Thursday, December 8, 2011

መጽሐፈ ሰዓታት ምን ይላል?

                               መጽሐፈ ሰዓታት.............to read in PDF click here





«ሰዓሊ ለነ ሰንበተ ክርስቲያን ቅድስት፣
ለውሉደ ሰብእ መድኃኒት፣
ወእስከ ለዓለም ሰፋኒት» ትርጉም--ለሰው ልጆች መድኃኒትና እስከዘለዓለም ገዢ የሆንሽ፣ የክርስቲያን ሰንበት ሆይ ለምኝልን ማለት ነው።
ሰንበተ ክርስቲያን የተባለችው ዕለት ለሰው ልጆች መድኃኒት በመሆኗ እንዲሁም እስከዓለም ፍጻሜ የሰው ልጆች ገዢ ስለሆነች እንድታማልደን እንጠይቃት ማለቱን መጽሐፈ ሰዓታት ይጠቁመናል።
እዚህ ላይ ጥቂት ጥያቄዎችን እናንሳ።
1/ሰንበተ ክርስቲያን የምትባለው ምናልባትም ዕለተ እሁድ ናት። ሐዲስ ኪዳን ግእዙ «ወበእሁድ ሰንበት መጽአት ማርያም መግደላዊት ኀበ መቃብር»ዮሐ20፣1 «ማርያም መግደላዊት ወደመቃብር በሳምንቱ መጀመሪያ ቀን መጣች»ይላል። ምንም እንኳን የእብራይስጡም ሆነ የጽርዑ መጽሐፍ ቅዱስ እሁድ ሰንበት የሚል ቃል ባይዝም እሁድ ብለው ያስቀመጡትን የግእዝ ተርጓሚዎች ተከትለን ብንሄድ እሁድ የተባለችው ቀን---
ሀ/እንዴት ሆና ነው የሰው ሁሉ ገዢ የምትሆነው?
ለ/ እሁድ በምን አፏ ነው የምልጃ ቃልን የምታሰማው?
ሐ/ እሷስ ከማነው የምታማልደን?
ሐ/ከሳምንቱ እለታት የተለየች ናት ካልን የጌታ እለታት ያልሆኑት የትኞቹ ናቸው?
መ/ድርሳነ ሰንበት የተሰኘው መጽሐፍ «ሰንበት» ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ይለናል። ታዲያ ሰንበት የተባለው መድኃኔዓለም ያማልደናል ማለታቸው ነው?
2/ አስታራቂና አማላጅ የሆነችው እለተ ሰንበት ስለመሆኗ የተቀመጠ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ ምንድነው?
ሐዋርያው ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ወንጌልን ከሰበከላቸው በኋላ ወደቀደመው ከንቱ የሆነ አምልኰ ሲመለሱ ተመልክቶ እንዲህ ብሎ ነበር።
«ነገር ግን በዚያን ጊዜ እግዚአብሔርን ሳታውቁ በባሕርያቸው አማልክት ለማይሆኑ ባሪያዎች ሆናችሁ ተገዛችሁ» ገላ 4፣8
እንደዚሁ ሁሉ እለተ እሁድ እግዚአብሔር ከቀናት እንደአንዱ የሰራት መሆኗ ተረስቶ ልክ አማልክት ወደመሆን የተቀየረች ይመስል አስታርቂን፣አማልጂን ማለት ጳውሎስ በባህሪያቸው አማልክት ለማይሆኑ ባሪያዎች ሆናችሁ የተገዛችሁ ነበረ ያለውን ቃል እኛ ዛሬም እየፈጸምን መገኘታንን ያሳያል።


ሐዋርያው አስተምህሮውን በመቀጠል እንዲህ ሲል ይታያል።
«አሁን ግን እግዚአብሔርን ስታውቁ ይልቅስ በእግዚአብሔር ስትታወቁ እንደ ገና ወደ ደካማ ወደሚናቅም ወደ መጀመሪያ ትምህርት እንዴት ትመለሳላችሁ? እንደ ገና ባሪያዎች ሆናችሁ ዳግመኛ ለዚያ ልትገዙ ትወዳላችሁን?»ገላ 4፣9
የሚገርመው የገላትያ እብራውያን ሰዎች ወደቀደመው ሥርዓታቸው መመለሳቸውን አዝኖ የተናገረው ልክ ዛሬ «እለተ እሁድ አማልጂን» እያሉ ሌሊቱን በዝማሬ እንደሚጮሁት እንደእኛዎቹ ሰዎች የተቸገረ መሆኑንና የወንጌል ድካሙ ሁሉ ከንቱ እንደሆነበት ማዘኑን እናያለን።
« ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ።
ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለሁ ብዬ እፈራችኋለሁ» ገላ 10፣11
የቀደመችውም ሰንበት የአዲስ ኪዳን ጥላ ናት እንጂ በራሷ መድኃኒት አይደለችም። ኋለኛ የምትባለው ቀን ካለችም መድኃኒት ክርስቶስ ስላደረገው የማዳን ሥራ ልንመሰክርባት፣ልናስተምርባት፣ የእምነት መሠረቶቻችንን ልናጸናባት የተፈጠረች ቀን እንጂ ከቀኖች በተለየ ራሷ መድኃኒት የሆነች፣የምታማልድና ገዢያችን አይደለችም።
ወደማክበር ወይም ወደማስታረቅ ትልቅ ደረጃ አድርሶ እንደልዩ ነገር ማሰብ በፍጹም ስህተት ነው።
«እንግዲህ በመብል ወይም በመጠጥ ወይም ስለ በዓል ወይም ስለ ወር መባቻ ወይም ስለ ሰንበት ማንም አይፍረድባችሁ።እነዚህ ሊመጡ ያሉት ነገሮች ጥላ ናቸውና፥ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው» ተሰሎ2፣16-17
ስለሆነም ገዢና መድኃኒት እውነተኛው የእርቅ መንገድ ክርስቶስ እንጂ እለተ እሁድ አይደለችም፣ ያማ ቢሆን ኖሮ ክርስቶስ ሥጋ ሳይለብስ የነበረችው እለተ እሁድ ራሷ አስታራቂና መድኃኒት መሆን በቻለች ነበር። ቀናት ሁሉ ለሰው ልጆች የሥራና አምልኰ ክፍልፋይ ሆነው የተሰጡን ናቸው እንጂ በራሳቸው ህልውና ኖሯቸው የሚናገሩ፣የሚሰሙ፣ ሰውን የሚገዙ፣ ወይም አንዱን አድነው ሌላውን የሚኰንኑ ግዘፍ የሚነሱ አካላት አይደሉም። አንዲት እለት የተለየ ነገር ስለተደረገባት የሆነውንና የተደረገውን ዋናውን ጉዳይ ትተን ቢደርግና ባይደረግ ምንም ድርሻ የሌላትን እለት ማክበርና እንደሰው ማናገር ክርስቲያናዊ ትምህርት አይደለም። ስለሆነም አቶ መጽሐፈ ሰዓታት «ለሰው ልጆች መድኃኒትና እስከዘለዓለም ገዢ የሆንሽ፣ የክርስቲያን ሰንበት ሆይ ለምኝልን» ያልከው ስህተት ብቻ ሳይሆን ክህደት ጭምር መሆኑን እንነግርሃለን።
በሌላ ቦታ የመጽሐፈ ሰዓታት አንደበት ምን እንደሚል እንቃኝ።
«ቁስቋም ተዐቢ እምኪሩቤል፣ ቁስቋም ትከብር እምሱራፌል፣
እስመ ኀብአቶ በወርኀ ቀትል ለወልደ ማርያም ድንግል»
ትርጉም- ቁስቋም ከኪሩቤል ትበልጣለች፣ ከሱራፌልም ትከብራለች፣ ሊገድሉት ሲሹ የድንግል ማርያምን ልጅ ሸሽጋዋለችና» ማለት ነው።
ቁስቋም በግብጽ ሀገር የምትገኝ ምድረ በዳ ናት ተብሎ ይታወቃል። አዲስ ኪዳን ስለቦታ የተለየ አምልኰ እንድንሰጥ ያላስተማረን ብቻ ሳይሆን ይህች ቁስቋም የምትባለዋን የመጽሐፈ ሰዓታት መጽሐፍ ምድረ በዳ እስከነአካቴው አያውቃትም። ከኪሩቤል የምትበልጥና ከሱራፌል በላይ የምትከብር ምድረ በዳ መኖሯን ለእኛ ለክርስቲያኖች ሳያስተምረን ዝም ብሎ ያልፈዋል ማለት ሞኝነት ነው። አዲስ ኪዳን በመንፈስ ቅዱስ የተጻፈ ስለሆነ በሌላ መንፈስ የሚጻፈውን ነገር ሁሉ በእርግጥም ለእኛ አይነግረንም። የሆነስ ሆነና ቁስቋም በምን ሚዛን ነው ሰማያውያን ከሆኑት ፍጥረታት ከኪሩቤልና ከሱራፌል የምትከብረው? የምትበልጠውስ?
መጽሐፍ ቅዱሳችን ስለኪሩቤልና ስለሱራፌል ሰማያውያን ፍጥረት መሆን በሚገባ ይነግረናል። እንዴት አድርገን ነው መጽሐፍ ቅዱስ ከነገረን ሰማያውያን ፍጥረታት በላይ መጽሐፍ ቅዱስ የማያውቃትን ቁስቋም የተባለች የግብጽ ምድረ በዳ ትበልጣቸዋለች ማለት የምንችለው?
«አቤቱ፥ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ የእስራኤል አምላክ የሠራዊት ጌታ ሆይ፥ አንተ ብቻህን የምድር መንግሥታት ሁሉ አምላክ ነህ ሰማይንና ምድርን ፈጥረሃል»ኢሳ 37፣16
በኪሩቤል ላይ ለሚቀመጠው የእስራኤል አምላክ የተሻለች ቦታ ግብጽ ሀገር መኖሯን የሚናገረው መጽሐፈ ሰዓታት አብዶ ይሆን?
ምናልባትም ማርያም ልጇን ይዛ ወደግብጽ ቢሸሹ ቁስቋም በምትባለው ምድረ በዳ አልፈው እንደሆነ ብንገምት እንዴት ሆኖ ነው የአንድ ወቅት ማለፊያ ምድረ በዳ ለዘለዓለሙ ትበልጣለች እየተባለ ምስጋና የሚቀርብላት? እግዚአብሔር ወልድ ግን ጥንት በሌለው ዘለዓለማዊነት ውስጥ በኪሩቤል ላይ ይቀመጣል።                                                                                           
«እኔም አየሁ፥ እነሆም፥ በኪሩቤል ራስ ላይ ባለው ጠፈር በላያቸው እንደ ሰንፔር ድንጋይ ያለ እንደ ዙፋን የሚመስል መልክ ተገለጠ።» ሕዝ 10፣1
«የእግዚአብሔርም ክብር ከቤቱ መድረክ ላይ ወጥቶ በኪሩቤል ላይ ቆመ» ሕዝ 10፣18
«ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ዘረጉ፥ መንኰራኵሮችም በአጠገባቸው ነበሩ የእስራኤልም አምላክ ክብር በላያቸው ላይ ነበረ» ሕዝ 11፣22
ይህንን ሁሉ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ክደን፣ የለም ቁስቋም ትበልጣለች እንል ዘንድ ተገቢ ነው?
ሱራፌልም የሰማያዊ ፍጥረታት አካል በመሆኑ ያመሰግናል። ነቢዩ ኢሳይያስ ያየውን እንዲህ ጽፎታል። «ሱራፌልም ከእርሱ በላይ ቆመው ነበር፥ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው በሁለት ክንፍ ፊቱን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ እግሮቹን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ ይበር ነበር።አንዱም ለአንዱ። ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች እያለ ይጮኽ ነበር» ኢሳ 6፣3
የማትለማ፣ የማትሰማዋ የግብጽ ምድረ በዳ ከኪሩቤል በተሻለ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እያለች ያለእረፍት በሰማይ እያመሰገነች ይሆን? ሰማያውያኑ ፍጥረታት የተፈጠሩት ለምስጋናና ለተልዕኰ ነው። ቁስቋምስ ለምን ይሆን? ሰማያውያኑ ፍጥረት ከተፈጠሩበት ጊዜ አንስቶ ያለእረፍት ያመሰግናሉ፣ ተልእኰአቸውን ይፈጽማሉ፣ ቁስቋምስ? ሰማያውያን ፍጥረታት ዘላለማውያን ናቸው፣ ቁስቋምስ? ሰማይና ምድር እንደሚያልፉ ባለቤቱ ነግሮናል፣ ቁስቋምስ? ምናልባት ቁስቋም እኔ በመጽሐፈ ሰዓታት የተመሰከረልኝ ስለሆንኩ ሰማይና ምድር ሲያልፉ እኔ ማለፍ የለብኝ ትል ይሆን? ምናልባት የመጽሐፈ ሰዓታት ዝማሬ አዝማሪዎች ቁስቋም ሰማያዊ ስለሆነችና ከኪሩቤል ስለምትበልጥ እሷን አይመለከታትም ብለው ይነግሩን ይሆናል፣ እኛ ግን ቁስቋም የመሬት አካል እንጂ የተለየች ሰማያዊ አካል ያልሆነች፣ ከኪሩቤልና ከሱራፌል የማትበልጥ ፣ሰማይና ምድር ሲያልፉ የምታልፍ መሆኗን ብቻ እናውቃለን።                                                                          
ከዚሁ ጋር አያይዘን ጥቂት ጥያቄዎችን ብናነሳ የቁስቋምን ነገር የበለጠ ያሳየናል።
ናዝሬትከተማ መድኅን ዓለም ክርስቶስ ያደገበት፣ እውር ያበራበት፣ሙት ያስነሳበት ሀገሩ ነው። ቤተልሔም በወርኀ ቁር የተወለደባት፣ በእሱ የተነሳ አእላፋት ህጻናት የተፈጁባት መንደር ናት። የኢየሩሳሌም ቅድስቲቱ ከተማ «ታሪክ ዘብሉይ ኪዳን ወሐዲስ» የተፈጸመባት መሆኗን እናውቃለን። ሌላው ሌላውን ትተን ከቦታ ምርጫና ከመንፈሳዊ ታሪክ መሰረትነት አንጻር እነዚህን ብቻ ብንመለከት ቁስቋም እዚህ ግቢ የሚባል ታሪክ የሌላት ዛሬ የእስላም ከተማ ናት። እነዚህ የጠቀስናቸው ክርስቶስ ሁሉን ያደረገባቸውና ሁሉን የተናገረባቸው ቅዱሳን መካናት በየትኛውም መመዘኛ ከኪሩቤልና ከሱራፌል አይበልጡም። ኪሩቤልና ሱራፌል ለዘለዓለሙ በምስጋናና በተልእኰ ሲኖሩ በአንድ ወቅት መንፈሳዊ ስራ የተፈጸመባቸው ከተሞችና መንደሮች ሁሉ ሰማይና ምድር ሲያልፉ አብረው ያልፋሉ። አዲስ ሰማይና ምድርም ይወርዳሉ። ራእይ 21፣1 «አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም»
ሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም እንደሙሽራ ስለመምጣቷ የማያውቀው መጽሐፈ ሰዓታት ቁስቋምን ዘላለማዊ አድርጎ ከኪሩቤል ትበልጣለች ይለናል። ቁስቋም ክርስቶስን ሸሽጋ ስለሆነ ወደ ሰማያዊ ክብር ካወጣናት ከቤተፋጌ ወደ ኢየሩሳሌም ተቀምጦባት የመጣባት የአህያ ውርጫ ክብርስ ምን ሊባል ይሆን? ዙፋኑን ከኪሩቤል ላይ የዘረጋ አምላክ ስለተቀመጠባት ውርጫዋን ከኪሩቤል ትበልጣለች ሊባል ይሆን? (ሎቱ ስብሐት)
እርሱ ውርጫዋን የተቀመጠው ወደሰማያዊ ፍጥረትነት ሊቀይራት ሳይሆን ራሱን አዋርዶና ሰማያዊ ክብሩን ሁሉ ትቶ ፣ ያጣነውንና የተነጠቅነውን ሰማያዊ ልጅነት ለእኛ ሊሰጠን የገለጸበት ፍጹም ሚዛን የለሽ ፍቅሩን መስጠቱን ልንረዳለት ይገባል።
አንገት ማስገቢያ ቤት ያልነበረው፣ ሁሉን ይዞ ሳለ ሁሉን ያጣው፤ የተንከራተተው፤ የተከሰሰው፣የተገረፈው፤ ጺሙን የተነጨው፣ የተተፋበትና የተጸፋው፣ መራራውን ከርቤና ሞትን የተጎነጨው ምድራዊውን መሬት ወደ ሰማያዊ ፍጥረትነት ለመቀየር ሳይሆን እኛን ምድረ ፋይድ የተወረወርነውን ልጆቹን ወደሰማያዊ ክብራችን ሊመልሰንና አባታዊ ፍቅሩን ሊያሳየን ነው።
ስለሆነም መጽሐፈ ሰዓታት ቁስቋምን ከቅድስቲቱ ከተማ ከኢየሩሳሌም ብቻ ሳይሆን ከኪሩቤልም ትበልጣለች ያልከው ከመንፈስ ቅዱስ በተገኘ ድምጽ ሳይሆን እውነት በምትመስል ክህደትን በሚያወጣው በጥንተ ጠላታችን የተወረወረ ቃልህን ትተህ ንስሐ ግባ፣ የምትጮሁለትም ንስሐ ግቡ። ሰይጣን «መላእክቱን ስለአንተ ያዝልሃል...» የሚለውን የልበ አምላክ ዳዊትን ጥቅስ ማንሳቱ እውነተኛ አማኝ መሆኑን አያመለክትም።
እኛም «እግዚአብሔር አምላክን አትፈታተኑት» የተባለውን ለቁስቋም አቀንቃኞች እንነግራቸዋለን።                                             ( http://dejebirhan.blogspot.com)
ይቀጥላል.........