Saturday, March 2, 2024

የኢየሱስ ክርስቶስ አማላጅነት!

የብዙ ሃይማኖቶች፣ መምህራን «ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ነው» በማለት ያምናሉ። ያስተምራሉ። በተቃራኒው ይህን የሚክዱም አሉ። ነገር ግን በመጽሐፍ ቅዱስ የተረጋገጠው እውነት " ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ የመሆኑ እውነት ነው። ፍጹም ሰው የመሆኑ ምስጢርን እንዲህ ይላል። “የሰው ልጅ የጠፋውን ለማዳን መጥቶአልና።”ማቴ 18፥11 ፍጹም አምላክ የመሆኑ ምስጢርን ደግሞ ራሱ እንዲህ ሲል ይነግረናል። “እኔና አብ አንድ ነን።” ዮሐንስ 10፥30 ሲል እናገኘዋለን። ታዲያ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር ወልድ፣ በመለኮታዊ ሥልጣኑ ማዳን ሲችል ሥጋ በመልበስ በሞቱ አዳምንና ልጆቹን ማዳን ለምን አስፈለገው? ለሚለው ጥያቄ የጠራ መልስ ማግኘት ስንችል ብቻ ነው የምልጃው ትርጉም ሊገባን የሚችለው። ወልድ ሠው በመሆን ራሱን ባዶ ማድረጉ ለምን እንደሆነ ካልገባህ ስለምልጃ የሚነገረው ነገር ሊገባህ አይችልም።። «እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ» ፊልጵ ፪፤፮-፯ እግዚአብሔር "ኰናኔ በርትዕ፣ ፈታኄ በጽድቅ" ነውና ኃጢአት የሚያስከፍለውን ዋጋ ሳያስከፍል አይተውምና ለአዳምና ለልጆቹ በደል የኃጢአት ዋጋ መከፈል ስለነበረበት ነው፣ ከሰማይ ለዚህ ሞት የተገባ ሆኖ ራሱን ባዶ ያደረገው። የፊልጵስዩስ መልእክት የሚነግረን ይሄንን ነው። የመጀመሪያው ሰው ከገነት ከወጣ በኋላ ትውልዱ በሙሉ በሞት ጥላ ሥር ወድቋል። ስቃይ፣መከራ፣ ድካም፣ በላቡ ወዝ ፍሬን የሚበላ፣ ሕመምና ሞት የሚገዛው ፍጥረት ሆኗል። ዘፍጥረት 3፣ 17—18 "አዳምንም አለው፦ የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና፥ ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝሁህ ዛፍም በልተሃልና ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤ እሾህንና አሜከላን ታበቅልብሃለች፤ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ" ስለዚህም ሰውም፣ ምድርም የተረገሙ ፍጥረቶች መሆናቸውን እናነባለን። በዚህም የተነሳ የእግዚአብሔር ቃል በአዳም ጥፋት ስለተጣሰ በእግዚአብሔርና በሰው ልጆች መካከል የጥል ግድግዳ ቆሟል። ሰው ከአምላኩ ዘላለማዊ ኑባሬ ውጪ በሞት የሚሸነፍ ፍጥረት ሆኗል ማለት ነው። የሰውን ልጅ በመቀደስ፣ በማንፃትና ከዘላለም ሞት በማዳን ማን የእግዚአብሔር ልጅ ያድርገው? ከወደቀው የሰው ልጆች መካከል ይህንን ማድረግ የሚችል አንድም ፍጥረት አልነበረም። ሊኖርም አይችልም። ገነት በሰው ልጅ ላይ ከተዘጋበትና በኪሩብ የሚጠበቅ ከነበረ ከፍጡር ገነትን መልሶ መክፈት የሚችል ምን ዓይነት መስዋእት ስለሌለ እግዚአብሔር ራሱ ከሰማይ ወርዶ ሰው ለመሆን የተገደደው ለዚህ ነው። የእግዚአብሔር ወልድ ሰው የመሆን ምስጢር በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ በደሙ ለማፍረስ ነው። “ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው።” ኤፌሶን 2፥16 ስለኢየሱስ ሰው የመሆን ምስጢርና የምልጃ ሥራው ከመግለጻችን በፊት ስለምልጃና አማላጅነት ጥቂት ሀተታ እናቅርብ። 1/ መማለድና አማላጅነት (Interceds & intercession) ተንበለ በዐሥሩ መራህያን ሲረባ ይተነብል፣ ይተንብል/ዘንድ/፣ ይተንብል/ትእዛዝ/ ይሆናል። አማለደ፣ ለመነ በግእዙ ግስ «ተንበለ» ማለት ሲሆን ትርጉሙም መለመን፣ መጸለይ፣ ማማለድ፣ አማላጅ መሆን፣ ማላጅ፣ አስታራቂ፣ እርቅ ፍቅር ይቅርታ መለመን ማለት ነው። አማላጅ ሲል አንዱ ለሌላው ይቅርታን፣እርቅን ሰላምን ለማስገኘት በአድራጊውና በተቀባዩ መካከል የሚያገናኝ መስመር ማለት ነው። ይህም ተቀባዩ ከአድራጊው ጋር የሚኖረውን ግንኙነት የተስተካከለ እንዲሆን በመካከለኛነት አገኛኝ ድልድል በመሆን ማገልገል የማማለድ አገልግሎት ይሰኛል። ፍጹም ሰው ሆነ ስንልም መለኮታዊ ማንነቱን ተወ ማለት ሳይሆን አምላካዊ ሥልጣኑን ሸሸገ ማለታችን ነው። ከኃጢአት ብቻ በቀር እንደእኛ የተፈተነውም ለዚህ ነው። መለኮታዊ ስልጣኑን የመሸሸጉ ምክንያትም ፍጹም ሰው በመሆን ከአብ ጋር ያለውን መለኮታዊ ዕሪናውን እንደተወ ሳይቆጥር እንደልጅ ለመታዘዝ ነው። ብዙዎች ኦርቶዶክሳውያን የሆኑ ሰዎች ልጅ ሆኖ በመታዘዙን ልክ፤ ምልጃ አቅርቧል ሲባሉ ከአብ ያሳነስን ይመስላቸዋል። አማለደ፤ አስታረቀ፤ ታዘዘ የሚሉ ቃላትን መስማማት የወልድን ባሕርይ ህጹጽ አድርጎ የሚያወርድ ነው በማለት ምልጃውን ለመቀበል የማይፈልጉ አስተሳሰቦች ሞልተዋል። አምላካዊ ባህርይውን ለመጠበቅ ሲባል ፍጹም ሰው የሆነበትን ምስጢር በመሸርሸር ከማማለድ፤ ማስታረቅና መካከለኛ የመሆን ማንነቱ ለመሸሽ መሞከር ምስጢረ ሥጋዌን በሽፍንፍኑ እንደመሻር ይቆጠራል። ማማለድ፤ ማስታረቅና መካከለኛ መሆኑን አምኖ መቀበል ከሌለ ፍጹም ሰው እንደሆነ ማመን በፍጹም ሊመጣ አይችልም። በመለኮታዊ ሥልጣኑ ማዳን እየቻለ ሥጋ መልበስ ያስፈለገው በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የሚችል ከኃጢአት ሁሉ ንጹህ የሆነ የእግዚአብሔር ልጅ በመካከል እንዲገባ በማስፈለጉ እንደሆነ አምኖ መቀበል የግድ ነው። ያለበለዚያ ነገረ ድኅነት የሚባል አስተምህሮ አይመጣም። 2/ የዕብራውያኑን መልእክት መጽሐፍ የጽርዑ ቋንቋ ምን ይለዋል? “ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።”ዕብ 7፥25 «ὅθεν καὶ σῴζειν εἰς τὸ παντελὲς δύναται τοὺς προσερχομένους δι’ αὐτοῦ τῷ Θεῷ, πάντοτε ζῶν εἰς τὸ ἐντυγχάνειν ὑπὲρ αὐτῶν» ዕብ ፯፤፳፭ በቀይ የተሰመረበት ቃል /ኢንታይኻኔየን/ ማለት «ሊያማልድ» ማለት ነው። ይህም « ἐντυγχάνειν የሚለው ግሳዊ መስተአምር - ἐντυγχάνω ἐντυγχανω በሚለው የአገባቡ ልክ (God on behalf of), plead, appeal) መካከለኛ የሆነ፤ አስታራቂ፣ አማላጅ ማለት ነው። 3/ ዕብራይስጥ «אשר על כן יוכל גם להושיע בכל וכל את הנגשים על ידו לאלהים כי חי הוא תמיד להפגיע בעדם׃»ዕብ ፯፤፳፭ / ሌሐፍጊያ/ ማለት ሲሆን ትርጉሙም ሁለት የተለያዩ ነገሮችን በመሃከል ሆኖ የሚያገናኝ፤ የሚለምን፣ መካከለኛ የሆነ አስታራቂ ማለት ነው። ይህም በ፩ኛ ጢሞ ፪፤፭ ያለውን የመካከለኛነት ተግባር በትክክል ገላጭ ሆኖ ይገኛል። 4/ ኢየሱስ በሰውነቱ አማላጅ፣ በአምላክነቱ ፈራጅ ነው! ኢየሱስ ከትንሣኤው በኋላ በ40ኛው ቀን በሥጋው አርጓል የሚለውን አምነው ሲያበቁ ዛሬም በግርማው ዙፋን በሥጋው በአብ ቀኝ እንደተቀመጠ የማያምኑ ሃይማኖተኞች አሉ። እነዚህ ሰዎች ካረገ በኋላ ሥጋውን አረቀቀው፣ መጠጠው፣ ለወጠው ብለው በአደባባይ የማይናገሩ፣ ነገር ግን በዝምታ ውስጥ የሚክዱ አውጣኪያውያን ናቸው። ኢየሱስ በክብሩ የተቀመጠው ዛሬም በሥጋው ነው። ያለዚያማ በሥጋ አልተዛመደንም ወይም በትንሣኤ ዘጉባዔ እኛ ሰዎችም በሥጋ አንነሳም ብሎ እንደመካድ ነው። ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ፣ “ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።” ዕብራውያን 9፥24 በጥቅሉ ቅዱስ ወንጌል ላይ የተጻፉት መሠረታዊ ትርጉሞች ሐዋርያት በጉስዐተ መንፈስ ቅዱስ የጻፏቸው ቃላት በስርዋጽና በኑፋቄ ቃላት ተተክተው በዕሥራ ምዕቱ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ከመታተማቸው በስተቀር የቀደሙት ጽሁፋት በትክክል የእግዚአብሔር ወልድን ፍጹም ሰውነትና አምላክነት ያለመጠፋፋት፤ ያለመቀላቀልና ያለመለያየት በፍጹም ተዋሕዶ ሰው ሆኖ መገለጹን የሚያስተምሩ ናቸው። ስለዚህም በርዕሳችን እንዳመለከትነው ክርስቶስ በአምላክነቱ ቃል ብቻ ማዳን ሲቻለው ሰው ሆኖ መገለጽ ያስፈለገው በሰውና በአምላክ ያለውን ልዩነት በማፍረስ መካከለኛ ሆኖ ለማገናኘት ነው እንላለን። ከሰው ልጆች መካከል፤ መካከለኛ መሆን የቻለና የሚቻለው ሌላ ማንም የለም። ይህንንም ካህኑ በጸሎተ ፈትቶ ላይ « እንዘ ባዕል ውእቱ በኩሉ አንደየ ርእሶ » በማለት የሚያውጀው አምላክ ሰው የሆነበትን ምሥጢር ነው። በዚህም የተነሳ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ወልድ በፈቃዱ የአብ የባህርይ ልጅ ሆኖ ሥጋችንን ለመልበስ በግብረ መንፈስ ቅዱስ በመካከላችን አደረ። እንደሰውነቱ ኃጢአት አያውቀውም። እንደካህንነቱ ዘላለማዊ ካህን ነው። እንደአዳኝነቱ ሞት አያሸንፈውም። እንደልጅነቱ የአባቱን ፈቃድ የሚፈጽም ነው። እንደስርየት መስዋዕትነቱ አንዴ፤ ግን ለሁል ጊዜ የሚሆን ነው። ይህም የነበረውን ጥል አፍርሶ በአብ የተወደደ መካከለኛና ለሕዝቡ ኃጢአት ዘላለማዊ ሥርየትን ማስገኘት የሚችል ሊቀ ካህን ሆኗል። ማማለድ ወይም ማስታረቅ ማለት ይህ ነው። መካከለኛ ማለትም ይህ ነው። በኃጢአት ምክንያት በተሰደደው ሕዝብና በእግዚአብሔር መካከል የነበረውን ጥል አፍርሶ እንደሰውነቱ ፍጹም ልጅ ሆኖ ያስታረቀ/ ያማለደ/ የሚያደርጉትን አያውቁምና አባት ሆይ ይቅር በላቸው ያለ፤ ስለጩኸቱም ድምጹ የተሰማለት ልጅ ማለት ይህ ነው። ይህንን ወልድ ሥጋ የመልበሱን አስፈላጊነትና የነገረ ድኅነት ምስጢር በመተው ወይም ለመቀበል ሳይፈልጉ መዳን የሚባል ነገር ፈጽሞ ሊታሰብ አይቻልም። አምላክነቱን እንደመተው ሳይቆጥር ፍጹም ሰው ሆነ ማለት ለማስታረቅ/ ለማማለድ/ ካልሆነ ሌላ ለምን? በመለኮታዊ ሥልጣኑማ ሰው መሆን ሳያስፈልገው በለይኩን ቃሉ ማዳን ይቻለው አልነበረምን? ሐዋርያው ጳውሎስም በግልጽ የወንጌል ቃል እንዲህ አለን። «እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው። ስለ እርሱም የምንናገረው ብዙ ነገር አለን፥ ጆሮቻችሁም ስለ ፈዘዙ በቃል ልንተረጕመው ጭንቅ ነው» ዕብ ፭፣፯-፲፩ ምልጃው እስከመስቀሉ ድረስ ብቻ ነው የሚሉ ከሀዲዎች አሉ። እንዴ ከሀዲዎች? ከመስቀሉ በኋላ የተፈጠርን ትውልዶች በሙሉ የኢየሱስ ክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ ያመንን እኛ ከአብ ጋር የታረቅነው በምንድነው? አንዴ የተደረገ ነገር ግን በአብ ዘንድ የተወደደ ያ የይቅርታና የምሕረት መስዋእት ዛሬም ይማልዳል። እንደኦሪቱ መስዋእት ዕለት፣ ዕለት የማይቀርብ፣ ነገር ግን አንዴ ለሁልጊዜ የተፈፀመ፣ ዕለት፣ ዕለት ለሚመጡ ነፍሳት የኃጢአትን ስርየት የሚሰጥ መስዋዕት ነው። «ብዙ ልዩ ልዩ የእግዚአብሔር ጥበብ አሁን በቤተ ክርስቲያን በኩል በሰማያዊ ስፍራ ውስጥ ላሉት አለቆችና ሥልጣናት ትታወቅ ዘንድ፤ይህም በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የፈጸመው የዘላለም አሳብ ነበረ፥ በእርሱም ዘንድ ባለ እምነታችን በኩል በመታመን ድፍረትና መግባት በእርሱ አለን» ኤፌ ፫፤፲-፲፪ ልጆቹ መሆን የቻልነው በሥጋ በተዛመደን በክርስቶስ በኩል ነው። ልጆች ደግሞ እንደመሆናችን የአባታችን የሆነውን ሁሉ እንወርሳለን። ሮሜ ፰-፲፯ «እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል። እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና» ዕብ ፯፤፳፪-፳፯ ራሱ የስርየት መስዋዕት፣ ራሱ ስርየት አቅራቢ ሊቀካህን፣ ራሱ ከአብ አስታራቂ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። አንዳንዶች ዛሬም ሊቀ ካህን ሆኖ ያማልዳል አትበሉ ይሉናል። እንደምድራዊው ሊቀ ካህን የአገልግሎት ጊዜው በዐረፍተ ዘመን ያበቃለትና የጨረሰ ሳይሆን ዘላለማዊው ሊቀ ካህን ሆኖ የዘወትር መስዋእት የሚያቀርብ ሳይሆን አንዴ ቀራንዮ ላይ ባቀረበው የዘላለም ምልጃ ዛሬም ወደአብ የሚመጡትን ሁሉ ዛሬም ያድናቸዋል ማለት ይህ ነው። እዚህ ላይ እስኪ አንድ ጥያቄ እናንሳ! አንድ ሃይማኖት የለሽ ወይም የአንድ ሃይማኖታዊ ድርጅት ተከታይ የሆነ ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ ስለአዳም ኃጢአት ከሰማይ ወርዶ እንደሞተና ለሚያምኑበት ሁሉ የኃጢአት ስርየት እንደሰጠው፣ ወደሰማይም እንዳረገና በአባቱ ቀኝ ስለእሱ ዛሬም እንደሚታይ፣ ለፍርድና ኩነኔ ዳግም እንደሚመጣ፣ ተምሮ ለሚያምን ሰው ድነት /ድኅነት/ የሚሆንለት እንዴት ነው? መልስ፣ ግለሰቡ ሲያምን ለአዳም ኃጢአት ስርየት በተደረገው ቀራንዮ ላይ አንዴ በፈሰሰውና ዛሬም ሕያው በሆነ ደሙ ከበደሉ በእምነት ይነጻል። ያ ደም ለዘላለም ሕያው ስለሆነ ከአብ ጋር ያስታርቀዋል። አባ፣ አባት የሚልበትን የልጅነት መንፈስ ይቀበላል። ሮሜ 8:15 የቀራንዮ ምልጃው ዛሬም ሕያው ነው። አንድ አማኝ የእግዚአብሔር ልጅ ይሆን ዘንድ ዛሬ ቢያምን በአብ ዘንድ ያለው አስታራቂው መስዋእት ያ የደም ስርየት ብቻ ነው። ይህንን የሚተካ ሌላ ምልጃ የለም። አንዳንዶች ሐዋርያው ጳውሎስ "“እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማልድ ስለ ክርስቶስ መልክተኞች ነን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን።” 2ኛ ቆሮ 5፥20 ያለውን ቃል አንጠልጥለው በአብ ዘንድ ያለን አስታራቂና አማላጅ ቅዱሳን ሰዎችና መላእክት ናቸው ሲሉ ይደመጣሉ። ይህ ትልቅ ስህተት ነው። የመጀመሪያ መታወቅ ያለበት ነገር አዲስ አማኝ ወደአብ የሚቀርበው በቀራንዮው መስዋእት በኩል ብቻ ነው። ሌላ ተኪ ፍጡር የለም። ሲቀጥል ቅዱሳን ሰዎችና መላእክት በምድር ሳሉ ይማልዱ የነበረው ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ፣ ከኃጢአት ውጡ፣ ንስሐ ግቡ እያሉ እንጂ የኢየሱስን ቦታ ተክተው ከአብ ጋር ማስታረቅ አይችሉም። ዛሬም መምህራኑ፣ ወንጌላውያኑ፣ ሰባኪያኑ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ እያሉ በስብከታቸውና በዝማሬያቸው አዎ ይማልዳሉ /ይለምናሉ/፣ ሰዎች ከኃጢአት፣ ከዐመጻና ከበደል ተመለሱ እያሉ ይለምናሉ፣ ይማልዳሉ። ከዚያ ባለፈ ለኃጢአተኛው ንጹሕ የኃጢአት ስርየት መስዋእት ሆነው በእግዚአብሔር ፊት ይታያሉ ማለት ከሆነ አደገኛ ክህደት ነው። ከአንዱ ከኢየሱስ በስቀተር ንጹሕና የተወደደ የኃጢአተኛ የምልጃ መስዋእት በእግዚአብሔር አብ ፊት ሌላ የለም። “እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።” ዕብ 7፥22 እኛ መክፈል ላቃታን የኃጢአት እዳችን አስተማማኝ የአዲስ ኪዳን ዋስ የሆነን ኢየሱስ ብቻ ነው። ሌላ ዋስ፣ ሌላ ጠበቃ፣ ሌላ መታያ፣ ሌላ አስታራቂ፣ ሌላ አማላጅ ከኢየሱስ በቀር በአብ ፊት የተወደደ ምልጃ ከፍጡር አንድም የለም። ክርስቶስ ለፍርድ ዳግም እስኪመጣ ድረስ ለኃጢአተኛ የሚቀርበው የሥርየት መስዋእት ሕያው የሆነውና በቀራንዮ አንዴ ለምልጃ የፈሰሰው የኢየሱስ ደም ነው። ወደአብ የምንቀርብበት ሌላ መንገድ የለም። “ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።” — ዮሐንስ 14፥6 በገብርኤል ይሁን በሩፋኤል፣ በሳዊሮስ ይሁን በገላውዴዎስ፣ በጅሩ አርሴማ ይሁን በክርስቶስ ሳምራ፣ በኪሮስ ይሁን በተክልዬ፣ በአድዋ ይሁን በዲላ፣ በዝቋላ ይሁን በጩቃላ፣ በአባ እንጦንስ ይሁን በእማሆይ ትብለፅ፣ በየትኛውም ሥጋ ለባሽ ፍጥረት በኩል ወደአብ መግባት ፈፅሞ አይቻልም! ምክንያቱ የጥል ግድግዳ የፈረሰውና የእዳ መስዋእት የተከፈለው በእነሱ ሞት በኩል አይደለምና። የኢየሱስ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ዛሬም ለሚያምኑበቱ ሕያው ነው። ደሙ የኃጢአት ስርየት፣ በሊቀካህንነቱ ዛሬም አስታራቂ ነው። በአምላክነቱ ለፍርድ ዳግም ይመጣል! “በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።” — ዮሐንስ 5፥28-29

Wednesday, January 17, 2024

“መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።” ሐዋ 4፥12

አዳም ከአምላኩ ትዕዛዝ በወጣ ጊዜ፣ ከሔዋን ጋር ከገነት ተባሮ አሜከላና እሾህ ወደምታበቅለው ምድር መጣሉን መጽሐፍ ቅዱሳችን ይነግረናል። ዘፍ 3:1—24 ይህ የአዳም በደል ከእሱ በተወለዱ ዘሮቹ በሙሉ በውርስ ሲተላለፍ ኖሯል። ከሰማይ ከወረደው ሁለተኛው አዳም/ ኢየሱስ/ በቀር ያለ ውርስ ኃጢአት የኖረ ማንም አልነበረም። የኢየሱስም ከሰማይ ወርዶ ሰው የመሆን ምስጢሩም የሚነሳው፣ የአዳም ዘር በሙሉ በሞት ፍርድ ሥር ያለ በመሆኑ ከሥጋ ለባሽ አንድም ሰው ዘሩን ነጻ ማድረግ ስለማይችል ነበር። ይህንንም ሐዋርያው ጳውሎስ አስረግጦ ሲያስረዳ ወደ ሮሜ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ እንደዚህ ብሎታል። “ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፥ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፤” ሮሜ 5፥12 ስለዚህም ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል "ወልድ" በሥጋ ሰብእ ከድንግል ማርያም ተወልዶ፣ ከኃጢአት ብቻ በቀር አዳማዊ ባህርይን ተዋሕዶ ሰው ሆነ። አዳምንና ልጆቹን ከዘላለም ሞት ማዳን የሚችለው ከኃጢአት ነጻ መሆን የቻለ ብቻ ስለነበር ኢየሱስም የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ለኃጢአተኞች ነጻ መውጣት የአብ መስዋእት ሆኖ ቀረበ። “በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።”ዮሐ 1፥29 ይህ የዓለምን ኃጢአትን የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ (ካልቪኒስቶች ለዓለሙ ሁሉ አልሞተም ይላሉ) መስቀል ላይ ውሎ የኃጢአት ሥርየት እርሱ መሆኑን አምነው፣ በስሙ ለተጠመቁና እስከመጨረሻው እምነታቸውን አጽንተው ለተጠበቁ በሙሉ እንጂ ለተወሰነ ዘር፣ ነገድ፣ ጎሣ፣ ብሔር ወይም ለተወሰነ ወገን የተፈፀመ ማዳን አልነበረም። ሐዋርያው ጳውሎስ ሞት ወደዓለም በአንዱ አዳም በኩል ለሁሉ እንደደረሰ ሕይወት ደግሞ በአንዱ በኢየሱስ በኩል ለተቀበሉት ሁሉ ሆነ በማለት ያስረዳናል። “በአንዱም በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፥ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ።” ሮሜ 5፥17 እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ወደዓለም የላከውና ለመስቀል ሞት የታዘዘው የአዳም ዘር በሙሉ በእርሱ አምነው እንዲድኑበት እንጂ የተወሰነ ቡድን ወይም በምርጫ ለተለየ ወገን ለይቶ ለማዳን አይደለም። በዚህ ዘመን ጆን ካልቪን የተባለ የ17ኛው ክ/ዘመን የተነሳ የአዲስ ሃይማኖት አስተማሪ ደቀመዛሙርት ነን የሚሉ በዚህ ዘመንም ኢትዮጵያ ውስጥ ሃይማኖታዊ ክሂዶትን አጠናክረው በመቀጠል ኢየሱስ የሞተልን ለእኛ ለተመረጥን፣ አስቀድሞ ለተለየንና ለተጠራን ብቻ እንጂ ለአዳም ልጆች ሁሉ ኃጢአት አይደለም እያሉ በታላቅ ድፍረት ሲናገሩ ይደመጣሉ። ብዙዎችንም እያሳቱ ይገኛሉ። በመጥምቁ ዮሐንስ የተመሰከረልንና "የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ" ዮሐ 1:29 የሚለው ቃል በካልቪኒስቶች አስተምህሮ "ለኛ ለተመረጥነው እንጂ ለዓለሙ ሁሉ አይደለም" በሚለው መቀየር አለበት እንደማለት ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ በአዳም አለመታዘዝ ሞት ለሁሉ እንደደረሰ፣ በአንዱ በኢየሱስ መታዘዝ ሕይወት ለሁሉ እንደበዛ እንዲህ በማለት ይነግረናል። “በአንዱ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ኃጢአተኞች እንደ ሆኑ፥ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ።” ሮሜ 5፥19 ከእኛ ከኃጢአተኞቹ የሚጠበቀው እግዚአብሔር በልጁ ሞት እንዳዳነን፣ ሕይወትም እንደሰጠን ማመንና መቀበል ብቻ እንጂ ከእኛ በሆነ ሥራ አይደለም። "ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም" ኤፌ 2:8—9 ነገር ግን ካልቪኒስቶች ሥራም፣ እምነትም፣ ማወቅም፣ መረዳትም፣ ማመንም ሳይጠበቅብን አስቀድሞ በእግዚአብሔር የተመረጥነውና የተለየነው እኛ ብቻ /predestination/ የተሰጠን ስንድን ለሲኦል የተዘጋጁት ደግሞ ያልተመረጡና አስቀድሞ የተፈረደባቸው ናቸው በማለት አምላካዊ ምህረቱን ለግላቸው በመውሰድ በሌሎች ላይ የፍርድ ቃል በድፍረት ሲናገሩ አይሰቀጥጣቸውም። ይህ አባባላቸው ኢየሱስ የተሰቀለው አስቀድሞ ለተመረጡና ለተወሰኑ ሰዎች እንጂ በእርሱ አምነው ለሚመጡ ለዓለሙ ሁሉ አይደለም ለማለት የሚረዳቸውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥቅስ ቦጭቀው ሲጠቀሙ ይህንን ይጠቅሳሉ። “አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው።” ሮሜ 8፥30 ይሄንን ቃል ሲያብራሩ እኛ /ካልቪኒስቶቹ/ ራሳቸውን ማለታቸው ነው። አስቀድሞ እንድንድን የተወሰነልን ነን። ከእንግዲህ የትኛውንም ኃጢአት ብንሰራ አንጠፋም። አስቀድሞ በተሰወነልን መሠረት የጠራን አንዴ ልጆቹ አደረገን። አፅደቆም በሰማይ አከበረን ይላሉ። ከዚህ ከእግዚአብሔር ቃል እውነት ፍፁም ተቃራኒ በሆነ ክህደት ውስጥ እንዲዘፈቁ ያደረጋቸው ሰይጣናዊ ትርጉም ሁለት መሰረታዊ ነገርን ከመሳት የመጣ ነው። እሱም፣ 1/ የእግዚአብሔር ሁሉን አዋቂነት ወደሰውኛ እውቀት ማውረድና 2/ የእግዚአብሔርን ምሕረትና የይቅርታ ሚዛን አለመረዳት ናቸው። እግዚአብሔር አምላክ የማያውቀውና የተሰወረበት ምን ምስጢር አለ? እግዚአብሔር ፍጥረትን ከፈጠረበትና ዓለማትን ከሚያሳልፍበት ሁሉን ቻይነቱ፣ የሉዓላዊነት ሥልጣን ውጪ የሆነና መሆን የሚቻለው አንዳችም ፍጥረት የለም። ይህም የእግዚአብሔር የሁሉን አዋቂነቱ /Omniscient/ እና የከሃሌ ኩሉነት /Omnipotent/ በራሱ አምላካዊ ባህርይው የሚገኝ ነው። ከዚህ ተነስተው እነዚህን ጥያቄዎች ብናነሳ የምናገኛቸው ትክክለኛ መልሶች ያሉት በእርሱ ዘንድ ብቻ ናቸው። የሰው ልጅ ከተፈጠረ ጀምሮ ስንት ሰው ተወልዷል፣ በፆታ ስንቱ ወንድ ስንቱስ ሴት ነው? ስንትስ ሰው ሞቷል፣ ስንት ሰውስ በሕይወት አለ? ስንቱ ገነት ገባ? ስንቱስ ሲዖል ወረደ? የሚሉትን ጥያቄዎች ብንጠይቅ ይህንን በትክክል የማወቅ ኃይሉ ያለው በእግዚአብሔር ዘንድ ብቻ ነው። በዚህም እግዚአብሔርን ሁሉን አዋቂ አምላክ እንለዋለን። “ፍጥረታችንን እርሱ ያውቃልና፤ አቤቱ፥ እኛ አፈር እንደ ሆንን አስብ።” መዝ 103፥14 “የጠለቀውንና የተሠወረውን ይገልጣል፤ በጨለማ ያለውን ያውቃል፥ ብርሃንም ከእርሱ ጋር ነው።”ዳን 2፥22 የእግዚአብሔርን ሁሉን አዋቂነት ካልቪኒስቶቹ ራሳቸውን ከፀደቁት ጎራ ጨምረው እግዚአብሔር ዓለም ሳይፈጠር የፈረደባቸውንና በሰማይ ያፀደቃቸውን ስለሚያውቅ እኛን ከፀደቁት አድርጎ አስቀድሞ ወደፅድቁ ስለጨመረን ኩነኔ የሚባለው ነገር አይመለከተንም እያሉ በአስቀድሞ መወሰን/Predestination/ ውስጥ ራሳቸውን ያስቀምጣሉ። እግዚአብሔር ሁሉንም አዋቂ ነው ማለት ጄምስን ኮንኜዋለሁ፣ ገብረማርያምን ደግሞ አፅድቄዋለሁ ብሎ አስቀድሞ ውሳኔ የሰጠበት ሰው የለም። እንደዚያ አስቀድሞ ከተወሰነ የኢየሱስ ሰው መሆን ለምን አስፈለገ? ለምንስ ተሰቀለ? እምነትስ ምን ሊጠቅመን? እምነትንስ በሥራ መግለፅ ምን ሊጨምር? አስቀድሞ ለፅድቅ የተወሰነ ሰው ስለኃጢአት የሚከፈል ዋጋስ ለምን አስፈለገው?ቢከፈልለትም ሆነ ባይከፈልለት አስቀድሞ የተወሰነለትን ከመቀበል የሚያግደው ነገር ምን አለ?የሚሉ ጥያቄዎችን ብናነሳ መሆን የሚገባቸው ትእይንቶች/ ትርኢቶች/ እንጂ በመሰረታዊ የሰው ልጆች የመዳን መንገድ ላይ ትርጉም የሌላቸው ሆኖ እንዲታዩ የሚያደርግ ነው። ውሳኔው ቀድሞ ስለተሰጠ መዳኑ አይቀርበትም። ቀራንዮ ላይ የተፈፀመው ስቅለት አስቀድሞ የተነገረለትን ለማሳየት የተደረገ ትርኢት ነው ማለት ነው። ይህ የጆን ካልቪን ትምህርት አደገኛና የእግዚአብሔርን ፍፁም የሆነ ፍቅር በመሻር ሰው የሚፈረድበት በራሱ ምርጫ ሳይሆን ለሲዖል እሳት እንደማገዶ እንጨት አስቀድሞ አዘጋጅቶት የነበረውን ሰው ወደእሳት በመወርወር የሚደረግ ድምዳሜ እንጂ በማመኑ ወይም ባለማመኑ የሚደረግ ፍፃሜ አይደለም የሚል ክህደት ነው። ይህም እግዚአብሔር ሰው በምርጫው እንዲወስን ነባቢት፣ ለባዊትና ሕያዊት ነፍስ አልሰጠውም የሚል አምላክን እንደጨካኝ ገዢ የሚስል ሰይጣናዊ ትምህርት ነው። ዮሐንስ በራእዩ የጻፈልን ቃል፣ "ዓመፀኛው ወደ ፊት ያምፅ፥ ርኵሱም ወደ ፊት ይርከስ፥ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅ ያድርግ፥ ቅዱሱም ወደፊት ይቀደስ አለ። እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ። አልፋና ዖሜጋ፥ ፊተኛውና ኋለኛው፥ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ"ራእይ 22:11—13 የሚለው ቃል አስቀድሞ በተወሰነ ነገር ላይ ዝም ብሎ የተጻፈ እንጂ ፅድቅም፣ ርኩሰትም በማድረግ እንደሥራው የሚባል ክፍያ የለም እያሉን ነው ካልቪኒስቶቹ። የጆን ካልቪን ክሂዶተ እምነትና አስቀድሞ የመወሰን /predestination/ ስህተቶች በ5 ነጥቦች የተመደቡ ናቸው። 1/ Total Depravity/ የሰው ልጅ ከውድቀት በኋላ በጭራሽ ጻድቅ መሆን አይችልም የሚል ነው። ይህ የስህተት ትምህርት በአዳም ስህተት የተላለፈው ውድቀት የሰውን ልጅ ከነአካቴው የክፋት ሁሉ ባለቤት ነው ብሎ በሰው ጆሮ የሚያንቃጭል የሰይጣን ውንጀላ ሲሆን ሰው ሁሉ እኔን መስሏል የሚል ሰይጣናዊ ድምፀት ያለበት ክስ ነው። ከውድቀት በኋላ ለአዳም ልጆች ሁሉ የተላለፈውን ሞት የሚያስቀር የጽድቅ ሥራና ወደወጣበት ገነት የሚመልስ ማንነት በሥራው አያገኝም ማለት፣ ሰው በጎነት፣ ደግነት፣ በፈሪሃ እግዚአብሔር መኖር፣ የጽድቅ ሥራ መፈፀም አይችልም ማለት አይደለም። በመጽሐፍ ቅዱሳችን በዚህ ተግባር የተመሰከረላቸው ሰዎች ነበሩ። ለምሳሌ ሄኖክ፣ ኖኅ፣ አብርሃም፣ ሎጥ፣ ሳሙኤል፣ ኤልያስ፣ ኤልሳዕ፣ ዳንኤል፣ ሠለስቱ ደቂቅ ወዘተን መጥቀስ ይቻላል። ከዚህም የተነሳ የካልቪኒስቶች ስሁት ትምህርት በምድር ላይ የጽድቅ ስራን መሥራት በመቻልና በሥራ በመጽደቅ መካከል ያለውን ልዩነት አቅላቅለው እውነትን ደፍጥጠው ይክዳሉ። 2/ Unconditional Election /አስቀድሞ መመረጥ/ እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የሚድኑትን አስቀድሞ መርጧቸዋል። ሲመርጣቸውም ምንም ዓይነት መስፈርትና መለኪያ አላደረገም። በቃ! ጻድቅ እንዲሆኑ ተፈጠሩ የሚል ነው። ኃጢአት፣ ሥርየት፣ እምነት፣ የሚባል ነገር ለፎርማሊቲ እንጂ ከተመረጡበት አያስቀራቸውም፣ አይጨምርላቸውም። የትኛውም ኃጢአት ከምርጫው አያስቀራቸውም የሚል ሲሆን እግዚአብሔር ለሲዖል መርጦ ያስቀራቸው አሉ በማለት ፍፁም ፍቅር የሆነውን የእግዚአብሔር ፍቅር ከሰው ልብ አውጥቶ የሚጥል ሰይጣናዊ ትምህርት ነው። ሲጀመር ሲዖል ለሰይጣንና ለመላእክቱ እንጂ ለሰው ልጅ አልተፈጠረም። ማቴ 25:41 3/ Limited Atonement የኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል ላይ ሞት የተከናወነው ለእኛ አስቀድሞ ለተመረጥነው ብቻ ነው የሚል አስተምህሮ ነው። ለዚህም እንዲረዳቸው ይህንን ጥቅስ ይጠቅሳሉ። “መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።”ዮሐ 10፥11 ኢየሱስ ነፍሱን የሰጠው ለእኛ ለተመረጥነው በጎቹ ብቻ ነው የሚል ነው። ሲጀመር ካልቪኒስቶች በ/Limited Atonement/ /ለበጎቹ ብቻ/ በሚለው አስተምህሮአቸው ውስጥ ሁለት ነገር ይስታሉ። አንደኛው በማይቀየር ማዳኑ ውስጥ አስቀድሞ በጎቹ ከተመረጡ ኢየሱስ ለምን መሰቀል አስፈለገው? ዝም ብሎ እነሱን እየለየ ወደገነት ማስገባት ተገቢ በሆነ ነበር። ሲቀጥል ካልቪኒስቶች የስህተት ትምህርታቸውን ተርጉመው የኢየሱስ በጎች እኛ ነን ያሉት ራሳቸው እንጂ ካልቪኒስቶች ብቻ የተመረጡ ናቸው የሚል ማረጋገጫ በመጽሐፍም፣ በመላእክትም የተመሰከረ አይደለም። ደግሞ የተነገረን እውነት የተለየ ወንጌል የሰበከ የተረገመ ይሁን የሚል ነው። ገላ 1:8 እኛ ግን እንዲህ ብለን እናምናለን። “በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤” ገላ 3፥26 በኢየሱስ አዳኝነት ያመነ፣ የተጠመቀና እምነቱን በሥራ የገለፀ አማኝ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኗል ብለን እንናገራለን እንጂ ኢየሱስ የዓለም መድኃኒት የተባለበትን ሞትና ትንሣኤውን የካልቪኒስቶች ብቻ መድኃኒት ብለን ስለሁሉ የሞተበትን ምስጢር አንክድም። 4/ Irresistible Grace/ የካልቪኒስቶች ሌላው ስሁት አስተምሮአቸው አስቀድሞ በፀጋው የተጠሩት መቼም እንዳይጠፉ ሆነው የሚል ነው። ለዚህም ደጋፊ እንዲሆናቸው ዮሐንስ በወንጌሉ የጻፈውን የራሳቸው ብቸኛ ማረጋገጫቸው አድርገው ያቀርባሉ። “አብ የሚሰጠኝ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፥ ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም” ዮሐ 6፥37 የሚገርመው ነገር በ30 ጠገራ ብር ኢየሱስን የሸጠው ይሁዳ ከተጠሩት ሐዋርያት መካከል አልነበረም ወይ? ሲባሉ ከሐዋርያነት የተደመረው ሽያጩን እስኪፈፅም እንጂ በዘላለማዊ ጥሪ ውስጥ አልነበረም ይላሉ። ለያህዌ ስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ካልቪኒስቶች እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ላይ ቁማር ይጫወታል፣ ያለምርጫህ ብትጠፋም ላንተ መጥፋት ግድ አይሰጠውም ወደሚል የአምላክን ባህርያዊ ፍቅር ወደማስካድ ይወርዳሉ። እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ ስለሆነ የሚጠፉትንና የሚድኑትን ያውቃል ማለት የሚጠፉትና የሚድኑት እግዚአብሔር አስቀድሞ ስለወሰነባቸው ሳይሆን ሰዎች በሚያደርጉት የራሳቸው ውሳኔ የተነሳ መሆኑን አይቀበሉም። አዳም ከገነት ከመባረሩ በፊት ፍጻሜውን እግዚአብሔር ያውቅ ነበር ማለት አትብላ ያለውን እፀ በለስ በግድ እንዲበላ ስለወሰነበት ነበር ብሎ ማቅረብ አደገኛ ክህደት ነው። ይህም የሰው ልጅ በራሱ ማሰብና መወሰን የማይችልና አስቀድሞ በተገጠመለት የውሳኔ ሶፍትዌር የሚንቀሳቀስ ቁስ ነው እንደማለት ነው። የተወሰነብህን ትኖራለህ እንጂ በእውቀትም፣ በእምነትም የምትጨምረውና የምትቀንሰው ነገር የለም ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችን የሚነግረን አንዴ በተሰጠ ምርጫ የለሽ ውሳኔ ሳይሆን የምናምነው አምላክ አውቀን በዚሁ በእምነታችን ፀንተን ስንቆይ እንደሆነ በግልፅ ይነግረናል። “የመጀመሪያ እምነታችንን እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ፥ የክርስቶስ ተካፋዮች ሆነናልና፤” ዕብ 3፥14 እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ከወጡ በኋላ ወተትና ማር ወደምታፈሰው ምድር ሳይገቡ በምድረ በዳ የቀሩት እግዚአብሔር በረሃ በልቷቸው እንዲቀሩ አስቀድሞ በወሰነባቸው ውሳኔ ሳይሆን ድንቅና ተአምራትን አድርጎ ከሰማይ መና፣ ቀን በደመና፣ ሌሊት በብርሃን ዓምድ እየመራቸው በነበረው አምላካቸው ላይ በማመፃቸው ነበር። " ዛሬ ድምጹን ብትሰሙት፥ በማስመረር እንደሆነ ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ። ሰምተው ያስመረሩት እነማን ነበሩ? በሙሴ ተመርተው ከግብጽ የወጡ ሁሉ አይደሉምን? አርባ አመትም የተቆጣባቸው እነማን ነበሩ? ሬሳቸው በምድረ በዳ የወደቀ፥ ኃጢአትን ያደረጉት እነርሱ አይደሉምን? ካልታዘዙትም በቀር ወደ እረፍቱ እንዳይገቡ የማለባቸው እነማን ነበሩ? ባለማመናቸውም ጠንቅ ሊገቡ እንዳልተቻላቸው እናያለን" ዕብ3: 15—19 5/ PERSEVERANCE OF THE SAINTS ይህ ማለት አንዴ ከዳንክ ለዘላለም ድነሃል። በየትኛውም ኃጢአት ወይም በዓመጻ የሚጎድልህ ማንነት አይኖርህም ማለት ነው። Once saved, always saved ይሉሃል። በካልቪኒስቶቹ ዘንድ በዕብራውያን 10:36 ላይ የተመለከተው በእምነት ፀንቶ፣ ፈቃዱን እያደረጉ መኖር ነገር እርባና የለውም። “የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና።” ዕብ 10፥36 አንዴ የዳነ፣ ለዘላለም የማይጠፋ ስለሆነ በካልቪኒስቶች ዘንድ የሐዋርያው ጴጥሮስ ምክር ምንም አያስቀርበትም። “ስለዚህ፥ ወዳጆች ሆይ፥ ይህን እየጠበቃችሁ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ ሆናችሁ በሰላም በእርሱ እንድትገኙ ትጉ፥” 2ኛ ጴጥ 3፥14 የእግዚአብሔር ፈቃድ ብታደርግም፣ባታደርግም አንዴ ድነሃልና አትጠፋም፣ አትጨነቅ። ዮሐንስ በመልእክቱ የፃፈው ካልቪኒስቶችን አይመለከትም። ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው የሚለው ቃል ቢኖርም አንዴ ስለዳንክ ችግር የለውም ይሉሃል። “ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፥ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና።”1ኛ ዮሐ 3፥8 አንዴ ስለዳንክ በኃጢአት የተነሳ ከዲያብሎስ ብትሆንም አትጨነቅ፣ አትጠፋም እያሉ ለድፍረት ኃጢአት ያበረታቱሃል። ኃጢአት መስራት፣ አለመስራትህ የሚቀንስብህ ወይም የሚጨምርልህ ነገር የለም ይሉሃል። “ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።”1ኛ ዮሐ 2፥17 ፈቃዱን ብታደርግ ጥሩ ነው። ሳትፈፅመው ብትቀርም ችግር አያስከትልብህም፣ አትጨናነቅ፣ አንተ ለዘላለም የተመረጥህ ነህና። ዮሐንስ በእግዚአብሔር ዘላለማዊ ዓላማ ውስጥ ለመኖር ፈቃዱን መፈፀም ተገቢ ነው ያለው የራሱ ግምት በመሆኑ ካልቪን ያሻሻለውንና አንዴ የዳነ፣ ለዘላለም ዳነ የሚለውን ትምህርት ተከተል ይሉሃል ከሃዲዎቹ! ማጠቃለያ፣ ካልቪኒስቶቹ የሳቱት እውነት፣ የምሥራቹ ቃል የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል እንጂ የጆን ካልቪን ትርጉም፣ አባባል፣ አገላለፅ ወይም የአስተምህሮ አቋም አለመሆኑን አለማወቃቸው ነው። ካልቪን በአንድ ወቅት የተለየ የወንጌል አስተምህሮ ተገልጾልኛል ብሎ የራሱን ትርጉም ይዞ የመጣ ሰው እንጂ የምሥራቹ ቃል ምንጭ ስላልሆነ ካልቪኒስት ነኝ ብሎ እሱን መከተል አደገኛ ስህተት ነው። ማንም አማኝ የወንጌልን ትምህርት በብዙ መንገድ፣ ከብዙ ሰዎች ሊሰማ ወይም ሊያገኝ ይችላል። ያ ማለት ግን የወንጌል እውነት እሱ ከሰማበት ቦታ ብቻ ይገኛል ማለት አይደለም። የየትኛውም ትምህርት ማረጋገጫና መመዘኛ መንፈስ ቅዱስና የምሥራቹ ቃል እውነት መሆኑን አለማወቃቸው ነው። ሉተር፣ ካልቪን፣ ዝዊንግሊ፣ ኤራስመስ፣ ኖክ፣ ዊክሊፍ፣ ኸስ፣ ሜላንክቶን ወይም ቲንዳል የእውነት ቃል ምንጭ ወይም የመጨረሻው የእውነት ማረጋገጫ ሊሆኑ እንደማይችሉ አለመረዳታቸው ነው። ከኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ይልቅ ግለሰቦቹ በሰጡት ትንታኔ ላይ በመመስረት ለማመን መሞከራቸው ነው ካልቪኒስት ሆነው ለመኖር የወሰኑት። እኛ ግን የተሰቀለልንና ከሞት ያዳነን የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይና ደቀመዛሙርት እንጂ የአጵሎስ ወይም የጳውሎስ አይደለንም። ከሰማይ በታች እንድንበት ዘንድ የተሰጠን ስም ማነው? ከሰማይ በታች ሊድኑበት ለወደዱና ወደእርሱ ለመጡ በሙሉ የሚያድነው ስም ኢየሱስ ብቻ ነው። ከሰማይ በታች የተሰጠ የካልቪን አስተምህሮ፣ ለካልቪኒስቶች ሊኖር ይችላል። እኛን ክርስቶሳውያንን አይመለከትም። የካልቪን የሚባል አስተምህሮም፣ መምህርም የለንም።

Saturday, January 13, 2024

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዋና ችግር ጳጳሳት ናቸው!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዋና ችግር ራሳቸው ጳጳሳቱ ናቸው። ምክንያቶቹ፣ 1/ አንድ ወጥ የሆነ የቀደምት አበው መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ የለውም። ተረት፣ ተረት፣ እንቆቅልሽና እንቶ ፈንቶውን ስህተት አርሞ በትክክለኛው የወንጌል ጎዳና ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትሄድ ማድረግ አልቻለም። ዳንኤል 5፣ 24—28 ስለዚህም እነዚህ የእጅ ጣቶች ከእርሱ ዘንድ ተልከዋል፤ ይህም ጽሕፈት ተጽፎአል። የተጻፈውም ጽሕፈት፦ ማኔ ቴቄል ፋሬስ ይላል። የነገሩም ፍቺ ይህ ነው፤ ማኔ ማለት፥ እግዚአብሔር መንግሥትህን ቈጠረው ፈጸመውም ማለት ነው። ፋሬስ ማለት፥ መንግሥትህ ተከፈለ፥ ለሜዶንና ለፋርስ ሰዎችም ተሰጠ ማለት ነው። ከዚህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል አንፃር ቤተክርስቲያኒቱ መፈረካከሷ ገና ይቀጥላል። 2/የጳጳሳቱ ጉባዔ በቤተ ክርስቲያኒቱ ትልቁ የሥልጣን ማዕከል ነው። ነገር ግን ቤተ ክርስቲያኒቱን በመንፈሳዊ ምሳሌነት፣ በእውቀት፣ በዘመናዊ አስተዳደርና መዋቅር መምራት አልቻለም። በዚህም የተነሳ ዘረኝነት፣ ሌብነት፣ ዘረፋ፣ ጉቦ፣ የፍትህ መጓደል፣ ጥንቆላና አስማተኝነት ከጳጳሳቱ ጀምሮ እስከታችኛው መዋቅር ድረስ የዕለት ከዕለት ተግባር ነው። ከዚህ የተነሳ የሚከናወነው አምልኮተ እግዚአብሔር ከምእመናኑ የሚገኘውን ገንዘብ ለመሰብሰብና ጥቅም ማስገኛ ምንጭ ከማድረግ ባለፈ እግዚአብሔርን ከመፍራትና ለቃሉ ለመገዛት ካለ መንፈሳዊ ብቃት የተነሳ አይደለም። 3/ ቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ፣ የቅርስ፣ የሥነ ፅሑፍ፣ የሰነድ ባለቤት ሆና ሳለ ይህንን ሁሉ አራግፋ በመጣል የገዢዎች ባለሟል፣ ትዕዛዝ ፈጻሚ እና የመከራ ጽዋ የምትጎነጭ እርስ በእርሷ የምትባላ ሆና እያየናት ነው። ሲጠቃለል፣ ቤተክርስቲያኒቱ ጥቋቁር ጨርቅ በተሸፋፈኑ ጳጳሳት ከመፍረስ አትድንም። ወደቀደመ ክብሯ አትመለስም። ከተረት፣ ተረት እና ከፈጠራ የስህተት አስተምህሮ ወጥታ ወደእውነተኛ የወንጌል መንገድ ልትገባ አትችልም። ቢመርም እውነቱ እሱ ነው።