Tuesday, June 24, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!


ካለፈው የቀጠለ (ክፍል ሦስት)
(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

በምዕ.  24  የተጻፈው  ለማርያም፥  ለመስቀልና  ለስዕል  የማይሰግዱ የተባሉት  የአባ  እስጢፋኖስ  እና  የነደቀ  እስጢፋ  ታሪክ  መጽሐፉ ተተረጎመ  በተባለበት  ዘመን  እንኳ  ተፈጽሞ  ያላለቀና  ገና  እየተከሰተ  ያለ ነገር  ሆኖ ሳለ  ገና  ያልተፈጸመውን  ነገር  ከብዙ  ዓመታት  በፊት  ግብጽ  አገር  እንደተፈጸመ ተደርጎ የመጣና  የተተረጎመ  ማለት  ጥሬ  ውሸት  ነው።  ዘርዓ  ያዕቆብን ንጉሣችን  እያለ  ከተናገረ  ደራሲው  የዘርዓ  ያዕቆብ  ዜጋ  ነው  ማለት  ነው። ተርጓሚው  ማለት የተጻፈውን  ተርጓሚ  እንጂ  ያልተጻፈውን  ጨማሪ  አለመሆኑ የታወቀ ነው።

2.  የተቃለለ  ክርስቶስ።

 በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  የምናየው  ኢየሱስ  ለመሞትና ለኃጢአታችን  ስርየት ደሙን  ለማፍሰስ  ከማርያም  ሥጋን  ነስቶ ሰው  የሆነ አምላክና  ፈጣሪ ጌታና  እግዚአብሔር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ከአምላክና  ጌታ  ይልቅ  የተነገረውን  በፍጥነት  የሚፈጽም ቀልጣፋ  ተላላኪና አገልጋይ  ሆኖ  ነው  የቀረበው። ከመጀመሪያ  እስከ  መጨረሻ  ክርስቶስ  የማርያም  ልጅ  ነው።  ኢየሱስ  ከድንግል  ማርያም  ሥጋን  መንሳቱ  እውነት  ቢሆንም  ማርያምን ጨምሮ የፍጥረታት ሁሉ  ፈጣሪ  በመሆኑ  በግዕዘ  ህጻናት ዘወትር እናቱን ለመላላክና ለማገልገል  የመጣ በማስመሰል አምላካዊ  ኃይሉን በሰውኛ ፈቃድ ፈጻሚነት ስር ማስቀመጥ ትክክል አይደለም።  ሥጋ  የለበሰው  ኢየሱስ  እናትነት  አንድ  ነገር ነው።  የዘመን  መጀመሪያ  ለሌለው  አምላክ  እናት መሆኗ ብቻውን  ማርያምን  ከፍጥረቷ  በላይ  ሊያደርጋት  የተገባ  አይደለም።

 ነገር ግን  በተአምረ  ማርያም ውስጥ  ከማርያም  ጋር  በተጻፈባቸው  ቦታዎች  ስትጠራው  ልጄ  ወዳጄ  ብላ  ነው።  ሰዎች  ደግሞ  ወደ  ማርያም  ሲጸልዩ  እርስዋን  እመቤታችን  (እግዝእትነ)  ብለው  ነው። ክርስቶስን ከመለመን ይልቅ ማርያምን በመለመን ከልጇ ምህረት ማግኘት የቀለለ ይመስላል። አንዳንድ የተአምራት ጽሁፎች ላይ ስንመለከት ኢየሱስ ለሰዎች ፈቃደኛ ያልሆነበትን ጉዳይ ማርያም ስትነግረው ቃሉን ሲያሻሽል ይታያል።  ከክርስቶስ ርኅራኄ ይልቅ የማርያም ልመና ምህረት ያስገኛል የሚል ሃሳብን የያዘ ነው። «ዓለም ያለማርያም አማላጅነት አይድንም» የሚለው አባባል ዓለም በኢየሱስ አምላካዊ ፈቃድ የተደረገለትን ድኅነት አምዘግዝጎ የሚጥል ነው።  ኢየሱስን  ግን  በቀጥታ  ሲያናግሩት  ወይም  ወደ  እርሱ  ሲጸልዩም  ሳይሆን  “ከልጅሽ  ከወዳጅሽ”  እያሉ እርሷኑ  ሲለምኗትና ሲጠይቋት ነው  የሚታየው።  «ለምኑ ይሰጣችኋል፤ አንኳኩ ይከፈትላችኋል» የሚለው የወንጌል ቃል ተሰርዞ በማርያም አማላጅነት ላይ ብቻ ተስፋ ጣሉ የሚለው ክህደት ትምህርት መነሻው ምንድነው?
የክርስቶስ ዘላለማዊ ኅላዌነት ማርያምን ያስገኘ ሳይሆን የማርያም መኖር ኢየሱስን እንዳስገኘ ከሚታሰብ ጭፍን ክህደት የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።  የፈጠረ፤ የቀደሰ፤ ያነጻና ሥጋን የለበሰው በአምላካዊ ፈቃዱ መሆኑ መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ ነው።  ይህንን መዘንጋት ኢየሱስ  በብዙ  የማርያም  ስዕሎች  ላይ  እንደሚታየው  የማርያም  አራስ  ልጅ፥  ጨቅላ  ልጅ፥  ወጣት  ልጅ፥  ታዛዥ  ልጅ፥ ሁሌ ጭኗ ላይ ሲቀመጥ የሚታይ፤ አንድ  ጊዜም  እርሷ የጠየቀችውን  ነገር  እንቢ  ያላለ፥  የተጠየቀውን  ሁሉ  በቅልጥፍና  የሚፈጽም፥  የተሳሳተ  ነገር ጠይቃ እንኳ  ቢሆን  አሳቡን  ስለ  ልመናዋ  ሲል የሚቀይር  ለስላሳ  ልጅ  ነው።

 አንዳንዴ  ስታስፈራራው፥  ለምሳሌ፥ ኢየሱስን  ክዶ ማርያምን  ያመነን  አንድ ሰው  ይቅር እንዲለው በለመነችው ጊዜ  እንደማይሆን  ሲነግራት፥  ልብሷን  ቀዳ፥  “እኒህን  ጡቶቼን እቆርጣቸዋለሁ”  ብላ  ፍርዱን  አስቀይረዋለች፤  (ምዕ.  110ን  ተመልከቱ )። ኢየሱስም  አሳቡን  ቀይሮ  ይቅር  አለው።  በታሪኮቹ  ሁሉ፥  ከትንሣኤ  በኋላ እንኳ፥  ኢየሱስ  በሚታይባቸው  ጊዜያት  ሁሉ  እንደ  ባለ  ግርማ  አምላክ ሳይሆን እንደ ሕጻን  ሆኖ ነው የሚታየው። እዚሁ ምዕራፍ 110 ላይ እንኳ ኢየሱስ  ከዙፋኑ ተነሥቶ  በደረቷ  ላይ ተቀምጦ ተብሎ ተጽፎአል። በምዕ.  90  ልጇ  የተሰቀለባት  አንዲት  ሴት  ማርያም  ልጇን  ከተሰቀለበት ካላወረደችው  እሷም፥  “ልጅሽን  (ኢየሱስን)  ከጭንሽ  እወስደዋለሁ”  አለች።  ኢየሱስ  ሁሌ  በማርያም  ጭን  ተቀምጦ  የሚኖር  ብቻ  ሳይሆን ነጥቀው የሚወስዱትም  ዓይነት ነው። በምዕ. 43  ጴጥሮስ  ለተባለ  ቤተ  ክርስቲያንን  ላነጸ  ሰው  መልኩ  ያማረ ልጅ  ሆኖ  ተገለጠለት።  ‘ቤተ  ክርስቲያን  ያሠራ  ሰው’  ስለተባለ  ምናልባት  በብዙ  መቶ  ዓመታት  በኋላ  ነው  ቢባል  እንኳ  በዚያን  ጊዜ  ጌታ  ሕጻን  አለመሆኑ  ግልጽ  ነው።  ግን ልጅ  (የግዕዙ ሕጻን ነው የሚለው) ሆኖ ነው የተገለጠው።  ኅብስቱ  ሲቆረስ  ደግሞ  የዚህ  ሕጻን  ደም  ፈሰሰና  ታቦቱንና  ልብሱን ሁሉ  አራሰ።  በምዕ. 82  ኢየሱስ በዓለም  ሁሉ ገዢ  የነበረ ንጉሥ  ሳቤላ  የምትባል  ሴት  አስጠርቶ  (ሴቲቱ  በስም  ስትጠቀስ  ንጉሡ አልተጠቀሰም፤  ይህ  የመጽሐፉ አንድ  ደካማ ገጽታ ነው) ምክር  ሲጠይቅ ሴቲቱ  ራእይ አይታ  ለንጉሡ  አሳየችው፤ ያም ማርያም  ሕጻን  አቅፋ  ነው። ኢየሱስ  ሁሌም  ሲታይ፥  ዛሬም  ጭምር፥  በእቅፍ  ያለ  ሕጻን  ሆኖ  ነው ለማርያም  አምላኪዎች  የሚታየው። ኢየሱስ የቀረበበት  አቀራረብም  ከማንነቱ  አውርዶ  ያቃልለዋል።

 በተአምረ ማርያም  ሕጻኑ  ኢየሱስም  ሲራገም  አይጣል  ነው፤  ማርያምም  ስትበቀልና  ስትራገም  የተለመደ  መሆኑ  በቀጣዩ ነጥብ  ይታያል።  በምዕ. 101  ቁ. 108፥ ያፈለቀውን  ውኃ  ለአገሩ  ሰዎች  «መራራ  ይሁንባቸው  የጠጣውም  አይዳን  ብሎ  ባረከው»  ይላል።  ረገመው  ላለማለት  ባረከው  አሉት  እንጂ  ቃሉ ግልጽ  እርግማን  ነው።  በቁ.  125  ግመሎችን  ድንጋይ  ሁኑ  ብሎ  አደነገያቸው።  [“እስከ  ዛሬ  ድረስ  ደንጊያ  ሆኑ”  ይላል።  ኋላ  ኢትዮጵያ ቆይተው  ሲመለሱ  ነፍስ  ተዘርቶባቸው  ተመልሰው  ግመል  ሆነው  ዕቃ ተጭነው እንደሄዱ  የተረሳ  ይመስላል።] በቁ.  159  ኢየሱስ  የግብጽን  አገር  ምድሩንም  ሕዝቡንም  መርገሙ  ተጽፎአል።  ይህ  እዚህ  መርገም የሚያፈስሰው  ኋላ  ላይ  ገና  አፉንም  አልፈታም  የተባለው  ኢየሱስ  ነው። ግጭቱን  ብንተወው  እንኳ  ይህ  የተአምረ  ማርያም  ፈጣሪዎች  የፈጠሩት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  አይደለም።  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  ያስተማረውም  ያደረገውም  ጠላትን መርገም  ሳይሆን  መውደድ ነው። «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ ወደባህርይ አባቱ የጸለየው ኢየሱስ የአገሩ ውሃ መራራ ይሆንባቸው፤ የጠጣውም አይዳን፤ ድንጋይ ሁናችሁ ቅሩ» እያለ በጭራሽ  አይራገምም።

3. የተጋነነች ማርያም።

 ተአምረ ማርያም  እንደ ስሙ የማርያም  ተአምራት  መጽሐፍ ነው። ተአምራቱ  ብዙና የተለያዩ  ናቸው። ማርያም  ብቻ  ሳትሆን በስሟ  የሚደረጉ  ነገሮች  ሁሉ  ክብራቸውና  ክብደታቸው  እጅግ  ነው።
ለምሳሌ፥  በተአምር  12  ውስጥ  78  ሰዎች  የበላ  ጭራቅ  በማርያም  ስም ውኃ  ስላጠጣ  ሞቶ  ወደ  ሲዖል  እንዲሄድ  ጌታ  ፈረደበት።  ማርያም  ቀርባ  78ቱ  ነፍሳትና  ውኃው  በሚዛን  ይደረጉ  ብላ  ተደርጎ  የውኃው  ክብደት  እንዲመዝን በዘዴ ጥላዋን እንዳሳረፈችበት፤ የሞቱት ሰዎች ነፍሳት ስለቀለሉ  ጌታ  አሳቡን  ቀይሮ  ወደ  መንግሥቱ  ያስገባዋል ሲል እናገኘዋለን። ይህ እንግዲህ የፈለጋችሁትን ዓይነት ኃጢአት ብትፈጽሙና አምላክን ስለበደላችሁ ቢፈረድባችሁ እንኳን «ማርያምን ካመናችሁ ትድናላችሁ» ለማለት የተዘየደ የመዳኛ ምክንያት ነው።  የተአምሯ ማርያም ፍርዱን ለመቀየር በጥላዋ ሳይቀር እስከማታለል የመሄድ ብቃት እንዳላት ጥንካሬዋን ለማጎልበት ሲጠቀሙበት ይታያል። በአምሳለ እግዚአብሔር  የተፈጠሩ  78  ሰዎች  ነፍሳት  ከጥርኝ  ውኃ  መቅለላቸው አሳዛኝ ነው።  በምዕራፎቹ  ሁሉ  ማለት  እስከሚቻል  ማርያም  ከእግዚአብሔር  ጋር ተስተካክላ  ነው  የምትገለጠው።  ለምሳሌ፥  በ41፥13  “በእግዚአብሔር  አምነው፥ በወለደችውም  በእመቤታችን  አምነው  ከቤተ  ክርስቲያን ወጡ”  ይላል።  በማን  አምነው?  በእግዚአብሔርና  በማርያም!  እዚሁ  ምዕራፍ  ቁ.  25፥  “እምነቱን  በናቱና  በእግዚአብሔር  ላይ  ያደረገ  ሁሉ  አያፍርምና”  ይላል።  እዚህ  እንዲያውም  ማርያም  ቀድማ  እግዚአብሔር  ተከተለ!  ምዕ.  76  መነኮሳቱ  ሲጸልዩ  እግዚአብሔርንና  ማርያምን  ነው፤  “እንለምንሃለን  .  . .  እንለምናታለን”  ቁ. 15።

  አንዱ  ቄስ  ደግሞ  የማርያምን  ውዳሴ  ብቻ እንጂ  ሌላ  የማያውቅ  ነው፤  ምዕ.  76።  ይህንን  ቄስ  ሌላ  ካላወቀ እንዳይቀድስ  የከለከለውን  ኤጲስ  ቆጶስ  ወደ  አገልግሎቱ  ካልመለሰው በ30  ቀን  ትሞታለህ  አለችው።  ከግዝቱ  ፈታውና  እርሱም  ማርያምን እያደነቀ  አብረው  ኖሩ።  እዚህ  የምትታየው  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም እርሷ እስከተወደሰች ድረስ  እግዚአብሔር  ባይመሰገንም  ደንታ  እንደሌላት ነው።
በምዕ. 86 ማርያምን በፍጹም አሳቧ፥ በፍጹም ልቧ የምትወድ የተባለላት ሴት  ታሪክ  ይገኛል።  እንዲህ  ባለ  መውደድ  መወደድ  ያለበት እግዚአብሔር  ብቻ  መሆኑን  ነው  መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚያስተምረን።  እና በቃሉ  (ዘዳ. 10፥12-13፤  ማቴ. 22፥37፤  ማር. 12፥30-32፤  ሉቃ. 10፥27)  እንደተጻፈው ሰው በፍጹም ልቡ መውደድ ያለበት  እግዚአብሔርን  ነውና  ማርያም  ይህንን  ማሳወቅ  ሲኖርባት  አለማድረጓ  የመለኮትን  ፍቅር ማስቀነሷ ነው። በዚህ  ምዕራፍ  የተጠቀሰው ሰው ጠንቋይን  ምክር  የጠየቀ ሰው  ሆኖ  ምንም  ወንጌል  ሳይሰማ  ግን  የማርያምን  ስም  ሲነገረው  በነፋስ  ፊት  እንዳለ  ገለባ  ሆነ።  ሲሞትም  ማርያም  ሬሳውን  አንሥተው  በገዳም እንዲቀብሩት ተናገረችለት።  ማርያም ሰው  የሚሞትበትን  ቀን  የምታውቅ ናት።  ከላይ ለቄሱ  በ30 ቀን እንደሚሞት  ተናግራው  እንደነበር  አይተናል።  ሌላ  ምሳሌ፥  በምዕ.  81  አንድ  መነኩሴን  በአንድ  ሌሊት  ተገልጣ  ወደ  ኢየሩሳሌም  ወስዳ  አዙራ አስጎብኝታ፥  በዮርዳኖስም  አጥምቃ  የሚሞትበትን  ጊዜ  ነገረችው፤ እንደተናገረችው  ጊዜ  ዐረፈ።  ከእግዚአብሔር በቀር የሚያውቃቸው የሌሉ ነገሮችን  ካወቀች  ሁሉን  አዋቂ  ናት  ማለት  ነው?  ሁሉን  አዋቂ  ከሆነች አምላክ ናት ማለት ነው? የዚህ  መጽሐፍ  ማርያም  ስትፈልግ  ርኅሩኅ  ሳትፈልግ  በቀለኛ  ናት።

  ለምሳሌ፥  በምዕ  35  አንድ  እስላም  ዘራፊ  የዘረፈው  በገዳም  የሚኖር  ቄስ ወደ  ማርያም  ስዕል  ሄዶ  ተማጸነ፤  ጸልዮ  ሲወጣ  ዘራፊው  ወድቆ  እጁ ተሰብሮ  አጥንቱ  ገጦ  ወጥቶ  አየው።  እስላሙ  ይቅርታ  ሲጠይቀው ሽማግሌው  ማርያም  ይቅር  ብትልህም  ባትልህም  እንደወደደች  አለው፤ ይህ  ሰው  ቄስ  ሆኖ  ስለ  ይቅርታ  አያውቅም።  ቄስ  ነው  እንጂ  ክርስቲያን  አይደለም  ማለት  ነው።  ክርስቲያን  ቢሆን  ክርስቶስን  ሊመስል  ይሞክር ነበር።  እስላሙ ስላደረገው ጥፋት ይቅርታ ሲጠይቅ፤ ቄሱ «ይቅር ብትልህ ባትልህ» ካለ  እስላሙን ማን አስተምሮና አሳምኖ ሊለውጠው ነው? የሚገርመው ደግሞ ቄሱ ብቻ ሳይሆን የተአምሯ የማርያም  ስዕል  አፍ አውጥታ  «በቄሱ  ላይ  ደፍሯልና  ይቅርታ አይገባውም  አለችው»  የሚለው የበለጠ አስገራሚ ነው።  ስለዚህ  እስላሙ  በቄሱም፤ በተአምሯ  ስዕል አንደበት ወንጌልም  ሳይሰማ፥  ይቅርታም ሳያገኝ ሞተ።  ነገር ግን በተአምር 33፥39 ላይ ደግሞ ማርያም የይቅርታ ሳጥን ተብላለች።  እዚህ ላይ ደግሞ ተቃራኒ ናት። በቀለኛና  የደግነት ባህርይዋ  በወንጌል ላይ ሳይሆን በድርጊቱ  የአተራረክ ሁኔታ ላይ የሚደገፍ ነው።

 በምዕ. 39 ላይ ደግሞ በቀለኛ ማርያም ትታያለች። ሌላ  እስላም  ዘራፊ  ገዳም  ዘርፎ  ሲሄድ  ሰዎች  አግኝተው  ገደሉት፤  ከቤተ  ሰቡ  10  ሰዎች  ከዘመዶቹ  18  ገደሉና  የተዘረፈውን  አምጥተው  ለገዳሙ  ሲመልሱ  በቁ.  35፥ “ልቡናችንን  እርሱን  ለመግደል  ያነሣሳችን  ማርያም  እንደሆነች  ፈጥነን አወቅን”  አሉ።  «መጎናጸፊያህን ለሚወስድ እጀ ጠባብህን ተውለት» ለሚለው የወንጌል ቃል ግድ የሌላቸው መነኮሳቱ  ዘራፊውን  ከመግደላቸውም በላይ በቦታው ያልነበሩትን 10 ቤተሰቦቹንና 18 ዘመዶቹን በመግደላቸው ደስ ተሰኝተዋል። ይህንን የግድያ ስራ እንዲፈጽሙ ያነሳሳቻቸው ማርያም ናት ይላሉ። የተአምሯ ማርያም  ሰዎችን  አስነሥታ  ታስፈጃለች። የሚያሳዝነው  መነኮሳቱም  በዚህ  ነገር  ፍጹም  ደስታ  ተደሰቱ።  ኃጢአተኛ ሲድን  ሳይሆን  ሲሞት  የሚደሰቱ  መነኮሳት  ወንጌልን  ያውቃሉ  ይባላል?  በምዕ.  98  ከአንድ  ሽማግሌ  አስተማሪያቸው  ጋር  ፍልሰቷን  ለማክበር ሲሄዱ  አስተማሪያቸውን  ወደ  ገደል  የጣሉ  40  ተማሪዎች  በእሳት  ጦር እየወጋ  የሚገድላቸው  መልአከ  ሞት  አዘዘችና  በአንዴ  አለቁና  ሽማግሌውን  ግን  ወደ  በዓሏ  መከበሪያ  አደረሰችው።

  በምዕ.  15  አንድ  ግመል  ጫኝን  ጎድኑን  ወግታ  ስትገድለው  ትታያለች።  ደራሲዎቹ  ማርያምን  በቀለኛ  ሲያደርጓት  እርሷን  ለማግነን  ሲሉ  አስቀያሚ  ቀለም እየቀቧት  መሆናቸውን  እንኳ  አያውቁም።  ወይስ  አውቀው  ነው  አያደረጉ ያሉት? የተአምረ ማርያሟ  ማርያም  በቀለኛ ብቻ  ሳትሆን ቀናተኛም  ናት።  በምዕ.  92  የአንድ  ንጉሥን  ወጣት  ልጅ  እርሱ  ከሚወዳት  የበለጠ  እርሷ እንደምትወደውና  እንደምትቀናበት፥  ሚስት  ሳያገባ  እንዲኖርም እንደመከረችውና  በእጇ  ስዕሏን  እንደሰጠችው  ተጽፎአል።  ንግግራቸው  የሁለት  ፍቅረኞች  ይመስላል።  ልጁ  ሲሞትም  ብዙ  መላእክት  እና  ደም ግባቷ  ያማረች  ማርያም  መጥተው  በሰው  ሁሉ  እየታዩ  ይዛው  ሄደች። በእግዚአብሔር  የተደነገገ  ጋብቻ  የተናቀበትና  የተዋረደበት  እንደዚህ  ያለ መጽሐፍ  አላነበብኩም።  ያላገቡ  እንዳያገቡና  ድንግልናቸውን  ለማርያም  ስዕለት  አድርገው  እንዲሰጡ  የሚበረታቱበት  ብቻ  ሳይሆን  የተጋቡ  እንኳ  ከተቀደሰ  መኝታ  የሚከለከሉበት  ነው። መመነን፥ መመንኮስ፥ ተሰባስበው  በገዳም  መኖር  በመጽሐፍ  ቅዱስ  የተደነቀና  የተመሰገነ  ልምድ አይደለም።
ምንኩስናና  ገዳማዊነት  በክርስትና  ታሪክ  ውስጥ  ብቅ  ያለው  ቤተ ክርስቲያን  ከምድራዊ  መንግሥት  ጋር  እንደ  ውኃና  ወተት በተደባለቀችባቸው  ዘመናት  ከምድራዊ  ርኩሰትና  መንግሥታዊ  ሃይማኖት  ጋር  ላለመርከስ  የተደረገ  ሽሽት  ነው።  በዚህ  መጽሐፍ  ግን  ነባር  ልማድ  ብቻ  ሳይሆን  የተሞገሰ  አኗኗር፥ እጅጉን  የተጋነነ ሥርዓትም  ሆነ። ተአምራት  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ብዙ  ጊዜያት  የተደረጉ  ሲሆን የተአምራት  ዋነኛ  ግብ  የእግዚአብሔር  ክብር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  በተደረጉት  ተአምራት  ግን  ክብር  እግዚአብሔር  ሲሰጥ  ከቶም  አይታይም።  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ሲጀምር  የእመቤታችን  ተአምር  .  .  .  ብሎ  ይጀምርና  ሲጨርስ  በረከቷና  .  .  .  ይደርብን  ይላል።  ሲጀምር ማርያም፥  ሲጨርስ  ማርያም።  ክብር  ለማርያም  እንጂ  ለእግዚአብሔር  የሚባል  ቋንቋ የለም።
 የኢትዮጵያ  ሰዎች  ለማርያም  የተሰጡ  ዐሥራት  ሆነው  ቀርበዋል።  ዐሥራት ማለት ከዐሥር አንድ እጅ ማለት ነው። ይህ አጠያያቂ  ቃል ነው። የኢትዮጵያ  ሕዝብ እንዴት ነው  1/10ኛ የሆኑት?  9ኙ እነማን  ናቸው?  ሕዝብ  እንደሕዝብ አስራት  ተደርጎ  የተሰጠበት  ታሪክ  ኖሮ  ያውቃል?  እንኳን  ሕዝብ  በሙሉ  ይቅርና  ከአዳም  ጀምሮ  ፈቃድ ያለው  አንድ ሰውስ  ያለ  ፈቃዱ  በመንፈሱ  ላይ  ሌላ  ሊሰለጥን  እንዴት ይገደዳል?  ደግሞስ  አስራት የሰጠው  ኢየሱስ ከሆነና ማርያም  አስራት ተቀባይ ከሆነች በተአምረ  ማርያም  ላይ  ምን  እየተነገረ  ነው?  አስራት ለማን  ነው  የሚሰጠው?  አምላክ  አስራት  ሰጪ፤  ማርያም  ደግሞ  አስራት ተቀባይ  ከሆነች ማርያምን መለኮት ማድረጋቸውም  አይደል? ከመለኮትም  በላይ እንጂ!  እግዚአብሔር ነዋ!  አስራት ሰጪው።
 በምዕ. 84 ሰንበትን  የሻረ አንድ አገልጋይ  ድዳ ሆነ። ጌታው ወደ ማርያም  ጸለየና  ፈወሰችው።  የተሻረው  ሰንበት  ነው።  የምትጠየቀው  ደግሞ ማርያም  ከሆነች  እርሷ  የሰንበት  ባለቤት  ናት  ማለት  ይመስላል።   «የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነውና» ማቴ 12፤8 የሚለው ቃል በተአምረ ማርያም ላይ ተቀባይነት የለውም።
በምዕ.  110  «እግዚአብሔርን  ክዶ  ማርያምን  ግን  አልክድም»  ያለ  ሰው  በማርያም  ኢየሱስን  አስፈራሪነት  ይቅርታ  ሲያገኝ  ይታያል።  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  ማምለክ  ክቡር  ቦታ  አግኝቶአል።  ጌታ  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  አለመካድ  ወይም  ማምለክና ማንን  የማግነን  ጉዳይ ነው?  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ማዕረጓ  ብዙ  ነው።  እመቤት  ናት፤  የአርያም ንግሥት  ናት  ወዘተ፤  ችሎታዋ  ድንቅ  ነው፤  ተፈጥሮ  በቁጥጥሯ  ስር  ነው፤ ተአምራት  ታደርጋለች፤  በሰው  ልብ  የታሰበውን  ታውቃለች፤  በሞትም  ላይ  ሥልጣን  አላት  ወዘተ፤  ሥልጣኗ  የመለኮት  ነው፤  መላእክት ይገዙላታል፥  ፍጡራን  ሁሉ  ያገለግሏታል፤  የመመረቅ፥  የመርገም፥ የመግደል፥  ከሞት  የማንሣት፥  ከእግዚአብሔር  ጋር  በእኩል  የምትለመንና የምትመሰገን  ናት  ወዘተ።  እንዲያውም እግዚአብሔርን የካዱ እርሷን ካመኑ ማዳን የሚያስችል አቅም አላት። እግዚአብሔርን ማመን አያስፈልግም። ማርያምን ብቻ ማመን በቂ ነው። ተአምረ  ማርያም  እንዲህ  በመሰሉ  ማርያምን በመጽሐፍ  ቅዱስ  ካላት  ትክክለኛ  ስፍራ  ፈንቅሎ፥  ተገቢ  ቦታዋን  ነጥቆ፥ ያልሆነችውን  አድርጎ፥  ያልተሰጣትን  ሰጥቶ፥  ያልለበሰችውን  ደርቶ የሚጸለይላት፥  የምትለመን፥  የምትመለክ  አድርጎ  መለኮታዊ  ሥልጣንና ኅልውና  ሰጥቶአታል። 

 ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,