃዳቸው ወይም ሰዎች ስለጠሯቸው እንደፍላጎታቸው ሊሄዱ አይችሉም፤ ያልተወሰነ የመስማት ብቃትም የላቸውም።  በኢጣሊቄ ይኖር ለነበረ ጭፍራ፤ የመቶ አለቃ የሆነው ቆርኔሌዎስ ጸሎቱና ምጽዋቱ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተወደደ ስሙ ያልተገለጸ የእግዚአብሔር መልአክ በተልእኰ መጥቶ መልእክት ማድረሱንና ማድረግ ስለሚገባው ነገር ሲናገረው እናነባለን።

እዚህ ላይ ሊሠመርበት የሚገባቸው ነጥቦች ሦስት ናቸው።

ሀ/ የመልአኩ ድርሻ  ማንነቱን ማስተዋወቅ ወይም የራሱን ሃሳብ መግለጽ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላለፈውን መልእክት ማስረዳት ብቻ ነው። ከነበረበት ሰማያዊ ሥፍራም በተልእኰ ወደቆርኔሌዎስ ሲሄድ የነበረበትን ዓለመ መላእክት ለቆ ይወርዳል እንጂ በስፍሐት በነበረበት ቦታም በተመሳሳይ ሁኔታ ሊገኝ አይችልም። መውጣትና መውረድ ያስፈለገውም ለዚህ ነው።
ለ/ መልአኩ ከቆርኔሌዎስ ቤት የተገኘው መልአኩ በስሙ ስለተደረገው ጸሎትና ምጽዋት ምላሽ ሊከፍለው መምጣቱን ለመንገር ሳይሆን ቆርኔሌዎስ በአምላኩ ስም ያደረገው ነገር በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ማግኘቱን  በመግለጽ የእግዚአብሔር መልእክት ለማድረስ ብቻ ነው።
ሐ/ በዚህ ሥፍራ ስሙ ያልተገለጸውን የመልአክ ስም በምትሃት ጠቅሰን በመናገር መልእክት አድራሽነቱን እንደባለቤት ቆጥረን እንድናመሰግነው የሚያደርገን አንዳች ነገር የለም።

 ይሁን እንጂ በዘጸአተ እስራኤል ታሪክ ላይ ያልተገለጸው መልአክ፤ ሚካኤል እንደመራቸው ተደርጎ የተጠራውና በትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ውስጥ እንደተመለከተውም፤ ሠለስቱ ደቂቅን ከእቶን እሳት ያዳናቸው፤  እግዚአብሔር ባወቀ ያልገለጸውን የመልአክ ስም በመስጠት ሚካኤልና ገብርኤል ናቸው እያሉ የስህተት ትምህርቶች ምሥጋናውን ሁሉ  ከእግዚአብሔር ላይ ለመውሰድ የተደረገ ትግል ከመሆን አያልፍም። በእግዚአብሔር ሥፍራ ላልተገለጹ መላእክት ክብርና ምስጋናን በመስጠት እግዚአብሔርን ማስቀናት የጠላት ሴራ ውጤት ነው። በእርግጥም ይህንን የሚያደርገው ሰይጣን ነው።  ምክንያቱም በቅዱሳን መላእክት ስም ተሸሽጎ ሰዎችን ከእግዚአብሔር ፈቃድ ለማስወጣት የብርሃን መልአክ ነኝ ቢል ማስመሰል የቆየ ተግባሩ ነው።  በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ  ሳይገልጽ በዝምታ ያለፈውን ነገር እንዳለ ለሱ በመስጠት በዝምታ እንደመተው የመሰለ ማለፊያ እውቀት የለም።

   እንደዚሁ ሁሉ ወደቆርኔሌዎስ የተላከውን መልአከ ማንነት እግዚአብሔር ብቻ ባወቀው ሁኔታ ስላልተገለጸ ከዝምታ ባለፈ ወደስም ገላጭነት የሚያሸጋግረን ምክንያት የለም። «እንደአናንያ፤ እንደአዛርያ፤ እንደሚሳኤል፤ አድነን ገብርኤል» እንድንል የሚያደርገን ከመጽሐፉ ባለቤትም የተሻለ እውነት እኛ ዘንድ የለም።
ስለሆነም ቅዱሳን መላእክቱ ሰዎች ወደእግዚአብሔር በሚያቀርቡት ልመናና ጸሎት ወይም እግዚአብሔር እንዲራዱ፤ እንዲታደጉ ሲልካቸው በትእዛዝ ብቻ ተልእኰአቸውን ለመፈጸም ከሚመጡ በስተቀር ሰዎች ስማቸውን ስለጠሩ፤ በስማቸውም ስለተማጸኑ፤ ለዚያ የሚሆን ዋጋ ለመስጠት ደስ ተሰኝተው፤ ላደረጉትም ትድግና ምስጋና ለመቀበል ሽተው በጭራሽ አይመጡም። ምክንያታችንም ከላይ ስንገልጽ እንደመጣነው መላእክቱም ይሁኑ ቅዱሳኑ በሰማይ ሳሉ በምድር ላይ በስማቸው የተደረገውን የሰዎችን ሁሉ ልመና መስማት፤ መቀበልና ምላሽ የመስጠት ብቃት ስለሌላቸው ነው። በምልዓት ተገኝቶ የመስማትና ጸሎት የመቀበል ችሎታ የእግዚአብሔር ብቻ ስለሆነ!!

ክፍል ሁለት ይቀጥላል ….

Sunday, January 11, 2015

ግን የምር ምን ዓይነት ትውልድ እያፈራን ነው?

(ደጀ ብርሃን፤ 3/5/2007)
ይህን  ጽሁፍ ለሚያስተውለው አስደንጋጭ የዘመኑ እውነት ነው። በየስርቻው በስመ ጸሎት ቤት የሚደረገውና የሚፈጸም ስንት ጉድ አለ? የተቀደሰ ውሃ፤ የተቀደሰ ጨርቅ፤ የተቀደሰ መጽሐፍ፤ የተቀደሰ ፓስፖርት፤ የተቀደሰ ዘይት ኧረ ስንቱ በስመ «የተቀደሰ» ይቸበቸባል? አንድ ቤተ ክርስቲያን በምእመናን ጉባዔ የማትመራ ከሆነና በአንድ ፓስተር ወይም ቄስ ስም በፈቃድ የተመዘገበች ከሆነች የግል ሱቅ ትባላለች እንጂ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ልትባል አትችልም። በዘመነ ሐዋርያት በግል የተመዘገበች ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን አልነበረችምና ነው። ሩኒ ከሚባል የማንቸስተር ዩናይትድ እግር ኳስ ተጫዋች ደመወዝ ጋር ራሳቸውን እያስተያዩ እነሱ ሰይጣንን በማስወጣታቸው 70 ሺህ ብር ደመወዝ ወይም 80 ሚሊየን ብር በባንክ አካውንታቸው ውስጥ መገኘቱ እንደማያስገርም ሲናገሩ ትንሽ አይሰቀጥጣቸውም። ደመወዝ ማግኘት አንድ ጉዳይ ነው። ሰይጣንን ለምናስወጣ ለእኛ ግን ይህ ትንሽ ገንዘብ ነው ማለት ደግሞ ሌላ ነው። በዚህ ጉዳይ ሌላ ጊዜ እንመለስበታለን። ለዛሬ ግን ከወደ ኬንያ የተገኘውን መረጃ እናካፍላችሁ!

ከዮናስ ሓጎስ ናይሮቢ
#‎አቋራጭ_የለመደ_ትውልድ‬
ልብወለድ…………………………ቢሆን ደስ ባለኝ ነበረ…
አዳራሹ ጢም ብሎ በመሙላቱ መግባት ያልቻሉ በሺህ የሚቆጠሩ «ምዕመናን» በር ላይ ከተመደቡ አስተናጋጆች ጋር ዱላ ቀረሽ ፀብ ላይ ናቸው። አስተናጋጆቹ ግን በተረጋጋ መንፈስ አዳራሹ ውስጥ የሚካሄደው ነገር ሁሉ በአዳራሹ ዙርያ በተተከሉ 80" ቴሌቨዢኖች በቀጥታ እንደሚተላለፍ ሕዝቡን ለማሳመን እየወተወቱ ነው።
ከአዳራሹ በር በስተቀኝ ያለ አንድ ሱቅ የሚመስል መስኮት ጋር በእጃቸው ብር ይዘው የሚያውለበልቡ ሰዎች ወርረዉታል። ፓስተር ኪኛሪ የፀለየበት ነው የተባለ «ቅዱስ» ውኃ እና እንደ መቁጠርያ የመሰለ ነገር እያንዳንዳቸው በ2000 ሽልንግ (400 ብር) እየተሸጡ ነው። ምንም እንኳ ሻጮቹ በብዛት እንዳለና እንደማያልቅ ለማሳመን ቢጥሩም ሕዝቡ እነርሱን መስሚያ ጆሮ ያለው አይመስልም
አዳራሹ ውስጥ ፕሮግራሙ ተጀምሯል። ፓስተር ኪኛሪ «መንፈስ ቅዱስ» በገለጠለት መሰረት ከሕዝቡ መሐል መርጦ ያወጣቸውን ለዕለቱ እንዲድኑ የተመረጡ ሰዎችን በሰልፍ መድረኩ ላይ ደርድሯቸዋል።
አንዱ አስተናጋጅ በእጅ ማስታጠቢያ ጎድጓዳ ሳህን ውኃ ይዞ ወደ መድረኩ ወጣና እጃቸውን ነክረው እንዲታጠቡ ትዕዛዝ ሰጠ። «የተመረጡት» እጃቸውን ሲታጠቡ አጁን ዉኃው ውስጥ በመጨመር እጃቸውን እየፈተገ ማጠብ ጀመረ። ፓስተሩ አሁንም በከፍተኛ ድምፅ ፀሎት እያደረሰ ነው።
በድንገት ማስታጠቢያው ውስጥ ያለው ውኃ እየቀላ እየቀላ ሄደና ደም መሰለ። የምትታጠበዋ ሴትዮ እጇን ከማስታጠቢያው መንጭቃ ለማውጣት ብትሞክርም አስተናጋጁ ጭምቅ አድርጎ በመያዝ አረጋጋት…
«ኃጥያትሽ፣ በሽታሽ፣ መርገምሽና ልክፍትሽ ሁሉ በዚህ ደም አማካይነት ከሰውነትሽ ወጥቷልና ደስ ይበልሽ!» አላት አስተናጋጁ።
ተረጋጋች!
ወድያውኑ በቅፅበት አስተናጋጁ ፈንጠር ብሎ «ፓስተር ፓስተር ና ተመልከት!!» ሲል በከፍተኛ ድምፅ ተጣራ።
ፓስተሩ ማይክራፎኑን ይዞ ወደ አስተናጋጁ ሲጠጋ ካሜራውም ተከተለው
«አየህ ከእጇ የወጣውን!» ሲል ትናንሽ መርፌዎች ከማስታጠቢያው ውስጥ አውጥቶ አሳየው።
«ኃሌሉያ!!!» ሲል ፓስተሩ አዲስ ሳይንሳዊ ግኝት እንዳገኘ ሁሉ ጮኸ። «አስማትና ድግምት ተደርጎብሽ ነበረ። ዛሬ ድነሻል! ፈጣሪ ይባረክ! ዛሬ ከእስራትሽ ነፃ ወጥተሻል!!» ሲል ጮኸ።
ከሰውነቷ መርፌ መውጣቱ የምር ያስደነገጣት ሴት መብረክረክ ስትጀምር አስተናጋጆቹ ደገፏት።
መድረኩ ላይ ያሉት «ዛሬ ለመዳን የተመረጡ ሰዎች በተራ በተራ ከአስማትና ድግምታቸው ተፈትተው ከአዳራሹ ጀርባ ወዳለ ክፍል በተራ ተራ ተወሰዱ።
በመሐል በመሐል በሚደረግ ዕረፍት ላይ የሚተላለፍ ማስታወቂያ አለ።
«ፍቅር ፣ ስራ ፣ ገንዘብ ማጣት አስቸግሮዎታል? ፓስተር ኪኛሪ ሊፀልይሎት ዝግጁ ነው!! አሁኑኑ በሞባይል ገንዘብ መላኪያ 310 ሽልንግ (60 ብር) ወደ ቁጥር ----------- ይላኩና ሁሉን ነገር በእጅዎ ያስገቡ!! ፓስተር ኪኛሪ የፀለየባቸው ውኃ እና መቁጠርያ በመሸጥ ላይ ናቸውና ፈጥነው ይግዙ!!!»
ኃጥያታቸው የተሰረየላቸው ሰዎችም ወደ አዳራሹ ጀርባ ካመሩ በኋላ ኪሳቸውን ሲዳብሱ ይታይ ነበረ።
**************************************************************
ምሽት ላይ የ KTN Investigative journalist JICHO PEVU በተሰኘ ታዋቂ ፕሮግራሙ ስለ ፓስተር ኪኛሪ አቀረበ።
ጋዜጠኛው በዘገባው ፓስተር ኪኛሪ ሕዝቡን እንዴት እንደሚያጭበረብር ወለል አድርጎ አሳየ። አስተናጋጆቹ እጃቸውን ፖታሲየም ተቀብተው በጣቶቻቸው መሐል መርፌ ይዘው በመግባት (ፖታሲየም ውሃ ጋር ሲቀላቀል ቀይ ከለር ይይዛል) ከዛም ባሻገር የእግዚአብሔር ስብከት አሰራጭበታለሁ በሚልበት ሬድዮ ፕሮግራም ላይ የተለያዩ ሐሰተኛ ምስክርነት የሚሰጡ ሰዎችን በገንዘብ እያማለለ እንደሚያቀርብ ተገለፀ። ለማስረጃነት ያህልም አንድ ከዚህ በፊት በፓስተሩ ፀሎት ከኤድስ በሽታ ድኛለሁ ብሎ ሁለት ፖዘቲቭና ኔጋቲቭ የሆነባቸውን የሐኪም ማስረጃ ያቀረበ ግለሰብ መጀመርያውኑም ኤድስ እንዳልያዘውና ፖዘቲቭነቱን የሚያሳየው መረጃ በዘገባው ላይ ቀረበ።
በማግስቱ የኬንያ ጋዜጠኞች ፓስተሩን ኢንተርቪው ለማድረግ ቢሯሯጡም አልተሳካላቸውም። በሁለተኛው ቀን ላይ አንዱ ዕድለኛ ጋዜጠኛ ፓስተሩ ምሳውን ከአንድ ሆቴል በልቶ ሲወጣ አገኘው።
«ፓስተር፤ በ JICHO PEVU ስለቀረበብህ ውንጀላ ምን ትላለህ?»
«ውንጀላ? ኧረ እኔ አልሰማሁም…»
«ከሕዝብ እፀልይላችኋለሁ እያልክ በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብ አካብታሃል ይባላል…»
«ስማኝ ወንድም!!» አለ መኪናው ጋር የደረሰው ፓስተር ለጋዜጠኛው መኪናውን እያሳየው። «እንዲህ ዓይነት መኪና በነፃ ይገኛል እንዴ ታድያ?»
ይሄው ምላሹም በቴሌቪዥን ተላለፈ።
በቀጣዩ እሁድ ፓስተር ኪኛሪ የሚሰብክበት አዳራሽ በብዛቱ ከባለፈው የበለጠ ሕዝብ ተገኘ። አሁንም ድረስ ፓስተሩ የስብከት አገልግሎት እየሰጠ ነው።
እኛም ሐገር ሚሌኒየም አዳራሽን ጢም ብሎ እንዲሞላ ያደረገ በግል ጄት የሚሄድ ፓስተር መጥቶ ሕዝቤን «የተቀደሰ ውኃ» ለመግዛት እርስ በርሱ ሲራገጥ ውሎ ነበር አሉ ባለፈው ሰሞን…
ለነገሩ የአባባ ታምራትን ሽንት ከፍሎ የጠጣ ሕብረተሰብ ለተቀደሰ ውሃ ቢከፍል ምኑ ይገርማል?
አሁን ሰሞን ደግሞ በ350 ብር ገነትን እና ሲዖልን በ preview ለማየት ሕዝቤ እየተጋፋ ነው አሉኝ…
በሕይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ልጆች ባለመውለዴ ተደስቻለሁ!!

Tuesday, December 30, 2014

አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋዩ ማነው?



     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ስንት ጠንቅዋይ እንዳለ ሰፊ ጥናት ተደርጎ ነበር። በተገኘው ጥናት የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ቁጥሩ እጅግ አስደንጋጭ ነው። ጥንቆላን መደበኛ ሥራቸው አድርገው ባለጉዳይ አዲስ አበቤዎችን በማስተናገድ ላይ የተሰማሩ 4000 /አራት ሺህ/ ገደማ ጠንቅዋዮች መኖራቸውን የተደረገው የዳሰሳ ጥናት ያረጋግጣል። 4000 ሺህ ገደማ ጠንቅዋይ በአዲስ አበባ ብቻ መገኘቱ እግዚኦ መሐረነ! የሚያሰኝ ነው። በመላ ሀገሪቱ በአጠቃላይ ቢጠናማ ሚሊዮን ጠንቅዋዮች ይኖራሉ ማለት ነው።
  አንዳንዶች «ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ናት» ሲሉ አያፍሩም። ቀላል ቁጥር የማይባለውን ጠንቅዋይ ስንመለከት ለጠንቋዮቹስ ደሴት የማትሆንበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ደግሞም በተደረገው ጥናት እንደተመለከተው አብዛኛዎቹ ጠንቋዮች ክርስቲያን ነን ባዮች ናቸው። ስለዚህ «የክርስቲያን ደሴት ናት» ባዮች ጠንቋይ ክርስቲያኖችንም ጨምረው ከሆነ አባባላቸው እውነትነት ሊኖረው ይችላል። ነገር ግን ክርስቲያን መሆን ማለት ምን ማለት ነው? በሚለው ጉዳይ ላይ ጥያቄን ያስነሳል።  ጠንቅዋይ ክርስቲያኖች በሞሉባትና ክርስቲያን ነን የሚሉ የጠንቅዋይ አገልግሎት ተጠቃሚዎች በበዙባት ኢትዮጵያክርስትናና የክርስትና ደሴት ማለት ከስም ባለፈ ትርጉም የለውም ማለት ነው። በአጭር ቃል ክርስትና ተነገረባት እንጂ አልተኖረባትም ማለት ነው።
ያልተኖረበት ክርስትና ደግሞ ሙት ነው።

«በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው» ኤፌ 2፤1-2

ሐዋርያው ጳውሎስና በርናባስ በቆጵሮስ ደሴት ጫፍ ላይ ወደምትገኝ ጳፉ/ ፓፎስ/ ከተማ በገቡ ጊዜ በርያሱስ የሚባል አንድ አይሁዳዊ ጠንቅዋይና ሐሰተኛ ነብይ አግኝተው ነበር። /የሐዋ 13፤6 / ይህ በርያሱስ /1/  የተባለው ሰው በሃይማኖት አይሁዳዊ በተግባሩ ግን ጠንቅዋይ ነው።  ይህ ሰው የሚያሳስተው የአገሩን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የሚመራ አገረ ገዢውን ጭምር ነበር።  በጠንቅዋይ የጥንቆላ ጥበብ የምትመራ አገር ምን ልትመስል እንደምትችል ለመገመት አይከብድም።  በሌላ ስምም «ኤልማስ» /2/ የተባለው ይህ ጠንቅዋይ አገረ ገዡን መቆጣጠር ማለት አገሪቱን በራሱ የመንፈስ ግዛት ስር ማስተዳደር ማለት በመሆኑ  የጳውሎስንና የበርናባስን የወንጌል ስብከት እንዳይሰማ አጥብቆ ሲቃወም እናያለን።  መንፈሱ እንዳይገለጥና እውነት እንዳይታወቅ አጥብቆ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ ሕዝቡን በመንፈሱ ባርነት ስር ከማስገባት ባሻገር መሪዎችንም አጥምዶ መያዝ ዋና ሥራው ነው። መሪዎች የያዙት ወንበር በሥራቸው ባለው ሕዝብ ላይ የሚፈልገውን ተጽዕኖ ለማሳረፍ እንደሚጠቅመው አሳምሮ ያውቃል። ልክ ማኅበረ ቅዱሳን የሲኖዶስ አባላት የሆኑ ጳጳሳትን በራሱ ፈቃድ ስር መቆጣጠር ማለት የሲኖዶስን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት እንደሆነ ገብቶት እንደሚሰራው ማለት ነው። የሲኖዶሱን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መቆጣጠር ማለት ነው።

 ይህ በርያሱስ በተባለው ሰው ላይ ያደረው የጥንቆላ መንፈስ  አገረ ገዢው ወደነጳውሎስ የእውነት ቃል ልቡን እንዳይመልስ አጥብቆ በተቃወመ ጊዜ «ጳውሎስ የተባለው ሳውል ግን በመንፈስ ቅዱስ ትኩር ብሎ ተመለከተውና አንተ ተንኰል ሁሉ ክፋትም ሁሉ የሞላብህ፥ የዲያብሎስ ልጅ፥ የጽድቅም ሁሉ ጠላት፥ የቀናውን የጌታን መንገድ ከማጣመም አታርፍምን?» ሲለው እንመለከታለን።( የሐዋ 13፤10 )

    ስለሆነም ጠንቅ ዋዮችና አሰተኛ ነብያት ሁሉ ተንኰልና ክፋት የሞላባቸው፤ የዲያብሎስም ልጆች፤ የጽድቅ ሁሉ ጠላት፤ ቀናውን የጌታን መንገድ የሚያጣምሙ ናቸው እንጂ ክርስቲያን በመሆናቸው ወይም በመሰኘታቸው ወይም ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች በግልጥም በስውርም የእነሱን አገልግሎት ተጠቃሚዎች ሁሉ የሚባሉት ክርስቲያን ሳይሆን የክፋቱ መንፈስ ተካፋዮች ነው።  እንዲያውም ከአሳቹና ከተቃዋሚው መንፈስ አገልግሎት ማግኘት አይደለም! ሰላም የሚላቸው ቢኖር ከክፉ ሥራቸው ተካፋይ የመሆን ያህል ነውና ሁሉም በመንፈሱ ተይዘዋል ማለት ይቻላል። 

   በዚህ መልኩ ከ4000 የአዲስ አበባ ከተማ ጠንቅዋዮች አገልግሎት የጠየቁ ተራ ሕዝብና ትላልቅ ሹማምንት ስንት ይሆኑ ይሆን? በቀላል ስሌት እያንዳንዱ ጠንቅዋይ በቀን ዐሥር ሰው ቢያስተናግድ 4000 ሲባዛ በ10= 40,000 /አርባ ሺህ/ ሰዎች በየቀኑ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ሆነዋል ማለት ነው። በወራትና በዓመታት ስናሰላው በተደጋጋሚ ሊሄዱ የሚችሉትን የስሌት ግምት ቀንሰን ሚሊዮን ተጠቃሚዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ በቀላል ሎጂክ ማወቅ ይቻላል። ይህ እንግዲህ እንደነታምራት ገለታ ያሉትን በቀን ውስጥ በሺህ ሰው የሚያንጋጉትን ከፍተኛ ቁጥር ሳይጨምር መሆኑን ልብ ይበሉ። እያንዳንዱ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ በሕይወት ዘመኑ ቢያንስ አንድ ጊዜ ከጠንቅዋይ፤ ከቅጠል በጣሽ ደብተራ፤ ከአስማትና ከክታብ ፀሐፊ ዘንድ ሊሄድ እንደሚችል አመላካች መረጃ ነው። እናስ? አገሪቱን የተቆጣጠረው ይህ መንፈስ እግር ተወርች አስሮ የግዛቱ ምርኮኛ በማድረግ የእግዚአብሔር ክብር እንዳይገለጽ ተግቶ እየሰራ አይደለምን?  
   የቀናው የጌታ መንገድ እየተጣመመ እውነት የማይገለጠው ወይም የተገለጠው የሚዳፈነው በዚህ የክፋት መንፈስ የታሰረ ሕዝብ በመኖሩ ምክንያት መሆኑን መካድ አይቻልም።  የክፋት ሠራዊት ራሱ፤ አራዊት ማኅበር ያቋቋመው ቀናው መንገድ እንዳይገለጥ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ መሆኑንም ልብ ማለቱ ጠቃሚ ነገር ነው።

   ሰርግዮስ ጳውሎስ የተባለው አገረ ገዢ ሳይቀር ከጠንቅዋይ መንፈስ ጋር ኅብረት ያደርግ እንደነበር ማሳየቱ የሚጠቁመን ነገር ሹማምንትም የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች መሆናቸውንና ከዚህ መንፈስ ምሪት በሚያገኙት ምክር የሚሰሩት ሥራ ምን ሊሆን እንደሚችል ያሳየናል።  ከዚያም ባሻገር ጠንቅዋዮች የባለሥልጣን ከለላ እንዲያገኙና በአገሪቱ ውስጥ ያለሥጋት የመንፈስ ሥራቸውን እንዲፈጽሙ እድል የሚሰጣቸው  እንደሆነ ለመገመት  ይቻላል።  በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የዚህን ያህል ቁጥር ያላቸው ጠንቅዋዮች የመብዛታቸው ምክንያትም ይኸው ነው።  የአዲስ አበባ ጠንቅዋዮች እንዲስፋፉ እድልና ጊዜን የሰጣቸው የመንፈሱ አገልጋዮች መኖራቸው እንጂ እግዚአብሔር ደስ ስለተሰኘና ሰለፈቀደላቸው አይደለም። የቤተ ክህነቱ ጠንቅ-ዋይ ማኅበርም ቢሆን የመቆየት እድል ያገኘው እሱ እንደሚለው እግዚአብሔር ስላቆመው ሳይሆን የጠንቅ-ዋይ ሰላባ የሆኑ የቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አመራሮች አብረው ለመንፈሱ አሰራር ስለተሰለፉ ብቻ ነው። እግዚአብሔር ለክፉው መንፈስ አሠራር ፈቃደኛ የሆኑትን ሰዎች ለፈቃዳቸው አሳልፎ በመስጠት የሚተዋቸው ሰዎች ማድረግ ለሚፈልጉት ነገር ነጻ ፈቃድ ያላቸው ፍጥረቶች ስለሆኑ ብቻ ነው።

   የዚህን ያህል ቁጥር ባለው ጠንቅዋይና አስማተኛ ደብተራ ተገልጋዩ ማነው? ብለን ብንጠይቅ በአብዛኛው እምነት አለን በሚሉ ክርስቲያኖችና ሌሎች ሰዎች መሆናቸውም በተደረገው ጥናት ላይ ተመልክቷል። ከዚህም ውስጥ ሰፊውን ቁጥር የያዙት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ናቸው። የዚህ ታሪክ ፀሐፊ ከአንድ የጥንቁልና አገልግሎት ተጠቃሚ ከነበረ ሀብታም ሰው ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው አዋቂ ከተባለ ባለዑቃቢ የተሰጠው ትእዛዝ « የልደታን ታቦት በደባልነት ከዚህ ቤተ ክርስቲያን አስገብተህ፤ ካህናቱን እየደገስህ አብላ፤ በየዓመቱም ዝክር ዘክር ተብለኻል» በማለት ቃል ያስገባው ሲሆን ይህንኑ ተግባር እስካሁን ሳያቋርጥ እየፈጸመው የመገኘቱ ጉዳይ ነው። ለዚህ ሰው ደባል ታቦት ፈቃጅነት፤ በአገልግሎት ሰጪነት የሚያገለግል ካህን፤ በንግሥ በዓል ላይ የሚሰማራው ሰጋጅና አንጋሽ ሕዝብ  እግዚአብሔርን እያከበረ ቢመስለውም የመንፈሱ አሠራር በሃይማኖት ከለላ ምን ያህል የነፍስ ወረራ እንደሚፈጽም ከሚያሳይ በስተቀር ከእግዚአብሔር ሃሳብ ጋር አንዳችም ግንኙነት የለውም። በተለይም በአዲስ አበባ ሀብታም የሆኑ አፍቃሬ ደብተራ ሰዎች የእገሌን ታቦት እያሉ በስማቸው ደባል አድርገው በማስገባትና በመትከል ላይ ተጠምደዋል።

 ከዚህም በላይ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ የሚፈልጉትን ነገር በሚፈልጉበት ደብር እያስነገሱ ሕዝቡን ለስውሩ መንፈስ አገዛዝ አሳልፈው መስጠታቸው ሳያንስ ከሰይጣን ጋር የተዋርሶ ኪዳን የፈጸሙ፤ ከጠላት መከላከያ የሚሆን ዐቃቤ ርዕስ የሚል አስማትና ድግምት ጭምር እንደሚይዙ ይነገራል። የጠላት መንፈስ ባለበት ሁሉ አድማ፤ ሁከት፤ ብጥብጥ፤ ክርክር፤ ጥል፤ ጭቅጭቅ፤ ቡድንተኝነት፤ ዝሙት፤ ሙስና መኖሩ በራሱ የክፉው መንፈስ ብርታት ምን ያህል አካባቢውን እንደወረረ ማሳያ ነው።  የመንፈስ ፍሬ የሆኑቱ ምልክቶች የማይታይባቸውም ለዚህ ነው።  እነዚህን ምልክቶችን አይቼባቸዋለሁ ብሎ ምስክርነት ሊሰጥ የሚችል ከተገኘ በእውነት ድንቅ ነው።   
                          
«የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው» ገላ5፤22

 በግልጥ የሚታወቁና ጥንቆላን የሚጠቀሙ ጳጳሳት እንዳሉ በመረጃ አስደግፎ ሥራቸውንና ቦታቸውን ጠቅሶ መናገር ይቻላል። ከብዙዎቹም አንዱ በናይሮቢ ከተማ የሚኖሩ አንዕስት ኢትዮጵያውያትን በስመ «አውቅልሻለሁ፤ አጠምቅሻለሁ» ሰበብ የአስማትና የቅጠላ ቅጠል ጭማቂ እየነከረ የሚያደነዝዛቸውና ኀፍረተ ሥጋቸውን ሳይቀር የሚዳብስ ጠንቅዋይ ጳጳስ የክፉው መንፈስ ተካፋይ ካልሆነ የቅዱስ መንፈስ ማደሪያ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው? ከዚያም በዘለለ ሁኔታ ውስጥ የድርጊቱ ሰለባ  ስለመኖራቸው በሀዘን የሚናገሩም ተገኝተዋል። የአገራችን ሰው ጉዳዩን ማውጣት ሲከብደው «ውስጡን ለቄስ ይላል» እኛም ውስጡን «ወኅቡረ ዐለወ» ለሚባለው ለሲኖዶስ ትተነዋል።

    ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደተቋም በአዋጅ የምትቃወመውና የምታወግዘው ብትሆንም በየትኛውም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጥንቆላ፣ ለአስማት፤ ለምትሃት፤ ለድግምት፤ ለመርበብት፤ ለተዋርሶና ለተመሳሳይ የመናፍስት አሠራር ያልተጋለጠ ሰው ማግኘት እጅግ አዳጋች ነው። ወይ ሰርቷል፤ አለያም አሰርቷል ወይም አይቷል፤ አለያም ከብጥስጣሽ ክታባት ጋር በሆነ አጋጣሚ ተገናኝቷል። ይህ በሕይወት ገጠመኝ ያየነው የማይታበል እውነት ነው። ይህ ልምምድ ሠርጎ ከገባ በኋላ ውስጥ ለውስጥ ነግሶ እንደቆየ ዘመናትን አሳልፏል። በአጠቃላይ ሲታይ አዲስ አበባ ትሁን መላ አገሪቱ በአንድም፤ በሌላ መንገድም የክፉ መንፈስ እስረኛ ሆናለች። «ለሞት መድኃኒት አለን» ከሚለው ማስታወቂያ በስተቀር ለቡዳ፤ ለመጋኛ፤ ለዛር፤ ለውቃቤ/ዐቃቤ/፤ ለሚያስቃዥ፤ ለሟርት፤ ለገበያ፤ ለመስተፋቅር፤ ለእጀ ሰብእ በደፈናው ለሌሎችም ችግሮች ፍቱን መፍትሄ እንሰጣለን» የሚሉ ማስታወቂያዎች ከተማውን ያጠለቀለቁት የክፉው መንፈስ አሠራር ተንሰራፍቶ በአገሪቱ የመንገሱ ምልክት ነው።  

  በአንድ ወቅት ጌታቸው ዶኒ የተባለ ሰው ቡዳ የበላውን መኪና ከቤተ ክርስቲያን ግቢ አስቁሞ ጸበል ሲረጨው ታይቶ ነበር። አሁን መኪናን ቡዳ የሚባለው እንዴት ነው? ድሮ ሰው ነበር ተበላ የሚባለው በዚህ ዘመን ደግሞ መኪናውንም ሳይቀር የሚቀረጥፍ ጥርስ ያለው ቡዳ ተፈጥሯል። ኢትዮጵያ የመኪና አደጋ የተበራከተባት ቡዳ እየበላባት ይሆናል። የትራፊክ መሥሪያ ቤትም የመኪና አደጋውን ለመቀነስ ጸበል እየገዛ መኪኖችን መርጨት አለበት ማለት ነው። የጌታቸው የግብር ታናሽ ወንድም የሆነው ግርማ ወንድሙ ደግሞ የሀገር ቤቱን ቡዳ ገድሎ የጨረሰ ያህል አበሾችን ብቻ የሚከተለውን ቡዳና እጀ ሰብእ ለመግደል ባህር ማዶ ሄዶ የማርከሻ ጸበል እየረጨሁ ነው ይለናል።  የነ ግርማ ወንድሙ ክህነት ሰጪ፤ ሻሚ ሸላሚዎች ደግሞ የመንፈሱ ደጋፊዎች እነዚያው ጳጳሳት መሆናቸውን ስንመለከት የክፉው መንፈስ ኃይል ምን ያህል ስር እንደሰደደ ያሳያል።

ጥንቆላና ቀጠል በጣሽ ደብተራ በአዲስ አበባ ምን እየሰራ እንዳለ የሚያሳይ «ፔሌማ» በሚል ርዕስ የተሠራ ፊልም የድርጊቱን ስፋት በሰፊው ያትታልና ቢመለከቱ ጥሩ ግንዛቤ ሊያገኙ እንደሚችሉ ይገመታል።

እግዚአብሔር አምላክ «አስማተኛም፥ መተተኛም፥ በድግምት የሚጠነቍልም፥ መናፍስትንም የሚጠራ፥ ጠንቋይም፥ ሙታን ሳቢም በአንተ ዘንድ አይገኝ» በዘዳ 18፤11 ላይ ቢናገርም በዚህ ዘመን ከመገኘት ባለፈ መደበኛ ሥራ ሆኗል። ስለዚህም የእግዚአብሔር ረድዔትና በረከት ርቆናል።

እርስዎ አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋይ ማነው ይላሉ? እንቅፋት መታኝ ፤ ጥቁር ውሻ አቋረጠኝ፤ እብድ ለከፈኝ፤ ሲቀዳ ያልሞላ አልጠጣም፤ በቀኝ አውለኝ፤ ኮከቤ አይወደውም፤ ሴጣኔን አታምጣብኝ፤ ዓይነ ጥላ አለበት፤ ገፊ፤ ከማያቁት መልዓከ የሚያውቁት ሴጣን ይሻላል ወዘተ ብሂሎች እርስዎ ብለው ወይም ያለ ሰው ሰምተው ያውቃሉ? እነዚህ አባባሎች ምንን ያመለክታሉ? እስኪ ይመርምሯቸው!
-----------------------------
/1/ በርያሱስ ማለት በአረማይክ ቋንቋ የኢያሱ ልጅ ማለት ነው።
/2/ ኤልማስ ማለት ጥበብ ማለት ነው።

Wednesday, October 1, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶችና ነብያት!



 ( ክፍል 3 ) 

ጂም ጆንስ (1931-1978)
በአሜሪካዋ ኢንዲያና ስቴት ህዳር 18, 1931 ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ህውከት ሲደርስ በኢንዲያናፖሊስ ከተማ የኮሙኒስት ፓርቲ አባል በመሆን በህውከት ስራ ላይ መሰማራትን «ሀ» ብሎ ጀመረ። የኮሙኒስት ርእዮት አራማጅ የሆነው ጆንስ በሜቶዲስት፤ በሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት ውስጥ ብቅ ጥልቅ እያለ ከቆየ በኋላ ዓለም በኒውክለር ትጠፋለች ስለዚህ ሐዋርያዊ ሶሻሊዝም በዓለም ላይ መምጣት አስፈላጊነት ይሰብክ ነበር። ጆንስታውን ወደተባለች የጉያና ከተማ በማቅናት «የህዝቦች ቤተ መቅደስ» የተሰኘ ቤተክርስቲያን ከመሠረተና ከተደላደለ በኋላ የእርሻ ተቋም ከፈተ።  በዚህ የእርሻ ተቋም ውስጥ ሶሻሊስታዊ እኩልነት የሰፈነበት ማኅበረሰብ እመሰርታለሁ በማለት የራሱን «የቀይጦር ሠራዊት» አደራጀ። ይህ የቀይ ጦር ሠራዊት ዋና ዓላማው የእርሻውን ሜካናይዜሽንና የቤተ ክርስቲያኑን ህልውና የመጠበቅ ዓላማ ይዞ የተነሳ ቢመስልም በተግባር ግን የጂም ጆንስን አንባገነንነት መንከባከብ ነበር። ወደተቋሙ የገባ ማንም አባል መውጣት አይችልም በማለት ማገድ ጀመረ። በዚህም ሳቢያ በዚያ ማኅበረሰብ ውስጥ የፈለገውን ማድረግ የሚችል አንባ ገነን መሆን ቻለ። ከዚህ ተቋም ሸሽተውና አምልጠው ወደአሜሪካ የገቡ ሰዎች ለአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተርና ለምክርቤቱ አቤቱታቸውን ማቅረብ ቻሉ። በሰብአዊ መብት ጥሰት የተከሰሰው  የጆንስን ጉዳይ የሚያጣሩ በኮንገረስ ማን ሊዮ ሪያን የሚመራ ብዙ የሚዲያ ሰዎችን የያዘ ቡድን ወደጉያና አመራ። ቡድኑ ከቦታው እንደደረሰ ከጆንስ ቀይጦር አባላት የጠበቀው የሞቀ ሰላምታ ሳይሆን የደመቀ የጥይት ተኩስ ነበር። ኮንግረስ ማን ሪያንና ሌሎች ብዙዎቹ በተኩሱ ተገደሉ።  ከፊሎቹም ቆሰሉ። ህዳር 18, 1978 ዓ/ም ጥዋት ላይ ይህ ግድያ ከተፈጸመ በኋላ ጆንስ ወደተከታዮቹ በመመለስ ከሚመጣባችሁ ቁጣ ለመዳን ራሳችሁን አጥፉ፤ ልጆቻችሁንም ጭምር ለመፍጀት ለሚመጡ ጠላቶች አሳልፋችሁ አትስጡ፤ ስለዚህ አብራችሁ ሙቱ በማለት ትእዛዝ ሰጠ።
ሳይናድ መርዝ እየጠጡና እያጠጡ 300 ህጻናት ያሉበት 900 ሰዎች በጥቂት ሰዓት ውስጥ አለቁ።
እኔ ቡድሃን፤ ሌኒንን፤ኢየሱስን እና ሌሎችን ሆኜ ተገልጫለሁ እያለ ያታልል የነበረው ጂም ጆንስ በአውቶማቲክ ጥይት ግንባሩን ብትንትንን አድርጎ ራሱን በራሱ ገደለ።




ማርሻል አፕልዋይት  (1931-1997)
ስፐር ፤ቴክሳስ ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ማሳሳት ከመድረሱ በፊት የአሜሪካ ወታደር በመሆን አገልግሏል። በሂውስተንና ኮሎራዶ ትምህርቱን የተከታተለው አፕል ዋይት በአላባማ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ሲሰራ በግብረ ሰዶም ተጠርጥሮ ከስራው ተባሯል። ይህንን ተግባሩን የመሰከረበት ደግሞ በስብከቱ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነትን አስፈላጊነት መናገሩ ነበር። አፕል ዋይት የሙዚቃ ባለሙያ ስለነበር በዚህ ሙያ ያገኘውን ችሎታ ተጠቅሞ «Heaven’s Gate» /የመንግሥተ ሰማይ በር/ የተሰኘ ሃይማኖታዊ ድርጅት መሠረተ።  አፕልዋይት በዩፎዎች መኖር የሚያምንና በነሱ ላይ ጥገኛ የሆነ ስብከት ያስተምር ነበር።
 በ1974  ዓ/ም የተከራያትን መኪና ባለመመለስ ወንጀል ተከሶ ስድስት ወር ተፈርዶበት ከርቸሌ ወረደ። ከዚያም እንደወጣ ጣዖታዊ ስብከቱን ቀጥሏል። መስከረም 25, 1995 ዓ/ም «እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ነኝ» በማለት ለተከታዮቹ አሳወቀ።
በመጋቢት 29/ 1997 ዓ/ም ዩፎዎች መጥተው ወደገነት ስለሚወስዱን ራሳችንን እናጥፋ ብለው በጅምላ ራሳቸውን ገደሉ። ከተከታዮቹ መካከል ማርሻል አፕል ዋይትን ጨምሮ 30 አባላቱ ሞተው ተገኙ። ነገር ግን ሁኔታው እንደተሰማ ከቦታው የተገኘ አንድም ዩፎ አልነበረም። ይልቁንም ፖሊስ ከቦታው ተገኝቶ እነአፕልዋይት ራሳቸውን በራሳቸው ማጥፋታቸውን አረጋግጦ የህዝብ መቃብር ውስጥ እንዲወርዱ አድርጓል።




ያህዌህ ቤን ያህዌህ (1935-2007) 

 ጥንተ ስሙ ኸሎን ሜሼል ጁንየር ይባል ነበር። ይህ ጥቁር አሜሪካዊ እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ለማለት ፈልጎ ስሙን  በ1979 ዓ/ም «ያህዌህ ቤን ያህዌህ» በማለት ቀየረ። ብዙዎቹም ተከታዮቹ ከክርስትናውና ከአይሁድነት ያፈነገጡ ሰዎች ነበሩ። በተለይም ጥቁር አሜሪካውያን ብዙ ቁጥር ያላቸው ሲሆን ትክክለኛው እስራኤላውያን እኛ ነን፤ ይሉ የነበረ ሲሆን በአሜሪካና በዓለም ላይ በ1300 ከተሞች ውስጥ አባላቱን ማደራጀት ችሏል። እግዚአብሔር ጥቁር ነው። እስራኤልውያንም ጥቁሮች ነበሩ። ነጮቹ ታሪካችንን ቀምተው ነው። ሰይጣን ማለት ነጮች ናቸው ይል ነበር። በዚህም ምክንያት ዓርብ ህዳር 13 ቀን አንገታቸው የተቀላ የነጮች ሬሳ በአቅራቢያው ዳዋ ውስጥ ተጥሎ በመገኘቱ ጥቁሩ መሲህ ቤንያህዌህ በ1992 ዓ/ም ሰው በመግደል ወንጀል ተጠርጥሮ ተያዘ። በፍርድ ቤትም በምስክሮች ስለተረጋገጠበት የ18 ዓመታት እስር ተበይኖበት ከርቸሌ ወረደ።  
በእስራቱም ነብይ በሀገሩ አይከበርም ያለው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው ሲሉ ተከታዮቹ ለፈፉ። ከ8 ዓመት እስራቱም በኋላ በ2001 ዓ/ም በምህረት ተለቀቀ። በ2007 ዓ/ም በፕሮስቴት ካንሰር ሞተ። ከሱ ሞት በኋላ ተከታዮቹ በሥጋ የተገለጠው እግዚአብሔር ማለታቸውን አልተዉም። ልቡ የደነደነ ዓለም ዓይኑ ታውሮ ሰው ያመልካል። ለጣዖትና ስዕል ይሰግዳል።

(ይቀጥላል % )

Wednesday, September 24, 2014

ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ ምን ይመስላል?


( ክፍል ሁለት )
 


3/የቅዱሳን መላእክት አገልግሎት


በክፍል አንድ ጽሁፋችን ስለመላእክት ስያሜ ትርጉም፤ ስለአፈጣጠራቸው፤ ስለፈቃዳቸውና ተልእኰአቸው በጥቂቱ ለማየት ሞክረን ነበር። በክፍል ሁለት ጽሁፋችን ደግሞ ቀሪውን ነጥብ እግዚአብሔርን እንደፈቀደ መጠን ለማየት እንሞክራለን።
ቅዱሳን መላእክት የፈጣሪያቸውን ትእዛዝ ሳይጠብቁ  የትም እንደማይንቀሳቀሱ እርግጥ ነው። በዚህም የተነሳ እግዚአብሔር በወደደውና በፈቃደው ቦታ ቅዱሳኑን መላእክት ለእርዳታና ለትድግና ይልካቸዋል። 

«የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል» መዝ 34፤7

እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ሰዎች የእግዚአብሔር ጥበቃና እርዳታ ዘወትር ይደረግላቸዋል ማለት መላእክቱ በራሳቸው ፈቃድ ይንቀሳቀሳሉ ማለት አይደለም። አንዳንዶች ይህንን ጥቅስ በመጠቀም «መላእክት በተጠሩ ጊዜ በተናጠል መጥተው ያድኑናል» ወደሚል ድምዳሜ በመድረስ ከመላእክት አማላጅነት ጋር ለማያያዝ የሚፈልጉ ወገኖች አሉ። ነገር ግን ዳዊት በመዝሙሩ በግልጽ እንደተናገረው
 «በልዑል መጠጊያ የሚኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል» ካለ በኋላ ሰው ሁሉን በሚችል በእግዚአብሔር ፈቃድ ስር ካደረገ «እግዚአብሔርን፦ አንተ መታመኛዬ ነህ እለዋለሁ አምላኬና መሸሸጊያዬ ነው» በማለት እግዚአብሔር ታዳጊ አምላክ እንደሆነ በማሳየት፤  ከእግዚአብሔር ዘንድ ደግሞ ለእንደዚህ ዓይነቱ አማኝ የተሰጠው የጥበቃ ተስፋ በቅዱሳን መላእክቱ በኩል መሆኑን ከታች ባለው ጥቅስ ይነግረናል።

«ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፥ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ አይገባም። በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና» 
 ይላል በዝማሬው። መዝ 91፤ 1-16 (ሙሉውን ያንብቡ)
በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔርን መታመኛቸው ላደረጉ ሰዎች የእግዚአብሔር ጥበቃ በመላእክቱ በኩል ሲፈጸም እንመለከታለን።

«ጴጥሮስም ወደ ልቡ ተመልሶ፦ ጌታ መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና የአይሁድ ሕዝብ ይጠብቁት ከነበረው ሁሉ እንደ አዳነኝ አሁን በእውነት አወቅሁ አለ» የሐዋ 12፣11

 ጴጥሮስን ሄዶ እንዲያድን የላከው ጌታ ነው። መልአኩ የተላከውም ጴጥሮስን እንዲያድን ነው። ቅዱሳን መላእክት እንደስማቸው ለሚገዙለት ጌታ ይላካሉ። አድኑ የተባሉትን ያድናሉ። ለመዓትም ይሁን ለምህረት መላእክቱ የሚላኩት በእግዚአብሔር ትእዛዝ እንጂ ሰዎች ስለጠሯቸው ወይም ስለፈለጓቸው አይደለም።
 በብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ውስጥ ወደቴስቢያዊው ኤልያስ መልአኩ በተላከ ጊዜም  አካዝያስ ስለህመሙ ምክንያት እግዚአብሔርን በጸሎት ከመጠየቅ ፈንታ ወደአቃሮን ብዔል ዜቡል ፊቱን ባዞረ ጊዜ መልአኩ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» በማለት የመጣበት ጉዳይ ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ትእዛዝ ለመፈጸም እንደሆነ አስረግጦ ሲናገር፤

 «የእግዚአብሔርም መልአክ ቴስብያዊውን ኤልያስን፦ ተነሣ፥ የሰማርያን ንጉሥ መልእክተኞች ለመገናኘት ውጣና። የአቃሮንን አምላክ ብዔልዜቡልን ትጠይቁ ዘንድ የምትሄዱት በእስራኤል ዘንድ አምላክ ስለሌለ ነውን? ስለዚህም እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ትሞታለህ እንጂ ከወጣህበት አልጋ አትወርድም በላቸው አለው። ኤልያስም ሄደ» 1ኛ ነገ 1፤3-4

«እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» ማለቱ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ተቀብሎ ለመፈጸም መምጣቱን ያስረዳል። ወደኤልያስ መልእክቱ ይመጣ ዘንድ ያስፈለገውም ኤልያስ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ይከተል ስለነበር መሆኑ እርግጥ ነው። በሌላ ቦታም የእግዚአብሔርን ፈቃድ ይፈጽሙ ከነበሩ ደጋግ ሰዎች መካከል አንዱ ወደሆነው ወደቆርኔሌዎስም ዘንድ ሲልክ  እንመለከታለን።

«ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለው፦ በዚች ሰዓት የዛሬ አራት ቀን የዘጠኝ ሰዓት ጸሎት በቤቴ እጸልይ ነበር፤ እነሆም፥ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ ሰው በፊቴ ቆመና። ቆርኔሌዎስ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ ምጽዋትህም ታሰበ»  የሐዋ 10፤ 30-31

የቆርኔሌዎስ ስለጸሎቱ መሰማትና ስለምጽዋቱም በእግዚአብሔርን ዘንድ መታሰብ የሚናገር መልእክተኛ መላኩን ስንመለከት ዳዊት በዝማሬው እንዳመለከተው በልዑል መጠጊያ ለሚኖሩ ሁሉ መላእክቱ እንደሚላኩላቸው በግልጽ ያረጋግጥልናል። በዚሁ ተመሳሳይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስረጂ በማቅረብ የመላእክቱን ተራዳዒነትና አጋዥነት መግለጽ  ይቻላል። ነገር ግን አስረግጠን ማለፍ የሚገባን ቁም ነገር መላእክቱ የሚመጡት በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ስር ላሉ ሲሆን ሰዎች የፈለጉትን መልአክ ስለጠሩ ወይም በልባቸው አምሮት የመረጧቸውን  መላእክት ስም ስለተናገሩ አለመሆኑን መገንዘብ ይገባናል። በሰዎች ጥሪ እገሌ የተባለ መልአክ መጣልኝ የሚል አንዳችም አስረጂ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ አይገኝም። በተራዳዒነትና አጋዥነት እንደተላኩ የሚነገርላቸው አብዛኛዎቹ መላእክትም በስም ተለይተው አይታወቁም። ቁም ነገሩ የትኛው መልአክ በታላቅ ኃይል ትእዛዙን ይፈጽማል በማለት በኛ ምርጫ የሚወሰን ሳይሆን በስም የተገለጹም ይሁን ያልተገለጹትን እግዚአብሔር መላእክቱን ልኮ የወደዳቸውን እንዴት ይታደጋል? የሚለውን ከመረዳቱ ላይ ልናተኩር ይገባል። ስለዚህም ተልከው ስላገዙን መላእክት የምንሰጠው ክብር እግዚአብሔር ለኛ ያደረገውን ታላቅ ሥራ ቀንሰን የምናካፍለው መሆን የለበትም። በርናባስና ጳውሎስ ከእናቱ ማህጸን ጀምሮ እግሩ የሰለለውን ሰው በፈወሱበት ወቅት የሊቃኦንያ ከተማ ሰዎች «አማልክት ከሰማይ ወደእኛ ወርደዋል» በማለት መስዋዕት ሊያቀርቡላቸው በወደዱ ጊዜ እነጳውሎስ ያደረጉትን ማየቱ ተገቢ ነው።

«ሐዋርያት በርናባስና ጳውሎስ ግን ይህን በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀደው ወደ ሕዝቡ መካከል እየጮኹ ሮጡ፥ እንዲህም አሉ። እናንተ ሰዎች፥ ይህን ስለ ምን ታደርጋላችሁ? እኛ ደግሞ እንደ እናንተ የምንሰማ ሰዎች ነን፥ ከዚህም ከንቱ ነገር ሰማይንና ምድርን ባሕርንም በእነርሱም ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር ትሉ ዘንድ ወንጌልን እንሰብካለ»                የሐዋ 14፤14-15

ጳውሎስና በርናባስ ቅዱሳን በአገልግሎታቸው ሐዋርያት ሆነው ብናከብራቸውና ብንወዳቸውም ቅሉ በእነሱ እጅ በተሰራው አምላካዊ  ድንቅ ሥራ ግን ምስጋናንና ክብርን በጋራ ሊቀበሉ አይችሉም። ክብርና ምስጋና ሁሉ ለእግዚአብሔር ብቻ እንደሆነ ራሳቸው እንደመሰከሩት የእግዚአብሔር  የብቻው የሆነውን ወደፍጡራን መስጠት ተገቢ እንዳልሆነ ማወቅ ይገባናል።

4/ የእግዚአብሔር መላእክት ሳይላኩ በሰዎች ጥሪ ሥፍራቸው ለቀው ይሄዳሉን?

ቅዱሳን መላእክትን ቅዱሳን ያሰኛቸው ዋናው ቁም ነገር የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ማክበር መቻላቸው ነው። ከእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ውጪ የሆኑትማ  ከማዕርጋቸው ተሰናብተዋል። ስለዚህ ቅዱሳን መላእክቱ ሰዎች ስለጠሯቸው ወይም ስማቸው ነጋ ጠባ ስለተነሳ ተጠርተናል በሚል ሰበብ ወደየትም አይሄዱም። ከላይ በማስረጃ ለማስረዳት እንደተሞከረው ቅዱሳኑ መላእክት የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለፈጸሙ ወይም እግዚአብሔር ፈቃዱ ይፈጸም ዘንድ በወደደበት ቦታ መላእክቱን ከሚልክ በስተቀር የትኛውም መልአክ ስሙ ስለተጠራ ወይም ስለተወሳ ተከብሬአለሁና ልሂድ፤ ልውረድ በማለት ከተማውን ለቆ የትም አይሄድም። አንዳንድ ሰዎች የመላእክቱን ስም ለይተው በመጥራት ናልኝ የሚሉት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ካልሆነ ትምህርት የተገኘ ልምምድ ውጤት ነው።
 ስሙ ተጠርቶ ይቅርና ገና ሳይጠራ ስፍራውን ለቆ የትም የሚዞረው ሰይጣን ብቻ ነው። ሰይጣን ቦታውን ለቆ የትም የሚዞረው ከእግዚአሔር ፈቃድ ውጪ ያፈነገጠ ሽፍታ ስለሆነ ነው። ቅዱሳን መላእክቱ ያለእግዚአብሔር ትእዛዝ ስማቸው ስለተጠራ ብቻ ሥፍራቸውን ለቀው እንደማይንቀሳቀሱ የሚያውቀው ሰይጣን ራሱን የብርሃን መልአክ አስመስሎ ሊያታልል እንደሚችል ወንጌል ያስረዳናል።
«ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና» 2ኛ ቆሮ 11፤14

ሰይጣን በራሱ ፈቃድ የሚተዳደር ዐመጸኛ ስለሆነ በዓለሙ ሁሉ እየዞረ ሰዎችን ሲያሳስት ይውላል። በተለይም የእግዚአብሔርን ፊት በሚሹ ሰዎች ዙሪያ የጥፋት ወጥመዱን ሊዘረጋ አጥብቆ ይተጋል። ጻድቅ የሆነው ኢዮብንም ያገኘው በዚህ የጥፋት አደናው ወቅት ዓለምን ሲያስስ እንደነበር ከንግግሩ ታይቷል።

«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ»ኢዮብ 1፣7

ስለዚህ ክርስቲያኖች እንደእግዚአብሔር ፈቃድ እየኖሩ ለትእዛዙ በተገዙ ጊዜ በመልካም ትሩፋታቸው ይሁን በችግራቸው ወይም በመከራቸው ወቅት እንዲራዷቸው ቅዱሳኑ መላእክት ከሚላኩ በስተቀር ሰዎች በቀጥታ መላእክቱን ስለጠሯቸው ወይም በስማቸው ስለተማጸኑ የሚመጡ ባለመሆናቸው ከመሰል ስህተት ልንጠነቀቅ ይገባል። ይልቁንም ከእግዚአብሔር ተልእኮ ውጪ ቅዱሳኑ እንደማይንቀሳቀሱ የሚያውቁት የሰይጣን ሠራዊት የብርሃን መልአክ በመምሰል ራሳቸውን ቀይረው ከሚፈጽሙብን ሽንገላ ልንጠነቀቅ ይገባል።

እንደማጠቃለያ፤

 ቅዱሳን መላእክት ሰዎችን ይራዳሉ፤ ያግዛሉ ማለት በሥልጣናቸው የራሳቸውን ክብር ስም ለማስጠበቅ ይሠራሉ ማለት አይደለም። በተፈጥሮአቸውም ውሱን ስለሆኑ በዓለም ላይ በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት የመገኘት ብቃት የላቸውም። በሁሉም ሥፍራ ተገኝተው ሰዎች ሰለጠሯቸው መልስ አይሰጡም።  ይሁን እንጂ በዓለም ላይ በስማቸው ተሠራ በሚባለው ቤተ ጸሎት በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት ተገኝተው ጸሎት እንደሚቀበሉ ተቆጥሮ ስማቸው ሲጠራ ይታያል። በቅዱሳን መላእክት ተራዳዒነት እናምናለን ማለት ቅዱሳን መላእክት በራሳቸው ፈቃድ ስለጠራናቸው ይደርሱልናል ማለት አይደለም። ቅዱሳን መላእክት ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ሳይደርሳቸው አይንቀሳቀሱም። የዚህ ጽሁፍ ዋና ዓላማም ቅዱሳኑን መላእክት ስናከብራቸው አስተሳሰባችንን በመለጠጥ የምንጓዝበት የእምነት ጽንፍ ወደስህተት እንዳይጥለን ለማስገንዘብ ነው። ቅዱሳኑን ያለትእዛዝ ስለጠራናቸው ብቻ በማይመጡበት ሥፍራ ሰይጣን የብርሃን መልአክ መስሎ ከሚፈጽመው ማታለል ለመጠበቅ ነው።
በአንዳንድ የእምነት ተቋማት ዘንድ ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ የተዛባ ምስልን እንደያዘ መገንዘብ ይቻላል። 

   በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አንዳንዶች የመላእክቱን ተፈጥሮ ዘንግተው ሁሉን የመስማት፤ የማወቅና በሁሉ ሥፍራ የመገኘት ችሎታ እንዳላቸው ሲቆጥሩ መታየቱ ተለምዷል። መላእክት በተጠሩ ጊዜ መልስ እንደሚሰጡና እንደሚራዱ የሚሰጠውም ግምት ያለትእዛዝ በራሳቸው ፈቃድ እንደሚንቀሳቀሱ ያደርጋቸዋል። ይህም ወደ እግዚአብሔር ሳይሆን በተራዳዒነት ሰበብ ወደ መላእክቱ ጸሎት የሚያደርሱ ሰዎችን አስገኝቷል። «እንደአናንያ፤ እንደአዛርያ፤ እንደሚሳኤል አድነን ገብርኤል» እያሉ መዘመር እንደተገቢ ከተቆጠረ ውሎ አድሯል። ሠለስቱ ደቂቅን ያዳነው ገብርኤል ነው ከሚለው የትርጉም ፍልሰት ጀምሮ «ገብርኤል አዳኝ ነው» ወደሚለው መልአኩን  ለይቶ የማመስገን የፍቺ ጽንፍ ድረስ ስለመላእክት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ ምስል መስጠት ጉዳዩን አደገኛ ያደርገዋል። እኛ የሚያድኑን እግዚአብሔር ፈቃዱን የፈጸመባቸው መላእክቱ ወይስ የእግዚአብሔር ኃይል? በሚለው ሃሳብ ላይም መቀላቀል የታየበት ሁኔታ ሕዝቡ መላእክቱን በተናጠል ወደመጣራት ሲገፋው ይስተዋላል። ከሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ሚካኤል አንተ ታውቃለህ? ብሎ የመጸልይ ልምምድ ስለመላእክቱና ስለእግዚአብሔር ፈቃድ የተቀላቀለ ትምህርት ውጤት ነው።
አንድ ክርስቲያን በአንድ ጊዜ ወደእግዚአብሔርም፤ ወደመላእክቱም ጸሎት ማድረስ አይችልም። ይህ መተላለፍ ነው። እግዚአብሔር ደግሞ ከክብሩም፤ ከምስጋናውም ለማንም አያጋራም። ቀናተኛ አምላክ የሚባለውም ለዚህ ነው። ኢያሱ ወልደነዌ ለህዝቡ እንዲህ አለ።
«ኢያሱም ሕዝቡን፦ እርሱ ቅዱስ አምላክ ነውና፥ እርሱም ቀናተኛ አምላክ ነውና እግዚአብሔርን ማምለክ አትችሉም መተላለፋችሁንና ኃጢአታችሁን ይቅር አይልም» ኢያ 24፤19
ስለዚህ ስለመላእክት ተፈጥሮ፤ ተልዕኰና አገልግሎት በደንብ ማወቅ የሚገባን የእግዚአብሔርን ለመላእክት፤ የመላእክትንም ለእግዚአብሔር በመስጠት የእምነት ሥፍራውን  እንዳናቀላቅል ሲባል ነው። ተፈጥሮአቸውን፤ ተልእኰአቸውንና ተግባራቸውን ለይተን እንወቅ። ከስህተትም ላይ እንዳንወድቅ እንጠንቀቅ። ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን። አሜን!

Wednesday, September 17, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶች!

ክፍል ሁለት )

ዘመኑ የቀሳጥያን፤ የሀሰተኛ ትምህርትና የክህደት መፍለቂያ መሆኑን የበለጠ ለማስረዳት ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ተግባር ላይ ተሰማርተው የነበሩትን ማሳየት ጠቃሚ ይመስለናል። የሰው ልጅ በወንጌል ላይ የተገለጠውን ክርስቶስን ሳይሆን በሰው ብልሃት የተቋቋመችውን ምድራዊ ተቋም፤ የሰዎች ድርጅት፤ የአስተምህሮ መንገድና ስብከት እየተከተሉ ከእውነት ሲያፈነግጡ ማሳየት ተገቢ እንደሆነም ይሰማናል። ዛሬም ቢሆን ሰዎች የድርጅት፤ የተቋምና የሰዎች ተከታዮች ሆነው ይታያሉ። እውነታው ግን ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ የመሠረተው አንድም የእምነት ድርጅት ወይም ተቋም  አለመኖሩ ነው። ጲላጦስ ከመሰቀሉ በፊት ኢየሱስን «እውነት ምንድር ነው?» ብሎ ስለሆነው ነገር ጠይቆት ነበር። ( ዮሐ 18፤38) እውነቱ ግን ሰዎች «እስኪ ራሱን ያድን» እያሉ እየተዘባበቱበት የሰቀሉትን ኢየሱስን ማመን ነበር። አይሁዳውያን ሰዎች ራሷን ማዳን የማትችል ምድራዊት የእምነት ተቋም ስለነበራቸው ከእምነት እንጂ ከተቋም ስላልሆነችው የኢየሱስ ስብከት ጆሮአቸውን አልሰጡም። ስለዚህም እውነቱ አመለጣቸው። ዛሬም ሰዎች ክርስቶስን እናምናለን ቢሉም ከተቋምና ከድርጅት ስብከት አልወጡም። በዓለም ላይ በተለያየ ስም የተከፋፈለው የእምነት ተቋም መሠረቱ በሰዎች አስተምህሮ ላይ የተንጠላጠለ ነገር ግን ክርስቶስ ያጠለቀ በሚመስል ድርጅት የሚጠራ መሆኑ ነው። እውነቱ ግን «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም» ባለው ቃል ጸንቶ መገኘት ብቻ ነው። የምናምነውን ነገር በወንጌል መነጽር እንመርምረው። ወንጌል ካስተማረው ውጪ የሆነው ሁሉ ከሰይጣን የተገኘ ነው።

 
ሚዝራ ጉላም አህመድ (1835-1908)

 ይህ በሃይማኖቱ እስላም የሆነ ሕንዳዊ ዜግነት የነበረው ሰው በአንድ ወቅት ራሱን እንዲህ ሲል ገልጾ ነበር። እስላሞች በመጨረሻው ቀን ከሰማይ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት «ማህዲ» የተባለውን ነብይና ክርስቲያኖች ለፍርድ ዳግም ይመጣል ብለው የሚጠባበቁት «ኢየሱስ»ን የምወክል ስሆን እነሆ ሁለቱም በእኔ ውስጥ በሥጋ ተገልጸዋልና ተከተሉኝ በማለት ሲለፍፍ ቆይቷል። ማሳሳት ጥንተ ግብሩ የሆነው ሰይጣን በህንዳዊው አህመድ ውስጥ አድሮ እሱን ብቻ ሳይሆን ለብዙዎች መሳሳት ምክንያት ሆኖ ከእስልምና ሴክት/ክፍል/ አንዱ የሆነውን «አህመዲያ» የተባለው ቅርንጫፍ ፈጥሮ በማለፍ ዛሬም ድረስ ከ20 ሚሊዮን ያላነሱ አባላትን በዓለም ዙሪያ ማፍራት ችሏል።

ሎ ደ ፓሊንግቦኸር (1898- 1968)

በዜግነቱ ኔዘርላንዳዊ የሆነው ፓሊንግቦኸር በሙያው የተዋጣላት ዓሳ አጥማጅ ነበር። በዓሳ አጥማጅነት ሥራው ከሱ ዘንድ ዓሳ ለመግዛት ለሚመጡ ሸማቾች በትንሹ የጀመረውን ስብከት አሳድጎ በስህተት ሰው ወደ ማጥመድ ሥራ አሳደገው። ተከታዮችን ማፍራቱን እንዳረጋገጠ የዓሳ ጀልባውን በመሸጥ ስብከቱን የሙሉ ጊዜው ሥራው በማድረግ የቀጠለ ሲሆን ዓለም ከክፉ ነገር ሁሉ የምትድነው እኔን በማመን ነው እያለ በየጎዳናው ይለፈልፍ ነበር። ትምህርቱን እንደትክክለኛ አድርገው የተቀበሉ ተከታዮቹ ትልቅ የመኖሪያ ቤት ገዝተው የሰጡት ሲሆን በስተመጨረሻም እኔ «ኢየሱስ» ነኝ በማለት ስብከቱን ገፍቶበታል። አንዳንዶች ይህ ሰው ከሀዲ ነው ብለው ቢያወግዙትም ፓሊንግቦኸር «እግዚአብሔር» ወደመሆን ይለወጣል በማለት ይከራከሩለት የነበሩ ተከታዮችን ማፍራት ችሏል። ይሁን እንጂ ብዙ ጊዜ አግብቶ በመፍታት የሚታወቀው ይህ ቀሳጢ እንኳን ሌሎችን ሊያድን ይቅርና ራሱን ከሞት ማዳን ሳይችል ቀርቶ እስከወዲያኛው አሸልቧል።

ኃይለሥላሴ (1892-1975)

 የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት የነበሩት አፄ ኃይለ ሥላሴ ራሳቸውን እንደመሲህ አድርገው ባይቆጥሩም መሢህ ናቸው የሚሏቸው ወገኖች አሉ። ንጉሡ በአንድ ወቅት በሳቸው ዙሪያ ስለሚባለው ነገር ተጠይቀው «እኛ ሰው ነን እንጂ መሲህ አይደለንም» ብለው የመለሱ ቢሆንም ተከታዮቻቸው በንጉሡ ምላሽ ዙሪያ የሰጡት ማስተባበያ «የኛ መሲህ ያለውን ትህትና ተመልከቱ» በማለት የንጉሡን ምላሽ ከአትህቶ ርእስ ጋር በማያያዝ ለማሳመን ቢሞክሩም እውነታው ግን አፄው መሲህ አለመሆናቸው ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ ለመታሰቢያቸው አርኬ እና መልክእ በመድረስ በነግህና በሰርክ ጸሎት ታስባቸው ነበር። አንዳንዶች የዋሃን አፄው አይሞቱም የሚል ግምት የነበራቸው ቢሆንም ደርግ የገደላቸው መሆኑ ይታወቃል። ከጃማይካ ህዝብ 5% የሚሆነው የራስ ተፈሪያን እምነት ተከታይ ሲሆን በአሜሪካም ብዙ አባላት አሉት።

ኤርነስት ኖርማን (1904-1971)


  አሜሪካዊ የኤሌክትሪካል ኢንጂነር ባለሙያ የነበረና (ዩራንየስ አካዳሚ ኦፍ ሳይንስ) መስራች የሆነ ሰው በአንድ ወቅት ከሙያው ውጪ እብደት መሰል ስብከት ጀምሮ ነበር። ከዚህ በፊት በዚህ ምድር ላይ የተገለጸው «ኢየሱስ» እኔ ነበርኩ። ወደሰማይ ባርግም በዚህ ምድር ላይ በሊቀ መልአክ ሩፋኤል አምሳል ነበርኩኝ እያለ ቢቀላምድም ተከታዮችን ከማፍራት የከለከለው ነገር አልነበረም። ይሁን እንጂ ይህ የዘመኑ ቀሳጢ እንኳን ለሌሎች ሊተርፍ ይቅርና ለራሱም መሆን ሳይችል ቀርቶ በጉሮሮ ህመም ሲሰቃይ ቆይቶ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

ክሪሽና ቬንታ (1911-1958)

 ቬንታ በሳንፍራንሲስኮ የተወለደው ሲሆን በሁለተኛው ዓለም ጦርነት የአሜሪካ ወታደር በመሆን አገልግሏል። ከተመለሰም በኋላ ቀደም ሲል አቋቁሞት የነበረውን ተቋም በማንቀሳቀስ 1948 ዓ/ም «የጥበብ፤ የእውቀት፤ የእምነትና የፍቅር ፏፏቴ» የተሰኘ የክህደት ድርጅት ሥራውን ጀምሯል። ቬንታ የክህደት ደረጃውን በማሳደግ «እኔ ኢየሱስ ነኝ» ከማለቱም ባሻገር የማኅበሩ አባል ለሚሆኑ ሰዎች «ያላችሁን ሀብትና ንብረት ለማኅበሩ ገቢ አድርጉና ሰማያዊ መዝገብ አከማቹ» በማለት ሀብታቸውን በመሰብሰብ ለበጎ አድራጎት ሥራ ለማዋል የሞከረ ቢሆንም ሀብታቸውን ተሞልጨው፤ ሚስቶቻቸውን በቬንታ የማማገጥ ተግባር የተፈጸመባቸው ሁለት ተከታዮቹ በቂም በቀል ተነሳስተው ቦንብ በማፈንዳት አብረው ሊሞቱ ችለዋል። የክሪንሽና ቬንታ የክህደት ተግባርም እስከወዲያኛው በዚያው አክትሟል።

አህን ሳንግ ሆንግ (1918- 1985)

 በደቡብ ኮሪያ የተወለደ ይህ ሰው  በ1964 ዓ/ም «የአዲስ ኪዳን ፋሲካ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን» የሚል የሃይማኖት ተቋም መስርቶ ነበር። በኋላ ላይ ደግሞ «ዓለም አቀፍ የተልእኮ ማኅበር የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን»  የሚል ሁለተኛውን ድርጅት አቋቁሟል። ሳንግ ሆንግ እሱ የኢየሱስ ዳግም ምጽአት ምልክት መሆኑን ይሰብክ ነበር። በአዲስ ኪዳን ፋሲካ ቤተ ክርስቲያኑ እንደመምህር ሲቆጠር በዓለም አቀፍ የተልእኮ ቤተክርስቲያኑ ደግሞ እንደእግዚአብሔር ይቆጠራል።  የቤተክርስቲያኒቱ ዋና አመራር የሆነችው ዛንግ ጊልጃህ የተባለችው ሴት በገላትያ 4፤26 ላይ የተመለከተውን ትንቢት የምታሟላ እሷ ናት ስለሆነች «የኢየሩሳሌም እናት» ወይም «የእግዚአብሔር እናት» ተብላ ትጠራለች።
የቤተ ክርስቲያኑ መሥራች ሳንግ ሆንግ ደግሞ «እግዚአብሔር አብ» ተብሎ ይጠራል።


ሱን ሚዩንግ ሙን (1920- 2012)


 በሰሜን ኮሪያ ተወልዶ በደቡብ ኮሪያ ያደገው ሙን «የውህደት ቤተ ክርስቲያን» መሥራች ሲሆን ራሱን ሁለተኛው ኢየሱስ እንደሆነና  ከዚህ ቀደም ኢየሱስ በሥጋ ተገልጦ ሳለ ሳይጨርሳቸው የሄደውን ጉዳይ የሱ መገለጽ ማስፈለጉን በአደባባይ የሚናገር ሰው ነበር። ሚስተር ሙን ባለቤቱን « ሃክ ጃን ሃን»ን የሚጠራት አዳምና ሔዋን ያበላሹትን ዓለም በማጽዳት መልካም ቤተሰብን በዓለም ላይ ለመመሥረት የተፈጠረች ናት በማለት ያሞካሻት ነበር። ሙን «የተባረከ የኅብረት ጋብቻ» በሚል ዘመቻ በአንድ ቀን እስከ 30 ሺህ የሚቆጠሩ ጥንዶችን  አሜሪካ ባለችው በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ጋብቻ በማስፈጸም ዝናው ይታወቃል። ሙን በአሜሪካን ሀገር ሳለ በፈጸመው የታክስ ማጭበርበር ወንጀል ተከሶ 18 ወራት ተወስኖበት፤ ከዚህ ውስጥ የ13 ወራት እስራቱን ቅሞ በአመክሮ ሊለቀቅ ችሏል። ሱን ሙን  ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ ሃብት ያለው ሲሆን የተለያዩ ኮርፖሬሽኖችንና የአክሲዮን ማኅበራት አሉት። ሃሳዊው ሙን በተወለደ በ92 ዓመቱ በኒሞንያ በሽታ ሞቶ እስከወዲያኛው ተቀብሯል። እሱ ቢሞትም በሱ የሀሰት ትምህርት የተታለሉ 4 ሚሊዮን አባላት በተለያዩ የዓለም ሀገራትን ለማፍራት ችሏል።

ይቀጥላል%

Saturday, September 6, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶችና ነብያት!


አን ኤልዛቤጥ  ሊ (1736-1784)
በእንግሊዝ አገር የተነሳችና «ተንቀጥቃጮች» የተሰኘ ሃይማኖት የፈለሰፈች፤ ተከታዮቿም «እናታችን» እያሉ የሚጠሯት ሀሳዊ ክርስቶስ ሆና ተነስታ ነበር። ስታስተምርም ራሷን የምትገልጸው እኔ በሴት መልክ የተገለጥኩ ሁለተኛው ኢየሱስ ነኝ እያለች ብትሰብክም እንኳን ለሌላው ልትተርፍ ይቅርና እራሷን ማዳን ሳትችል ቀርታ እስከምጽአት የመጨረሻውን ፍርድ ድረስ ላትነሳ ሞታ በድንጋይ ታትማለች።


        **************************************************


ጆን ኒኮላስ ቶም (1799-1838)
በእንግሊዝ ሀገር ኮርንዎል ተወልዶ ያደገና  የወይን ነጋዴ ሆኖ ሲሰራ የቆየ ሰው ነው። በሥራውም ላይ በታክስ ማጭበርበር ተከሶ እንደነበር የህይወት ታሪኩን የመዘገበው የኮርንዎል ቤተ መዛግብት ፋይል ያስረዳል። ቶም ሽቅርቅርና መዓዛው በሚያውድ ሽቶ ልብሱን ነክሮ፤ ጢሙን አሳድጎ የሚዞር ሰው ሲሆን የብዙዎችንም ቀልብ መሳብ የቻለ ነበር። ቶም ከወይን ነጋዴነት፤ ከጋዜጣ አዘጋጅነትና ገበሬዎችን ከአነስተኛ ንግድ ባለቤቶች ጋር በጥምረት የዐመጽ መሪነት ድረስ ሲ,ሰራ ቆይቷል። የሕይወት ስኬት ሲጎድለው ከእለታት አንድ ቀን ድንገት ተነስቶ «ሁለተኛው ኢየሱስ ሆኜ በሥጋ ተገልጫለሁ» በማለት ወደስብከት የገባ ሲሆን ተከታዮችን ካፈራ በኋላ በ1834 ዓ/ም ጀምሮ ወደቅዱስ መንፈስ ተቀይሬአለሁ ቢልም ባልተላቀቀው የዐመጽ መሪነቱ ተግባሩ ቀጥሎ በግንቦት 31/1838 ኬንት ከተማ ላይ በጥይት ተገድሎ እስከወዲያኛው ላይነሳ ያሸለበ ሰው ነው።

**************************************************


አርኖልድ ፖተር (1804-1872)
«የኋለኛው ቀን ቅዱሳን» የተባለው የክርስትና ክፍል መሪ የነበረ ሰው ነው። ፖተር በኒውዮርክ ተወልዶ፤ በኢንዲያና ውስጥ በኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለ ቤተ ክርስቲያን የተጠመቀ ሲሆን በኢሊኖይስ ላይ ደግሞ የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን መሥራች በሆነው በጆሴፍ ስሚዝ «ካህን፤ ሽማግሌና የቡራኬ አበው» ተብሎ ደረጃ በደረጃ የተሾመ ሰው ነበር። እስከአውስትራሊያ ድረስ ለስብከት የተጓዘው ፖተር «የኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ በኔ ውስጥ በመግባቱ ከዛሬ ጀምሮ እኔ ሌላው ኢየሱስ ነኝ» እያለ ሲያስተምርና ተከታዮችን ሲያፈራ ቆይቷል። በኋላ ላይ ወደካሊፎርኒያ ተመልሶ በ1872 ዓ/ም ወደሰማይ የማርግበት ሰዓት ደርሷል በማለት የአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ከገደል አፋፍ ላይ በደመና ለማረግ ሲጋልብ ወደላይ መውጣቱ ቀርቶ ቁልቁል እስከነ አህያዋ በመምዘግዘግ  ፖተር ዳግም ላይመለስ እስከወዲያኛው አሸልቧል።

         **************************************************

ጆንስ ቬሪ 1813-1880
 ፀሐፊ ተውኔት፤ ገጣሚና በሐርቫርድ የግሪክ ቋንቋ መምህር የነበረ ሰው ነው። ቬሪ እጅግ የጠለቀ እውቀትና ሙያ ያለው ሰው ቢሆንም ከእለታት አንድ ቀን  ለተማሪዎቹ «በማቴዎስ 24 ላይ ዳግም ይመለሳል የተባለው ኢየሱስ እኔ ነኝ» በማለት የተናገረ ሲሆን ይህንኑ ስብከቱን ቀጥሎበት ቀይቷል። በኋላ ላይ  በአእምሮ በሽታ ክፉኛ በመጠቃቱ ለከፍተኛ ጭንቀት ህመም ተጋልጦ  እህቱ እሱን የማስታመም ኃላፊነት ወድቆባት ነበር።  ቬሪ «ኢየሱስ ነኝ» እያለ ቢሰብክና ብዙዎችንም ቢያታልል ከአእምሮው በሽታ ሳይድን  በ1880 ዓ/ም በተወለደበት በማሳቹሴትስ ሞቶ በትልቅ ሃውልት መቃብሩ ተደፍኖ ዛሬ ድረስ ይታያል።




******************************************



ባሃ ኡላህ (1817-1892)
የእስልምናው አንዱ ክንፍ ከሆነውና በዛሬይቱ ኢራን ያለው የሺአይት እስላም ቤተ ሰብ የተወለደው ባሃኡላህ በዚሁ እምነት ስር ያደገ ሲሆን ሃይማኖታዊ ፍልስፍናው በፈጠረበት ስሜት ተነሳስቶ ዓለም በአንድ እምነትና መተሳሰብ ስር መጠቃለል አለባት ብሎ በመነሳት ራሱን «የባቢ እምነት» ፍጻሜ ነብይ አድርጎ በመቁጠር ከሺአት ተገንጥሎ በስሙ የባሃኡላህ እምነትን የመሠረተ ሰው ነው። ትምህርቱንም በባግዳድ ጀምሮ በእስልምና ህግ ተይዞ በሃይፋ/ እስራኤል/ እስከተሰቀለበት ቀን ድረስ እኔ የመጨረሻው የእግዚአብሔር ነብይ ነኝ፤ በኋለኛውም ቀን ለፍርድ እመጣለሁ ሲል የነበረ ሰው ነው። ይህ የሃይፋው ዋናው የባሃኢ እምነት ማእከል በዓለም ላይ ላሉ የእምነቱ ተከታዮች ቅዱስ ስፍራ ሲሆን አጠቃላይ መመሪያው የሚመነጨው ከዚሁ ከሃይፋው ማእከል ነው። 
 እግዚአብሔር ራሱን በሰው አምሳል ከገለጸባቸው መንገዶች አንዱ ባሃኡላህ ሲሆን የሰዎችን ነፍስ በማጥራት ምድርን ወደገነት የመቀየር ተልዕኮ ያነገበ እሱ ብቻ መሆኑን ሲሰብክ ቆይቷል። ባሃኢዎች እንደመንፈስ አባታቸው ሲዖልና ገነት ተብለው በሰዎች አእምሮ የተሳሉ ግምቶች እንጂ በእውን ሰዎችን ለመቅጫ በእግዚአብሔር የተፈጠሩ አይደለም ይላሉ። ባሃኡላህ የሞተው በ1892 በስቅላት ነው።
ሃይፋ/እስራኤል የባሃኢ ዋና ማእከል


*******************************************


ዊሊያም  ዳቪየስ (1833-1906)
የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን ቅርንጫፍ በሆነውና የኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መሪ የነበረ ሰው ነው። በደቡብ የዋሽንግተን ስቴት ዋላዋላ ከተማ ላይ «የእግዚአብሔር መንግሥት» ማኅበርን መስርቷል። ተከታዮቹንም «እኔ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚካኤል ነኝ» በማለት ያስተማረ ሲሆን «አዳም፤ አብርሃም፣ ዳዊት» ሆኖ ከዚህ በፊት በምድር ላይ የመጣውም እሱ ራሱ መሆኑንም በድፍረት ይናገር ነበር። በኋላ ላይ ሚስት አግብቶ በየካቲት 11/1868  «አርተር» የተባለ ልጁን እንደወለደ  ልጁን «በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ» ነው በማለት ሲናገር «ዴቪድ» የተባለ ሁለተኛ ልጁን ሲወልድ ደግሞ እኔ ወደ «እግዚአብሔር አብነት» ተቀይሬአለሁ እያለ ይሰብክ ነበር። ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ ሁለቱም ልጆቹ በጉሮሮ በሽታ ሲሞቱ ተከታዮቹ ባቀረቡበት ክስ የቤተ ክርስቲያኑን ንብረት ሸጦ በመክፈልና ከተማውን ለቆ ወደካሊፎርንያ በመሰደድ መልሶ ለመደራጀት ሞክሮ ሳይሳካለት ልጆቹን እንደቀበረ ሁሉ እሱም ሞቶ ድንጋይ ተጭኖት ይገኛል።



 ይቀጥላል%

Wednesday, July 23, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)
የመጨረሻ ክፍል

የተአምረ  ማርያም  ጸሐፊዎች  ሰዎችን  በማስፈራራትና  በማስደንገጥ የማይመረምሩትና  ከገዢው  ቃል  ጋር  የማያስተያዩት  ሃይማኖት  ግዞተኛ አድርገው  ለማኖር  የፈጠሩት  ፈጠራ  ከተፈጥሮና  ከስነ  ፍጥረትም ከአእምሮም  ጋር  የሚጋጭ  ነው።  እነዚህ  ናሙና  ከስነ  ፍጥረት  ሕግ  ጋር የሚጋጩ ያፈነገጡ ታሪኮች ናቸው።

ጥቂት ተጨማሪ ናሙና ግጭቶች

መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚናገረው  መደመጥና  መከበር  እንዳለበት  ሁሉ  ዝም ባለበት  ጉዳይ  ሁሉ  ዝምታውም  መከበር  አለበት  እንጂ  በራሳችን  ምናብ የተፈተሉ  ነገሮችን  እየፈጠርን  ያላለውን  ማስባል  የለብንም።  የኢየሱስ የልጅነቱ  ዘመናት  ታሪኮች  በወንጌላት  ውስጥ  አልተጻፉም።  ያልተጻፉት አስፈላጊ  ስላልሆኑ  ነው።  ቢሆኑ  ኖሮ፥  እኔ  ደግሞ  ስለ  ተማርኸው  ቃል እርግጡን  እንድታውቅ  በጥንቃቄ  ሁሉን  ከመጀመሪያው  ተከትዬ በየተራው  ልጽፍልህ  መልካም  ሆኖ  ታየኝ    ያለውና  ከወንጌላቱ  ሁሉ በዝርዝር የዘገበው ሉቃስ ይህን አይጽፍም ኖሮአል?

   ስሟስ? የማርያምን  የስሟን ትርጉም በመቅድሙ  ላይ  “መንግሥተ  ሰማይ መርታ  የምታገባ”  ማለት  ነው  ሲል  ይተረጉማል።  በሌሎችም  ቦታዎች፥ ለምሳሌ፥  ምዕ.  12፥  74፥  98  ወዘተ፥  በዕብራይስጥ  ማሪሃም  የተባለች እያለ ተመሳሳይ ስምና ትርጉም ያቀርባል። እንዴት ፈጥረው ቢተረጉሙት ነው  ባለ  አራት  ፊደል  ስም  ይህ  ሁሉ  ቃል  ያለበት  ትርጉም  የሚሰጠው?
መምራት፥  ማስገባት፥  እና  መንግሥተ  ሰማያት  የሚባሉት  ቃላት  ማርያም ወይም  ሚርያም  በሚባለው  ስም  ውስጥ  ከቶም  የሉም።  በመጀመሪያ በዕብራይስጥ  ማሪሃም  አትባልም፤  ሚርያም  ናት።  ማርያም  በምንም ቋንቋ፥  በዐረብኛም  እንኳ  ማሪሃም  አልተባለችም።  ደግሞም  የስሟ ትርጉም  የተለያዩ  አገባብ  ትርጉሞችም  እንኳ  ተጨምረው  ዓመጽ፥ እንቢተኝነት፥ መራራ፥ መራራ ባሕር ማለት ነው እንጂ መንግሥተ ሰማይ መርታ  የምታገባ  ማለት  አይደለም።  ይህ  አልዋጥ  ካለንም  በግድ እንዋጠው፤ ዕብራይስጥ ብለን ከጠቀስን ትርጉሙ ይኸው ነው። በተአምር  21  ኢየሱስና  ማርያም  ለሐዋርያት  ተገልጠው  ጌታ  ለሐዋርያት በእርሱና  በእናቱ  ስም  በ4ቱ  ማዕዘናት  አብያተ  ክርስቲያናት  ይሠሩ  ብሎ አዘዘ።  በስሟ  ቤተ  ክርስቲያን  ማነጽ  ቀርቶ  ሐዋርያት  ስሟን  ጠርተው ሰብከው  ያውቃሉ?  በምዕ. 7  ደግሞ  ዕርገቷን  በ4ቱ  ማዕዘን  እንዲያውጁ አዘዛቸው  ይላል።  ሐዋርያት  እንዲህ  ተብለው  ይህን  አለመጻፋቸው ይደንቃል!  የታዘዙትን  ቤተ  ክርስቲያን  አለመሥራታቸውም  ዕርገቷን
አለማወጃቸውም  ያስጠይቃቸዋል።  አንዱን  ቤተ  ክርስቲያን  ጴጥሮስ እዚያው  ማነጹ  ተጽፎአል።  በአዲስ  ኪዳንና  በመጀመሪያዎቹ  የቤተ ክርስቲያን  ታሪክ  ዘመናት  ውስጥ  ክርስቲያኖች  ምእመናንን ሲያንጹ እንጂ ሕንጻ  ሲሠሩ  አይታወቅም።  ያመልኩ  የነበረውም  በምኩራቦችና  በቤት ውስጥ  እንጂ  ሕንጻስ  አላነጹም።  ማርያም  ለመጨረሻ  ጊዜ  በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ  የተጠቀችውም  ይኖሩበት  በነበረው  በተባለው  ሰገነት ውስጥ  ከጌታ  ሐዋርያት፥  ከደቀ  መዛሙርትና  ከወንድሞቹ  ጋር  በጸሎት ስትተጋ  ነው  የታየችው  እንጂ  ሰዎች  ወደ  እርሷና  ወደ  ስዕሏ  ሲጸልዩ አትታይም፤  ሐዋ. 1፥14  እነዚህ ሁሉ  ከሴቶችና  ከኢየሱስ  እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር ይላልና።

     ይኼ ሁሉ  የተደረተባት  ድሪቶ  ማርያምን  እንደሚያሳዝናት  የታወቀ  ነው። በእውነቱ  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ደራሲዎቹ  በመልካቸው እንደምሳሌያቸው  የፈጠሯት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ከቶም አይደለችም።  እምነታችንንም  ራስና  ፈጻሚውን  ኢየሱስን  ተመልክተን ከተባለለት  ከኢየሱስ  ሰዎች  ዓይናቸውን  እንዲያነሡ፥  እንዲያውም ከቶውኑ  እንዳያዩት ተብሎ  የተፈጠረችና ማርያም  ተብላ  የተሰየመች  ሴት ናት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ዛሬም  ብትጠየቅ  ያኔ  እንዳለችው፥ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ የምትል ናት።
በተአምር  4  ላይ  ማርያምን  ለመገነዝ  ሲሄዱ  ታውፋንያ  የተባለ  አይሁድ አልጋዋን  ስለያዘ  እጁ  በመልአክ  ተቆርጦ  አልጋው  ላይ  ቀረ።  ይህ  ሰው ሐዋርያትን  ይቅርታ  ጠየቀ፤  ክርስቶስንም  ይቅር  እንዲለው  ለመነ። ሐዋርያት  ግን  ወደ  እመቤታችን  ለምን  አሉት።  ማርያም  ቀድሞውኑ ከሞት  ተነሥታ  ነበርና  ለመናት።  ማርያምም  ጴጥሮስን  እንዲቀጥልለት ነገረችው። ጴጥሮስም በክርስቶስ ስምና በማርያም ስም እጁን መለሰለት። ይህ  ጴጥሮስ  ሐዋርያው  ጴጥሮስ  ከሆነ  መቸም  ይደንቃል።  ይህ  ጴጥሮስ በሐዋ.  3፥6  ብርና  ወርቅ  የለኝም፤  ይህን  ያለኝን  ግን  እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው ያለውና በኋላ በዚህ ስም ላይ ሌላ የለጠፈበት ነው? ይህ ጴጥሮስ በሐዋ. 4፥12 መዳንም በሌላ  በማንም  የለም፤  እንድንበት  ዘንድ  የሚገባን  ለሰዎች  የተሰጠ  ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና  ያለው ነው? እንዴት ያለ ቁልጭ  ያለ ግጭት ነው?  ይህ  የተከሰተው  ከሐዋ. 3  እና  4  በኋላ  ነው  ቢባል  ጴጥሮስ  ብዙ ቆይቶ  በጻፈው  በመልእክቱ  ምነው  የማርያምን  ስም  እንዲያው  አንዴ እንኳ  ያላስገባው?  ይህ  በኢየሱስና  በማርያም  ስም  ብሎ  እንደተናገረ የተጻፈለት  ጴጥሮስ  በመልእክቱ  ውስጥ  በ1ጴጥ. 4፥14  ስለ  ክርስቶስ  ስም ብትነቀፉ የክብር መንፈስ የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ላይ ያርፋልና ብፁዓን  ናችሁ  ያለውና  የክርስቶስን  ስም  ብቻ  ያጎላውና  የእርሱን  ብቻ ማንነት  አጉልቶ  የገለጠው  ነው?  ነው  ቢባል  እንኳ  የቱን  እንቀበል?  መጽሐፍ ቅዱስን ወይስ መጽሐፍ ቅዱስን የሚጻረረውን ሌላ መጽሐፍ? በተአምር  3  ማርያምን  ለመቅበር  ሲሄዱ  ሐዋርያት  ሁሉ  ጥለዋት  ተበተኑ ከዮሐንስ  በቀር  ይላል።  ልክ  ጌታ  ሲያዝ  እርቃኑን  በነጠላ  ከሸፈነው ዮሐንስ  በቀር  ሁሉ  እንደሸሹ  ይህንንም  የጻፈው  ይህ  ደቀ  መዝሙር መሆኑ  እንደተጻፈ  እዚህም  የፍልሰቱን  መጽሐፍ  የጻፈ  እርሱ  መሆኑ
ተጽፎአል።  የዚህ  ምዕራፍ  ግጭት  ከምዕ.  6  ጋር  ነው።  በተአምር  3  ጥለዋት  ተበተኑ  ሲል  በተአምር  6  ፈጽሞ እንዳልጣሏት፣  ግን  ገንዘው፥ ታቅፈው፥  ተሸክመው  እጅ  ነስተው  በጌቴሴማኒ  ቀበሯት  እንጂ አልጣሏትም ይላል። የቱ ነው ትክክል? ምዕ. 3 ወይስ 6? ለነገሩ የተለያዩ ሰዎች  ያዋጡት  መጽሐፍ  ስለሆነ  እንዲህ  እርስ  በርሱ  ቢጋጭ አያስገርምም።
በምዕ. 10  ኢየሱስ  በዋሻ  ውስጥ  መወለዱና  በጨርቅ  መጠቅለሉ  ሳይሆን የበለስ ቅጠል መልበሱ፥ በምዕ. 11 ደግሞ በጨርቅ መጠቅለሉ ተጽፎአል። በመንገድ  መካከል  ተወለደም  ይላል።  ይህ  የራስ  ከራስ  ግጭት  ነው።
መልአክ  ሄዶ  ለሰብዓ  ሰገል  እንደነገራቸው፥  ሰብዓ  ሰገል  ደግሞ  ሽቱም አምጥተውለት  እንደነበር  ተጽፎአል።  እነዚህ  ሁሉ  የተጻፈ  ታሪክን የሚያፋልሱ ናቸው።

    ከንጉሥ  ልጇ  ደም  በፈሰሰ  ደሟ  እኛን  ንጹሐን  አድርጋ  . . .  ይላል  ምዕ. 12፥54።  የማን  ደም  ነው  የፈሰሰ?  የማን  ደም  ነው  ያዳነ?  የማርያም  ደም ያዳነ በሆነማ  ኖሮ  ክርስቶስ ምነው  በመስቀል መዋሉ? ቃሉ በኤፌ. 2፥13  የሚለው አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ  በክርስቶስ  ደም  ቀርባችኋል  ነው  እንጂ  ከልጇ  በፈሰሰው በማርያም ደም  ቀርባችኋል  አይልም።  ጳውሎስ  ኤፌሶንን  ሲጽፍ ማርያም ሞታ  ወይም  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  አርጋ  ስለነበረ  ጳውሎስ ይህንን  ማወቅ  ነበረበት።  ቆላ.  1፥19  በመስቀሉ  ደም  ሰላም  ማድረጉን ይናገራል፤  ሌላ  ደም  አይናገርም።  ዕብ.  9  በሙሉው  ይህንን  ደም ይናገራል  እንጂ  የማርያም  ደም  አይልም።  1ጴጥ. 1  የተዋጀንበትን  ክቡር ደም የክርስቶስ ደም ይለዋል እንጂ የማርያም አይለውም።
በምዕ.  7  በፍልሰቷ  ቀን  (ለነገሩ  ቀኖቹ  ሁሉ  በኛ  አቆጣጠር  ነው የተጻፉትና  በግብጽ  ወይም  በአይሁድ  ቆጠራ  ተጽፈው  መመንዘራቸው አልተነገረም)  በነሐሴ  16  ተዝካሯን  ለዘከረ  ኃጢአቱ  እንደሚሰረይ  ጌታ እንደሰጠ  ይናገራል።  በጣም  ትልቅ  ግጭት!  ኃጢአት  የሚደመሰሰው በነሐሴ  16  ተዝካር  ማድረግ  ከሆነ  መጽሐፍ  ቅዱስ  ከሚለው  ጋር  ፈጽሞ ይጣላል።  በክርስቶስ  በማመን  በጸጋ  ድኖ  በመስቀል  ላይ  በፈሰሰ  ደሙ የኃጢአት  ማግኘት  ወይስ  ደግሶ  አብልቶ  መዳን?  ወይስ  ከሁለቱ  ደስ ያለንን መርጠን መውሰድ?
በተአምር  32  ስለ  አንዲት  ዘማዊት  ይናገራል።  እንደ  ሙሴ  ሕግ እንድትወገር  እንደተፈረደ  ይናገራል  ደግሞም  ቤተ  መቅደስ  ውስጥ  ገብታ ይላልና  ደግሞም  በአዲስ  ኪዳን  ኃጢአተኛን  በድንጋይ  መውገር  የለምና ይህ  የብሉይ  ኪዳን  ዘመን  ይመስላል።  እንዳይባል  ደግሞ  ዘማዊቷ የማርያምን  ስዕል  አግኝታ  ለመነች  ይላል።  መልእክቱ  ወደ  ስዕል  ለምኖ መፍትሔ  ማግኘት  ቢሆንም  በመቅደስ  ውስጥ  የማርያም  ስዕል  ሊኖር አይችልም።  የቤተ  ክርስቲያን  መቅደስ  ነው  ከተባለ  ደግሞ  በቤተ ክርስቲያን  ወይም  በክርስትና  ዘመን  ኃጢአተኛን  መውገር  ከየት  የመጣ ፍርድ ነው? እርስ በራሱ የተማታ ታሪክ ነው።
ሰይጣን  መንፈስ  ነው  እንጂ  ስጋዊ  አካል  አይደለም።  በምዕራፍ  34  ሰይጣንን ማርያም በጥፊ አጩላው ልቡናውን ሲስት ይታያል። በምዕራፍ 51  ደግሞ  የመነኮሳትን  ምድጃ  ስላፈረሰ  አንድ  ሰይጣን  ተጽፎአል። መነኮሳቱ  ወደ  ማርያም  ጮኹና  ለ12  ዓመታት  ባሪያ  ሆኖ እንዲያገለግላቸው  ምድጃቸውን  ያፈረሰውን  ያንኑ ሰይጣን ሸለመቻቸው።
እነዚህ  መነኮሳት  ሰይጣንን  ተቃወሙት  የሚለውን  ቃል  አይታዘዙም ማለት  ነው።  ወይም  ቃሉን  ጨርሶውኑ  አያውቁም  ማለት  ነው።  ሳያውቁ ግን  መነኩሴዎች  ናቸው።  ማዕድ  ቤት  አስገብተው  እየፈጨ፥  እያቦካ፥ እየጋገረ ዓሳ ነባሪ እያጠመደ ከመርከብ ጋር እየተሸከመ አምጥቶ መርከቡ ውስጥ  የነበሩትን  ሰዎች  የሚያስመነኩስ  ይህ  አገልግሎት  ከማዕድ  ቤት ሥራ ያለፈ ነው!
    በምዕራፍ  37  ማርያም  ቴክላ  ወደተባለች  ሴት  ሄዳ  ስታስተዛዝናት፥ ልጇን  30 ዓመት በሆነው  ጊዜ  ከእርሷ ቀምተው  በእንጨት  ላይ ሰቅለው እንደ  ገደሉት  ነገረቻት። ጌታ ከማርያም  ተቀምቶ  ተገደለ  ወይስ ቀድሞም ሊሞት  ነው  የመጣው?  ደግሞስ  በ30  ዓመቱ  ነው  የተገደለው?  ሉቃ.  3፥23  በሠላሳ  ዓመቱ  አገልግሎቱን  መጀመሩን  ነው  የጻፈው።  ሳያገለግል ነው የተሰቀለው ማለት ነው? ተአምረ ማርያም ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ገድሎች ጋርም ይጋጫል፤  ይጣላል።  አንድ  ብቻ  ምሳሌ  ለመውሰድ፥  በገድለ  ተክለ ሃይማኖት  በመግቢያው  ምዕራፍ  ቁ.  40-46  እና  80-81  “.  .  .  አባቴ የሚለው  ግን  ዝክሩን  የሚዘክር  ስሙን  የሚጠራ  ከሱ  ጋራ  የዘላለም ሕይወት  ያገኛል  ዝክሩን  ያልዘከረ  ቃሉን  ያልጠበቀ  ከርስቱ  ከመንግሥተ ሰማያት  የተለየ  ይሆናል  የሞቱ  ሰዎችን  ነፍስ  ሁሉ  ክርስቲያን  የሚባሉ ጻድቅም  ኃጥእም  ቢሆን  የሞቱትን  ከክቡር  አባታችን  ከተክለ  ሃይማኖት ዘንድ  ሳያደርሱ  አይወስዳቸውምና  . . .  ለሥጋችሁ  መጠበቂያ  ለነፍሳችሁ መዳኛ  ነውና፤  ኃጢአታችሁን  የሚያነጻ  .  .  .”  ይላል።  እዚህ  ተክለ ሃይማኖት  የመንግሥተ  ሰማያት  መንገድ፥  የነፍስ  መዳኛና  የኃጢአት ስርየት  ሆኖ  ተገልጦአል። 16
   ማርያም  ወደ  መንግሥተ  ሰማይ  መርታ የምታስገባ  ተብላለች  ተክለ ሃይማኖትም በሩ  ከሆነ  የመዳን መንገዱ ብዙ ነው ማለት ነዋ! የማርያም ዝክር ነው መዳኛው ወይስ የተክለ ሃይማኖት?
በምዕ.  98  ስለ  ይሁዳ  እግረ  መንገድም  ቢሆን  የተነገረው  ጌታን  ሽጦ እናቱን  አግብቶ  አባቱን  መግደሉ  ተጽፎአል።  ቅደም  ተከተሉ  እንደዚያ ከሆነ  እናቱን  አግብቶ  አባቱን  የገደለው  ጌታን  ከሸጠ  በኋላ  ነው  ማለት ነው።  በትክክል  የሞተው  መቼ  እንደሆነ  ባይታወቅም  ተጸጽቶ  ወዲያው ሄዶ  ነው  ታንቆ  የሞተውና  (ማቴ.  27፥1-10)  ጋብቻውም  ግድያውም በሰዓቶች  ውስጥ  ምናልባት  በደቂቃዎች  መሆን  አለበት።  ያለዚያ  እናቱን አግብቶ  አባቱን  የገደለውንና  የአይሁድ  ሕግ ዝም  ያለውን  ሰው  ነው  ጌታ ከሐዋርያቱ ክልል ያስገባው።
     በምዕ. 121  ኢየሱስን  በ8  ዓመቱ  በጎች  እንዲጠብቅ  ላከችው  ይልና  ወደ ደብረ ዘይት መጥቶ በጎቹን አሰማራ ይላል። ለማያውቅ ሰው ልክ  እሰፈር ዳርቻ  በጎቹን  ወስዶ  የመሰገ  ይመስላል።  የሚኖሩት  ናዝሬት  በጎች የሚጠብቀው  ደግሞ  ደብረ  ዘይት  መሆኑን  እንደገና  እናስተውል።  ደብረ ዘይት እኮ ከናዝሬት የ105 ኪሎ ሜትር ሩቅ አገር ነው። በኛ አገር ከአዲስ አበባ  ናዝሬት  ማለት  ነው።  መልክዓ  ምድሩን  ለማያውቁና  ለማይጠይቁ ወይም  የተባለውን  ሁሉ  እውነት  ነው  ብለው  ለሚቀበሉ  አድማጮች የተጻፈ  በመሆኑ  ደራሲዎቹ  ይህን  እና  ይህን  የመሰሉትን  ግጭቶች ለመመርመር ሙከራ አላደረጉም።
በምዕ.  120  ኢየሱስን  በ5  ዓመቱ  የሚያስተምረው  አስተማሪ፥  “ይህ የመበለት  ልጅ”  ይለዋል።  ማርያም  መበለት  ሆነችሳ!  ዮሴፍ  ሞተ  ይሆን?
መቼም  የኢየሱስ  አስተማሪ  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  ዮሴፍ “ጠባቂዋ”  መሆኑን  አያውቅም።  በምዕ. 121  ደግሞ  በ8  ዓመቱ  አሳዳጊው ዮሴፍ  ተጠቅሶአል።  በወንጌሉ  ውስጥ  ደግሞ  በ12  ዓመቱም  በሕይወት መኖሩ  ተዘግቦአል።  በተአምረ  ማርያም  ዮሴፍ  የማርያም  እጮኛ  እንኳ ሆኖ  አልቀረበም።
ሲደመደም፥  ተአምረ  ማርያም  ለሥጋዊ  አኗኗርና  ለኃጢአተኛ  ተፈጥሮ የሚስማማ  መጽሐፍ  ነው።  መጽሐፍ  ቅዱሳዊ  የቅድስና  አመላለስ፥ ክርስቶስን  መምሰል፥  ዋጋ  መክፈል፥  ለእውነት  መሰደድ  በውስጡ የሉበትም።  ክርስቶስን  አዳኝ  አድርጎ  መቀበልና  የሕይወት  ጌታ  አድርጎ እርሱን  መከተል  የሉበትም።  በምንም  ኃጢአት  ውስጥ  ተኑሮ  ለስዕል አቤት  ከተባለ፥  ዝክር  ከተዘከረ፥  በማርያም  ስም  አንዳች  ከተደረገ መንግሥተ  ሰማያት  የመግባት  ተስፋ  አለ።  ስለዚህ  እንደፈለጉ  ኖሮ ማርያምን  ጠርቶ  መናገርና  እርሷ  ደግሞ  ለልጇ  ተናግራ  የሚሹትን  ሁሉ ማድረግ ስለምትችል መልካሙን ገድል መጋደል አይታወቅም። ተአምረ  ማርያምን  ማሔስን  ካላቆሙት  በቀር  መቆም  አይችልም።
ምክንያቱም  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ከራሱ  ከመጽሐፉ  ሌላ  ምዕራፍ፥ ከታሪክና  ከእውነት፥  ከአእምሮና  ከተፈጥሮ፥  በተለይም  ከመጽሐፍ  ቅዱስ ጋር  በምሬት  የሚጣላ  መጽሐፍ  ነው።  በአጭር  ቃል  ተአምረ  ማርያም ጠላት ከዘራቸው ብዙ እንክርዳዶች አንዱ ነው።
ጌታ ከአርያም ይባርካችሁ።
ዘላለም መንግሥቱ  © 2012 (፪ሺህ፬) ዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት
1 ሰውና እግዚአብሔር በኃጢአት ምክንያት ተለያዩ
3. ሰው በራሱ ጥረት ወደ እግዚአብሔር መድረስ አይችልም።
በመጣጥፉ ውስጥ የተጠቀሱ መጻሕፍት፤
በአባቶቻችን  አፈርን፥  ባዩ  ታደሰ  እርዳቸው  (መምህር)፥
[ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም] አዲስ አበባ፥ ፪ሺህ፫ ዓ. ም.።
ይነጋል፥  ጽጌ  ስጦታው  (ዲያቆን)፥  አፍሪካ  ማተሚያ፥  አዲስ
አበባ፥ Ŧ ŹƃƂƋ ዓመተ ምሕረት።
ገድለ  አቡነ  እስጢፋኖስ  ዘጉንዳጉንዶ፥ 1997   ዓ.  ም.  አሳታሚ፥
መምህር ወማኅበር ዘጉንዳጉንዶ ደብረ ገሪዛን።
ለእውነት እንቁም፥ ስሜ ታደሰ፥ SIM Publishing፥ አዲስ አበባ፥
፪ሺህ ፬ ዓ. ም.።
ገድለ ተክለ ሃይማኖት፥ [አሳታሚና ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም]
አዲስ አበባ፥ 1989 ዓ. ም. ።
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በአስተዋጽዖ፥ መሠረት ስብሐት
ለአብ፥  አሳታሚ  ፍኖተ  ሕይወት  ማኅበረ  መነኮሳት፥  የኅትመት
ዘመን አይታወቅም፥ አዲስ አበባ።
ገድለ  ክርስቶስ  ሠምራ፥  ትንሣኤ  ዘጉባኤ  ማተሚያ  ቤት፥  አዲስ
አበባ፥  1992ዓ. ም. ።
Schaff, Philip,  History of the Christian Church,  Nicene
and Post Nicene Christianity,  T & T Clark, Edinburgh,
1884.
Tamrat, Tadesse,  Church  and State in Ethiopia  1270-1527, Oxford University Press, London, 1972.

Sunday, July 13, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!



( እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)
ክፍል አምስት

6.  የተጣረሰ  ደኅንነትና  የተቃወሰ  ክርስትና።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ ተዝካር  ያድናል፤  ማርያምን  ማመን  ያድናል፤  ተዝካሯን  መደገስ  ያድናል። በምዕ. 67  እረኞች  ያጠመቁት  አይሁድ  ውኃ  በቋጫ  ስለረጩበት  ብቻ ክርስቲያን  ሆነ፤  በ94  በንጹህ  እጅ  መቁረብ  መንግሥተ  ሰማያት ያስገባል።  78  ሰዎች  ቆርጥሞ  በልቶ  በማርያም  ስም  ጥርኝ  ውኃ  ከተሰጠ  ያ  ሚዛኑን  ደፍቶ  ከገሃነም  ፍርድ  ነጻ  ያወጣል።  ምጽዋት  መስጠት መንግሥተ  ሰማያት  ያስገባል፤  ምዕ.  44፤  ወዘተ።  ክርስትና  በተአምረ ማርያም  መመነን፥  መመንኮስ፥  ያለማግባት  ወይም  ጋብቻን  መጠየፍ፥ ከተጋቡም  በኋላ  አብሮ  ከመተኛት  ያለመገናኘት፥  ወደ  ስዕል  መጸለይና  መስገድ፥ ወዘተ፥ ናቸው። በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ግን  ደህንነትና  የክርስትና  ኑሮ  በቃልና  በሥራ ክርስቶስን  እየመሰሉ፥  እየተከተሉ  የመኖር፥  መስቀሉን  የመሸከም  የደቀ መዝሙርነት  ኑሮ  ነው።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  መዳን  በሌላ  በማንም እንደሌለ፥  እንድንበት  ዘንድ  የተሰጠ  የኢየሱስ  ስም  ብቻ  መሆኑ፥ ክርስቶስን  የተቀበሉ  ሁሉ  የእግዚአብሔር  ልጆች  መሆናቸው፥  ለመዳን ማመን  ብቻ  እንጂ  ልፋት  እንደማያስፈልግ፥  ያመነ  የተጠመቀ እንደሚድን፥  መዳን  ደግሞ  የሚታወቅና  የሚረጋገጥ  እንደሆነ  በግልጽ  ቋንቋ  ተጽፎአል።  በተአምረ  ማርያም  ግን  ይህ  አዳኝ  እና  የማዳኑ  ደስታ  ሲሸፈንና  እንዳይታይ  ሲደበቅ  ይስተዋላል። በምዕ.  41፥13  “በእግዚአብሔር  አምነው፥  በወለደችውም  በእመቤታችን አምነው  ከቤተ  ክርስቲያን  ወጡ”  ይላል።  ቁ.  25  እምነቱን  በናቱና  በእግዚአብሔር  ላይ  ያደረገ  ሁሉ  አያፍርምና  ይላል።  53፥55  ላይ  እግዚአብሔርን  አመሰገኑ  እመቤታችንንም  አመሰገንዋት  ይላል።  እምነት ክርስቶስ  ሲደመር  ሌላ  ነገር  ሆነ  ማለት ነው! በምዕ. 56  ማርያም  አንዱን መነኩሴ፥ “ከሚያልፈው ዓለም እስክወስድህ  ድረስ  ልጄ  ካንተ  አይለይም”  አለችው። ወሳጇ  እርሷ ስትሆን እስክትወስደው  ከመነኩሴው  የማይለየው  ልጇ  ነው።  ልክ  እንደ  አገልጋይ  ማለት  ነው።  በመጽሐፉ  ማርያም  ብቻ “ከልጇ  ጎን  በፈሰሰው  ደሟ”  አዳኝ  ሆና  ቀርባለች።  ታዲያ  ይህ የሰሚዎችን  ጆሮ  እያደነቆረ  የጠፉቱ  የምሥራቹን  ወንጌሉን  እንዴት ይስሙ?

7.  የተላቀቀ  መልክዓ  ምድር።

 በተአምረ ማርያም  ውስጥ  የተናጋ  መልክዓ  ምድርም  ይታያል።  ኢየሱስ  በዋሻ  ውስጥ  ተወለደ  ይላል፤  ለምሳሌ፥  ምዕ. 10።  ግርግምና  ዋሻ  እንደምን  አንድ  ሆኑ?  በ106  በኢያሪኮ  ባህር  ዳርቻ  ገዳም  ያለባት  ደሴት  መኖሯን  ይናገራል።  ደሴት  በባህር  ውስጥ  እንጂ  በባህር  ዳርቻ  አይኖርም።  ይሁን  እዳሩጋ  ጠጋ  ብሎ  ነው  ይባል።  ግን ኢያሪኮ  እኮ  ከተማ  እንጂ  ባህር  አይደለችም።  ኢያሪኮ  የሚባል  ባህር ኖሮም  አያውቅም።  በኢያሪኮ  አቅራቢያ  የዮርዳኖስ  ወንዝ  ነው  ያለው፤ ያም ቢሆን ገዳም የተገደመበት ደሴት የለበትም። ምዕ. 9  እና  ምዕ. 118  ከእስራኤል  ወደ  ግብጽ  ወይም  ከግብጽ  እስራኤል ሲሄዱ  ባህር  ሲሻገሩ  ይታያሉ።  በሁለቱ  አገሮች  መካከል  የየብስ  መንገድ ሳለ  በባህር  የሚያስዞር  ምክንያት  የለም።  ምናልባት  ከእስራኤል  ባህረ  ኤርትራን  መሻገር  ጋር  ለማቆራኘት  ይሆናል።  ወይም  ምናልባት  ከክብረ ነገሥት  ታሪክ  ጋር  ለማመሳሰል  የተደረገ  ሙከራ  ነው።  በጉዞውም  ተጋንነው  የተጻፉት  ነገሮች  ከክብረ  ነገሥት  ጋር  መመሳሰል  ስላላቸው  ከዚያ  የተኮረጀ  ይመስላል።
በምዕ. 72  ከሄሮድስ  ሸሽታ  ወደ  ዮሳፍጥ  ሸለቆ  ሄዳ  መሸሸጓ  ተጽፏል። ሊያያት  የመጣው  ገዢ  ከሄሮድስ  ሌላ  ሲሆን  ይህ  ሰው  ከሄሮድስ  ጋር ሊዋጋ  ዘምቶ  በማርያም  አማላጅነት  ተመለሰ።  እንደ  ፀሐይ  የሚያበራ ግርማ  ኖሯት  መሸሿ ወደ  ጎን ይቅርና፥ ጫካውም  ጫካ  ሆኖ ገዳም  መሆኑ ወይም  መባሉም  ይቅርና  በዮሳፍጥ  ሸለቆ  መደበቋና  ሁለቱ  ኃያላን  ሊዋጉ  መሰላለፋቸው  ሁለት  አገሮች  ብቻ  ሳይሆኑ  የሩቅ  አገሮችም  ያስመስላቸዋል።  ግን  የዮሳፍጥ  ሸለቆ  ከኢየሩሳሌም  በ20  ኪሎ  ሜትር ርቀት  የሚገኝ  ስፍራ  ነው።  በዚህ  አጭር  ርቀት  በሄሮድስ  ግዛት  ውስጥ ሌላ ገዥ ያውም  ከሄሮድስ  ሊዋጋ  የቃጣ  አልኖረም።

8.  የተዋረደ  ጋብቻ። 

መጽሐፍ  ቅዱስ  ጋብቻ  ክቡር  መኝታውም  በሁሉ  ቅዱስ  መሆኑን  ያስተምራል።  ጋብቻ  በማኅበራዊ  ረገድ፥  ለቤተ  ሰብ  ጤናማነት፥  በቅድስና  ለመኖር፥  ዘርን  ለመጠበቅ  በሙሉ  መልኩ፥ የተከበረ  ተቋም  ነው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የሚታየው  ግን  የዚህ ተቃራኒ  ነው።  ጋብቻ  የተናቀ  ነው።  ያላገቡ  ሰዎች  በተአምረ  ማርያሟ ; ማርያም  እንዳያገቡ  ይመከራሉ።  የተጋቡም  ሳይቀሩ  ትዳራቸው  ፈርሶ  እንዲመንኑ  ይደፋፈራሉ።  ምዕ.  65፥  66፥  68፥  75፥  86፥  92፥  100 እንዳያገቡ  የተከለከሉ  ሰዎች  ታሪኮች ይነበባሉ።
በምዕ. 30  ካህን  ዘራፊዎችን  ግደሉ  አባለ  ዘራቸውንም  ስለቧቸው  ብሎ  ሲያዝ  ይታያል።  ለነገሩ  ከተገደሉ  በኋላ  ብልት  ዋጋ  የለውም፤  ግን የተደረገው  ሁሉ  ተደርጎ  ይህ  ሁሉ  በማርያም  አማላጅነት  ተደረገ  ብሎ ይደመድማል።  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  አባለ  ዝርም  እንዲሰለብ  ታደርጋለች።  በምዕ. 85  ከገዛ  ሚስቱ  ጋር  መተኛቱ  እንደ  ኃጢአት  ሆኖበት  አባለ  ዘሩን  የቆረጠ  ሰው  ይገኛል።  ይህ  ሰው  ከደም  ፍሰት  የተነሣ  ሞቶ  መንግሥተ  ሰማያት  ሄዶ  በማርያም  ትእዛዝ ነፍሱ  ወደ  ሥጋዋ  ተመለሰችና  በሕይወት ኖረ።  መንግሥተ  ሰማያት  ከገባ  በኋላ  ነፍሱን  ብትመልስም  ቅሉ  ብልቱን ግን  አልቀጠለችለትም።  የሽንት  መሽኛ  ቀዳዳ  ብቻ  ተደርጎለት  መንኩሶ ኖረ።  በተአምረ  ማርያም  ትዳር  የቀለለ  ብቻ  ሳይሆን  የረከሰ  ነገር  ነው።
ከመነኮሰች  በኋላ  በፈቃደ  ሥጋ  ተሸንፋ  ከገዳም  የወጣችና  ያገባች  ሴት በመካንነት  ተቀጥታ  ወደ  ገዳሟ  ተመለሰች።  ሌሎችም  ይህም  የመሰሉ ታሪኮች ታጭቀውበታል።

9.  ያፈነገጠ  ተፈጥሮ።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የበዙ  ከተፈጥሮ ሥርዓት  ጋር  የማይስማሙና  የሚቃረኑ  ነገሮች  ይነበባሉ።  በምዕ.  70  አንድ  ሰው  ሥጋ  ወደሙን  ከወሰደ  በኋላ  አውጥቶ  በንብ  ቀፎው  ውስጥ አደረገው።  በኋላ  ሥጋ  ወደሙ  ወደ  ብርሃንና  የማርያም  ስዕልነት  ተለወጠ።  በእጅግ  ብዙ  ቦታዎች  የማርያም  ስዕል  ከስዕል  ተፈጥሮ  ውጪ  ድምጽ ሲወጣው፥  ሲደማ፥  ወዝ  ሲወጣውና  ሰዎች  ያንን  እየተቀቡ  ሲፈወሱ ይታያል።  እጅ  ዘርግቶ  ከተንቀሳቀሰ  ወይም  ሌላ  ስዕል  ከሰጠ፥  የቆሰለበት  ስፍራ  ጠባሳ  ከኖረው፥  ስዕል  ሲወጉት  ከደማ  (ለምሳሌ፥  ምዕ. 31)  ስዕሉ  ሕይወት  አለው  ማለት  ነው።  ምክንያቱም  መጽሐፍ  ቅዱስ  ሕይወት በደም  ውስጥ  መኖሩን  ይመሰክራል።  ከላይ  እንደተጠቀሰው  ስዕል  በራሱ  የተፈጠረ  ካልሆነ  ስዕል  እየሠሩ፥  እየሸጡ  የሚተዳደሩ  ሰዎች  አሉና  ስዕሎቹ  በሰው  የተሠሩ  ለመሆናቸው  ጥርጥር  የለበትም።  የስዕል  አምልኮ  በመጽሐፍ  ቅዱስ  የተወገዘ  መሆኑ  እንዳለ  ሆኖ  ስዕሎቹ  ተአምራት ካደረጉ፥  ሲወጉአቸው  ከደሙ  ሕይወት  አላቸውና  ሠሪዎቹ  ምን  ሊባሉ ነው?  ፈጣሪ?  አምላክ?  በተአምረ  ማርያም  ስዕል  ብቻ  ሳይሆን  ዳቦም ሲቆርሱት ደምቷል። በተአምረ  ማርያም  ወደ  ዓሳነት  ሳይለወጡ  በባህር  ውስጥ  ሆኖ  መተንፈስም፥  መጸለይም፥  እንዲያውም  መውለድም  ይቻላል።  በተአምር 97  አንድ  መነኩሴ  የውኃ  ሙላት  አማታውና  ሰይጣን  ወስዶ  እባህር ከተተው። እዚያ ሳለ ማርያምን  ጠርቶ ሲጸልይ ማርያም  መጥታ  ሰይጣንን  ገሰጸችለት።  እሱም  ውዳሴውን  ቀጠለ፤  የሚጸልይበትን  ቦታ  አሳየችውና በዚያ  ሲጸልይ  አደረ።  ዋናተኞች  ለፍለጋ  ሲጠልቁ  ውዳሴዋን  ሲደግም  አግኝተው  አወጡት።  እዚያ  ለመቆየት  ሲል  ባትመጡብኝ  ይሻለኝ  ነበር አላቸው።  በተአምር  88  ደግሞ  አንዲት  ነፍሰ  ጡር  ከመስጠም  መዳኗ  ብቻ ሳይሆን  በባሕር  ውስጥ  ሳለች  በቤት  ውስጥ  እንዳለች  ሆና  በማርያም  ተሸፍና  ወልዳለች።  ያውም  ያለምጥ  ነው  የወለደችው።  ከተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ሌላ  ያለምጥ  የወለደች  ሴት  ናት  ይህች  ሴት።  በ375  ዓመቷ  የሞተችው  ክርስቶስ  ሠምራ  በጣና  ባህር  ውስጥ  ሰውነቷ  ተበጣጥሶ  ዓሳዎች  በውስጧ  እየሾለኩ  12  ዓመት  ጸልያ  ወጣች  እንደሚባለው  የመሰለ  ታሪክ  ነው። 15 በምዕ. 59  አንድ  የቤተ  ክርስቲያን  ጠባቂ  አንድ  ቀን  ከራት  በኋላ  የሥጋ ድቀት  አግኝቶት  ዝሙት  ፈጸመ።  በመልአክ  ተነክቶ  የሴት  መርገም ደረሰበትና  ከዚያ  በኋላ  ማርያም  ያደረገችበትን  ይህን  ነገር  አገር  ላገር  እየተናገረ  በመዞር  ኖረ።  መልአክ  ቢነካውም  ይህን  ያደረገችው  ማርያም  ናት።  ይህች  የዚህ  መጽሐፍ  ማርያም  ምንም  ነገር  ማድረግ  ትችላለች።

ሰብዓዊ  ተፈጥሮንም  ትቀይራለች።  የወር  አበባ  ካየ  ማኅጸን  ተሠራለት ማለት  ነው።  ማመንዘሩ  ኃጢአት  ሳለ  ቅጣቱ  ሴት  መደረግ  ወይም  እንደ ሴት  መደረግ  ከሆነ  ይህች  ማርያም  ሴትነቷንም  ትጠላዋለች  ማለት ይሆን? በምዕ.  107  ብዙ  ኃጢአት  ፈጽማ  ተስፋ  የቆረጠች  ተቅበዝባዥ  የሆነች ሴት  ታሪክ  ይገኛል።  ይህች  ሴት  ወደ  በረሃ  ሂዳ  ጊንጥ  አገኘችና ዋጠችው።  መርዙ  በሰውነቷ  ተሰራጭቶ  ስትሰቃይ  የማርያም  ስዕል  መጥቶላት  በዚያ  ሆዷን  እያሸች  ማርያምን  ለመነች።  ማርያም  ወደ  ቄስ ልካት  ለዚያ  ቄስ  ተናዝዛ  አምጣ  ወለደች።  የወለደችው  ሕጻንን  ሳይሆን 40  ትልልቅና  ትንንሽ  ጊንጦችን  ነው።  ወደ  አፍ  የገባ  ወደ  እዳሪ እንደሚወጣ  ጌታ  የተናገረው  ስሕተት  ተደርጎ  ወደ  ማሕጸን  ገብቶ  በ40  ተባዝቶ ወጣ!  እንደዚህ  ትምህርት  ከሆነ  ሴቶች ላም  እንወልዳለን  ብለው  በመፍራት  ወተት  መጠጣት  ማቆም  አለባቸው።  ወይም  አስር  ዶሮ  እንወልዳለን  ብለው  እንቁላል  መብላት  መተው  ይኖርባቸዋል።  ደግሞ  ሁሉም  እንደየወገኑ  እንዲዋለድ  በፍጥረት  መጀመሪያ  የተነገረውም  ተሰረዘና  ሴት  ጊንጥ  ወለደች።  ለተአምሩ  ትክክልነት  ሲባል  መጽሐፍ ቅዱስ  መስተካከል  አለበት።
ጊንጥ ብቻ  ሳይሆን  ሌላም  የከፋ  ወሊድ ታሪክ  አለ። በምዕ. 55 የሌላ  ሴት  ባል  የቀማች  አንዲት  ሴትና  ሌላኛዋ  ሴት  በማርያም  ታቦት  ፊት  እውነተኞች  መሆናቸውን  ይማማላሉ።  የቀማችው  ሴት  ኃጢአተኛ  ኖራለችና  እርጉዝም  ነበረችና  ቆይታ  ወለደች። የወለደችው  ሕጻን  ሳይሆን  በትል  የተሞሉ  ሁለት  የላም፥  ሁለት  የበግ  ቀንዶችን  ነው።  ይህች  ሴት እብድ  ሆና  እየዞረች  ይህንኑም  ያደረገችው  ማርያም  መሆኗን  እየተናገረች  ቆይታ  ሞተች። ቀንዶቹ  ደግሞ  ከማኅጸን  እንደወጡ  እንኳ  አልተቀበሩም።
በማርያም  ቤተ  ክርስቲያን  መስኮቶች  ተሰክተው  ይኖራሉ።  የትኛዋ  ቤተ ክርስቲያን  እንደሆነች  እንኳ  ቢናገሩ  ጉዱ  ይታይ  ነበር።  አገሩ  ብሔረ አግዓዚ  ከመባሉ  ሌላ  አይታወቅም።  በቀጣዩ  ምዕራፍ  (ምዕ. 56)  የያሬድ ቅኔ  ማኅሌት  እውስጡ  ስለተጠቀሰ  ብሔረ  አግዓዚ  የኛው  አገር  መሆኑን  እንረዳለን።  ቀድሞውኑም  የሌለ  ነገር  ስለሆነና  እንዲጠየቅና  እንዲመረመርም  ስለማይፈለግ  ስፍራው  አይገለጥም።  ወይስ  ዛሬም  ቀንዶቹ  ከአገራችን  ቤተ  ክርስቲያኖች  ባንዷ  መስኮቶች  እንደተሰኩ  ይሆኑ?