Saturday, June 4, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን አሁን የቤተ ክርስቲያን፤ ቆይቶ የመንግሥት መጥበሻ ምድጃ ነው!


በታሪክ አጋጣሚ የደርግን መውደቅና ግርግርን ተተግኖ የተፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን የመጥበሻ ምድጃ ከሆነ እነሆ 23 ዓመታት አለፉት። ብዙዎችን በትኗን፤ አሳዷል። ዳግም እንዳይመለሱ በማድረግ እንደተዋጊ በሬ እየበጠበጠ ከበረት አስወጥቷል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አፋፍተው ያሳደጉትን አቡነ ጳውሎስን ሳይቀር በአድማ የመጥበሻ እሳት እየለበለበ እስከመቃብር ሸኝቷል። የአሁኑን ፓትርያርክ የአቡነ ማትያስን ወንበር በተሾሙ ሰሞን ለመረከብ ተፍ ተፍ ብሎ ሳይሳካለት ቢቀር በተለመደ የመጥበሻ ምድጃው ላይ አስቀምጦ ላለፉት 3 ዓመታት  በአድማው ግሪል / GRILL/ እየጠበሰ ይገኛል።

ፓትርያርክ ማትያስ ብቻቸውን ሆነው ይህንን መጥበሻ ምድጃ ሊያስወግዱ ብዙ ታግለዋል። ነውራም ጳጳሳቱ እዳ በደላቸው በዚህ ማኅበር የኃጢአት መዝገብ ላይ ስለሰፈረ ከፓትርያርኩ በተጻራሪ ቆመው ውግንናቸው ለማኅበሩ ሆኖ ታይቷል። የማኅበሩ ሥፍራ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የት ነው? በሚለው ነጥብ ላይ ጥያቄ ያላቸው ፓትርያርክ ማትያስ ድርሻውን፤ አቅሙንና ተጠሪነቱን የሚወስን አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣለት ያደረጉት ተጋድሎ ላይ ውሃ በመቸለስ የሲኖዶስ ጉባዔ በመጣ ቁጥር የሚያጨቃጭቅ አጀንዳ እያስገባ ሲሾልክ ቆይቷል። ዘንድሮም ይህን የቤት ሥራ ሰጥቶ በአንድ አጀንዳ ላይ ለ4 ቀናት ካጨቃጨቀ በኋላ የሲኖዶስ አባል የሆነው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር መፍትሄ አስምጦ ሊገላግላቸው ችሏል። ይህ ሁሉ የሆነው በማኅበሩና በጉዳይ ፈጻሚ ጳጳሳቱ የተነሳ ነው።

የእንደራሴ መኖር አለመኖር ለማኅበረ ቅዱሳን አሳሳቢው አይደለም። ነገር ግን በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ማንሳት ያስፈለገው የራሱ ስሌት ስላለው እንጂ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ድክመት ከሱ መኖር በላይ አስቸጋሪ ፍጡር ስለመጣ አይደለም። በዚህም የተነሳ በአቅም ማነስ ሰበብ ፓትርያርኩን አሸመድምዶ በማስቀመጥ ለ3 ዓመታት ያህል እሳት ካነደዱበት ሥጋት ነጻ ለመውጣት የተያዘ መላ ከመሆን አይዘልም። ከዚህም በፊት እንዳልነው ጳጳሳቱ በሀገረ ስብከታቸው መሥራት ያልቻሉትን የመንፈሳዊና ሥጋዊ የልማት ሥራዎች  እንደራሴው እየዞረ የሚሰራላቸው አለመሆኑንም በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን እስካለ ድረስ ታዛዥ ያልሆነ የትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለሥልጣን  ማኅበሩ ባዘጋጀው መጥበሻ ላይ ይጣዳል። ምርጫቸው ከማኅበሩ ጋር መቆም አለያም በተጻራሪ ሆነው ለመጥበሻው ራሳቸውን ከማዘጋጀት የግድ ነው። አባ ሳዊሮስ ከአዲስ አበባ ማኅበረ ካህናት ጋር ቆመው ማኅበሩን ሲያጋልጡ ምድጃውን አዘጋጅቶ መጥበስ ሲጀምር እጃቸውን አንስተው ለማኅበሩ ለማስረከብ መገደዳቸውን አይተናል። አባ ፋኑኤል ማኅበሩ የሌለበት ቦታ የት ሄጄ ልሥራ? እንዳላሉ ሁሉ ምርኮኝነታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን ከማኅበሩ መጥበሻ ግሪል ላይ ወርደው እረፍት ሊያገኙ ችለዋል። ሌሎቹ ግን የሚደርስባቸውን እሳት አስቀድመው ስለሚያውቁ ቃላቸውን አክብረው የጫናቸውን በማራገፍ ግንቦትና ጥቅምት በመጣ ቁጥር በማኅበሩ አጀንዳ አስፈጻሚነታቸው ቀጥለዋል።

 ማኅበረ ቅዱሳን በስመ ተሐድሶና ሙሰኛ ነጠላ ዜማው የፈጃቸውና ያቃጠላቸው ካህናት ቁጥራቸው ብዙ ነው። ስለቅድስናና መንፈሳዊ ንጽህና በዋለበት ያልዋለ የዋልጌዎች ስብስብ ይህ ማኅበር ስም እያጠፋ ያሳደዳቸው፤ ስለኃጢአታቸው ንስሐ የሚገቡበትን በር እየዘጋ ተስፋ በማስቆረጥ ያስወጣቸው የትየለሌ ናቸው። የሚገርመው ግን ነውራም ጳጳሳቱን በቅድስና ካባ ሸፍኖ ለአገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው የከባቴ አበሳ ተፈጥሮ ስላለው ሳይሆን እስካለገለገሉት ድረስ ብቻ ነው። እያንዳንዱ የማኅበሩ አባል በተለይም አመራሩ እነአቡነ እገሌ እስከምን ድረስ የጉስቁልና ባሕር ውስጥ እንደሰጠሙ እያወቀ በስምምነት አብሮ ይሰራል። ነገር ግን ከማኅበሩ አቋም ካፈነገጡ ከዚህ በፊት እንዳደረገው የእዳ ደብዳቤአቸውን ከማንበብ አይመለስም። ይህ በተግባር የተረጋገጠ እውነት ነው።

አንዳንዶች ማኅበሩን የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ብቻ አድርገው ያያሉ። ነገር ግን ማኅበሩ  እንደግብጹ የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር በፖለቲካው መድረክም የረቀቀ ተልእኮ ያለው ማኅበር ነው። በአባልነት ያቀፋቸው ሚኒስትሮች፤ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች፤ ሥራ አስኪያጆች፤ ፖሊሶች፤ ዳኞች፤ የሕዝብ አገልግሎት ሠራተኞች፤ መምህራንና ተማሪዎች፤ የሙያ ማኅበራት፤ በ44 አኅጉረ ስብከት ውስጥ ያሉ ሚሊዮኖች የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ የጥምቀት ተመላሽ ተጠባባቂ ጦር የመሳሰሉትን በአባልነት እየመለመለ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የራሱን ዶክትሪን በመጋት ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን ካሰኛቸው ውሎ አድሯል። ዛሬ ከሲኖዶስ ወይም ከፓትርያርኩ በላይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪና ጠባቂ ከማኅበሩ በላይ የለም የሚለው አስተሳሰብ በእያንዳንዱ ሰው አእምሮ ውስጥ እንዲሰርጽ በሰፊው ተሰርቷል። ዘመናዊ የክርስቲያን ብራዘር ሁድ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው።

ሌላው የማኅበሩ ተንኮል አሁን ካሉት ታማኝና ታዛዥ ጳጳሳት በተጨማሪ ከእንግዲህ የሚሾሙ ኤጲስ ቆጶሳት በራሱ መስፈርት የተመለመሉና ወደፊት ችግር እንደማይፈጥሩ የተረጋገጠላቸው ብቻ እንዲሆኑ ይፈልጋል። እነዚህ የማኅበሩ እጩ ኤጲስቆጶሳት ያለፈ ታሪካቸው የቱንም ቢመስል አሳሳቢ አይደለም። ተቀባይነታቸው አርአያነት ባለው ሁኔታ ቢሆንም፤ ባይሆንም ለማኅበሩ አስጊ እስካልሆኑ ድረስ እንዲመረጡ አጥብቆ ይሰራል። ነገር ግን በተቃራኒ ማኅበሩን የሚፋለሙ ከሆነ እንደአባ ሠረቀብርሃን ወ/ሳሙኤልን የመሳሰሉት በልዩ ልዩ ስምና ወንጀል በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ እጃቸውን ካልሰጡ በስተቀር ለእጩነት ሊቀርቡ አይችሉም።

በአጠቃላይ ማኅበሩ በታሪክ አጋጣሚ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የተገኘ መጥበሻ ምድጃ ነው። በዚህ ምድጃ ዲያቆናት፤ ቀሳውስት፤ መነኮሳት ተጠብሰዋል። ሰባኪያነ ወንጌልና አስተዳዳሪዎች ተጠብሰዋል። ጳጳሳትና ፓትርያርኮች ተጠብሰዋል። እውነቱን እያወቁ ከመናገር ብዙዎች የተቆጠቡት ማኅበሩ መጥበሻው ላይ ከጣዳቸው የሚያወርዳቸው ስለሌለ ነው። ልክ እንደ መንግሥታዊ የስለላ መዋቅር የማኅበሩን ስም በተቃውሞ በአውቶቡስ፤ በታክሲ፤ በሬስቶራንት፤ በየካፌውና በሕዝብ መሰብሰበቢያ ቦታዎች መጥራት ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። መንግሥት ላይ ምን ዓይነት የአንኮበር መድኃኒት እንደተረጨበት ባናውቅም እሱም በፍርሃት ይሁን በድንዛዜ ፈዞ ቀርቷል።  እውነታው ግን ማኅበሩ ለየትኛውም ወገን መጥበሻ ምድጃ መሆኑ በተግባር የተረጋገጠ ነው።

Wednesday, June 1, 2016

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?




አበው ዘይቤያዊ ምሳሌ ሲሰጡ፤ ፍሬ ነገሩን  ሊገልጥ የሚችል ጥሩ ኃይለ ቃል ይጠቀማሉ። በአንድ ዐረፍተ ነገር ብዙ ሐተታ ሊወጣው በሚችል መልኩ የጉዳዩን ብስለትና ጠጣርነት በደንብ ያሳዩበታል። ለዚህም ነው «ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» በማለት መሆን የማይገባው ነገር ሆኖ ቢገኝ መፍትሄው ግራ የሚያጋባ እንደሆነ ለማስረዳት ይፈለጉት። አዎ፤ በዘመነ አበው ምላጭ፤  እባጭ እንዲፈነዳ፤ የተቋጠረው መግል እንዲፈርጥ ይበጡበት ነበር። በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ዛሬም አልፎ፤ አልፎ ይሰራበታል።  ነገር ግን ምላጭ ራሱ ቢያብጥ በምን ይቆረጣል? ውሃስ ቢያንቅ በምን ማወራረድ ይቻላል? ግራ የሚያገባ ነገር ነው። መሆን የሌለበት ሆኖ ሲገኝ ያስገርማል፤ ያስደነግጣል፤ መፍትሄውም ሩቅ ይሆናል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየታየ ያለው ድርጊት የዚሁ ምሳሌ ተመሳሳይ ነገር ነው። በቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ የቅዱስ ሲኖዶስ መንበር ከተመሠረተ ከ50 ዓመታት እጅግም ያልዘለለ ጊዜን ያስቆጠረ ቢሆንም በዚህ አጭር እድሜው 50 ጉድ አሳልፏል። ፓትርያርኳን አሳልፋ በመስጠት ለደርግ ጭዳ ማቅረቧም በማስረጃ የተረጋገጠ እውነት ነው። ፓትርያርክ አውርዳ ፓትርያርክ ሾማለች። ለሁለት የተከፈለ ሲኖዶስም የያዘችው በዚሁ አጭር እድሜዋ ነው። የሐዋርያትን መንበር ተረክቤአለሁ የምትለዋ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያት እንዳደረጉትና የራሱን ሥፍራ በለቀቀው በይሁዳ ምትክ እንደሾመችው ሐዋርያ በመንፈስ ቅዱስ ምርጫ እጣ ማጣጣል ሲገባት እንደፖለቲካ የካድሬ ምርጫ በሰውኛ አሳብና እንደተሰጣቸው ተልእኮ በሚመለመሉ ሰዎች ምርጫ መሾሟም የዚሁ የአጭር ዘመን ታሪኳ አንዱ ክፍል ነው። 

ነውርና ነቀፋ የሌለበት፤ ራሱንና ቤተሰቡን በአግባቡ ስለመምራቱ በምእመናንና ምእመናት የተመሰከረለት አገልጋይ ሰው ኤጲስ ቆጶስ እንዲሾም ቃለ ወንጌሉ ቢናገርም ከንባብና ከአንድምታው በዘለለ ተግባር ዳገቷ ቤተ ክርስቲያን ሆና ለሰሚ የሚቀፍ፤ ለሚያውቁት የሚያሳፍር ሹመት እየፈጸመች በመገኘቷ እነሆ ጥቅምትና ግንቦት በመጣ ቁጥር የዘራችውን እያጨደች ትገኛለች።
   «መልካም ዘር መልካም ፍሬ ያፈራል» እንዲል ወንጌል የዚህ ተቃራኒ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለመዘራቱ ደግሞ ፍሬውን ሲኖዶስ በመጣ ቁጥር ጭቅጭቅ፤ ንትርክ፤ ሁከትና አድማ ሲያስተናግድ ማየት የተለመደ ሆኗል። ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ለትውልድ የፈውስና የምሕረት መልእክተኛ መሆን የሚገባው አካል ለራሱ ከፈውስም ሆነ ከምሕረት ስለራቀ መሆን በማይገባው ሁኔታ ውስጥ ይገኛል። 

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡታል፤ ውሃስ ቢያንቅ በምን ይውጡታል?» ማለት ይኼ ነው። ሰው በልቡ መታደስ ካልተለወጠና የማይሞተውን የሞት አሸናፊ ካልለበሰ አዲስ ፍጥረት እንደማይሆን ሐዋርያው በመልእክቱ ነግሮናል።  ካልተለወጠና የቀድሞ ግብሩን ካልተወ አሮጌነት ደግሞ አብሮት ያለው ማንነት በክፋትና በተንኮል ተግባር እየተገለጠ በዘመኑ ሁሉ ይቀጥላል። ዛሬም በሲኖዶስ ጉባዔ ላይ የሚታየው ችግር ሁሉ የውስጥ ማንነቱ ማሳያ መስታወት ነው። ሰው የሌለውን ውበት ከየትም ሊበደር አይችልም።
ሰሞኑን እየተካሄደ ባለው ሲኖዶስ (ቅዱስ ለማለት ይከብደኛል) ምክንያቱም ካልተወሻሸንና ሞራል እንጠብቅ ካልተባለ በስተቀር መንፈስ ቅዱስ የሁከትና የንትርክ አምላክ ስላይደለ ቅዱስ ለማለት ይከብዳል። በስብሰባው ላይ እየታየ ያለው ኢ-መንፈሳዊና ኢ-ሥነምግባራዊ ድርጊት ከስምና ከማዕርግ እድገት በስተቀር ያልተለወጠ ማንነት የተንጸባረቀበት እጅግ አሳፋሪና አሳዛኝ ክስተት የታየበት ስለሆነ ነው። 

 «ከእናንተ አንዱ ከባልንጀራው ጋር ሙግት ቢኖረው በቅዱሳን ፊት በመፋረድ ፋንታ በዓመፀኞች ፊት ሊፋረድ ይደፍራልን? ቅዱሳን በዓለም ላይ እንዲፈርዱ አታውቁምን? በዓለምስ ላይ ብትፈርዱ ከሁሉ ይልቅ ትንሽ ስለሚሆን ነገር ልትፈርዱ አትበቁምን?» 1ኛ ቆሮ 6፤1-2

በቅዱስ ስም ተሰብስቦ፤ በዓለማውያን ምናልባትም እግዚአብሔርን በማያውቁ ዐመጸኞች ፊት የጉባዔ ዳኝነት ከመጠየቅ ወዲያ ለሲኖዶስ ምን ሞት አለ? አሁን እውነት ሕይወት ያለው ሲኖዶስ የሚባል አካል አለ ማለት ነው? ይህ ሁሉ የሆነውና እየሆነ ያለው በሞተ አካል ውስጥ ያለው የሙት መንፈስ ፍሬውን እያፈራ በመገኘቱ የተነሳ ነው።  ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ፤

 «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ» በማለት የተናገረው። የሐዋ 20፤28-30

መንጋው ተበትኗል፤ ለሚጠፋው በግ የሚራራ እረኛ የለም፤ ቤተመቅደሱ በርግብ ሻጮችና በለዋጮች ተሞልቷል፤ እርስ በእርሳቸው የሚነካከሱና የሚበላሉ ሆነዋል፤ ነገር ግን በሕይወት አለን ይላሉ። ለሥልጣን ሽሚያ፤ ለመፈንቅል፤ ለቡድን አሸናፊነት፤ ለማኅበር የበላይነት ይጋደላሉ።
 በየተመደቡበት ሀገረ ስብከት እንደነገሥታት የሚሰጣቸው ስግደት ሳይጎድል፤ እንደሰማያዊ ሹም ሆነው መታየታቸው ሳይጠፋ ምንም የሰሩትና ያለሙት በሌለበት ሁኔታ ዓይናቸው ሁል ጊዜ የሚያየው እዚያ ጣሪያ ላይ ነው። ጣሪያው ደካማ ይሁን ሰነፍ የሚያስቀምጠው አንድ ሰው ነው። ጣሪያው ላይ ሰው ሲቀመጥ ያልታገሉ ፈራህያን ዛሬ የሚያደቡት ምን ለማግኘት ነው? ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስበው? ተጨንቀው? በጭራሽ አይደለም።
 ጳጳሳቱ ሰው ከመቅጠርና ከማባረር ባለፈ ሚሊዮን ተከታዮቻቸውን አሰልፈው ትምህርት ቤት፤ ጤና ጣቢያ፤ የንጹህ መጠጥ ውሃ፤ የብሎኬት ማምረቻ፤ የእንጨት መሰንጠቂያ፤ የመስኖ ልማት፤ የልብስ ስፌት፤ የጧፍና ሻማ ማምረቻ፤ የአልባሳትና ቅርሳ ቅርስ ተቋም፤ የዶሮና የከብት እርባታ፤ የዳቦ መጋገሪያ፤ የካህናት ማሰልጠኛ፤ ኮሌጆች፤ ዩኒቨርሲቲዎች፤ የህጻናት ማሳደጊያ፤ የአረጋውያን መጦሪያ ለምን አያቋቁሙም? ለምን አይሰሩም? ማን ከለከላቸው?
ከ15 ሚሊዮን ያልበለጠ ተከታዮች ያሏት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት በረሃውን ገነት ያደረጉት፤ ምርትና ሃብታቸው የተትረፈረፈው እንደእኛ ጳጳሳት በፎጣ በመሸፋፈን ሳይሆን በአጭር ታጥቀው ከእስላም ሰይፈኞች ጋር በመታገልና ተግተው በመስራታቸውና በማሰራታቸው ነው። ከላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ያልሰራችው የልማት ስራ የለም።  በጀት ተመድቦላቸው፤ ባለሙያ ተቀጥሮላቸው ሳይሆን መነኮሳቱን፤ ካህናቱን፤ ምእመናኑን በማስተማርና በማሰልጠን በራስ አገዝ የልማት ተሳትፎ የተመሰረተ ነው።
 የኛዎቹ ለግንቦቱ ጉባዔ ከጥቅምት ጀምሮ ከመዶለትና ለጥቅምቱ ጉባዔ ደግሞ ከግንቦት ጀምሮ ሴራ ከመጎንጎን በስተቀር በሀገረ ስብከታቸው የልማት ርእይ፤ እቅድና ግብ በጭራሽ የላቸውም። ከሐውልት ምርቃት፤ ከቀብር ክፍያ፤ ከክርስትና፤ ከጋብቻ፤ ከፍትሃት፤ ከጸበል፤ ከሰበካ ጉባዔ አባልነት ወዘተ የሚሰበስቡትን ሚሊዮኖች ብር ለደመወዝና ለስራ ማስኬጂያ ከማዋል ባለፈ ተመልሶ ለሕዝቡ ልማት የዋለው ምን ያህሉ ነው? በደቡብ ክልል አካባቢ ያሉ የኦርቶዶክስ ምእመናን «እናንተ አምጡ እንጂ እንደሌሎቹ እንኩ አታውቁም» ማለታቸውን ስንሰማ የኛዎቹ መስጠትን ሳይማሩ አምጡን ከየት ለመዱት ያሰኛል።

    በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውድቀትና ማሽቆልቆል ተጠያቂዎቹ ጳጳሳቱ ናቸው። ለመንጋው መበተን፤ ለስርቆትና ሥነ ምግባር ጉድለት ኃላፊነቱን መውሰድ አለባቸው። የታጣው መሪ እንጂ  ለመመራት ፈቃደኛ፤ ለመስጠት እጁን የማይዘረጋ  ምእመን የለም። ደግሞስ እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ምእመን እጁን የሚዘረጋ አለ እንዴ?
 በሀገረ ስብከታቸው ልማት ሳያሳዩ ወደላይ መንጠራራት ስንፍናቸውን እንጂ አዋቂነታቸውን አያመለክትም። ጳጳሳቱ ለድክመታቸው ምክንያት ፓትርያርኩ ላይ አመልካች ጣታቸውን ከመቀሰራቸው በፊት እኔ በሀገረ ስብከቴ ምን ሰራሁ? ብለው ራሳቸውን ይጠይቁ። ብዙዎቹን ጳጳሳት ከምንኩስና ጀምሮ ስለምናውቃቸው ስለማንነታቸው ነጋሪ አያሻንም። ከታች ጀምሮ ያልተገነባ ስብእናና ችሎታ ደረጃቸው ስላደገ ባንዴ አብሮ አይመነደግም። ቁም ነገሩ እንደእኛው ችሎታ የሚያጥራቸው ሰዎች መሆናቸው ሲሆን አሁን አለቃቸውን ማስቸገር ቀደም ሲል በአለቅነታቸው ካዳበሩት ችግር የተማሩት ብቸኛ እውቀት ይመስለኛል።  ከዚያ ባሻገር በልማታቸው ለሕዝቡ የመኖር ተስፋ ወይም በጸሎታቸው ለሀገር የሚተርፉ ሆነው 15 ሚሊዮን ሕዝባችንን ከድርቅ ሲታደጉ አላየንም። ከመንጋ ጳጳስ እንዴት አንድ ኤልያስ ይጥፋ? ተግባር እንጂ ስም አላልኩም።

በግንቦቱ ሲኖዶስ ተሰብስበው በፓትርያርክ ማትያስ የችሎታ ማነስ ላይ ከመሳለቅ አስቀድመው በራሳቸው የአቅም ማነስ ላይ ቢወያዩ የተሻለ ነበር። ምሳሌ እንስጥ፤  ከ1985 ዓ/ም ጀምሮ 23 ዓመት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ሆነው የቆዩት የአሁኑ አባ ጎርጎርዮስ፤ ሟቹ አቡነ ጎርጎርዮስ ከመሰረቱት የዝዋይ ካህናት ማሰልጠኛና የአትክልት ልማት ወዲህ ስንት ማሰልጠኛ አቋቋሙ? ስንት የልማት አውታር ተከሉ? እውነታው ምንም ነው። አባ ቄርሎስስ በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት ስንት የካህናት ማሰልጠኛ፤ ስንትስ የእደ ጥበብ ተቋም ተከሉ? ስንት የከብት ማድለቢና የዶሮ እርባታ አቋቋሙ? ማን እንዳያደርጉ ከለከላቸው? ሟቹ አባ ጳውሎስ ወይስ ሕያው አባ ማትያስ?

 በምሥራቅ ጎጃምና በምዕራብ ጎጃምስ ምን ተሰራ፤ በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ሀ/ስብከትስ ምን ልማት ተቋቋመ? በአጭር ጊዜና በረጅም ጊዜ እቅዳችሁ ምን አሳካችሁ?  በደን ልማት ላይ ሕዝቡን በማስተባበር በዚህ ዓመት ስንት ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል ተዘጋጅታችኋል?
እርግጥ ነው ጳጳሳቱ በሌላ የሥራ መስክ ላይ አልቦዘኑም። የግል ቤታቸውን ገንብተዋል፤ ዘመናዊ መኪና አስገዝተዋል። በባንክ ገንዘባቸውን አጭቀዋል። ዘመድ አዝማዳቸውን በየቤተ ክርስቲያናቱ ቀጥረዋል።  
በአንድ ወቅት መንግሥቱ ኃ/ማርያም ሚኒስትሮቹን ሰብስቦ « የምትነዱትን የመኪና ዓይነትና ብዛት፤ ያላችሁን ቤት፤ የምትውሉበትን፤ የምታድሩበትን ቦታና ጭምር ይኽ ሕዝብ ብታምኑም ፤ ባታምኑም አሳምሮ ያውቃል» ብሏቸው ነበር።  ሕዝብ ምን የማያውቀው አለ? ተከድኖ ይብሰል ብለነው እንጂ የኛዎቹን ስንቱን ጉድ እናውቃለን።
 አሁን እነሱ ምን ስለሆኑ ነው፤ እንደራሴ ይሾም የሚሉት?  እንደራሴ ምን ያድርግላቸው? መፈንቅለ ፓትርያርክ መሆኑ ነው ወይስ እንደራሴው በየሀገረ ስብከታቸው እየሄደ ት/ቤት ሊሰራላቸው ነው? ጉዳዩ ፓትርያርኩን ወደጎን አስቀምጦ ለጳጳሳቱና ለማኅበረ ቅዱሳን ያደረ ሰው ለማስቀመጥ እንደሆነ ሳይታለም የተፈታ ነው። እቅዱም የኃጢአታቸው ዐቃቤ ኃጢአት ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ሴራነት የዘለለ አይደለም።  የሚያሳዝነውና የሚያስገርመው ነገር የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር እንደራሴ ለመሾም ይችሉ ዘንድ እንዲያግዛቸው መለመናቸው ነው።
 የፖለቲካ ሰው ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ቅዱስ በሚባለው ጉባዔያችሁ ተቀምጦ ሲነገራችሁ ከመስማት ሞት ይሻላችሁ ነበር። ዳሩ ግን የሞታችሁት ቀድሞ ነውና ይኼ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ውርደት ለእናንተ ግን ክብር ነው። ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር በጠሩት ጉባዔ ላይ አንድ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተወካይ የተናገረውን ጠቅሼ ልቋጭ። «ፖለቲከኛው እጣን፤ እጣን ሲሸት፤ የሃይማኖት አባት ፖለቲካ፤ ፖለቲካ ሲሸት አስቸጋሪ ነው» ማለቱን አስታውሳለሁ።
አዎ፤«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» እንዲሉ።




Monday, May 23, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



(Part two) www.chorra.net
ትምህርተ ተዋሕዶ ምን ይላል?[3]
“ክርስቶስ አሁን መካከለኛ አይደለም” የሚለው ኑፋቄ ምንጩ የአውጣኪ ትምህርት መሆኑ ይታወቃል። አውጣኪ በአንዱ በክርስቶስ የቃልና ሥጋ መደባለቅ (ቱስሕት)፣ የሰውነት ወደ አምላክነት መለወጥ (ውላጤ) ወይም መለዋወጥ (ሚጠት) ተከናውኗል ብሎ የተነሣ መናፍቅ ሲሆን፣ እርሱም ትምህርቱም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተወግዘው ከተለዩ ብዙ ምእት ዓመታት ተቈጥረዋል። በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት አንጻር ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ትምህርተ ተዋሕዶን አምልተውና አስፍተው አስተምረዋል።
የተዋሕዶ ትምህርት “አንቀጸ ተዋሕዶ” እንደሚባል ሊቃውንቱ ያስረዳሉ። ተዋሕዶ ሊገኝ የቻለውም አንቀጸ ተከፍሎን መነሻ በማድረግ ነው ሲሉ ያክላሉ። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ የአንቀጸ ተከፍሎ ትምህርት የሚያመለክተው ከተዋሕዶ በፊት የነበረውን የሥግው ቃልን ባሕርያውያን ምንጮችን ነው። ይኸውም ከሁለት ባሕርያተ ልደታት፣ ማለትም ቃል እም ቅድመ ዓለም ከአብ መገኘቱን፣ ትስብእትም ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም አብራክ መገኘቱን (መከፈሉን) ነው። በጥቅሉ የሁለቱም ምንጭና ተረክቦ (መገኘት) የሚታሰበብትን ጊዜ ያሳያል። አንቀጸ ተከፍሎን ፊልክስ ሰማዕት እንደሚከተለው አብራርቷል፤ “ወካዕበ ይቤ ንጠይቅ ክፍላተ ፪ቱ ህላዌያት ወስመ ፪ቱሂ ክፉል በኵሉ ጊዜ በምግባር ወበነገር ዘውእቶሙ መለኮት ወትስብእት። ወሶበ ንቤ ከመዝ ኢይምሰልክሙ ዘንከፍሎ እም ድኅረ ፩ዱ ከዊን ወዳእሙ ናጤይቅ ህላዌ መለኮት ወህላዌ ትስብእት ወዓዲ ነአምር እስመ ቃል አኮ ዘተመይጠ እም ህላዌ መለኮቱ ለከዊነ ትስብእት ሶበ ኀደረ ላዕሌነ። - ዳግመኛ [ቅድመ ተዋሕዶ የነበረ] የሁለቱን ባሕርያት (የመለኮትንና የትስብእትን) ልዩነት፣ የሁለቱም ስም በጊዜው ሁሉ በሥራ በአነጋገር ልዩ እንደ ነበረ እንወቅ፤ እነዚህም መለኮትና ትስብእት ናቸው። እንደዚህም ባልን ጊዜ ከተዋሕዶ በኋላ የምንለየው አይምሰላችሁ፤ የመለኮትን ባሕርይ የትስብእትን ባሕርይ እናስረዳለን እንጂ፤ ዳግመኛም ቃል ባሕርያችንን በተዋሐደ ጊዜ ከመለኮቱ ባሕርይ ሥጋ ወደ መሆን እንዳልተለወጠ እናውቃለን።” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 131)።
“በዚህ መሠረት የአንቀጸ ተዋሕዶ ትምህርት በአንቀጸ ተከፍሎ መሠረት ከጥንት ተለያይተው ከኖሩ ከሁለቱ … የአንዱን የዐማኑኤልን ህላዌ ቅውም አድርጎ የሚያሳይ የምስጢረ ተሠግዎ ወይም የምስጢረ ተዋሕዶ ትምህርት ነው።”[4] ስለዚህ በተከፍሎ የነበሩት ከተወሐዱ በኋላ አንዱን ከሌላው መለየትና እየብቻቸው ማድረግ አይቻልም። ቄርሎስ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ኢትፍልጥ ሊተ እም ድኅረ ትድምርት እስመ ዘፈለጠ እንተ ባሕቲቶ ብእሴ ወእንተ ባሕቲቶ አምላከ ቃለ ክልኤተ ይሬስዮ ለዐማኑኤል። - ከተዋሕዶ በኋላ አትለይብኝ፤ ከተዋሕዶ በኋላ ብቻውን ሰው፥ ብቻውን አምላክ ቃል የሚል ሰው ቢኖር ዐማኑኤልን ሁለት ያደርገዋል።”[5]
የአንጾኪያው ባስልዮስም፣ “አይትከፈል ኀበ ክልኤቱ ህላዌያት እም ድኅረ ተዋሕዶ እስመ ለምንታዌ አእተታ ተዋሕዶ፤ ወተዋሕዶኒ ያግሕሥ ኵነኔሁ ለምንታዌ እስመ ውእቱ ተዋሕዶ አካላዊ ዘኢይትከፈል። - ከተዋሕዶ በኋላ ወደ ሁለት ህላዌያት አይከፈልም፤ ተዋሕዶ መንታነትን አስወግዷልና፤ የመንታነትንም ፍርድ አርቋል። እርሱ የማይከፈል አካላዊ ተዋሕዶ ሆኖአል” ብሏል (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 422)።  
ከእነዚህ ምስክርነቶች ስለ ወልድ ከትስብእትና ከተዋሕዶ በፊት ስለ ነበረው አቋም በአንቀጸ ተከፍሎ ሊነገር እንደሚገባና ከተዋሕዶ ወዲህ ስላለው አቋሙ ደግሞ በአንቀጸ ተዋሕዶ ሊነገር እንደሚገባ እንረዳለን። ምስጢረ ተዋሕዶ የተከናወነው በተለመደውና በሚታወቀው የውሕደት ሕግ ሳይሆን በሕገ ተዐቅቦ ነው። “ተዐቅቦ ማለት በቀላል አገላለጽ መጠበቂያ ማለት ነው። ለምሳሌ መጠበቂያ ያለው ነገር ከተፈለገ፣ ለጊዜው የጠመንጃ ሁኔታ ሊታወስ ይቻላል። ጠመንጃው ጥይት ጐርሶአል እንበል። ነገር ግን በአስፈላጊው ሁኔታና ጊዜ ምላጩ ተስቦ እስኪተኰስበት ድረስ መጠበቂያ ይደረግበታል። መጠበቂያም ስላለው፣ ምላጩን ወይም ቃታውን ሲስቡ፣ ጥይቱ አይተኰስም፤ አይባርቅም። ለዚያውም (ለተኳሹም) ለሌላውም ሰው ጕዳት አያስከትልበትም። መጠበቂያው እንዳይተኰስ ጠብቆታልና። እንግዲህ የመጠበቂያው መኖር በአስፈላጊነቱ መጠን ጠቀመ ማለት ነው።”[6] በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ ሕገ ተዐቅቦ ያስፈለገውም ቃልና ሥጋ እንዲጠባበቁ ለማድረግ ነው። “ተዐቅቦ ተራርቀው ይኖሩ የነበሩትን ባዕል፣ ምሉእና ፍጹም የሆነ አካለ ቃልን እና ድኻ፣ ውሱንና ትሑት የሆነ አዳማዊ ትስብእትን አገናዝቦ የሚገኝ” የምስጢረ ተዋሕዶ መጠበቂያ ነው።
ምስጢረ ተዋሕዶ የተመሠረተው “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ ዐደረ” በሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ላይ ነው (ዮሐ. 1፥14)። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ በጥቅሱ ውስጥ የምናገኛቸው “ኮነ” እና “ኀደረ” (ሆነ እና ዐደረ) የሚሉት ቃላት ተዋሕዶንና ተዐቅቦን በኅብረት ይዘዋቸዋል። አንዱ ለብቻው ተነጥሎ ማለትም “ኮነ” ለብቻው “ኀደረ”ም ለብቻው የተዋሕዶን ምስጢር ለመጠበቅ አያስችሉም። ስለዚህ ኮነ እና ኀደረ በአንድነት ምስጢረ ተዋሕዶን የሚጠብቁ ቍልፍ ቃላት ናቸው ማለት ነው። ቃላቱ ለተዐቅቦ ሕግ የተወሰኑት ሁለቱን ነጣጥለው በመጠቀም የተዋሕዶን ምስጢር ያፋለሱትን የንስጥሮስንና የአውጣኪን የተሳሳተ ትምህርት ለማረም መሆኑን ከሊቃውንቱ ማብራሪያ እንገነዘባለን።
ንስጥሮስ ምስጢረ ተዋሕዶን ለመግለጽ ኮነን ትቶ ኀደረን ነው የወሰደው። ስለዚህ “ ‘በአንዱ ክርስቶስ ሁለት ህላዌያት አሉ’ እስከ ማለት ደረሰና ውስጣዊ መለያየትን (ቡዓዴን) እና መከፋፈልን (ፍልጠትን) በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ አመጣ። ለዚህም የኮነን እውነተኛ ትርጕም ወይም ፍቺ የያዘና ከኀደረ ጋር የሚያገናኝ መጠበቂያ እንዲኖር አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቡዓዴ (ያለመለያየት)፣ ዘእንበለ ፍልጠት (ያለመፈራረቅ/ያለመከፈል)፣ በኢተላፅቆ (ያለመነባበር)’ የሚሉ መጠበቂያዎች፣ የኮነን ምስጢር ይዘው “ኀደረ” ያለውን እንዲጠብቁ ተደረገና የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ። ለዚህ ለንስጥሮስ ንጥል ሐሳብ ተዐቅቦ ባይደረግበት ለተዋሕዶ ትምህርት አደገኛ ይሆናል። የመጻሕፍት አተረጓጐምም ይጥበረበርበታል።”[7]    
ከንስጥሮስ በተቃራኒ አውጣኪም እንዲሁ ምስጢረ ተዋሕዶን የሚያጠፋ ትምህርት አስተማረ። “በአንዱ ክርስቶስ ቱስሕት (መደበላለቅ)፣ ውላጤ (የሰውነት መለወጥ)፣ ሚጠት (መለዋወጥ) እንዳለበት፣ ሰውነቱ ወደ አምላክነቱ እንደ ተለወጠ ተናገረ። አውጣኪ ኀደረን በመተው የኮነን ፍቺ በተሳሳተ አተረጓጐም ተመለከተና ኮነን ‘ተለወጠ’ በሚል ቃል ተርጕሞ ተሳሳተበት። እንደርሱ ዐሳብ ቢሆን የተዋሕዶን ምስጢር ተዋሕዶንም ደመሰሰበት። ለዚህም መጠበቂያ ልጓም አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቱስሕት (ያለመደበላለቅ)፣ ዘእንበለ ውላጤ (ያለመለወጥ)፣ ዘእንበለ ሚጠት ያለመለዋወጥ/ያለመመላለስ)’ የሚሉ ቃላት የኀደረን ምስጢር ይዘው የኮነን ፍቺ ወደ ሌላ እንዳይሄድ፣ ይኸውም በመለወጥ እንዳይተረጐም ይጠብቁ ዘንድ ተደረገ። በዚህም ተዐቅቦ የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ፤ ታወቀ። ይህ ተዐቅቦ ባይኖር የአውጣኪን ግንጥል ዐሳብ ለተከተለ ሰው የተዋሕዶ እምነቱንና በቅዱሳት መጻሕፍት ያለው የአተረጓጐሙን መንገድ ያቃውስበታል።”[8]
በአጠቃላይ ምስጢረ ተዋሕዶን “የምንጠብቀው በእነዚህ ሕጋውያን የውሳኔ ቃላት መጠበቂያዎች /ሕገ ተዐቅቦ/ ነው። ተዋሕዶ ባለበት ሁሉ ተዐቅቦም ዐብሮት ይገኛል።” ስለዚህ በተዐቅቦ በሆነው ተዋሕዶ አንዱ ክርስቶስ ያለመለያየት፣ ያለመፈራረቅ/ ያለመከፈል፣ ያለመነባበር፣ ያለመደበላለቅ፣ ያለመለወጥ፣ ያለመለዋወጥ ወይም ያለመመላለስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑ ከትምህርተ ንስጥሮስና ከትምህርተ አውጣኪ የተለየ የተዋሕዶ ትምህርት ነው።
ምስጢረ ተዐቅቦን በተመለከተ ቄርሎስ፣ “ኢይደልወነ ንፍልጦ ለ፩ዱ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመ ውእቱ ብእሲ በዐቅሙ ወለእመኒ ነአምሮሙ ለ፪ቱ ህላዌያት በዘዘዚኣሆሙ ወነዐቅቦሙ ዘእንበለ ቱስሕት በበይናቲሆሙ ንብል እንከ ፩ዱ ውእቱ ክመ ኢየሱስ ክርስቶስ። - በዐቅሙ እንደ ዕሩቅ ብእሲ አድርገን አንዱን ኢየሱስ ክርስቶስ ልንለየው አይገባንም፤ ሁለቱን ባሕርያት በየገንዘባቸው ብናውቃቸውም ያለመቀላቀል በየራሳቸው ብንጠብቃቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መቸም መች አንድ ነው እንላለን” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 338)።

Tuesday, May 17, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



Part One (www.chorra.net)

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ላይ በዚህ ዐምድ በተከታታይ የወጡትን ጽሑፎች አስመልክተው፣ የተለያዩ አንባብያን የስልክ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ለዝግጅት ክፍሉ አቅርበዋል። ከአንባብያኑ መካከል አንዳንዶቹ የክርስቶስን መካከለኛነት ላለመቀበልና ለሌሎች ቅዱሳን ለመስጠት አለን ያሉትን ማስረጃ በማቅረብ ጭምር ለመከራከር ሞክረዋል። ለክርክራቸው እንዲረዳቸውም፣ “ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም” (2ቆሮ. 5፥16) የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል የጠቀሱ ሲሆን፣ በመጨረሻም፣ “አሁን እርሱ መካከለኛ መሆኑ ቀርቷል፤ አሁን አምላክ ነው” ሲሉ ደምድመዋል። ክርስቶስን ከመካከለኛነቱ ስፍራ አንሥተውም፣ “አሁን መካከለኛው ሥጋ ወደሙ ነው” ሲሉም አክለዋል። ስለ ሥጋ ወደሙ የተባለውን ለቀጣዩ ዕትም እናቈየውና በጥቅሱ ላይ የተላለፈውንና ክርስቶስ አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም የሚለውን አውጣኪያዊ ትምህርት በመመርመር የክርስቶስን መካከለኛነት መጽሐፍ ቅዱስንና የአበውን ምስክርነት በመጥቀስ ወደ ማሳየት እንለፍ።
‘ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ብቻ ነበረ እንጂ አሁን ወደ ክብሩ ከገባ በኋላ መካከለኛ አይደለም’ የሚሉት በትምህርተ ሥጋዌ ላይ በቂ ዕውቀት የሌላቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ተምረዋል የሚባሉትም ጭምር እንደ ሆኑ ይታወቃል። በተለይም የተማሩት ክፍሎች እንዳልተማሩቱ አፋቸውን ሞልተው አሁን አምላክ ብቻ ነው እንጂ ሰውም አይደለም አይሉም፤ ክርስቶስ ዛሬም ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን እናምናለን ይላሉ። ክርስቶስ አሁን በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ ግብረ አምላክን (የአምላክን ሥራ) እንጂ ግብረ ትስብእትን (የሰውነትን ሥራ) አይፈጽምም ስለሚሉ ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእትን ያስተባብላሉ። ለምሳሌ፣ “… ነቢረ የማን (በአብ ቀኝ መቀመጥ) ክርስቶስ ግብረ ትስብእት ከፈጸመ በኋላ እንደ ገና የሰውነትን ሥራ የማይሠራ፥ ነገር ግን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በክብር መለኮታዊ ሥራውን እየሠራ የሚኖር መሆኑን የሚያስረዳ ቃል ነው”[1] ያሉ ይገኛሉ። አባባሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በአብ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ሥራውን ለትስብእት ትቶ ትስብእት ብቻ ይሠራ ነበር፤ ትስብእት ደግሞ አሁን በተራው የሥራ ጊዜውን ስለ ፈጸመ ሥራውን ለመለኮት ተወ ያሰኛል። እንዲህ ከሆነም ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ግብረ ትስብእትን ብቻ እንጂ ግብረ መለኮትን አይፈጽምም ነበር የሚል አንድምታ ያለው ይመስላል። ቅዱሳት መጻሕፍትና በእነርሱ ላይ የተመሠረቱ የአበው ምስክርነቶች ግን የሚነግሩን ከዚህ የተለየ እውነት ነው።

“አንሶሰወ ከመ ሰብእ እንዘ ይገብር ከመ እግዚአብሔር። ርኅበ በፈቃዱ ከመ እጓለ እመ ሕያው ወአጽገቦሙ ለርኁባን ብዙኃን አሕዛብ እም ኅዳጥ ኅብስት ከመ ከሃሊ። ጸምአ ከመ ዘይመውት ወረሰዮ ለማይ ወይነ ከመ ማሕየዌ ኵሉ። ኖመ ከመ ውሉድ ዘሥጋ ነቅሐ ወገሠጾሙ ለነፋሳት ከመ ፈጣሪ። ደክመ ወአዕረፈ ከመ ትሑት ወሖረ ዲበ ማይ ከመ ልዑል። ወኰርዕዎ ርእሶ ከመ ገብር ወአግዐዘነ እም አርዑተ ኀጢአት ከመ እግዚአ ኵሉ።”
ትርጓሜ፥ “እንደ እግዚአብሔር እየሠራ እንደ ሰው ተመላለሰ። ሰው እንደ መሆኑ በፈቃዱ ተራበ፤ ከሃሊ እንደ መሆኑ የተራቡ ብዙ አሕዛብን ከጥቂት እንጀራ አጠገባቸው። የሚሞት እንደ መሆኑ ተጠማ፤ ሁሉን የሚያድን እንደ መሆኑ ውሃውን ወይን አደረገው። እንደ ሥጋ ልጆች ተኛ፤ ፈጣሪ እንደ መሆኑ ነቅቶ ነፋሳትን ገሠጻቸው። ትሑት እንደ መሆኑ ደክሞ ዐረፈ፤ ልዑል እንደ መሆኑ በባሕር ላይ ሄደ። እንደ ተገዢ ራሱን መቱት፤ የሁሉ ጌታ እንደ መሆኑ ከኀጢአት ቀንበር ነጻ አደረገን።”[2]
በዚህ ቃለ ቅዳሴ ውስጥ አንዱ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ይመላለስ በነበረ ጊዜ በሰውነቱ የተከናወነውንና ያከናወነውን ግብረ ትስብእትን፣ በአምላክነቱም የሠራውን ሥራ (ግብረ መለኮትን) በንጽጽር እንመለከታለን።
· መራብ የሰውነት ግብር ነው (ማቴ. 4፥2፤ 21፥18)፤ - በጥቂት እንጀራ ብዙዎችን ማጥገብና ዐሥራ ሁለት መሶብ ተረፍ ማስነሣት ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ዮሐ. 6፥10-13)።
· መጠማት የሰውነት ግብር ነው (ዮሐ. 4፥7፤ 19፥28)፤ - ውሃውን ወደ ወይን መለወጥ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ዮሐ. 2፥7-11)።
· ማንቀላፋት የሰውነት ግብር ነው (ማቴ. 8፥24፤ ሉቃ. 8፥23)፤ - ነፋሱንና ባሕሩን መገሠጽና ጸጥ ማድረግ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ማቴ. 8፥26-27፤ ሉቃ. 8፥24-25)።
· መድከምና ማረፍ ግብረ ትስብእት ነው (ዮሐ. 4፥6)፤ - በባሕር ላይ መሄድ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ማቴ. 14፥25-26)።
· ተኰርዖተ ርእስ (ራስን በዘንግ መመታት) ግብረ ትስብእት ነው (ማቴ. 27፥29-30)። - ሰውን ከኀጢአት ማዳን ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (1ጢሞ. 1፥15፤ ዕብ. 2፥14-15)።
ክርስቶስ አሁን ያለው በክብር እንጂ በዚህ ምድር በነበረበት ሁኔታ አይደለምና በዚህ ምድር በሰውነቱ የተቀበለው ግብረ ትስብእት ማለትም፦ መራብ፣ መጠማት፣ መድከም፣ ማረፍ፣ ማንቀላፋት፣ ወዘተ. አሁን የለበትም። ይሁን እንጂ ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ አንድ ጊዜ በፈጸመውና ለዘላለም በሚያገለግለው የአድኅኖት ሥራው አሁን በክብር ባለበት ሁኔታ፣ በእርሱ በኩል አምነው ለሚመጡትና ከመጡም በኋላ ጠላት የሆነው ሰይጣንና ኀጢአት ለሚከሷቸው ሁሉ ዋስትናቸውና መታረቂያቸው ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለ መሆኑን መካድ አይቻልም። የሚከተሉት መጽሐፍ ቅዱሳውያን ጥቅሶች ይህን ያስረዳሉ፤
· “እግዚአብሔር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነው፥ የሚኰንንስ ማን ነው? የሞተው፥ ይልቁንም ከሙታን የተነሣው፥ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለው፥ ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” (ሮሜ 8፥33-34)።
· “ልጆቼ ሆይ፥ ኀጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኀጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። እርሱም የኀጢአታችን ማስተስረያ ነው፥ ለኀጢአታችንም ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኀጢአት እንጂ” (1ዮሐ. 2፥1-2)።
በክብር የሆነውና ክርስቶስ በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ የሚያከናውነው ግብረ ትስብእት ከሊቀ ካህናትነቱ ጋር የሚያያዝ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያት ያለፈ በድካማችንም ሊራራልን የሚችል ታላቅ ሊቀ ካህናት ነው (ዕብ. 4፥14-15)። “ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኀጢአት መባንና መሥዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ ጌታ ሊቀ ካህናት የሆነው በሰውነቱ ነው (ዕብ. 5፥1)። ስለዚህም በሰማያዊቱ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ የሚከናወነው የሊቀ ካህናትነቱ ተልእኮ ግብረ ትስብእት ነው። እርሱ “በሥጋው ወራት (በዚህ ምድር ሳለ) ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ … ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው” (ዕብ. 5፥7፡9-10)። በዚህ ጥቅስ ውስጥ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በነበረበት ጊዜ ጸሎትንና ምልጃን እንዳቀረበና እንደ ተሰማለትም ተገልጿል። ከዚያ በኋላ ባለው ጊዜ ደግሞ በሊቀ ካህናትነቱ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ አለ።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአድኅኖት ሥራውን ፈጽሞ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጧል (ማር. 16፥19፤ ሐ.ሥ. 2፥33፤ 7፥55-56፤ ሮሜ 8፥34፤ ቈላ. 3፥1፤ ዕብ. 10፥12፤ 1ጴጥ. 3፥22)። በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠውም በዚህ ምድር ሳለ ይፈጽም የነበረውን ግብረ ትስብእትን የማይፈጽም ሆኖ፣ ነገር ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእት እየፈጸመ ነው። የዕብራውያኑ ጸሓፊ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛዪቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት” (ዕብ. 8፥1-2)። ልብ እንበል! በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠው ሊቀ ካህናት፣ በዚያው ሁኔታ በሰማይ ያለችውና በእግዚአብሔር የተተከለችው የእውነተኛዪቱ ድንኳን አገልጋይ ነው። ወደዚያች የገባውም፣ ስለ እኛ ቀዳሚ ሆኖ በእግዚአብሔር ፊት አሁን ይታይልን ዘንድ ነው (ዕብ. 6፥20፤ 9፥24፡28)። ይህም በክብሩ ሆኖ ግብረ ትስብእትን እንደሚፈጽም ያመለክታል።
ከዚህ ቀደም በተከታታይ ለማስገንዘብ እንደ ሞከርነው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ እንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃ (ዮሐ. 17፥9፡20-21) እና አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት (ዕብ. 10፥12፡14) ለዘላለም መካከለኛችን ነው። ይህም ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም በሰማይ ምልጃና መሥዋዕት ያቀርባል ማለት ሳይሆን፣ አንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃና መሥዋዕት ዛሬም አስታራቂያችንና መታረቂያችን እርሱው ብቻ ነው ማለት ነው። ዛሬ አንድ ኀጢአተኛ ሰው የወንጌልን ቃል ሰምቶ፣ በክርስቶስ አዳኝነት ቢያምንና በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ቢጸልይ ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቀውና የኀጢአቱን ስርየት የሚቀበለው፣ ክርስቶስ አንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃና መሥዋዕት (በደሙ) አማካይነት ነው። በክርስቶስ ያመነውና በልዩ ልዩ ምክንያት በኀጢአት የወደቀ ክርስቲያንም ንስሓ ሲገባ ስርየተ ኀጢአትን የሚቀበለው በዚሁ መንገድ ነው። በእርሱ በኩል አምነው ለሚመጡት ለዘላለም የመዳን ምክንያት ሆነላቸው ተብሎ የተነገረውም ስለዚህ ነው (ዕብ. 5፥9-10፤ 7፥25)።
ክርስቶስን አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም፤ ወይም የአምላክነቱ ግብር እንጂ የሰውነቱ ግብር ቀርቷል ማለት ያስፈለገው ታዲያ ለምን ይሆን? ብለን መጠየቅ ይገባናል። የምናገኘው ምላሽም ከሁለቱ ውጪ እንደማይሆን እንገምታለን። የመጀመሪያው ‘ክርስቶስ አሁንም መካከለኛ ነው ካልን የሰውነቱን ግብር መግለጻችን ነውና እርሱን ዝቅ ማድረግ ይሆናል’ ከሚል ሥጋት ነው። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፣ ‘ክርስቶስን አሁንም መካከለኛ ካደረግነው እኛ መካከለኛ ያደረግናቸው ቅዱሳን ምን ሊሆኑ ነው?’ የሚል ይመስላል።

Sunday, May 8, 2016

የፊልም አክተር እንጂ ክርስቶስ አይደለም!!


 በኢትዮጵያ ውስጥ ግን አብዛኞቻችን "የኢየሱስ ክርስቶስ" የመሰለንን ፎቶ በየቤታችን ግድግዳ ለጣጥፈናል። ምንም እንኳን በመለጠፉ ረገድ ኦርቶዶክሳዊያን ቢያይሉም፥ ካቶሊኩም፣ ጴንጠውም፣ ሞርሞኑም፣ ጂሆባውም፣ አድቨንቲስቱም በቃ ሁሉም ለማለት በሚያስደፍረኝ መልኩ በቤቱ ግድግዳ ላይ ወይም የሆነ የሆነ ነገሩ ላይ ለጥፏል። ለምሳሌ በስቲከር መልክ መኪናው ውስጥ፤ ባጃጅ ውስጥ፤ ላፕቶፕ ላይ፤ የሞባይል ስልኩ ላይ እና በመሳሰሉት ላይ ለጥፏል። በነዚህ ሁሉ ባይለጥፍ ደግሞ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓልን በማስመልከት የፌስቡክ ግድግዳው ላይ መለጠፉን አይተውም። ከፎቶውም ግርጌ ከሚጻፉ ጽሑፎች መካከል "ያዳነኝ ይኼ ነው፤ የሞተልኝ ውዴ ይኼ ነው፤ የሕይወቴ ትርጉም ይኼ ነው.. ይኼ ነው.. ይኼ ነው" የሚል ይበዛበታል።

   ለመሆኑ ይኽ የሚለጠፈው ፎቶ አንዳንዶች እንደሚሉት ለሰው ልጆች ኃጢአት የሞተው የኢየሱስ ክርስቶስ ፎቶ ነው? እውነታው ግን አይደለም! የኢየሱስ ክርስቶስ ሳይሆን የጂም ካቪዘል መሆኑ መታወቅ አለበት። በመሠረቱ ወንጌልን ለማስረዳትና ለማስተማር ኢየሱስ ክርስቶስን የሚመስል ሰው ማዘጋጀት ነፍሴ ከማትቀበለው ድርጊት መካከል አንዱ ነው። ምክንያቱም እምነት በጆሮህ ሰምተህ፣ በልብህ አምነህ የምትቀበለው እንጂ በሚመስል ነገር ማረጋገጫ ወይም የበለጠ ስዕላዊ ማሳመኛ ሲቀርብልህ “ለካ እንደዚህ ነው?” ብለህ ተደንቀህ፣ የምትቀበለው የማስታወቂያ ውጤት አይደለም። ፊልም ሠሪዎች ገበያቸው ስለሆነ ግድ ላይሰጣቸው ይችላል። ለኔ ለአማኙ የኢየሱስ አዳኝነት በወንጌል ቃል እንደተጻፈው እውነት መሆኑን አምኜ እቀበለዋለሁ እንጂ በጭራሽ እርሱን ሊወክል በማይችል ሰው ትወና ሳለቅስና አንጀቴን ሲበላኝ የማረጋግጠው የፊልም ጥበብ ለውጥ አይደለሁም። ለዚያ ስዕልና ምስል መንበርከክም አይገባንም የምንለው።

ኢየሱስ ምን መልክ አለው? ደም ግባት የሌለው ሆኖልናል ወይስ የአገልጋይና የባርያን መልክ? የውበቱ ነፀብራቅ የሚያበራ ውብ ነው? ወይስ የሕማም ሰው? እኮ የትኛውን ይመስላል። ደቡባዊ አፍሪካውያን ኢየሱስን ጥቁር አድርገው ይስላሉ። ኢትዮጵያውያንም በሚችሉት አቅም የመሰላቸውን ለመሳል ሞክረዋል። በኢየሱስ ላይ ተሳልቆና ፀያፍ ስድብ የጻፈው ሊኦናርዶ ዳቬንቺ ባቅሙ በምሴተ ሐሙስን የነበረውን ሁኔታ ለማስቀመጥ የሞከረበትን ስዕል በየቤታችንና ቤተመቅደሱ ሰቅለናል። ዳቬንቺ በኢየሱስ ላይ የተናገረው ምንድነው? “The Davenci Code” ያነበበ ሰው ከክፉ ሥራው ተባባሪ ሆኖ ዳቬንቺ የሳለውን ስዕል ይቀበል ነበር?




   አንዳንዴ ሀበሻ እያየ ለምን እንደሚታወር፤ እየሰማ ለምን እንደሚደነቁር ግራ ይገባኛል። ይህንን ሰውየ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በሚባል ፊልም ላይ ስንመለከተው ኖረናል። በዕድሜአችን በሰል ስንል ግን፥ አንድ ተራ አሜሪካዊ ፊልም ሰሪ መሆኑን አለመገንዘባችን እጅግ ያሳዝናል!! በተለይ ደግሞ በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ ዛሬም ድረስ ሰውየው የኢየሱስ ክርስቶስን ቦታ ወስዶ ስዕሉ በየቤቱ በየቤተ መቅደሱ ሰቅሎ ሲሰገድለት፣ ሲሳለመውና ሲስመው ይገኛል። የተለያየ የሃይማኖት ሥርዓቶች በሚከወንባቸው አድባራት በትልቁ ተስሎ መገኘቱም እጅግ አሳዛኝ ነው። ምክንያቱም ለእግዚአብሔር እንጂ ለፊልም ባለ ሙያ ወይም ለሰዓሊ ሙያ ስገድ የሚል ቃል መጽሐፍ ቅዱስ የለም። ነገር ግን በኢየሱስ ሽፋን የሰው ስዕል እየተመለከ ይገኛል።
    እናም ይኽ አብዛኞቹ ሃይማኖተኞች የሚሰግዱለት ግለሰብ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በተሰኘ ፊልም ላይ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ በመላበስ የተወነ አሜሪካዊ የፊልም አክተር ሲሆን፤ ስሙም ጂም ካቪዘል (Jim caviezel) ይባላል። ወይም ደግሞ በሙሉ መጠሪያው ጃምስ ፓትሪክ ካቪዘል ነው። ሃይማኖቱ ደግሞ የሮማ ካቶሊክ ተከታይ ነው። ተወልዶ ያደገው በአሜሪካ ዋሽንግተን ስቴት ውስጥ ሲሆን ወደ ፊልሙ ኢንዱስትሪ ከመግባቱ አስቀድሞ፥ የተማረባቸውን ትምህርት ቤቶች በመወከል የቅርጫት ኳስ ይጫወት ነበር። በዃላ ግን እግሩ ላይ ጉዳት ስለደረሰበት ሙሉ በሙሉ የቅርጫት ኳስ መጫወቱን ትቶ የፊልም አክተር በመሆን እ.አ.አ በ1991 የመጀመሪያ ፊልሙ ላይ በጥሩ ትወና ተሳትፏል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘውን ፊልም ጨምሮ ከሠላሳ በሚበልጡ ፊልሞች ላይ ተውኗል (በመሪነት፣በረዳትነት እና..) የተወሰኑ ፊልሞቹን ርዕሳቸውን እና የተሰሩበትን ዓመት እንደሚከተለው መጥቀስ ይቻላል…

My own private idaho – 1991
Diggstown – 1992
Wyatt erap – 1994
Ed – 1996
The rock – 1996
G.j. jane – 1997
The thin red line – 1998
Ride with the devil – 1999
Pay it forward - 2000
Frequency – 2000
Madison - 2000
Angel)
Person of interest- series drama (up to 2011) እና ሌሎችን ፊልሞች ሰርቷል።

   እንግዲህ እውነቱ ይኽ ነው። "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘው ፊልም ዳይሬክተር የሆነው ሚል ጊብሰን፥ ይህን ግለሰብ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ ተላብሶ እንዲጫወት ያደረገበት ምክንያት፥ ሰውየው ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሆነ ወይም ደግሞ በመልክ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለሚመስለው ሳይሆን፥ አስቀድሞ በሰራቸው ፊልሞች በተለይም "The thin red line" እና "Frequency" በተባሉ ፊልሞች ላይ ባሳየው ጥልቅ የትወና ጥበብ ነው። እውነቱ እንዲህ ሆኖ ሳለ፥ ያገሬ ህዝብ ግን አምላክ አድርጎት ይሰግድለታል። ….እግዚኦ..!!

    በርግጥ በኦርቶዶክስ ሃይማኖት አስተምህሮ መሰረት በየአድባራቱ ብዙ ታሪክ ያዘሉ ቅርጻ ቅርጾች እና ሥዕሎች እንዳሉ ይነገራል.. ይህንንም አስመልክቶ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት SUNDAY, APRIL 25, 2010 "የቤተክርስቲያን ሥዕሎች ታሪካዊ ፋይዳ" በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፉ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"…የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሀገሪቱን (የኢትዮጵያን) ባሕል እና ታሪክ ለትውልድ ካቆየችባቸው መንገዶች አንዱ ሥዕሎቿ ናቸው፡፡ በዚያ ፎቶግራፍ እና ፊልም ባልነበረበት ዘመን የነበረውን ባሕል፣ሥርዓት እና ታሪካዊ ሁነቶች የምናገኘው በቤተ
ክርስቲያን መጻሕፍት እና ግድግዳ ላይ በሚገኙ ሥዕሎች ነው፡፡ ለምሳሌ በሆሎታ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ግድግዳ ላይ የሚገኙት እና ከ100 ዓመታት በላይ ያስቆጠሩት ሥዕላት ለዚህ ምስክር ናቸው፡፡ ከአዲስአበባ 44 ኪሎሜትር በሆሎታ ከተማ የምትገኘው ይህች ቤተክርስቲያን በዐፄ ምኒሊክ አማካኝነት በ1895 ዓ.ም የተገነባች ሲሆን ታቦቷ የገባችው በዚሁ ዓመት የካቲት 16 ቀን ነው፡፡ ሥዕሉን የሳሉት አለቃ ሐዲስ መሆናቸውን ከመቅደሱ ምሥራቃዊ ግድግዳ ላይ ከሣሉት ሥዕል ላይ «ለዛቲ ሥዕል እንተ ሰዓላ አለቃ ሐዲስ እምቤተ ሌዊ፣ ወዘተምህረ በጎንደር» በሚለው ማስታወሻቸው ይታወቃል፡፡
  ሰዓሊው የቤተክህነቱን እና የቤተመንግሥቱን ወግ እና ሥርዓት በሚገባ የሚያውቁ መሆናቸው በአሣሣላቸው ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ ወለተ ሄሮድያዳን ሲሥሏት አለባበሷን እና የፀጉር አቆራረጧን ኢትዮጵያዊ አድርገውታል፡፡ ሹሩባ ተሠርታለች፣ነጭ ሻሽ አሥራለች፣ አሸንክታብ ሠትራ እስክስታውን ታስነካዋለች፡፡ የሄሮድስን የቤተ መንግሥት ሥርዓት ሲስሉት በምኒሊክ ቤተመንግሥት ሥርዓት ነው። ቢላዋው፣የእንጀራው አጣጣል፣ ሙዳ ሥጋው የዘመኑን የግብር ሥርዓት በሚገባ ነው የሚያሳየው፡፡"
   አንባቢ ሆይ ልብ በል፥ እንደ ዳንኤል ክብረት ገለጻ ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ውሰጥ የምናውቃት ሄሮድያዳ ኢትዮጵያዊ መስላ ስትሳል ምናልባት ሰዓሊው በነበረበት ዘመን የኢትዮጵያ ሴቶች ምን እንደሚመስሉ ሊገልጽ ይችል ይሆናል። ነገር ግን የመጽሐፍ ቅዱሷ ሄሮድያዳን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ታሪክ ያበላሸዋል። ሲቀጥል ደግሞ የምኒልክን ቤተ መንግሥት ለማሳየት የሄሮድስን ቤተ መንግሥት ማረሳሳት ተገቢ አይሆንም። እንግዲህ በየአድባራቱ ታሪክ አዝለዋል የሚባሉ ሥዕሎች ሁሉም እንደዚህ ዓይነት ከሆኑ መሆናቸው ለማወቅ ፈላስፋ ወይም የነገረ መለኮት ምሁር መሆንን አይጠይቅም። በአንድ ዘመን የተከናወነውን መንፈሳዊ ድርጊት ለማስታወስ ወይም ሃሳባዊ እይታን ለማሳየት ተብሎ የሚሳለው ስዕል የእውነታው ነፀብራቅ እንደሆነ አድርጎ በመሳል ለስዕሉ መስገድ፣ መንበርከክና መማፀን ኢክርስቲያናዊ አምልኮ ነው። ያሳፍራል.። ያሳዝናልም!!
ሲጠቃለል ስዕል ለአንክሮ፣ ለተዘክሮና ለማስተማሪያነት ከሚያገለግል በስተቀር በየቤተ መቅደሱ ተሰቅሎ አይታጠንም፣ አይሰገድለትም። መንበርከክና ከፊት አቁሞ መማፀን የወንጌል አስተምህሮ አይደለም። አንዳንዶች ለጥፋታቸው መሸፈኛ “የኪሩብ ምስል በታቦቱ ላይ ነበር” ይላሉ። የኪሩቡን ምስል ማን አዘዘ? ከምን ይቀረፅ፣ ስንትስ ነበረ? ለማን በተሰጠ ኪዳን ላይ ታዘዘ? በቂ መልስ የላቸውም። የዛሬውን ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ጋር ለማገናኘት መሞከር ሰማይና ምድር ለማጣበቅ እንደመሞከር ይቆጠራል። እግዚአብሔር አእምሮውን ለብዎውን ያሳድርብን።

   

Friday, April 29, 2016

«በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር…»!

የራስ ቅል ኮረብታ በ19ኛው ክ/ዘመን 

የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?» ገላ 3፤1
ኢየሱስ ክርስቶስ በየዓመቱ የሚከበርለትን የመታሰቢያ ትንሣኤ ሊመሠርት እንዳልመጣ እሙን ነው። የከበረ እንጂ የሚከብር፤ የሚፈጸም እንጂ የሚታሰብ ትንሣኤ ትቶልን አልሄደም። እንደዚያማ ከሆነ ከሕግ አገልግሎት ገና አልወጣንም ማለት ነው። ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች እንደዚህ ያላቸው።

 «የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?»ብሎ ይጠይቃቸዋል።
 እውነት ነው፣ የኢየሱስ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ዕለት፤ ዕለት በዓይናችን ፊት እንደተሰቀለ ሆኖ የሚታይ እንጂ በማስታወሻ መልክ በየዓመቱ «ዬ፤ዬ፤ዬ» እያልን የምናስበው የአንድ ሳምንት አጀንዳ አይደለም። የኦሪት ሕግ በዓላት በተወሰነላቸው ቀናት በየዓመቱ ይከበራሉ። ከዚያን ቀን ውጪ የሕጉ በዓላት በሰው ሕይወት ላይ የተደነገገላቸውን ኃይል ሊፈጽሙ ሥልጣን የላቸውም። አይሁድ ፋሲካቸውን  ከግብጽ ምድር የወጡበትን ዕለት በማሰብ በየዓመቱ ለአንድ ሳምንት በወርኀ ሚያዚያ ያከብራሉ። ያልቦካና እርሾ ያልገባበትን ኅብስት የሚመገቡት በፋሲካ ሳምንት ብቻ ነው። ከዚያ በኋላ የፋሲካው የሕግ ሥልጣን ስለሚያበቃ ወደቀደመው አመጋገብና መደበኛ ኑሮ ይመለሳሉ። የክርስቲያኖች ፋሲካ ግን በአማኞች ሕይወት ላይ ያለምንም የብልጫ ቀናት ልዩነት በእምነት የሚፈጸምና ዓመቱን ሙሉ ኃይልና ሥልጣን ያለው አገልግሎት ነው። እንደገላትያ ክርስቲያኖች ወደ ሕግ ሥርዓት ተመልሰን በዓመት የምናስበውና የምንዘክረው እንዲሁም ከጥሉላት በስተቀር ሌላውን ገድፈንና የገደፍነውን መልሰን የምንረከብበት፣ እስከሆድ ድረስ የምግብ ዓይነት ነጻነታችንን የምናስከብርበት ዘመቻ ምግብ ፋሲካ አልተሰጠንም።  ፋሲካችን «እንኳን አደረሰህና እንኳን አደረሰሽ» በመባባል ያልደረስንበት የድነት ቀን ያለ ይመስል የሚታወስ የአንድ ሳምንት የስጦታ ካርድ መለዋወጫ በዓል በላይ የላቀ ሰማያዊ ነው።
ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳለው: «በመንፈስ ብትመሩ ግን ከሕግ በታች አይደላችሁም። የሥጋ ሥራም የተገለጠ ነው እርሱም ዝሙት፥ ርኵሰት፥ መዳራት፥ ጣዖትን ማምለክ፥ ምዋርት፥ ጥል፥ ክርክር፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥ መለያየት፥ መናፍቅነት፤ ምቀኝነት፥ መግደል፥ ስካር፥ ዘፋኝነት፥ ይህንም የሚመስል ነው። አስቀድሜም እንዳልሁ፥ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም"

«ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአል» ስንል እነዚህን የሥጋ ሥራዎች ሁሉ ከሕይወታችን አስወግደን በመንፈሱ ሥልጣን እየተመራን ነው ማለታችን ነው። እነዚህን ደግሞ የምናስወግደው በየዓመቱ በሚከበር ፋሲካ ሳይሆን ዕለት፤ ዕለት የኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ በፊታችን ተስሎ ሲገኝ ብቻ ነው። አለበለዚያ ከገላትያ ሰዎች የበዓል አከባበር አስተሳሰብ ገና አልወጣንም ማለት ነው። የገላትያ ሰዎች «አባ፤ አባት» ብሎ ለመጣራት የሚያበቃ የተሰጣቸውን የልጅነት ሥልጣን ትተው በባርነት ቀንበር ሥር ወደምትጥል ወደወር፤ ቀንና ዘመንን የማክበር ቁልቁለት ወርደው በተገኙ ጊዜ የተናገራቸው ቃል በዚህ ዘመንም ቦታ አግኝቶ መታየቱ ምን ዓይነት አዚም ቢወድቅብን የሚያሰኝ ነው።

«ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ። ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለሁ ብዬ እፈራችኋለሁ» ገላ 4፤ 1-11

ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን ፍለጋ የት መሄድ ይገባናል? የእግዚአብሔር መገኛው የት ይሆን? ከምድራዊት ቤተ መቅደስ? ከገሪዛን፤ ከጌባል? ወይስ በኢየሩሳሌም?
 አንዳንዶች ኢየሩሳሌምን የተሳለመ የ40 ቀን ሕጻን ይሆናል ይላሉ። የቆረበ ደግሞ የበለጠ የ40 ቀን ሕጻን እንደሚሆንም ይሰበካል። ከተሳለመ የ40 ቀን ሕጻን በመሆንና ከቆረበ የ40 ቀን ሕጻን በመሆን መካከል ያለው ልዩነት አይገባኝም።  ኢትዮጵያ በመቁረብና ኢየሩሳሌም ከጎልጎታ ሄዶ በመቁረብ መካከልስ ያለው ልዩነት ምንድነው?  ሰዎች ክርስትናን እንደሕግ ሥርዓት ማክበር ሲጀምሩ የሕግ የብልጫ ልዩነት ክርስትናውን መውረስ ይጀምረዋል። ኢየሩሳሌም ሄዶ በመሳለም ወይም በመቁረብና ኢትዮጵያ በመቁረብ መካከል ልዩነት የሚመጣውም ለዚህ ነው። መቱ ባለች ቤተ ክርስቲያን ጓሮ በመቀበርና ደብረ ሊባኖስ በመቀበር መካከል ያለው የመብት ልዩነትም ውጤቱ የሕግ ተፋልሶ ክርስትናውን በመዋጡ የመጣ ነው። የወንጌል እውነት ግን ያንን እንድል አይነግረንም። እግዚአብሔር መንፈስ እንጂ በቦታና በሥፍራ የሚወሰን አምላክ አይደለም። ስለዚህም እግዚአብሔር በመንፈስ ይመለካል፤ በእምነትም፤ የመንፈስ  የሆነ ሥራ በሕይወታችን ላይ ሊገለጥ ይገባዋል። ያኔ ዲላ ሚካኤል ተቀበርን፤ ደብረ ሊባኖስ፤ ደሴ ቆረብን ሞቻ በማንነታችን ላይ ለውጥ የለውም። በሕይወቱ የክርስትና ማንነት የሌለው ሰው ደብረ ሊባኖስ ጓሮ መቀበሩ በፍርድ ወንበር ፊት ለውጥ አያመጣለትም። ሰው ሲሞት ይዞት የሚሄደው በምድር የነበረውን ሥራ እንጂ በሰማይ የሚፈጸም የክርክር ዳኝነት የለም። «እስመ አንተ ትፈድዮ ለኩሉ በከመ ምግባሩ» እንዳለ ዳዊት በመዝሙር 62፤12
ስለዚህ እግዚአብሔር በመንፈስ ይመለካል፤ በመንፈስ ይሰገድለታል፤ በመንፈስ ይታመናል እንጂ በቦታና በሥፍራ አይደለም። እሱን ይይዝ ዘንድ የሚችል ምድራዊ መቅደስ የለንም። «ለእኔ ምን ዓይነት ቤት ትሠራላችሁ? ይላል ጌታ» የሐዋ 7፤50

«ወትቤሎ፤ አበዊነሰ በዝንቱ ደብር ሰገዱ፤ ወአንትሙሰ ትብሉ ከመ በኢየሩሳሌም መካን ውእቱ ኀበ ይሰግዱ። ወይቤላ ኢየሱስ፤ እመንኒ ብእሲቶ ከመ ትመጽእ ሰዓት አመ ኢበዝንቱ ደብር፤ ወኢበኢየሩሳሌም ዘይሰግዱ ለአብ፤ አንትሙሰ ትሰግዱ ለዘኢታአምሩ፤ ወንሕንሰ ንሰግድ ለዘናአምር፤ እስመ መድኃኒት እምነ አይሁድ ውእቱ። ወባሕቱ ትመጽእ ሰዓት፤ ወይእዜ ይእቲ፤ እመ እለ በርቱዕ በአማን ሰጋድያን፤ ይሰግዱ ለአብ በመንፈስ ወበጽድቅ እስመ አብኒ ዘከመዝ የኀሥሥ እለ ይሰግዱ ሎቱ። እስመ እግዚአብሔር መንፈስ ውእቱ፤ እለሂ ይሰግዱ ሎቱ በመንፈስ ወበጽድቅ ሀለዎሙ ይሰግዱ ሎቱ»

ትርጉም፤ 
«አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው ትላላችሁ አለችው። ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል። እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን። ነገር ግን በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል፤ አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል» ዮሐ 4፤20-24

የኢየሱስ ስቅለት የሚታሰበው በመንፈስ መሆኑን ለማመልከት ጳውሎስ ለገላትያ  ሰዎች እንዲህ አላቸው። ኢየሱስ የተሰቀለው ኢየሩሳሌም እንጂ ገላትያ አለመሆኑን እያወቀ ለገላትያ ሰዎች ግን «በዓይናችሁ ፊት እንደተሰቀለ ሆኖ ተስሎ ነበር» እያለ ይወቅሳቸዋል። ምክንያቱም ስቅለቱ በአማኞች ፊት የሚታየው በየዓመቱ ለሁለት ወር በሚደረግ ጾምና ለአንድ ሳምንት በሚታሰብ  የሕማማት ሳምንት ሳይሆን በየትኛውም ቦታ ብንሆን ያለምንም ዕረፍት በዘመናችን ሙሉ ነውና።
 የሕማማቱ ሳምንት ካለፈ በኋላስ? በዓለ ፍስሐ ወሀሴት፤ በዓለ ድግስ ወግብዣ፤ በዓለ ምግብ ወመጠጥ ነው? የኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ ለሁለት ወር ከምግብ የመከልከል ማዕቀብና ለሁለት ወር ተከልክለው የነበሩ ምግቦች በተራቸው ድል የሚቀዳጁበት በዓል አይደለም። ዓመቱን ሙሉ በፊታችን እንደተሰቀለ ሆኖ የምናስብበት፤ በመንፈስና በእውነት የምንሰግድለት ቋሚ የሕይወታችን መርህ እንጂ በአርብ ቀን የወይራ ጥብጣብ የሚያበቃ ዓመታዊ ልምምድ ካደረግነው ከገላትያ ሰዎች በምን እንሻላለን? 

ለዚህም ነው፤ ብዙ ክርስቲያኖች ከነገሠባቸው የሥጋ ሥራ ሳይላቀቁ ፋሲካን እያከበሩ ዘመናቸውን ሁሉ የሚፈጽሙት። ጋብ ብሎ የነበረው የሥጋ ሥራ ከፋሲካ በዓል በኋላ ይደራል። ዝሙቱ፤ ውሸቱ፤ ስርቆቱ፤ ማጭበርበሩ፤ ሃሜትና ነቀፋው ያለማንነት ለውጥ እንደነበረው ይቀጥላል። ዓመቱን ሙሉ ያጠራቅሙትን ኃጢአት የፋሲካ ጾም ሲመጣ ለማራገፍ እንደሚቻልበት አመቺ ጊዜ ጠብቀው ብዙ ሰዎች ጥሬና ቆሎ ቋጥረው በየዋሻውና ፍርክታው ልክ እንደሽኮኮ ይመሽጋሉ። ሀብት ያላቸው ኢየሩሳሌም ሄደው ለመሳምና ለመቁረብ ገንዘባቸውን በየዓመቱ ይከሰክሳሉ። የክፉ ቃል ምንጭ የሆነውን አንደበቱን ሳይዘጋ ሥጋ መሸጫ ቤቱን የሚዘጋ የት የለሌ ነው። ከተማውን ሁሉ የወረረው የሚዛን መሥፈሪያ በፈሪሃ እግዚአብሔርና ያለማጭበርበር ሳይሰሩበት ጾም የሚሉትን ፈሊጥ የሚጠብቁት ለምንድነው?   አቤት! የዘንድሮ ሚዛን የሚባለው የድሮና የዚህ ዘመን ሚዛን ልኬታ የተለየ ሆኖ ይሆን?

የሕዝብና የመንግሥት ሀብት የሚዘርፉ የሕግ ፋሲከኞች ቁጥራቸው ብዙ ነው። የቤተ ክርስቲያን ደወል ሲደወል የሚከንፉ ነገር ግን የቤታቸውን የፍቅርና የሰላም ደወል የተነጠቁ ቤቱ ይቁጥራቸው። ሠራተኞቻቸውን የሚያስጨንቁ፤ በፍትህ አደባባይ ፍርድን የሚጨፈልቁ፤ በመማለጃም የእንባን ዋንጫ የሚጎነጩ የሁለት ወር ጸዋሚዎችና ተሃ ራሚዎች አያሌ ናቸው። የልምድ ክርስቲያኖች የሕይወት ምስክርነት በሥራቸው ሊታይባቸው አይችልም።  ስለዚህም ይመስለኛል፤ በክርስቲያን ቁጥር ብዙ ሆነን በበረከት መትረፍረፍ አቅቶን እድሜ ልካችንን ከእምነት የለሾች ምጽዋት ጠባቂ ሆነን የቀረነው። እንደእምነት የለሾቹ፤ እምነት የለሾች ብንሆን ያለእምነት ስለሚፈረድብን በሥጋ ረሃብ ባልተገፋንም ነበር። እግዚአብሔርን እየጠራን፤ እንደፈቃዱ ለመኖር ባለመቻላችን በራሳችን የእምነት ጉድለት በሥጋችን እንቀጣለን።  ብዙ ባወቅህ ቁጥር ብዙ ሥራ ይጠበቅብሃል። ካልሰራኸው ግን ባታውቅ ቢቀርብህ ይሻልህ ነበር። ስለዚህ ማወቅህ ለመዳንህ ዋስትና የሆነውን ነገር ካላትርፈረፈልህ ክርስትናህ ምንድነው? ኢየሱስ በባዶ ተስፋ አልተወንም። እኛ ግን አስሮ በያዘን በገላትያውያን አዚም ፈዘን ሳለ ስለገላትያ አዚም እናስተምራለን።

  የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለትና ትንሣኤ በየዓመቱ እየዞረ የሚመጣ በዓል ሳይሆን ዕለት፤ ዕለት በፊታችን ተስሎ የሚታየን የሕይወታችን አካል ነው መሆን ያለበት። በቦታ፤ በሥፍራና በጉዞ ብዛት የሚከበር ሳይሆን በእውነትና በመንፈስ እንድናመልከው የተደረገልን የማዳን ሥራ ነው። በአዲስ ሰውነት ለውጥ እንጂ በሕግ ሥነ ሥርዓት ልናሳልፈው አይገባም።  ሰላምና እርጋታ በውስጡ መኖሩን መንፈስ ቅዱስ የሚመሰክርለት አማኝ ሀገር ለሀገር፤ ተራራ ለተራራ ትንሣኤውን ፍለጋ ሲዞር አይገኝም። ምክንያቱም፤ ሁል ጊዜ በዓይኑ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ይታየዋልና»! ከተያዝንበት አዚም ተላቀን በልባችን የተሳለውን ትንሣኤ፤ በኑሮአችን ፍሬ የሚታይበት እንዲሆን እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን።

Sunday, April 24, 2016

ትንሣኤ አንድ ነው፣ ሕይወትም እሱ ነው!



ቀልጣፋ ሬስቶራንቶች በቀላሉ የሚስቡን የፈለግነውን ምግብ በምንወደው መንገድ እንድናዝ መንገድ ስለሚከፍቱልን ነው። ጥቂት ካፌዎች ደግሞ ከመቶ በላይ የተለያዩ የቡና ጣዕም እንደሚያቀርቡ በጉራ ይናገራሉ። መኖሪያ ቤቶችና መኪናዎችን ስንገዛ እንኳ የምንፈልገው ምርጫ እንዲያሟላ እንሻለን። በቼኮላት፣ በቫኒላና በእንጆሪ ዓለም ታጥረን መኖር አንፈልግም። ፍላጎት ንጉሥ ነው! እንደግላዊ ፍላጎትህና ምርጫህ የምታገኝበት ሁሉ የተሟላበት ዘመን ነው። የዓይን አምሮትና ፍላጎትን የሚያሟላው ዓለም የእምነት መንገድንም ለዘላለማዊ ሕይወት ይበጃል ያለውን በአማራጭ አቅርቧል።

ታዲያ ለአንተ /ለአንቺ/ ትክክለኛ እምነት የማግኘቱ ሁኔታስ ምን ይመስላል?

ወቀሳ አልባ፣ ብዙ ጫና የሌለውና ይህንን አድርግ አታድርግ እያለ የማያስቸግር ሐይማኖት ብታገኝስ? ቀደም ብዬ እንደገለፅኩት ያውና እዚያ አለ እንደሚሉት ነገር፣ ሃይማኖት እንደሚወዱት አይስክሬም የሚመረጥ ነው እንዴ?
እድሜው፣ ሥርዓቱና ደንቡ ስለሚስብህ ይሆን? ወይስ በባለብዙ መንገድ የሕይወትህ ቤዛ ቃል ስለተገባልህ በአንዱ ላይ ተስፋህን ለማኖር?

ትኩረታችንን ለመሳብ የሚሻሙ በርካታ ድምፆች ስላሉ ለምን? ብሎ ነው አንድ ሰው ኢየሱስን ከሌሎች ማለትም ከመሐመድ ወይም ከኮንፊሸየስ፣ ከቡድሐ ወይም ቻርለስ ቴዝ ራስል ወይም ከጆሴፍ እስሚዝ አስበልጦ የሚመርጠው? ዞሮ ዞሮ ሁሉም መንገዶች የሚያደርሱት ወደ መንግስተ ሰማይ አይደለም እንዴ?

 “በኢየሱስ እናምናለን” የሚሉቱ ራሳቸው የማዳኑን ተስፋ የሚገልጡበት መንገድ የተለያየ ስለሆነ እንደገበያ ላይ ሸቀጥ ገብተን ድነትን የምንሸምትባቸው አይደሉም።
 በመሰረቱ ሁሉም ሃይማኖቶች አንድ አይደሉምና። እንደ እውነቱ ከሆነ ሁሉም ሃይማኖቶች ወደ መንግስተ ሰማይ አያመሩም። ሁሉም መንገዶች ወደ ኢንዲያና መቼም አያደርሱም። የእምነት ድርጅቶች ሳይሆኑ ወደመንግሥቱ የሚያስገባው ላመኑበት ሁሉ “ኢየሱስ ብቻ ነው” የምንለው ማለት ስለፈለግን ሳይሆን እንድንል የሚያስገድደን እውነት ያለው በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ስለተፈፀመ ነው።

ኢየሱስ ብቻውን በእግዚአብሔር ሥልጣን ይናገራል።

1/ ምክንያቱም ኢየሱስ ብቻ ነው ሞትን ያሸነፈው። እስካሁን ድረስ መሐመድ፣ ኮንፊሸየስና ሌሎች በመቃብር በስብሰው ይገኛሉ። ነገር ግን ኢየሱስ በራሱ ስልጣን በጨካኙ የሮማውያን መስቀል ከሞተና ከተቀበረ ከሦስት ቀን በኋለ መቃብሩን ፈንቅሎ ተነስቶአል። በሞት ላይ ስልጣን ያለው ማንኛውም ሰው ትኩረታችን ሊስብ ግድ ይላል። ማንም በሞት ላይ ስልጣን ያለው ግለሰብ ሲናገር ልናደምጠው አስፈላጊ ነው። ሞትን ማሸነፍ የቻለ ከፍጥረታት መካከል ማንም የለም። ከሰማይ የመጣው ብቻ ሞትን አሸንፎ ወደሰማይ ወጥቷል።ስለዚህ እንዲህ ያለው አሸናፊ የተናገረው የእምነት መሠረት መሆን አለበት። ሰው ሟች መሆኑን ያውቃል። ሟች ደግሞ ከሞት ለማምለጥ የሚችለው በሞት ላይ ባለሙሉ ሥልጣን በሆነ ክንድ ላይ ሲያርፍ ነውና ኢየሱስን ማመን የግድ ይለዋል። በሞት ላይ ሥልጣን ያለው፣ ለሞታችን ብቸኛ ዋስትና የመሆን ብቃት አለው። ሌላ መንገድ፣ ሌላ ቃል ኪዳን፣ ሌላ አዳኝ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ማንም የለም። ይህንን እውነት ያለምንም ድርድር ማወጅ ያልቻለ እምነት፣ ምድራዊ የሃይማኖት ድርጅት እንጂ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ምስክር አይደለም።

2/ የኢየሱስ ሕይወትና ትንሣዔ ምስክር ያለውና እውነት ነው።
የኢየሱስን ትንሣዔ የሚደግፈው መረጃ የሚያጥለቀልቅ ነው። ሮማውያንና ሰቃልያኑ ካህናት የኢየሱስን መቃብር ማስጠበቅ ያስፈለጋቸው «በሦስተኛው ቀን እነሳለሁ» ያለውን ቃሉን ይዘው እንጂ የሞተ ሰው መቃብር ስለሚጠበቅ አልነበረም። አዎ ትንሣኤውን ለመከላከል ወታደሮች ከመቃብሩ ማንም እንዳይወጣ፤ ወደመቃብሩም ማንም እንዳይደርስ አድርገው አስጠብቀው ነበር። ነገር ግን የመቃብሩ ቦታ ባዶ ሆኗል! እንደተናገረው አልተነሳም እንዳይሉ የኢየሱስ ጠላቶች ያን ሁሉ ስለትንሣኤው የተነዛውን ወሬ ለማክሸፍ የበሰበሰውን አካሉን በማቅረብ በቀላሉ ያስታግሱት ነበር። ግን አልቻሉም፤ መላው ሲጠፋባቸው ደቀመዛሙርቱ ሬሳውን ሰርቀውት ይሆን? አሉ። ከሐዋርያቱ መካከል ከዮሐንስ በስተቀር ሌሎቹ የሸሹት በጊዜ ነው። የሸሹ ሰዎች ተመልሰው ከሮማ ወታደሮች ጋር ተዋግተው ሰረቁት ማለት የማይመስል ነገር ነው። የመቃብሩ ባዶ መሆን ሳያንስ ሞቶ የተቀበረ ሰው ዳግም ተነስቶ በሰዎች ፊት ራሱን በመግለጥ ያረጋገጠ በታሪክ ማንም የለም። ኢየሱስ ብቻ ይህን ማድረግ ችሏል።
ትንሣዔውን ያለምስክር ያልተወ ኢየሱስ ግን በአንድና በሁለት ሰዎች ፊት ብቻ ሳይሆን በአምስት መቶ ሰዎች ፊት ትንሣዔውን አስመስክሯል።

«መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ፥ለኬፋም ታየ በኋላም ለአሥራ ሁለቱ፤ ከዚያም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታየ፤ ከእነርሱም የሚበዙቱ እስከ አሁን አሉ አንዳንዶች ግን አንቀላፍተዋል፤ከዚያም በኋላ ለያዕቆብ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ ታየ፤ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ» 1ኛ ቆሮ 15፤4-8

ስለዚህ ሰዎች ኢየሱስን ለማመን የሚያስችላቸው በቂ የእምነት ማስረጃ ስላላቸው ነው። በዚህ ምድር ላይ ካሉ ሃይማኖቶች ውስጥ እንደኢየሱስ ሞትን ያሸነፈ፤ ትንሣኤውን በምስክር ያረጋገጠ ማንም የለም። ስለዚህ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው ማንም ሰው ሊደመጥ ይገባል። ኢየሱስ በሞት ላይ ያለውን ሥልጣን አረጋግጧል። ስለዚህ የሚናገረውን መስማት ይገባናል። ለድነት ብቸኛው መንገድ ኢየሱስ መሆኑን ራሱ ይናገራል።(ዮሐንስ 14፡ 6)። ኢየሱስ ክርስቶስ ካሉትም ብዙ መንገዶች አንዱ አይደለም። ኢየሱስ ብቸኛ የድነት መንገድ ነው። ሌላ መንገድ ሁሉ በትንሣኤና በሕይወት ላይ ሥልጣን የሌለው የሞት መንገድ ነው። በሞትና በትንሣኤ ላይ ሥልጣን በሌለው ማንኛውም የመዳን ተስፋ ቃል ላይ አትታመኑ። እውነት የምትመስል ነገር ግን የጥፋት መንገድ ናት። “በዚህና በዚያም ትድናላችሁ” የሚሉ ድምጾች መጨረሻቸው ሞት ነው። ሟች ለሟች የተስፋ መንገድ መሆን አይችልም።

3/ ኢየሱስ ከሸክም ያሳርፋል።

በዚህ ምድር ላይ ከሸክም አሳርፋችኋለሁ ብሎ ቃል የገባ አንድም ሥጋ ለባሽ የለም። ይህ ብቸኛ ኢየሱስ እንዲህ ይላል “እናንተ ደካሞች፤ ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፣ ወደእኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” (ማቴዎስ 11፡ 28)። ሕይወትም አስቸጋሪ ነው። ብዙዎቻችን ደምተናል፣ ቆስለናል፣ ጦርነትንም እንፈራለን። ዓለምም አስጨናቂ እየሆነች ነው። ስለዚህ የሚያሳርፈንን ብንፈልግ ተገቢ ነው። ነገር ግን ከኢየሱስ በቀር ሸክም የከበዳችሁ ወደእኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ ያለ ማንም ሌላ የለም። በትንሣኤውና በሕይወቱ የታመነ ኢየሱስ ይህንን የማለት ብቃት ስላለው በእርሱ ላይ ማረፍ ከአስጨናቂው ዓለም ለመዳናችን ዋስትናችን ነው። ከድካማችሁ በማያሳርፉ በማንም ላይ አትታመኑ። ትድኑበት ዘንድ ብቸኛው ቃል ኪዳን ኢየሱስ ለመሆኑ “ወደእኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ” የሚል ቃል ነግሮናልና ነው። በዚህ ተራራ ወይም በዚያ ሸለቆ የሚያሳርፍ ቃል የለም። ቃል፣ ቀራንዮ ላይ ስለእኛ አንድ ጊዜ ተሰጥቷል። በሞቱ ሞታችንን ሽሮ፣ በትንሣኤው ሕይወት በሰጠን በክርስቶስ ኢየሱስ ላይ ብቻ እንድንታመን የሚያስፈልገን የሚያስተማምን ምስክርነት ስለተወልን ነው።
ስለዚህ ምን ትፈልጋላችሁ? ከኃጢአት፤ ከድካም፤ ከተስፋ መቁረጥ በንስሐ መታደስ ወይስ የአንዱ ሃይማኖት አባል በመሆን ብቻ መኖር? ሕያው የሆነ አዳኝ ወይስ “ከሞቱት በርካታ ነቢያት ወይም ጻድቅ” አንዱን ተስፋ ማድረግ? ትርጉም ያለው ግንኙነት ወይስ ተራ የአምልኮ ሥነ-ሥርዓት መከተል?

4/ ኢየሱስ አማራጭ ሳይሆን ምርጫ ነው!

ሃይማኖት ማለት አንድ መንፈሳዊ ድርጅት ወይም የአንዱ ተቋም ስያሜና የዚያ አባል ሆኖ መኖር ማለት አይደለም። ከእግዚአብሔር አብ ጋር ትርጉም ያለው ግንኙነት ትፈልግ እንደሆን ሃይማኖትህ ኢየሱስን ማመን ነው። «በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው» ይላል መጽሐፍ። (ዮሐንስ 3፡ 36) አንዳንዶች ይህንንማ እናምናለን ነገር ግን ትክክለኛው እምነት ያለው በኛ ሃይማኖት ውስጥ ስለሆነ አባል ሁነን ይላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ፣ በማኅበር ስለመጸለይ ይነግረናል እንጂ ኢየሱስን ለማመን የዚህ ወይም የዚያ ሃይማኖት ተቋም አባል የመሆን ትዕዛዝ የለውም። ኢየሱስ በሱ የሚያምኑ ሁሉ እንዲድኑ እንጂ የሃይማኖት ድርጅት ሊመሠረት አልመጣም። ለጸሎት በኅብረት መሆን ቢያስፈልግ መጀመሪያውም መጨረሻውም የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ብቻ የሚከብርበት እንጂ ሰው፣ ሰው የሚሸትበት፣ ብቃትና የሰዎች ማንነት የሚደሰኮርበት ከሆነ ድርጅትን ማምለክ ይሆናል። በዚህ ዘመን ብዙዎች ተሰነካክለዋል።
 በራሱ ሥልጣን ከሙታን የተነሳ ማን አለ? ወይም በዓለም ላይ ካሉ የተለያዩ የሃይማኖት ድርጅቶች መካከል ለሰው ልጆች ዘላለማዊ የሕይወት ተስፋ ለመስጠት አስተማማኝ ማን አለ? መሐመድ፣ ኮንፊሽየስ፣ ራስል፣ ስሚዝ፣ ሉተር፣ ካቶሊክ፣ ኦርቶዶክስ፣ ፕሮቴስታንት ወዘተ ማንም ቢሆን ይህን ማድረግ አይችሉም።
እምነት ከሞት በላይ በሆነ በትንሣኤው ምስክርነት ላይ ይታመናል። ሕይወት ከድርጅት ሥልጣንም ባለፈ ብቸኛ የድነት መንገድ በሆነው ኢየሱስ ላይ ይጸናል።

“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው” ዮሐ 6:47 ያለን ኢየሱስ ብቻ ነው።

Friday, April 22, 2016

የከፍያለው ቱፋ ጥፋቱ "ኢየሱስ፣ ኢየሱስ"ማለቱ!!



 ከፍያለው ቱፋ ወጣት መንፈሳዊ ተማሪና ሰባኪ ነበር። በዚህ ለጋ እድሜው ከስሞች ሁሉ በላይ ስም የሆነውን "ኢየሱስ ክርስቶስን" ከአፉ አይለይም።  በእርግጥም ያንን ማለት እንደጥፋት ከተቆጠረ ለጉባዔ ቀርቦ ቢቻል እውነቱን ነግሮ ወደሚፈለገው እውነት እንዲመለስ ማድረግ አለያም እኔ የያዝኩት እውነት ሌላ መልክ የለውም ካለም የራሱን ምርጫ አድርጎ ማሰናበት ሲቻል በበለው በለው ዘመቻ አስፈንጥሮ ማስወጣት አሳዛኝ ነው።  ከታች የቀረበው ጽሑፍ የሚያስረዳን ነገር በየቦታው የተደራጁ የዚያ ማኅበር ሰዎች ረጅም እጅና ቅብብሎሽ ምን ያህል የረዘመ ብቻ ሳይሆን የሰዎችን የኃጢአት ሸክም ለራሱ ፍላጎት መሳካት እንዴት መጠቀም እንደሚችል ያሳያል። ያንብቡ!

‹መንፈሳዊ ጉባኤ አዘጋጅተህ፥ ሰዎችን ሰብሰበሃል›› በሚል ተቃውሞ ክስ ተመስርቶበት፥ ከሰሞኑ 18 ከሚደርሱ ቅዱሳን ጋር መታሰሩን ሐራ ዘተዋህዶ መዘገቧ የሚታወቅ ነው፡፡ አሁን በደረሰን መረጃ መሰረት ደቀመዝሙር ከፍያለው ቱፋ የተከሰሰበት ክስ ፍሬ ከርስኪ መሆኑን ተረድቶ፥ ትላንት ማለትም 12/08/2008 ዓ/ም በአንድ ሺህ ብር ዋስ ፍርድ ቤቱ ሊለቀው ችሏል፡፡ ፍርድ ቤቱም አክሎም “የማንንም ሃይማኖት መስደብ፣ መንቀፍና መዝለፍ በሕግ ፈጽሞ የተከለከለ ነው፤ ደግሞም ማንም ሰው ያማነበትን እውነት መመስከርና መስበክ እንደሚችል” ገልጿል፡፡ በቦታው ላይ ፖሊስ ደርሶ ነገሩን ባይቆጣጠር ኖሮ ደም በማፍሰስ የሚያምነው ማህበሩ፥ የወንድሞችንና የእህቶችን ደም ከማፍሰስ እንደማይቦዝን የታወቀ ነው፡፡ ኽረ ለመሆኑ ለሃይማኖት የተደባደበ ሐዋርያ ማን ነው?

         አሁን አሁን በእናት ቤተክርስቲያናችን ውስጥ ባሉ አንዳንድ ጽንፈኛ ግለሰቦች ምክንያት ወንድሞች በጋራ ተሰባስበው መጽሐፍ ቅዱስን ከተማማሩ፣ በአንድነትም በመዝሙር በቅኔ ለአምላካቸው ከተቀኙ እንደ ምንፍቅና መታየት ከተጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ይሁንም እንጂ ቅድስት ቤተክርስቲያን፥ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ቀዳሚ ትምህርት መሰረት አድርጋ ወንጌል ለፍጥረት ሁሉ በየትኛውም ሥፍራ መሰበክ እንዳለበት ታስተምራለች፡-

· “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፡፡” ማቴ 28፡-19፡፡

         ደቀመዝሙሩና ከእርሱ ጋር የታሰሩ ወገኖች፥ ይሄንን የሐሰት ክስ ያቀነባበሩባቸውን ግለሰቦች መልሳችሁ መክሰስ ትችላላችሁ ቢባሉም እንኳ “በቀል የእግዚአብሔር ነው” በማለትና “ከአባታችን ከእግዚአብሔር የተማርነው ይቅርታና ምህረት ማድረግ ነው” በማለት አንዳችም አጸፋ ለማድረስ እንዳልፈለጉ ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ፡፡ ይሄ ደግሞ የአሰበ ተፈሪ ሐገረ ስብከት ሠራተኞችን ትዝብት ውስጥ የሚጥልና በቤተክርስቲያንም ወንጌል ለምን ተማማራችሁ በማለት የሚያሳስርና የሚከስ አባት የላትም፡፡ ይህንን ያደረጉት “የገባውን እውነት ቀብሮ ልጆቼን በምን አሳድጋለሁ ብሎ በግልጽ ወንጌልን የሚቃወመው ላዕከ ወንጌል ምንዳ ጉታ፥ ትዳሩን አያከብርም በሚባለው ሊቀ ብርሃናት ከሀሊ በቃሉ፥ እና በፀያፍ ቅጽል ስም የሚጠራው መልአከ ጸሐይ ዮሐንስ፣ ቀሲስ የማታ ወርቅ በተባሉ ግለሰቦች ሲሆኑ እነዚህ ሰዎች በዓመጻ ተነሳስተው ከማህበሩ በሚያገኙት. ድጋፍ ተነሳስተው  መሆኑ ታውቋል፡፡

“ወጥመድ ተሰበረ እኛም አመለጥን” እንዲል መጽሐፍ ክብር ሁሉ ለእግዚአብሔር ብቻ ይሁን! አሜን!

በዲሲ ቅ/ማርያም ቤተክርስቲያን የሥልጣንና የገንዘብ ጦርነቱ ተባብሶ ቀጥሏል!


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየተለመደ የመጣ ችግር አለ። በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በሁለትና ሦስት ጎራ ተከፋፍሎ የመጣላት፤ የመደባደብና ፍርድ ቤት ድረስ የመካሰስ አደጋ ከመቼውም ጊዜ በላይ እየሰፋ መጥቷል። መሠረታዊው የግጭቱ ምክንያት ሲገመገም በሁለት ነጥቦች ላይ ያጠነጥናል።


                       የሴራው መነሻ፤
1/ በተለያየ መንገድ ገንዘብ ለመዝረፍ እና

2/ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የማይነቃነቅ ባለሥልጣን  ለመሆን ነው።


                      የሴራው ተሳታፊዎች፤
የተወሰኑ ምዕመናንና ምዕመናት ግን በሴራው ተዋናዮች ዓላማ ተጠልፈው በቅንነት ቤተ ክርስቲያናቸውን ከአደጋ ለመከላከል ሲሉ ወደጦርነቱ ይገባሉ። የፖለቲካ ክፍፍሉም የራሱ ሚና ይኖረዋል። የሁለት ጎራ ሴረኞች ሕዝቡን የሚቀሰቅሱት ለቤተክርስቲያን ያለነሱ የተሻለ አሳቢ የሌለ በማስመሰል እንጂ ሁለቱም ጎራዎች ድብቅ ዓላማቸው አንዱ አንዱን በመንቀል በቦታው ላይ ራሳቸውን ለመትከል ነው። ይህ ሲባል በቅን አስተሳሰብ የተነሱ የለም ማለት አይደለም። ነገር ግን ቅኖቹ «ከነገሩ ጦም እደሩ» ብለው ራሳቸውን ስለሚያገሉ በመፍትሄው ላይ ተሳታፊ አይደሉም። ሁከቱና ብጥብጡ በውጪው ዓለም ባሉ አብያተክርስቲያናት ማለትም በለንደን፤ በሮም፤ በደቡብ አፍሪካ፤ በሰሜን አሜሪካ እየከፋ ሄዷል።


                            የሴራው ተዋናዮች
የሴራው ተዋናዮች ዓይነት ደግሞ የተለያዩ ናቸው። በአብዛኛው በየአኅጉረ ስብከቱ የሴራው ባለቤቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሲሆኑ በየአድባራቱ ደግሞ አስተዳዳሪዎች፤ ቦርዶች፤ የሰበካ ጉባዔ አባላትና ማኅበረ ቅዱሳን  ናቸው።  ከታች የተመለከተው ቪዲዮ ጦርነቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲካሄድ ያሳያል።
«ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ» ገላ 5፤15




Thursday, April 14, 2016

ውስጤ መኖር ያለበት ቃና ቲቪ ሳይሆን መንፈስ ቅዱስ ነው!!

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከወዳጅ ጓደኞቼ ጋር በተገናኘን ቁጥር የመወያያ አጀንዳችን የሆነው ጉዳይ የዛሬውን ፅሁፍ እንድፅፍ አስገደደኝ፡፡ ዋና መቀመጫውን በዱባይ አድርጎ በቅርብ ጊዜ በሀገራቸን ስርጭቱን የጀመረው ቃና ቴሌቪዥን በአማረኛ እየተረጎመ (dubbing) በሚያቀርባቸው የቱርክ፣ የጣሊያን፣ የህንድ፣ የጃፓን እና የመሳሰሉት ሀገሮች ተከታታይ ፊልሞቹ የበርካታ ሰወችን ቀልብ እንደገዛ ሁላችንም እናውቃለን፡፡ በእጅጉ የሚገርመው ደግሞ በዙሪያየ ያሉና የማውቃቸው በርካታ ክርስቲያኖች ጭምር ለእነዚህ የባህር ማዶ ፊልሞች እጅ ሰጥተው በጉጉትና በከፍተኛ ናፍቆት ሲጠብቁ ማየት ነው፡፡ የቃና ቲቪ ፊልሞች የሚታዩበት ሰዓት ደግሞ ወላጆች ከስራ፣ ልጆች ከትምምርት ቤት፣ ወጣቶችም ከሚውሉበት ስፍራ በቤት በሚሰበሰቡበት፣ የእግዚአብሔርን ቃል በሚያጠኑበት፣ በጋራ በሚፀልዩበት ሰዓት ነው፡፡ እውነትም በስጋ አይን ለተመለከታቸው ፊልሞቹ በከፍተኛ ሁኔታ የሰውን ቀልብ የመግዛት አቅም እንዲኖራቸው ሆነው ተሰርተዋል፡፡ አንደኛው ፊልም ሲያልቅ በቅፅበት ሌላው ይቀጥላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ከምሽት 12፡00 ሰዓት የተቀመጠ ሰው እስከ ምሽት 4፡00 ሰዓት ሌላ ስራ ሳይሰራ ያለምንም እንቅስቃሴ ይቀመጥ ዘንድ ግድ ይለዋል ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ልብ እንበል የተቀማነው ወትሮ ለፀሎትና ለእግዚአብሔር ቃል ጥናት በእጅጉ ይመቸን የነበረውን ሰዓት ነው፡፡ ከዛም ደክሞን እንተኛለን፡፡ እዚህ ጋር ግን እንደመንፈሳዊ ሰው ልንነቃ የሚገባን ይመስለኛል፡፡ ሰባት በየቀኑ ለየአንድ አንድ አዓት የሚታዩ መሳጭ የባህር ማዶ ፊልሞች እቤታችን ድረስ መጥተው በራሳችን ቋንቋ እየተመለከትናቸው ነው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ቀድሞ ለጌታ የምንሰጠውን ሰዓት እየተውን፣ በፀሎት የምናሳልፈውን ጊዜ እየሸረሸርን ከክርስትና በእጅጉ የራቁ ሐገሮች ሰርተው በሚልኩልን ነገር ስንጠመድ የእነሱን ባዕድ፣ አምልኮ ኢ-ክርስትናዊ ነገሮች በሙሉ ወደ ውስጣችን እየሰገሰግን ነው፡፡ ልጆቻችንም ከክርስትና በእጅጉ ያፈነገጠ ነገር በየቀኑ እየተመለከቱ እንዲያድጉ እየተፈረደባቸው ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችን በቆላስይስ 2፥8 ላይ ‹‹ እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን፥ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ›› ብሎ በዓለማዊ ነገር እንዳንጠመድ ያስጠነቅቀናል፡፡ ኢየሱስም በማርቆስ ወንጌል 4፥24 ‹‹ምን እንድትሰሙ ተጠበቁ›› ብሎ ከምንሰማውና ከምናየው እንድንጠበቅ ያዘናል፡፡ ዓለማችን ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ኢየሱስ በማቴዎስ ወንጌል ስለመጨረሻው ዘመን የተናገራቸውን የዘመን መጨረሻ ምልክቶች አንድ በአንድ አስተናግዳ ወደ ማገባደደዱ ትገኛለች፡፡ ብዙ ነገሮች ሆነዋል ብዙ ነገሮች ተፈፅመዋል፡፡ ባጠቃላይ ሰይጣን ዲያብሎስ ጥቂት ጊዜ እንደቀረው አውቆ ከመቸውም ጊዜ በላይ በኃይለኛ ቁጣ እየተጋ ያለበት ዘመን ነው፡፡ ዲያብሎስ በዚህ ዘመን በተለይም ወጣቱን ክፍል ከቤተክርስቲያን ለማራቅ ወደ እግዚአብሔር ቃል ትኩረት እንዳያደርግ ከሚጠቀምባቸው ዋና ነገሮች መሀል የፊልምና የሙዚቃው ኢንደስትሪ እጅግ ወሳኙን ድርሻ ይዟል፡፡በዘመናችን የሚሰሩ ፊልሞች በአብዛኞቹ ሰወችን ለዓለማዊ ምኞትና ለርኩሰት አብዝተው የሚጋብዙ ናቸው፡፡ ስለዚህም እኛ ክርስቲያኖች እንንቃ። ሰይጣን በረቀቀ መንገድ በእኛ ላይ እንዲሰለጥን እድል አንስጠው፤ የቱርክና የህንድ ፊልሞችን እያሳየ ከእግዚአብሔር መንግስት የሚለየን ጣቢያ ውስጣችን "ቃና ውስጤ ነው" እያልን ውስጣችን ሊሆንብን አይገባም፡፡ ምክንያቱም እኛ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ነን፡፡ ውስጣችን እሱ ብቻ ነው መኖር ያለበት። ብናምንም ባናምንም ዘመኑ የመጨረሻ ነው፡፡ ያኛው መንግስት እኛን በመዝናኛ ነገር ጠምዶ ከጌታ መንግስት ሊለየን እየተጋ ነው። እኛ ታዲያ ነቅተን ብዙ ምርኮ ልንበዘበዝ ሲገባን በወጥመዱ ከገባንለት እጅግ ከባድ ይሆናል፡፡ ስለዚህም እንንቃ በኢንተርቴመንት ስም ውድ ጊዜያችንን እንዳናስበላ፤ ይልቀንስ የእግዚአብሔርን ዓለምን በልጁ የመጠቅለል አላማ ለማሳካት አብሮ ሰራተኞች እንሁን!ስለወንጌል ግድ ይበለን፡፡
እኛ "መንፈስ ቅዱስ ውስጣችን ነው!"

Friday, April 8, 2016

ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም!!!


ማቴ 7፣21
በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም። እንዳለው ጌታችና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላውያን ነን ባዮቹ የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰደብ እያደረጉ. "ጌታ ሆይ፣ ጌታ በማለታቸው የዳኑ ቢመስላቸውም የተጠበቁት ለፍርድ ነው። በነሱም የከፋ አድራጎት ሰዎች ወደተገለጠው እውነት እንዳይደርሱ በማድረግ ላይ ተጠምደዋል። በተለይም በአፍሪካ ክፍለ አህጉር ክርስቲያን ነን በሙሉ ፓስተሮች እየተፈፀመ ያለው ዘግናኝ ድርጊትና በቤታችን በኢትዮጵያ ላይ መርገም የሚያመጣ ፀረ ክርስትና ሁኔታ እየተፈፀመ ነው። ሌብነት፣ ዝሙት፣ የእግዚአብሔርን ቃል ማጣመም፣ መዋሸት፣ አድማና ክፍፍል ዋነኛ መለያ ሆኗል።  ከዚህ በታች የቀረበው ጽሁፍ (ከምስባከ ጳውሎስ) የፌስቡክ ገጽ የተወሰደ ሲሆን ነገሩ ከዚህ በፊት እየታየ ከቆየው አሳፋሪ ተግባራት አንዱ ክፍል ነው።

ነገሩ መታወቅ የጀመረው እንዲህ ነው፡፡ አንድ ወዳጃችን በራሱ ምክንያት “ፓስተር” ተዘራ ያሬድ ወደሚያስተዳድሯት ቤ/ክ ይሄዳል፡፡ በዕለቱ የአምልኮ ፕሮግራም እየተካሄደ ነበር፡፡ መባ እና ዐሥራት ተሰበሰበ፤ ከዚያ በኋላ ማስታወቂያ ተነገረ፡፡ ማስታወቂያው ይህን መሳይ ነው፤ “ፓስተራችን የተዘራ ያሬድ ዳግመኛ የተወለደበትን ዕለት በየዓመቱ እንደምናከብር ይታወቃል፡፡ ለዚህም ዓመት ክብረ በዓል ብዙዎቻችሁ ገንዘብ ማዋጣታችሁ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ገንዘብ መስጠት እየፈለጋችሁ ሳትሰጡ ለገንዘብ ማሰባሰቡ የተመደበው ጊዜ ያለፈባችሁ ሰዎች መቸገራችሁን ነግራችሁናል፡፡ በመሆኑም ፓስተራችንን ተጨማሪ ዕድል እንዲሰጣችሁ ለምነነው፣ አንድ ዕድል ብቻ - ይኸውም ዛሬን ሰጥቶናል፡፡ ስለዚህ ገንዘብ መስጠት የምትፈልጉ ሰዎች ዛሬ ካልሰጣችሁ በቀር ሌላ ዕድል አይኖራችሁም፡፡ ምናልባት የተለየ ፈቃድ በፓስተራችን ካልተሰጠ በቀር …”፡፡

ከዚያ ደግሞ፣ ሌሎችም መረጃዎች በየጊዜው ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ፡፡ በእርግጥ ፓስተሩ ለልደታቸው ራቭ4 መኪና ስጦታ የተሰጣቸው በመሆኑ፣ በልደት ማክበር ስም የሚገኘው ጥቅማጥቅም ይጠፋቸዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡

በቅርቡ ለማጣራት እንደ ተሞከረው ደግሞ፣ መዳናቸውን እንኳን ከሰውዬው መዳን ጋር የሚያስተሳስሩ አባላት መኖራቸው ነው፡፡ ለልደቱ ገንዘብ የሚያዋጡት መዳናቸውን እያሰቡ ነው!

እኚህ “ፓስተር” “ሬማና ሎጎስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሲኖራቸው፣ ለጉባኤያቸው እንደተነናገሩት ከሆነ፣ “ማንም ሰው መጽሐፋቸውን አንብቦ መጠቀም የሚችል ሲሆን ከዚያ ባሻገር ግን መጽሐፋቸውን የመተቸትም ሆነ የመቃወም መብት እንደሌለው፣ ለዚህም ከፌዴራል መንግሥት ፈቃድ እንደ ተሰጣቸው” ይናገራሉ፡፡ “ፓስተር” ተዘራ፣ ከአባላቶቻቸው መካከል በርካታ የደኅንነት አባላት መኖራቸውንና የሚፈልጉትንም ነገር በቀላሉ ማስፈጸም እንደሚችሉ በድፍረት በመናገር ይታወቃሉ፡፡

እንዲህ ዐይነት አገላለጾች “ፓስተር” ተዘራ ያሬድ ስለ ራሳቸው ያላቸውን ግምት የት ድረስ የተወጠረ እንደሆነ ያስረዱናል፡፡

Tuesday, April 5, 2016

ደቀ መዝሙር ከፍያለው ቱፋ ወደኮሌጁ እንዲመለስ ተወሰነለት!



ሰበር ዜና
       ደቀመዝሙር፥ ዲያቆን፥ ዘማሪ፥ መምህር ከፍያለው ቱፋ ‹‹በሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ›› በነጻነት እየወጣ እየገባ እንዲማር የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ምድብ አንድ ፍ/ብሔር ችሎት ወሰነ!!
       የሞት ጣር የሚያቅረው ማህበረ ቅዱሳን የተባለ የባንዳ ስብስብ፥ ባሳለፍነው ሳምንት ደቀመዝሙር ከፍያለው ቱፋ ከሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ፥ ከትምህርት ገበታው እንዲነሳ በላካቸው ጀሌዎቹ በኩል ተሟግቶ ‹‹እንዲታገድ›› ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡ ይህችም እንደትልቅ ድል ተቆጥራ ‹‹ሐራ ዘተዋህዶ›› በተባለችው የደከመች ብሎጋቸው ላይ ሁለት ጊዜ ዜና ሰርተው ማናፈሳቸውም የሚታወስ ነው፡፡ የሚገርመው ግን ደቀመዝሙሩ እንዲታገድ በተወሰነው ‹‹ውሳኔ›› ላይ የኮሌጁ የበላይ ኃላፊ ‹‹ብጹዕ አቡነ ሕዝቅኤልና የኮሌጁ ዋና ዲን ሊቀ ኀሩያን ሰርጸና ብዛት ያላቸው የኮሌጁ አመራሮች›› አለመፈረማቸውን ሸሽገዋል፡፡ ያልፈረሙበት ምክንያት ደግሞ ደቀመዝሙሩን ከኮሌጁ የሚያስወጣ የሃይማኖት ሕጸጽ ባለማግኘታቸው ነው፡፡ የማህበሩ ጀሌዎች ግን ኃላፊነቱን በመውሰድ፥ ያልስልጣናቸው የኮሌጁን ማህተም ተጠቅመው፥ ደቀመዝሙሩን ያሰናበቱት፡፡ ይህ ደግሞ ወንጀል በመሆኑ ምክንያት ደቀመዝሙር ከፍያለው ቱፋ ለሚመለከታቸው የቤተክርስቲያናችን አባቶች በማሳወቅ፥ ጉዳዩን ‹‹ወደ ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ምድብ አንድ ፍ/ብሔር ችሎት›› ለመውሰድ ተገድዷል፡፡
        ከታች ለማስረጃነት ያቀረብነው የፍርድ ቤት ትዕዛዝ፥ በቀን 23/07/2008 ዓ/ም፥ የፌ/መ/ደ/ፍ/ቤት/ኮ/ቀ ምድብ 1ኛ ፍ/ብሔር ችሎት፥ በቁጥር የኮ/መ/ቁ 50074 ያሳለፈው ውሳኔ ሲሆን፥ ደቀመዝሙር ከፍያለው ቱፋ ላይ በኪራይ ሰብሳቢነት የማህበረ ቅዱሳን ጀሌዎች በኮሌጁ ስም ያሳለፉትን ውሳኔ፥ ከመሰረቱ ያፈረሰ ‹‹አጭርና ግልጽ›› ትዕዛዝ ነው፡፡ ትዕዛዙም እንዲህ የሚል ነው፡-
“ሌላ ተለዋጭ ትዕዛዝ እስከሚሰጥ ድረስ ተከሳሽ በከሳሽ ላይ ትምህርቱን እንዳይማር የሰጠው ውሳኔ እንዳይፈጸም ታዟል፡፡ ለሚመለከተው አካል ይጻፍ፡፡ ማለትም በደብዳቤ ቁጥር 399/2/233/08 በ19/07/2008 ዓም የተጻፈው እንዳይፈጸም ታዟል፡፡”
       እንግዲህ ሽንፈት ለማን ነው? ለጠላት፥ ለዲያብሎስ አይደለምን? አሸናፊውስ፥ የልባችን ንጉስ፥ ጌታችን ኢየሱስ አይደለምን? እነሆ መስፋትና ማሸነፍ ለእግዚአብሔር ልጆች ሲሆን በአንጻሩ ደግሞ መክሰር ለዲያብሎስ ሆኗል!!
      ይህ በእንዲህ እንዳለ ደቀመዝሙር ከፍያለው ቱፋ ከትምህርት ገበታው እንዲነሳ ውሳኔ በማሳለፍ ሥራ ላይ የተጠመደው፥ በሙስና የኮሌጁ ምክትል ዲን የሆነው አቶ ማሞ ከበደ፥ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ አልፈጽምም በማለቱ ምክንያት እስራት ይጠብቀዋል፡፡ በተጨማሪም አቶ ማሞ ከበደ በማህበሩ የተሰጠውን አጀንዳ ለማስፈጸም ሲል ብቻ፥ ብጹዕ አቡነ ሕዝቅኤልና የኮሌጁ ዋና ዲን የሆኑት ሊቀ ኀሩያን ሰርጸ ፊርማቸውን ሳያስቀምጡ፥ ካለስልጣኑ በኮሌጁ ስም በወሰነው ወንጀል ሌላ ዘብጥያ ይጠብቀዋል፡፡ ሲጀመር አቶ ማሞ ከበደ የኮሌጁ ሠራተኛ ነው እንጂ የሃይማኖት ህጸጽ መርማሪስ ማን አደረገው? የሃይማኖት ህጸጽ ቢኖር እንኳ ሊጠይቀው የሚገባው፥ ቤተክርስቲያን ሥልጣን የሰጠችው አካል የሊቃውንት ጉባኤ ነው እንጂ፥ አንድ ጤና የጎደለው ሠራተኛ አይደለም፡፡ ሲኖዶስ ያልወሰነውን፥ ሊቃውንት ጉባኤ ያልወሰነውን ግለሰቡ የማሕበረ ቅዱሳንን አጀንዳ ተሸክሞ ለማስፈጸም መድከሙ ነውረኛነቱን የሚሳይ ነው፡፡ ሲቀጥልም ግለሰቡ የሃይማኖት ሕጸጽ የመመርመር ሥልጣንም ይሁን ብቃት የለውም፡፡ በርግጥ አቶ ማሞ ከበደ በደቀመዝሙሩ ላይ የእግድ ደብዳቤ የጻፈው ‹‹የሃይማኖት ህጸጽ›› ተመልክቶ ሳይሆን፥ ከማኀበሩ በሚያገኘው የኪራይ ሰብሳቢነት ልክፈት በመለከፉ ምክንያት እንደሆነ የቅርብ ወዳጆቹ ይመሰክሩለታል፡፡
ይህን ጉዳይ እየተከታተልን የምናቀርብ መሆኑን ከወዲሁ እንገልጻለን፡፡

Friday, April 1, 2016

ያገር ያለህ ወይም የዳኛ ያለህ!!!


ከእውነቱ ( ክፍል ሁለት)

በማህበሩ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ላይ ያስተዋልኩት ድካም፡

 የግብጽ ቤተ ክርስቲያን የጫነችብንን ኢመጽሐፍቅዱሳዊ የባእላት አከባበርን ሕዝቡ በበለጠ
መልኩ እዲቀጥልበት ለማድረግ ሰምተናቸው ለማናውቃቸው ሰዎች የቅድስና ማእረግ
በመስጠት/በማሰጠት ሕዝቡ ከሥራ ይልቅ ባእል አክባሪ እንዲሆን መደረጉ፣
 በሌለ የጉልበትና የገንዘብ አቅም ሕዝቡ ለጽድቅ እየተባለ ወደ ተለያዩ ስፍራዎች በመጓጓዝ
እንዲደክም መደረጉ /ፈጣሪ በቦታ የሚወሰን ይመስል/
 በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ታሪክ ውስጥ ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ የጽላት ቀረጻና
የታቦት ተከላ ሥራ መሥራት፣
 እግዚአብሔርን ተርቦና ተጠምቶ በአውደ ምህረቱ ዙሪያ ለተሰበሰበው የዋህ ሕዝብ ፍቅር
የሚያስተምረውን የወንጌል ቃል ከመስበክ ይልቅ በእለቱ የሚከበረውን የጻድቅ ገድልና ታሪክ
ከሃይማኖትህን ጠብቅ የማስፈራሪያ መርገም ጋር በማሰማት ለጦርነት ማዘጋጀት፣
 ሕዝቡ በራሱ መረዳት ማን ምን እንደሆነ በእግዚአብሔር ቃል እውቀት እየመዘነ ሃሰቱንና
እውነቱን በመለየት የሚጠቅመውን እንዳይዝ መረጃ በሌለው አሉባልታ ተሞልቶ በውስጡ
ጥላቻና ቂም አዝሎ የራሱን ወገን እንዲጠላ በልዩ ወንጌል ሰባኪዎች መሰበኩ፣
 የበጉ ሐዋርያትና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን ቀደምት የእምነት አባቶች አድርገውት የማያውቁትን
መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ በጸበል ተገኘ ጋጋታ ሕዝቡን ማንገላታታቸው፣
 በአጠቃላይ ሕዝቡን በቃል እውቀት ሳይሆን በቅርስና በባንዲራ ፍቅር የራሱን ወንድም
በጭፍን ወግሮ የሚያሳድድ ሃይማኖተኛ እንዲሆን እየተደረገ መሆኑን ይህ ጸሐፊ በራሱ ቤተ
ሰብ መካከል ባደረገው አጭርጥናት ሊያረጋግጥ ችሏል።

2/ ኦርቶዶክስ ተሐድሶ ማነው?

በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተወልደው በማደግ ባህሏንና ትምህርቷን ጠንቅቀው የሚያውቁ
የቤተ ክርስቲያኒቷ ልጆች ነን ይላሉ፤ የኦርቶዶክስ ተሐድሶ ማህበር በሚል መጠሪያ ስም፡ ኦርቶዶክስ
ቤተ ክርስቲያናችን ከውጭና ከውስጥ በደረሱባት ልዩ ልዩ ተጽእኖ ምክንያት ከተመሰረተችበት
የክርስቶስ ኢየሱስ ወንጌል ርቃ ልዩ ወንጌል በመስበክ የመስቀሉን የማዳን ሥራ ቸል ብላለች፤ ስለዚህ
ወደ ቀደመ የወንንጌል ጅማሬዋ ትመለስ፤ በእግዚአብሔር ቃል /መጽሐፍ ቅዱስ/ መስተዋት ፊቷን
በማየት ክፉ ሰዎች ያለበሷት የደብተራዎች፣ ያስማተኞችና የደጋሚዎች ልብስ በንጹሁና እንከን የለሽ
በሆነው በእግዚአብሔር ቃል ልብስ /በክርስቶስ/ ይተካ በማለት ይጮሃሉ።

እንዲያውም እነዚህ ሰዎች የቤተ ክርስቲያናችን ወይም ያገራችን ታሪክ ይፈተሽና ይመርመር፤ ይዘነው
የተነሳነውንም የተሐድሶ ጥያቄና ሃገራዊ አጀንዳ ያገራችን ሽማግሌዎች፣ ጳጳሳት፣ ምሁራን፣ ተማሪዎች
በአጠቃላይ ሕዝቡ ይስማውና ማን የኦርቶዶክስ ጠላትና ወዳጅ እንደሆነ ጠቅላላ ምእመኑ እውነቱን
ይረዳ በሚል ግልጽነት በይፋ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን መረዳት ችያለሁ።
እኔም እነዚህን አንዳንድ የኦርቶዶክ ቤተ ክርስቲያንን የተሀድሶ ሥራ አራማጆችን ጠጋ ብየ በመጠየቅ
የሚከተሉትን መረጃዎችን አግኝቻለሁ፡

1. የቤተ ክርስቲያናችን ጅማሬ ከኢየሩሳሌም ቀጥሎ በወንጌል ላይ ብቻ የተመሰረተች መሆኗን፣

2. በመጀመሪያው ጳጳስ በወንጌል ላይ የተጀመረው ክርስትናችን ግን እኒሁ ጳጳስ ከሞቱ በኋላ፡
 በእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ቁጥጥር ስር በመውደቅ ለ1600 ዓመታት ከ110 በላይ በሚሆኑ
የውጭ ሀገር ጳጳሳት /የግብጽ የፖለቲካ ሠራተኞ/ መንፈሳዊ ቅኝ ተገዢዎች በመሆን አባይን
በመገደብ ሥራ ሠርተን እንዳንበላ እስካሁን ድረስ የ30 ቀናት ባእላት ባሪያዎች መደረጋችንና
ከእነዚህ መካከል አንዱ የካሊፋው ዋና ወኪል /አቡነ ሳዊሮስ/ እነደነበረ፣
 የዮዲት ጉዲት የ40 ዓመታት ግዛትና የቤተ ክርስቲያኗ መጽሐፍትና ካህናት መቃጠል፣
 የግራኝ ሙሐመድ የ15 ዓመታት ግዛትና የሙስሊም ክርስቲያኑ ሬሽዮ 9፡1 መድረሱና የቤተ
ክርስቲያኒቷን ውበት ማበላሸቱ፣

 ዘርዓ ያእቆብ በንግስናው ወራት በመጽሐፍ ቅዱስ ያልተመዘኑ የድርሰት ጽሑፎችን በቤተ
ክርስቲያኒቷ ውስጥ ያለገደብ ማስገባቱና የተሃድሶን ጥያቄ ያነሱ መነኮሳትን መጨፍጨፉ
/የፕ/ር ጌታቸውን ደቂቀ እስጢፋኖስን መጽሐፍ መረጃ ይጠቅሳሉ/፣
 የቤተ ክርሰቲያኒቷ ሲሦ መንግሥት ውል መዋዋልና ከዚህ ጋር በተያያዘ መልኩ መንግሥትን
ከሰሎሞንና ከዳዊት ጋር በማያያዝ የታቦትና የጽላት መጥቷል አፈታሪክ ጅማሬ /አቡነ ተክለ
ሐይማኖትን ተጠያቂ ያደርጋሉ/፣

 የደብተራ ቡድን በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ ተነስቶ የመናፍስት አሠራር እስካሁን ድረስ
በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ በሰፊው መለመዱ ……….. ወዘተ።
የመሳሰሉትን ነጥቦች በድፍረትና በማስረጃ በማቅረብ ቤተ ክርስቲያኒቷ ከተመሰረተችበት የወንጌል
መሰረቷ ፈቀቅ ብላለችና ወደ ቀደመ የወንጌል ጅማሬዋ ትመለስ በማለት አጥብቀውና በነፍሳቸው
ተወራርደው ለዚህ ሥራ እንደተነሱ ጨክነው ይሟገታሉ። ይህም መንፈሳዊ መታደስ በአገሪቱ ውስጥ
ላለው ሁለንተናዊ ችግር /ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ሃይማኖታዊ ችግር/ ዋና መፍትሄ ይሆናል
ብለው በማስራጃ ለማሳመን ይሞክራሉ።
ይህን ጉዳይም የኢትዮጵያ ሕዝብ በሙሉ ተረድቶና ማን ምን እንደሆነ ተገንዝቦ ለመንፈሱ፣ ለነፍሱና
ለሥጋው የሚበጀውን በመጽሐፍ ቅዱስ/በወንጌል ሚዛን መዝኖ የሚረባውን ይይዝ ዘንድ
ራእያቸውንና ዋና ተልእኳቸውን ለሕዝብ በይፋ ያቀርባሉ፡

የተሐድሶ ራእይ፡

‘‘ጥንታዊና ሐዋርያዊት የነበረች ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናችን በየዘመናቱ ከደረሰባት ውስጣዊና
ውጫዊ ተጽዕኖ የተነሳ ከተተከለችበት የእውነት ወንጌል በማፈንገጥ አሁን ላለችበት ውድቀት
በመዳረጓ ይህን ሁኔታዋን በከበረው የጌታችንና የመድኃኒታችን ቅዱስ ወንጌል በመመዘንና ወደ ቀደመ
የወንጌል ክብር በመመለስ በእጇ የሚገኘውን ተከታይና የተቀረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ክርስቶስ
ኢየሱስን በማወቅና በማመን የሚገኘውን የዘላለም ሕይወት በማግኘት ለጌታችን ቀን ያለነውርና
ያለነቀፋ ሆኖ እንዲገኝ በማዘጋጀት ለአፍሪቃና ለተቀረው ዓለም የሚላኩ ቅዱሳን አገልጋዮችን
በማፍራት የሚጠበቅባትን የወንጌል አደራ ስትወጣ ማየት ነው’’

የተሐድሶ ተልዕኮ፡

1. የቤተ ክርስቲያኒቷን አንድነትና የሀገራችንን ጥቅም በጠበቀ መልኩ ምዕመናን በጌታችንና
በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ትክክለኛና እውነተኛ ተሀድሶ በማድረግ ለዘላለም
ሕይወት እንዲዘጋጁ መርዳት፣

2. በየደረጃው የሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች እንደ የደረጃው በተዘጋጁ የወንጌል
ትምህርቶች በማሰልጠንና በማሳወቅ ለስብከተ ወንጌል ሥራ ማዘጋጀትና የአገልግሎት ቦታዎች
ሁሉ እውነትን በተረዱ አገልጋዮች እንዲሸፈኑ ማድረግ፣

3. በየዘመናቱ ወደ ቤተ ክርስቲያኗ የገቡትን የስህተት ትምህርቶች ሥርዓቶችና ባሕሎች በቅዱሱ
ወንጌል በመዳኘት ከሕዝባችንና ከቤተ መቅደስ ዕቃ ቤቶቻችን እንዲወገዱ ማድረግ፣

4. ለአገራችን ኢትዮጵያ ዕድገትና ለዓለማችን ጥቅም በክርስቲያናዊ አስተሳሰብ ከመልካም ዜጋ
ግንባታ ጀምሮ ለልማትና ለመልካም አስተዳደር መስፈን ግዴታቸውን የሚወጡ ትጉህ
ሠራተኞችን ማፍራት፣

5. ጸረ ወንጌል ያልሆኑና ለክርስቶስ ወንጌል መስፋፋት ጠቀሜታ ያላቸውን ሥርዓቶች፣ ባህሎችና
ልማዶች ለክርስቶስ ወንጌል መሰበክ እንዲያገለግሉ መጠበቅና ማስጠበቅ።

Tuesday, March 29, 2016

የሕይወት ጉዞ ጠላቶች አይለወጡም!


/ኤፍሬም ባለጊዜ/
ሁለት ሰዎች በከፍተኛ ሁኔታ ክርክር ገጥመዋል። አንዱ አማኝ ሲሆን ሌላኛው ከሀዲ ነው፣ ያውም የፈጠረውን አምላክ የካደ። ክርክራቸው ወዲህ ነው። አማኙ እግዚአብሔር አለ ይላል። ከሀዲው ሰው ደሞ በፍጹም የለም ይላል። አማኙ ሰው የእግዚአብሔርን መኖር ለማስረዳት መጽሐፍ ቅዱሱንም፣ ሳይንሱንም እያጣቀሰ ብዙ ተናገረ። ነገር ግን ሰሚ አልነበረውም። ከብዙ ክርክር በኋላ ይህ አማኝ ሰው አንድ ጥበብ መጣለትና ከሀዲውን ሰው እንዲህ ሲል ጠየቀው። እግዚአብሔር ቢኖር ይሻላል ባይኖር? ይህን ጊዜ ከሀዲው ሰው ፈጠን ብሎ ባይኖር ይሻላል አለ።        ልብ በሉ!  እንግዲህ ከሀዲው ሰው እግዚአብሔር የለም ብሎ ሲከራከር የነበረው የመረጃ ችግር ስለነበረበት አልነበረም። እግዚአብሔር የለም የሚለው እግዚአብሔር እንዳይኖር ስለሚፈልግ ብቻ ነው። ጠላቶችሁ ያላችሁን የከበረ ነገር በፍጹም ማመን አይፈልጉም።  ያ ማለት ግን የከበረ ነገር እንዳላችሁ አያውቁም ማለት አይደለም። አንዳንዶች ግልጡን እውነት በጭራሽ መስማት አይፈልጉም ወይም ቢያውቁም ለማመን አይፈልጉም።

  በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንደተፃፈው ዳዊት ለወንድሞቹ ምግብ ለማድረስ ወደ ጦሩ ሰፈር በመጣ ጊዜ የኤልያብ ቁጣ በዳዊት ላይ ነዶ " ለምን ወደዚህ ወረድህ? እነዚያንስ ጥቂት በጎች በምድረ በዳ ለማን ተውሀቸው? እኔ ጠማማነትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁ፣ ሰልፉን ለማየት መጥተሀልና" ነበር ያለው።  አሁን ኤልያብ ለዳዊት መንገር የፈለገው ዋና ሀሳብ ግልጽ ነው። አንተ እረኛ ነህ፣ አርፈህ በጎች ጠብቅ የሚል ነው። ነገር ግን እረኝነት ለዳዊት የስልጠና ስፍራ እንጂ የህይወቱ ጥሪ ላለመሆኑ ከኤልያብ የተሻለ ምስክር የለም። ምክንያቱም ዳዊት ለንጉሥነት በተቀባ ጊዜ ኤልያብ እዚያው ቦታ ላይ ነበር። (ሳሙኤልም የዘይቱን ቀንድ ወስዶ በወንድሞቹ መካከል ቀባው። 1ኛ ሳሙ 16፥13)

  ነገር ግን ኤልያብም እንደዚያ ከሀዲ ሰው ችግሩ የመረጃ ሳይሆን የፍላጎት ነበር። ፍላጎቱ ደግሞ ዳዊት በእረኝነት ዘመኑን እንዲጨርስ ነው።  በሥራችሁ፣ በሙያችሁና በንግግራችሁ ሁሉ እውነተኞች ብትሆኑም የሚቃወሟችሁ ሰዎች ቁልቁል ሊደፍቋችሁ ይሞክራሉ። መንገዳችሁን በወጥመድ ያጥራሉ። የምትወድቁበትን ጉድጓድ ይቆፍራሉ። እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ከሆነ ማን ሊቃወማችሁ ይችላል?

በመጨረሻም ለማለት የምፈልገው በከንቱ በሚጠሏችሁና ሁልጊዜ ውድቀታችሁን በሚመኙ ሰዎች ልባችሁና መንገዳችሁ አይያዝ። ከዛሬ ነገ በእኔ ላይ ያላቸውን አቋም ይቀይራሉ ብላችሁም አታስቡ።  እንዲህ አይነት ሰዎች የሕይወት ዘመን ቋሚ ጠላቶች ናቸው። ነገር ግን እንደ ክርስቲያን በብዙ ፍቅርና ጸሎት አስቧቸው። እኔም እናንተም እዚህ የደረስነው በሰው ፍቅር አይደለም፣ በእግዚአብሔር ምህረት እንጂ!

Saturday, March 26, 2016

ቀሲስ የ“ክብረት ልጅ”፥ ምነው በስድብ ቃል በጣም ጮኸ?!


ምንጭ፦ የአቤኔዘር ተክሉ ገጽ http://abenezerteklu.blogspot.com/
የክብረት ልጅ እይታዎቹን በሚያቀርብበት ብሎጉ፥ “ፓትርያርኩ፦ ለኢትዮጲያ የደኅንነት ፣ ለምእመናን የድኅነት ሥጋት” በሚል አንድ ጽሁፍ፥ ዛሬ አስነብቦ ድንገት ያየ ሰው ጠቆመኝና ወደጡመራው መድረኩ ገብቼ አነበብኩት፡፡ ዳንኤል በዚህ ጽሁፉ “100% ማኅበረ ቅዱሳን ሊያዘጋጀው ከጫፍ የደረሰውን ዐውደ ርእይ የከለከሉት ፤ ያስከለከሉት ፓትርያርኩ ናቸው”፥ ብሎ ደምድሞ አስቀምጦታል፡፡ የዐውደ ርእዩ ባለቤት ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ፥ በዋናው ጸሐፊው አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ በኩል ትላንት ማምሻውን ለጋዜጠኞች በሰጠው ጋዜጣዊ “መግለጫ”፥ “ለመታገዱ ፓትርያርኩ እንደሌሉበትና በመንግሥት አካላት መመሪያ መታገዱን”ይፋዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡

ዳንኤል ፓትርያርኩን ከሰይጣን እኩል ነበር የሳላቸው ፤ “... ፓትርያርክ ማለት በግሪክ “ታላቅ አባት” ማለት ነው፡፡ የታላቅ አባት ተግባር የልጆቹን ሥራ ማፍረስ አይደለም ፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፤ ...” በማለት፡፡ እንደከዚህ ቀደም ልማዱ ዳንኤል ሌሎች ማስጮኺያዎችንም በዚህ ጽሁፍ ለማካተት ጥሯል፡፡ አዳዲስ ስድቦችንም ለፓትርያርኩ እንደእጅ መንሻ አቅርቦላቸዋል፡፡

ቅዱስ ቃሉ ግን እንዲህ ይላል፥ “ፈራጆችን አትስደብ፥ የሕዝብህንም አለቃ አትርገመው።” (ዘጸ.22፥28) የሕዝብ አለቃ ወይም መሪ የሆነ ገዥ በምድር ላይ የእግዚአብሔር ተወካይ ፤ እንደራሴም ነው፡፡ ስለዚህ ልናከብረው ፤ በመውደድም ከሁሉ በፊት ልንጸልይለት ይገባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሳያስበው ይህን ቃል በመተላለፉ ምክንያት ወዲያው ተጸጽቶ ተመለሰ ፤ አለማስተዋሉንም ተናገረ፡፡ (ሐዋ.23፥4-5) ፍትሐ ነገሥቱም “በእነርሱ ላይ የተሾመውን ጳጳስ ... እንደትልቅ ወንድም ያክብሩት መሪና አስተዳዳሪ እንደመሆኑ መጠን ሊታዘዙለት ይገባል” ይላል፡፡ (አን.4 ቁ.53) ዳኒ! ይህ የሕግ ቃል አንተን አይመለከትም ይሆን?!

የቤተ ክርስቲያን የቀኖና መጽሐፍ ፍትሐ ነገሥት በአንቀጽ.6 ስለቀሳውስት ድርሻ ባሰፈረበትና ቀሳውስት ከማዕረገ ክህነታቸው ስለሚሻሩበት ሁኔታ ሲዘረዝር “... ሕግን አውቆ የማይሠራባት ... ቄስ ይሻር፡፡” በማለት በግልጥ ያስቀምጣል፡፡ ዳኒ! እንኳን መንፈሳዊውን ሥጋዊውን የዚህን አለም ምድራዊ ሕግ መጣስህን አውቀኸዋል? ማኅበሩ ፓትርያርኩ አልከለከሉኝም እያለ፥ አንተ ግን ለፓትርያርኩ የስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍተሃል፡፡ እንደቤተ ክርስቲያን ቀኖና ከቅስናህ ትሻር ይሆን? እውነታው ግን አይመስልም፡፡

ፓትርያርኩ ቢያጠፉ እንኳ የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ምን ነበር የሚለው? ጅል ፣ ሰይጣን ፣ የክፋት አነሳሽ ... እያሉ በአደባባይ ፓትርያርክን መዘርጠጥ አለበት የሚል “ቀኖና” አለን?! ለመሆኑ ስድብ ከማን ነው? የሕዝብን አለቃ አለማክበርስ? ያንን ሁሉ መጽሐፍ የጻፈው “ደራሲና ተመራማሪ” ምነው ምራቅ እንዳልዋጠ “ፍንዳታ”(የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴራችን ቃል ናት) ደርሶ ቱግ አለ?! እንዴ ይህ ነበር እንዴ በውስጡ የነበረው?!

ውድ ወንድሜ ቀሲስ ዳንኤል፦ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አላት ፤ በየትኛውም የቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና ሽቅብ ፓትርያርክን እንዲህ መዘርጠጥ አይደለም ምእመንን መናገር አጸያፊ ነው፡፡ ተግሳጽ ነው ብትለኝ፥ ለመሆኑ ተግሳጽ መቼ ነው የሚመጣው? ደርሰህ ከመገሰጽህ በፊት ስንቴ ይሆን የመከርካቸው? ስንቴ ይሆን የወቀስካቸው? ስንቴ ይሆን ካሉበት ነቀፌታ እንዲርቁ በሚራራ ልብ አዝነህላቸው እንደእግዚአብሔር ቃል በጸሎት ቃል ወደጌታ የማለድክላቸው? ... ደጋፊ ስላገኙ ብቻ ብዙ ማለት፥ ከማያዳላ ኅሊና ጋር ያፋጥጣል፡፡ ወንድምን ሰባት ጊዜ ሰባ ይቅር ማለትና መቀበል እኮ ከአባት ባሻገር ወንድም ለሚሆነን ፓትርያርክንም ያካትታል ፤ ለመሆኑ ይህን ታውቀዋለህን?!

ፓትርያርኩ ቢያጠፉ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አላት፡፡ “...የአገሩ ሁሉ ኤጲስ ቆጶሳት ስለእርሱ የሚገባውን ይመረምሩ ዘንድ እርሱንም ለማየት በየዓመቱ ሁለት ጊዜ ከጳጳሳቸው (ፓትርያርካቸው) ዘንድ ይሰብሰቡ፡፡ ስለተሰጣቸው ሥልጣን በምታስፈራዪቱ ቀን መልሳቸው የጸናች ትሆን ዘንድ፡፡” (አን.4 ቁ.55) የሚል፡፡ የሚያዩት ፊቱን ብቻ አይደለም ፤ ሥራውን በማየት ያመሰግኑታል ፤ ነቀፌታም ካለ ይነቅፉታል፡፡ ዳኒ! ይህችን አላነበብካት ይሆን?! ፓትርያርኩን መውቀስና መምከር ፤ መገሰጽም ካለብህ መንገዱን አልሳትከው ይሆን? ይህን ያህል ግን ለምን ይሆን የጠላሃቸው? ዳኒ! ወንድምን ስለመጥላት ቃሉ በትክክል ይወቅስሃል፡፡

በእርግጥ ዳንኤልና ማኅበሩ መንገድ ሲተላለፉ ይህ የመጀመርያው አይደለም፡፡ ግን እውነት ለመናገር ባልተጣራ ወሬ ፤ በተራ አሉባልታ ያውም ስንት ሽልማት ያግበሰበሰው ሰው ይቺን ትንሿን ነገር ከማጣራት ቸኩሎ “በሚቆረቆርላት” ቤተ ክርስቲያን መሪ ላይ የስድብ ናዳ ያወርዳል ብሎ ማን ይጠብቃል?! ከዚህ ስህተቱ ይማር ይሆን ዳንኤል? ወይስ ወደፊትም ሌላ የስድብና የመዘርጠጥ ጽሁፍ ያስነብበን ይሆን? ወይስ እንደጳውሎስ በግልጥ የይቅርታ ልብ ይዞ “የሕዝብን አለቃ” ስለተሳደበበት ስድቡ ንስሐ ይገባ ይሆን? የምናየው ይሆናል፡፡ ፈጥነህ ንስሐ ብትገባ ግን ማሰናከያን ታስወግዳለህና እስኪ ቀድመህ ወደራስህ እይ!!!

ጌታ ማስተዋሉን ያብዛልን፡፡ አሜን፡፡

Tuesday, March 22, 2016

እነሆ ሁለቱ ኪዳናት!!!


ከእውነቱ (ክፍል ሁለት)

መግቢያ

ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ስለ ትምህርተ ድነት በኛ ቤተ ክርስቲያን ተረስቶ ኖሯል፤ አሁንም እንደ ተረሳ ነው፡፡ አምስቱ አዕማደ ምስጢር የሚባል የዶግማ ትምህርት አለ፡፡ ግን እንኳንስ ለህፃናትና ላልተማሩ ሰዎች ዕድሜ ልኩን በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ኖርኩ ለሚልም በቀላሉ ሊረዳ አይችልም፡፡ ዋናውና የሕይወት ትምህርት ወደ አንድ ጎን ተጥሎ ነው የኖረው፤ አሁንም ቢሆን ያሰበበት የለም፡፡ ከቃል ትምህርቱ ከዜማው፣ ከቅኔውና ከአንድምታው መቅደም የነበረበት የክርስቶስ ቤዛነት ትምህርት ነው፡፡ ትምህርተ መለኮትን (ቲኦሎጂን) ተማረ ቢባል ትምህርቱ ተንሳፋፊ ነው፡፡ መሠረቱን ለቆ አየር ላይ እየተንጠለጠለ የሚሄድ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የአመራር መንፈሳዊ አገልግሎትና በምእመናን መካከል እውነተኛው የእግዚአብሔር ፍቅር ፈጽሞ ተረስቷል፡፡ እኔነት፣ ትዕቢት፣ ትምክሕት፣ መናናቅ፣ መገፋፋት፣ መጠላላትና ርኩሰት በክርስቲያኖች መካከል ሰፍኗል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የወንበዴዎች ዋሻ ሆናለች (በጌታችን እንደ ተነገረው)፡፡ ከላይ በጥቂቱ እንደተጠቆመው ከህፃናት ጀምሮ በየዕድሜ ክልሉ ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ትምህርተ ድነት መስጠቱ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ፈጽሞ አይታወቅም፡፡ ባሁኑ ጊዜ ሰባክያን ተብዬዎች በየደብሩ ተቀጥረው ምንም ፍሬ የሌለው ጩኸት ያስተጋባሉ፡፡ በሌላ በኩል እያወቁ ዝም ከማለት አሁንም ቢሆን በየደረጃው ትምህርት ለመስጠት የሚያስችል ትምህርትን ብናዘጋጅ ኃላፊነታችንን እንድንወጣ ያስችለን ነበር (ገብረዮሐንስ 2002፡ መግለጫ)፡፡ ይህንን መልእክት የጽሑፌ መንደርደሪያ እንዲሆን የመረጥኩት በውስጤ የሚመላለሰውን የ‹‹ችላ ተብሏልና ወደ እግዚአብሔር ሃሳብና ዓላማ እንመለስ›› ጥያቄ አጭርና ግልጽ በሆነ መንገድ ስለሚያስረዳልኝ ነው፡፡
 ደግሞም ቤተ ክርስቲያናችን ያለችበትን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ድክመት እንዲሁም በሰባክያኑ ውስጥ ሳይቀር ተንሰራፍቶ የሚገኘውን ፍሬ አልባነት በማሳየቱ ረገድ በዐይን ያየንና በውስጡ አልፎ ያገናዘበን ሰው ያህል ማስረዳት ስለሚያስቸግር፥ ከእኔ ይልቅ ረዘም ላለ ዘመን ባለፉበት የሕይወት ተሞክሮ ውስጥ ያከማቹትን እምቅ ትዝብት እጥር ምጥን አድርገው ያስተላለፉልንን የእኚህን አባት ቃል ቃሌ አድርጌ መናገር የተሻለ ብቻ ሳይሆን ተገቢም ነው ብዬ ስላመንኩ ነው፡፡ ይህም የሆነው እንደተባለው በውስጡ ላለፉት ሳይቀር ግልጥ ያልሆነ የትምህርት አቅርቦትን፣ ትኩረት ያልተሰጠውንና ወደ አንድ ጎን ተጥሎ የኖረውን ደግሞም አሁንም እንኳ ያሰበበት የሌለውን መንገድ እየተከተልን ይህን ያህል አማኝ አለን እያሉ መመካቱ ገበናችንን ሊሸፍንና በትምህርትና በአስተዳደር ዘርፍ ያለብንን ሥር የሰደደ መንፈሳዊ ችግር ሊሸሽግልን ባለመቻሉ በብዙ ወገኖች ተደጋግሞ እየተነሳ ያለውን ‹‹የትምህርትና የአስተዳደር ተሐድሶ›› ያስፈልጋል ጥያቄ ተገቢነት የበለጠ ትኩረት እንድሰጠውና እኔም እንዳስተጋባው በመገደዴ ነው፡፡ ይህ እንደ ተጠበቀ ሆኖ በክርስቲያናዊ ትምህርት ተኮትኩቶ ያላደገውን ምእመን ግራ እያጋቡ እነርሱ ጭምር በውል ወዳልተረዱትና በምናልባት ወደሚጓዙበት ፍልስፍና ሲጎትቱት የሚስተዋሉት ‹‹ፍሬ የሌለው ጩኸት የሚያስተጋቡት ሰባኪያን ተብዬዎች›› ሁኔታዎች ያስገኙላቸውን ክፍተቶች ተጠቅመው እየዘሩት ያለውን የትምህርት እንክርዳድ ነቅቶ ሊጠብቅና በወቅቱ ሊያስተካክል የሚችል ቢያንስ አንድ መንፈሳዊ አባት ማጣት ያስከተለው ችግር ውስብስብነትም ምንቸገረኝ የሚያሰኝ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡

ከዚህ የተነሳ የእነዚያ ‹‹የሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍ ጸሐፊ፣ አርታኢና አሳታሚ ማኅበር ቅንጅታዊ ተግባር ይህንን ለዘመናት እውነቱን እንዳያይና በዕውቀት እንዳይመራ የተደረገ ሕዝብ በባሰ የጨለማ ሕይወት እንዲዳክር ለማድረግ በቃልና በጽሑፍ የሚከናወን ጥረት አካል በመሆኑ ይህንኑ ለማሕበረሰባችን ገልጦ በማሳየት የደረሰውንና ሊደርስ ያለውን ብርቱ ችግር መከላከል አስፈላጊ ሆኗል፡፡ በእኔ እምነት ትውፊትንና ልማድን መከለያ አድርጎ የእግዚአብሔርን ቃል መቃወም ከተወቃሽነትና ከተጠያቂነት አያድንም፡፡ በክርስትና ስም ተሰባስቦና ታሪክና ቅርሳ ቅርስ እንጠብቃለን ወደሚል ዝቅታ ዝቅ ብሎ ለባሕልና ለቅርሳ ቅርስ በመወገን የእግዚአብሔር ሃሳብና ፈቃድ እንዳይፈጸም መከላከልም ተቀባይነት የለውም፡፡ ቅርሳ ቅርስ መጠበቁና ማስጠበቁ የሚያስከፋ ባይሆንም ከታሪክና ከቅርሳ ቅርስ በፊት ለእነርሱ መገኘት ምክንያትና ባለቤት የሆነው ክርስቶስ የሞተለት ሕዝብ መንፈሳዊ ሕይወት ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ትኩረት የተነፈገው ምእመን ከሁሉ አስቀድሞ የእምነቱን ቀዳሚ ፍሬ (ድኅነተ ነፍሱን) እንዲያረጋግጥ የሚያስችለውን እውነተኛ የክርስትና ትምህርት ሊገነዘበው በሚችለው መንገድ ግልጥልጥ አድርጎ ማስተማር ያስፈልጋል፡፡ አቡነ መልኬ ጼዴቅ እንዳሉት ሕዝባችን በእምነቱ ፍጹም መታመን ኖሮት ‹‹… ኢየሱስ ክርስቶስ ብለን ጌታችንን ስንጠራው የዳንን ወገኖች መድኅንም ያለን ሕዝቦች መሆናችንን፤ ክርስቶስ ከግብርናተ ዲያቢሎስ ነጻ ያወጣን መሆናችንን ማመናችንና መናገራችን ነው›› ወደሚልበት እውቀትና ድፍረት መድረስ አለበት (መልከ ጼዴቅ 1984፡37)፡፡
 የክርስቲያን መመዘኛው የተጠለለበት ተቋም ህንጻ ውበት አሊያም ተቋሙ የኖረበት ዘመን ርዝማኔና የምእመናን ብዛት ሳይሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በማመኑ ያገኘውን ዘላለማዊ ድኅነትና የሕይወት ዋስትና በእርግጠኛነት ተገንዝቦ እንደ ቀደሙት አባቶቹ፡- ከሰማይ የመጣ የእግዚአብሔርን ቃል በሥጋው ብቻውን ከሙታን ተቀድሞ እንደ ተነሳ እናውቃለን፤ በተነሳ ጊዜ አባቱ በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ ለእርሱ የሰጣቸው ምእመናን በትንሳኤ ይመስሉት ዘንድ እንግዲህ ወዲህ በቀድሞው ሰው አዳም ትእዛዝ ማፍረስ ምክንያት ፈርሰው በስብሰው አይቀሩም፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እሺ በጄ ብሎ እስከ ሞት በመድረሱ እነርሱ ፈጽመው ይድናሉ እንጂ (ዘቄርሎስ 1982፡309 ቁጥር 52) እና ያን ጊዜ በዚያ ወራት ነፍሳት ከሥጋቸው በተለዩ ጊዜ ከምድር በታች ወደ ሲዖል ይወርዱ ነበር፤ የሞት ቤቶችም እስኪመሉ ድረስ ወደ ገሃነም ይሄዱ ነበር፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባቱ ሥልጣን ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ግን ወደ መንግስተ ሰማያት ለመግባት አዲስ መንገድ አዘጋጀልን፤ እንግዲህ ወዲህ ወደ ገሃነም አንሄድም፤ ፈጣሪያችንን እንከተለዋለን እንጂ … (ዘቄርሎስ 1982፡80 ቁጥር 17)፡፡ እያለ በሚያውጀው የእምነት ቃሉ፥ በሚመራበት የክርስቶስ መንግሥት ትምህርትና ሥርዓት በመኖሩ (በፍሬው) (ዮሐ 15፥16) እንዲሁም የመንግሥቱን ዜጎች በማብዛት ሥራው ሊሆን የተገባ ነው (ማቴ 28፥20፤ ማር 16፥15)፡፡ ለዚህ መጽሐፍ መጻፍም ድምር ምክንያቶቹ እነዚሁ እንደ ዘመን አመጣሽ ትምህርት እየተቆጠሩ ያሉትና ቸል የተባሉ የእምነት ቃሎችና ፍሬዎች አማኝ በሚባለው ሕዝብ ውስጥ ስፍራ ማጣታቸው የፈጠረው ስጋት ነው፡፡ ‹‹ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ስለ ትምህርተ ድነት በኛ ቤተ ክርስቲያን ተረስቶ ኖሯል፤ ዋናውና የሕይወት ትምህርት ወደ አንድ ጎን ተጥሎ ነው የኖረው አሁንም ቢሆን ያሰበበት የለም፤ በቤተክርስቲያን የአመራር አካላትና በምእመናን መካከል እውነተኛው የእግዚአብሔር ፍቅር ፈጽሞ ተረስቷል፤ ከህፃናት ጀምሮ በየዕድሜ ክልሉ ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ትምህርተ ድነት ትምህርት መስጠቱ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ፈጽሞ አይታወቅም፤ ባሁኑ ጊዜ ሰባክያን ተብዬዎች በየደብሩ ተቀጥረው ምንም ፍሬ የሌለው ጩኸት ያስተጋባሉ›› በሚለው የገብረ ዮሐንስ ገለጻ ተስማማንም አልተስማማን፥ ነቀፍነውም ደገፍነው በእኔ እምነት ደግሞም እውነትን በሚፈልጉና በሚከተሉ ዘንድ ያለንበትን ተጨባጭ ሁኔታ ገልጦ የሚያሳይና የዘነጋነውን የቀደመችውን ቤተ ክርስቲያን ሕይወትና ተልዕኮ እንድናስብ የሚያነቃ ደወል ነው፡፡ በቅንነትና ሽንገላ በሌለበት ኅሊና ከመዘንነው የተጠራንበትን ትክክለኛ ተግባር መፈጸም በሚያስችለን የትምህርት፣ የአስተዳደር፣ የሥርዓትና የአምልኮ ሂደት ላይ አለመሆናችንን የሚያስገነዝብና ልባዊ ተሐድሶ እንድናደርግ የሚያሳስብ ሕያው መልእክት ነው፡፡ ‹‹ማን ያርዳ …›› እንዲሉ ከነበሩትና አሁንም ካሉት በላይ አስረጅ አይገኝምና መስማት ለሚችልና እውነትን ለሚፈልግ ሁሉ የ‹‹ተሐድሶ››ን ማለት የእምነት ለውጥ ሳይሆን እውነቱን ፈልጎ የማግኘትን፣ በፈጸሙት በደል ተጸጽቶ ንስሃ የመግባትንና በከበረው እውነትና መሠረት ላይ ጸንቶ የመኖርን አስፈላጊነት የሚያሳይ ፋና ነው፡፡

 ይህንን የተንደረደርኩበትን የገብረ ዮሐንስን አባባል የትምህርት ተሐድሶ አያስፈልግም በሚለው ግትር አቋሙ የሚታወቀው ማኅበረ ቅዱሳን ሳይቀር ይጋራዋል፡፡ ይህንንም በራሱ መንገድ እንዲህ በማለት ይገልጸዋል፡፡ … በሥነ ምግባር የተዋበ ዜጋን የማፍራት አቅሙ እያላት አልሰራችበትም (እንዲያውም ምግባረ ብልሹነት፣ ሙስና ወዘተ አሁን አሁን በቤተ ክርስቲያን ተንሰራፍቷል) የሚሉ ትችቶችና ዘለፋዎች ከየማዕዘኑ ሲሰነዘሩ ተደምጠዋል፡፡ ትችቱ የተጋነነ ቢሆንም እውነትነት የጎደለው ግን አይደለም፡፡ … ከዚህም በተጨማሪ ቤተ ክርስቲያን ወጣቱን በትምህርትና በሥነ ምግባር ኮትኩታ ለማሳደግና ለመያዝ አለመቻሏ ሳይነሳ የሚታለፍ አይደለም፡፡ … እንደዚሁም በ1982 እና በ1983 ዓ.ም በመናፍቃን (በተሐድሶ) እንቅስቃሴ ምክንያት በቤተ ክርስቲያን በቅንዓት የተሰበሰበውን ወጣት ተገቢውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት በመስጠት በሃይማኖትና በምግባር እንዲጎለምስ፣ አገልግሎቱም እንዲፋጠን አልሆነም፡፡ … ለእረኛነት ተመርጠው በጎቹን በለመለመ መስክ እንዲያሰማሩና ከተኩላ እንዲጠብቁ የተላኩ ካህናት ከተኙበት እንዲነሱ በየዕለቱ ከሚተረከው ዓለም አቀፋዊነት ሌላ የተሻለ ቀስቃሽ ከቶ ሊመጣ አይችልም፡፡ (ሐመር 1999፡53-54) የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሀብተ ብዙ በመሆኗ ብዙ ሥራዎች ይጠብቋታል፡፡ … በዚህ መሠረት ቢያንስ ሁለት መሠረታዊ ሥራዎች ይጠብቁናል፡፡ አንደኛ እውነተኛውን ትምህርት መስጠት … የዋሕ ልጆቿም በእምነት ቢቀበሉትም ዕውቀቱ አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ በዕውቀት ያልተደገፈ እምነት ደግሞ እየቆየ መላላቱ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ ለአማኞቿ የሚሆንና ችግሮቿን የሚፈታ ለሚጠይቋቸውም መልስ በመስጠት የሚያስጨንቁበት አንዳንዶችንም ከእሳት የሚያድኑበት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ይጠበቃል፡፡ ሁለተኛ መለየትና ማዘጋጀት፡- ምንም እንኳ ቀደም ብለን እንዳየነው የአዋልድን ቁጥር መወሰን ባይቻልም የመለየትና ለአገልግሎት የመለየት ሥራው ግን ለአራተኛው ሺህ ዓመት ሊገፋ አይገባውም፡፡ … እኛ ደግሞ በመግለጽ ጊዜ ስርዋጽ የገባባቸው ካሉ በማጥራት የተጓደሉትን በማሟላት ዲቃሎቹንና እውነተኞቹን አዋልድ በመለየት ለአገልግሎት ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ … ጌታ በሚገለጥ (ዳግመኛ በሚመጣ) ጊዜ በቀኝ የሚቆም መጽሐፍና ቅርስ የለም፡፡ የሚቆሙት ሰዎች ናቸው፡፡ …ካለበለዚያ ቆፍሮ በመቅበር መጠየቃችን አይቀርም፤ እንደ ገብረ ሀካይ (ሐመር 1999፡71)፡፡

ይህንን መሠረተ ሃሳብ መነሻው አድርጎ ትክክለኛውንና ቸል የተባለውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ገልጦ ለማሳየትና ከአጥፊዎች ለመከላከል የተዘጋጀው ይህ መጽሐፍ በሰባት ምዕራፎች የተከፈለ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኪዳናት›› የሚል ርዕስ የተሰጠው የመጀመሪያው ምዕራፍ ስለ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኪዳናት ምጥን፣ ነገር ግን አሁን ለደረስንበት አዲስ ኪዳናዊ ሕይወት መሠረት የሆኑ ሃሳቦችን ያስዳስሳል፡፡ ኪዳናቱ ከአንዱ ወደ ሌላኛው እየተሸጋገሩ ፍጹም ወደ ሆነው የመጨረሻው ኪዳን (አዲስ ኪዳን) እንዴት እንደ ደረሱ ያሳያል፡፡ በተለይም ሁለቱ ኪዳናት (ብሉይና ዐዲስ) ከተሰጡበት ዓላማና ከተመረቁበት ደም አንጻር በክብርም ሆነ በአገልግሎት እንደሚበላለጡ (አንዱ ከሌላው እንደሚለይ) ማሳየት የምዕራፉ ዋነኛ ዓላማ ነው፡፡ ምዕራፍ ሁለት ‹‹የሁለቱ ኪዳናት ቅኝት›› በሚል ርዕስ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡
ምዕራፉ ከዚህ በፊት ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ በማኅበረ ቅዱሳን ታትሞ ለሕዝብ በተሰራጨ መጽሐፍ መግቢያ ውስጥ የሚገኙ የእውነተኛው ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ትምህርት ይዘት የሌላቸው ሁለት ሃሳቦችን ነቅሶ በማውጣት በመጽሐፍ ቅዱስና በቀደሙት አባቶች አስተምህሮ የሚመዘንበት ክፍል ነው፡፡ በተለይም የመጽሐፉ አርታኢና የመግቢያው ጸሐፊ የ‹‹ሁለቱ ኪዳናት››ን (የብሉይና የአዲስን) ውሕደት አስመልክቶ ያስተላለፈውን መልእክት መነሻ በማድረግ ኪዳናቱ ሊዋሐዱ የማይችሉበትን መሠረታዊ ነጥቦች በስፋት ይዳስሳል፡፡ የማይዋሐዱትን ለማዋሐድ የሚደረገውንም መደፋፈር በብርቱ ይሞግታል፡፡ ድርጊቱም ክርስቲያናዊ ተግባር እንዳልሆነ ያስገነዝባል፡፡ ምዕራፍ ሦስት ‹‹ታሪካዊ ስህተትን ላለመድገም›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህ ክፍል መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት ያደረጉ ውሳኔዎች የተላለፉባቸውን የመጀመሪያዎቹን ሦስት ዓለም አቀፍ ጉባኤያት መንስዔና የተደረሱባቸውን ውሳኔዎች ያስታውሳል፡፡ በዚህ ክፍል የሚነሳው ሃሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን እውነት በ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍና መሰል የኅትመት ውጤቶች እየተሰራጩ ከሚገኙት ኢ-ክርስቲያናዊ ትምህርቶች ጋር በማነጻጸር ያሳያል፡፡ ይህም አንባቢው ትክክለኛውን መሠረተ እምነት ተገንዝቦ ትክክለኛ ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያስችል ዕድል ይፈጥራል፡፡ ለመግለጽ እንደሞከርኩት ይህ ክፍል ይህንን መጽሐፍ ጨምሮ ማናቸውንም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ስም ተጠልለው የሚሠራጩ ትምህርቶችን በተለይም በቀጣዩ ምዕራፍ የሚዳሰሱትን ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጎልተው የታዩትን ሦስት ቡድኖች አስተምህሮ ለመመዘንና የየትኛው ወገን ትምህርት ከሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ውሳኔዎች ጋር እንደሚስማማና እንደማይስማማ ለመለየት ያስችል ዘንድ እንደ ቱንቢ ሆኖ ተቀምጧል፡፡ እነዚህ ሶስት ዋነኛ ጉባኤያት ሲነሱ ሊታለፉ የማይገባቸው ሁለተኛው የኤፌሶን ጉባኤ (ምዕራባውያን የወንበዴዎች ጉባዔ የሚሉት) እና በምዕራባውያኑ አራተኛው ዓለም አቀፍ ጉባኤ በመባል የሚታወቀው የኬልቄዶን ጉባኤ (በኦርየንታሎቹ ጉባኤ ከለባት የሚባለው) የመጀመሪያዎቹ ሶስቱ ጉባኤያት ያስተላለፏቸውን የእምነት ድንጋጌዎች በግልጽ ለመረዳት ከሚያደርጉልን እገዛ አንጻር ጥቂት ስፍራ ተሰጥቷቸዋል፡፡ በዚህም ከእነዚሁ ጉባኤያት ጋር የተያያዙ ዋና ዋና ሃሳቦች ይዳሰሳሉ፡፡ ምዕራፍ አራት ‹‹የግጭቶቻችን ማጠንጠኛዎች - ቅባት፣ ካራ፣ ጸጋ›› በሚል ርዕስ የቀረበ ነው፡፡ ይህ ክፍል ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አንስቶ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የርስ በርስ ግጭቶችና ደም መፋሰስ ያስከተሉትን ሦስት በአመለካከት የተለያዩ ቡድኖች አስተምህሮ አስመልክቶ ምጥን፥ ነገር ግን ጠቃሚ መረጃዎችን የያዘ ነው፡፡ ክፍሉ ዛሬ ዛሬ የ‹‹ተዋሕዶ›› አማኝ ነኝ የሚሉን ቡድኖች አስተምህሮ (ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ) ከእነዚህ ከሦስት ቡድኖች (ካራ፣ ቅባት፣ ጸጋ) ቢያንስ ከአንዱ ተቀድቶ አለበለዚያም የአንዱ ቡድን ትምህርት ከሌላው ቡድን ትምህርት ጋር ተዳቅሎ ሲወርድ ሲወራረድ የመጣ በመሆኑ አስተምህሯቸውን አዳምጦና መዝኖ ከየትኛው ወገን እንደሆኑ መገምገም እንደሚያስችል ይታመናል፡፡ በተለይም በቀዳሚው ምዕራፍ የተዳሰሱትን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ውሳኔዎችና ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶች ከእነዚህ ቡድኖች አስተምህሮ ጋር በማነጻጸር የትክክለኛውን ተዋሕዶ ባህለ ትምህርት ለመገንዘብ የሚኖረው ጠቀሜታ ከፍ ያለ ነው፡፡ በምዕራፍ አምስት ‹‹ልዩነቶቻችን በመጽሐፍ ቅዱስ ሲዳኙ›› የሚል ሃሳብ ይነሳል፡፡ የዚህ ክፍል ዓብይ ዓላማ በዘመናት ሁሉ ለተነሱት ሃይማኖታዊ ችግሮች (ልዩነቶች) መንስኤው ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ያለን አመለካከት መለያየት መሆኑን በማስቃኘት የ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍ አዘጋጅ መሪጌታ ኃየሎምና አሳታሚው ማኅበር ማኅበረ ቅዱሳን የሚያራምዱት የእምነት አቋም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው የእግዚአብሔር ሃሳብ የሚቃረንና ጤነኛ የተዋሕዶ ትምህርት አለመሆኑን ማስረጃዎች ጠቅሶ ያሳያል፡፡
በአንጻሩም ቤተ ክርስቲያናችን የምትቀበላቸው ቀደምት ኦርቶዶክሳውያን አባቶች ያስተላለፉትን ትምህርት በእማኝነት በማቅረብ ጥንታዊውንና እውነተኛውን የተዋሕዶ ትምህርት ያስገነዝባል፡፡ ምዕራፍ ስድስት ‹‹ሕግና ትእዛዝ›› በሚል ሃሳብ ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ ሕግጋትና ትእዛዛት ለጸጋ ስፍራቸውን እንዳልለቀቁና እነርሱን መጠበቅ የጽድቅ ምንጭ እንደሆነ ሊሰብኩን ለሚሞክሩት ‹‹የሙሴ ደቀ መዛሙርት›› ሕግን የምንጠብቀው ገና ለመጽደቅ እያሰብን ሳይሆን በክርስቶስ ኢየሱስ የመስቀል ላይ ሥራ ስለ ጸደቅን መሆኑን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ እያቀረበ ያስረዳል፡፡ ምዕራፍ ሰባት ‹‹መቅደስ - የእግዚአብሔር መገለጫ›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህም መቅደስ የተባለውና ክርስቶስ የገባበት ሰማያዊ ስፍራ ‹‹መስቀል›. ነው ለሚለው የስህተት ትምህርታቸው መልስ የተሰጠበት ክፍል ነው፡፡ ከብሉይ ኪዳን የቤተ መቅደስ ጅማሬ አንስቶ ክርስቶስ የገባባት ተብላ እስከ ተገለጸችው ቤተ መቅደስ ድረስ ያለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሃሳብ በአጭሩ በማቅረብ ‹‹ቤተ መቅደስ የተባለው ጌታ የተሰቀለበት መስቀል ነው›› የሚለውን ኢ-ክርስቲያናዊ ፍልስፍና ይፋለማል፡፡ በአጠቃላይ መጽሐፉ ጤናማውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ባህለ ትምህርት ከጥፋት ለመከላከልና እውነቱን ገልጦ ለማሳየት መጽሐፍ ቅዱስንና የቀደሙ አባቶችን ትምህርት መሠረት አድርጎ የተጻፈ በመሆኑ ስለ እምነቱ ተገቢውን ግንዛቤ ለማግኘትና እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር የሚፈልግ ሁሉ ጠቃሚ ትምህርት እንደሚያገኝበት እምነቴ ነው፡፡

Sunday, March 20, 2016

በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት!

መዝ 150
ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ አመስግኑት፤ በኃይሉ ጠፈር አመስግኑት።
በችሎቱ አመስግኑት፤ በታላቅነቱ ብዛት አመስግኑት።
በመለከት ድምፅ አመስግኑት፤ በበገናና በመሰንቆ አመስግኑት።
በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት።
ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑት፤ እልልታ ባለው ጸናጽል አመስግኑት።
እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን፦ ሃሌ ሉያ።



Saturday, March 19, 2016

ያገር ያለህ ወይም የዳኛ ያለህ!!!


ከእውነቱ /ለውይይት የቀረበ/

 1/ መግቢያ

በድሮ ጊዜ ሰው በሰው ሲበደልና ፍትሕ ሲጓደል ‘ያገር ያለህ’ ወይም ‘የዳኛ ያለህ’ በማለት ይጮህ ነበር፤ ይህ ዓይነቱ የተበዳይ ጮኸትም ለትውልድ መርገም እንዳይሆን ተብሎ በአካባቢው በሚኖሩ እድሜና ልምድ ጠገብ ሺማግሌዎች ገላጋይነት/ዳኝነት የበደለ እንዲክስ የተበደለ ደግሞ እንዲካስ በማድረግ ጉዳዩ እልባት እንዲያገኝ ይደረግ ነበር፤ እኔም ዛሬ በዲሞክራሲ ስም በምድራችን ውስጥ እየሆነ ያለውን አጠቃላይ እንቅስቃሴ /በተለይ ባለውለታ በሆነችው በኦርቶዶክስ ቤ/ክ ውስጥ/ ቀረብ ብየ ስመለከት ይህ እውነተኛ የፍትህ ፈላጊዎች ያገር ያለህ ጩኸት ትዝ ብሎኝ ለኢትዮጵያውን በሙሉ ለውይይትና ለመፍትሄው ፍለጋ ጭምር የሽማግሌ ዳኞች ያለህ በማለት ጮኸቴን ላቀርብ ተገደድኩ። መቸም ለተወሰኑ ዓመታት ከአገሩ ራቅ ብሎ ለኖረ ኢትዮጵያዊ የአዲስ አባባ ገጽታ ቀየር እንደምትልበት ይታመናል፤ በርካታ ሕንጻዎችና መንገዶች ተሠርተዋል፤ ባቡርም ተጀምሮ ሕዝቡ እየተጠቀመበት መሆኑን በግልጽ ማየት ይቻላል፤ ለራሴ ሕሊና ታማኝ መሆን ስላለብኝ የሚታዩትን መልካም ነገሮች እሰየው በማለት፣ ደስ የማይሉትንና ደካማ የሆኑትን ደግሞ ለእርምት በግልጽነት ብጠቁም ሰውነቱን የሸጠ ካልሆነ በስተቀር ቅር የሚሰኝ እውነተኛ ሰው የሚኖር አይመስለኝም። እዚህ ላይ የሕንጻዎችና የመንገዶች መገንባት መልካም ቢሆንም፤ በራሳቸው ግን ያንድ አገር እድገት ዋና መስፈርቶች ናቸው ብሎ መውሰዱ ተገቢ አይመስለኝም፤ ሕንጻ ያለሰው ከንቱ የድንጋይ ክምር ብቻ ስለሚሆን! በሌላ መልኩ ደግሞ አብዛኛው ሕዝብ በኑሮ ችግር እየተጠበሰና ያገሪቱ ሃብት በጥቂቶች እጅ ውስጥ ሆኖ እያለ ኢኮኖሚስቶች በነፍስ ወከፍ የገቢ ስሌት ተመስርተው አድገናል ማለታቸው በሕዝቡ አጠቃላይ የኑሮ ምጥ ላይ የሚታየውን የህይወት ማቃሰት በግልጽ መካድ ነው የሚሆነው፤ የተመጣጠነ የሃብት ክፍፍል በሌለበት አገር ውስጥ ይህ ዓይነቱ የሂሳብ ቀመር እንዴት ሆኖ እውነተኛ ሚዛን እንደሚሆን ፈጽሞ አይገባኝም። ማየት ከመስማት የበለጠ ጥሩ መረጃ እንደሆነ ይታመናል፤ በመሆኑም አገራችን ኢትዮጵያ ምን እየሆነችና ወዴት እየተጓዘች እንደሆነ ከዚህ በፊት በጆሮዬ የሰማሁትን ዛሬ በዓይኔ አይቼ ለራሴ ህሊና ያገኘሁትን መረዳት በሚከተሉት ርእሶች ላይ ያለኝን ስጋት በትንሹ ላካፍል፡

 1. ፖለቲካውና ኢኮኖሚው በሕዝቡ ኑሮ ላይ ያስከተለው አውንታዊና አሉታዊ ተጽእኖ፣ /በሁለተኛ ደረጃ የሚታይ ይሆናል/

 2. በሐይማኖታዊ ተቋማት /በተለይ አብዛኛው ሕዝብ ችግሩን ለፈጣሪው የሚያቀርብባትና ለመጽናናት የሚሞክርባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን/ ውስጥ እየሆነ ያለው መተራመስ፤ በምድራችን ውስጥ በርካታ የሃይማኖት ተቋማት ይገኛሉ፤ ሆኖም ግን ከአገሪቱ ታሪክ ጋር ከፍተኛ ትስስር ያላትና በበርካታ ጠንካራ ጎኗ ጉሉህ ስፍራውን ይዛ የምትገኘው ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስለመሆኗ የሚክድ ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለኝም፤ ካለ ግን ልሟገተውና ጣሊያንን በምስክርነት ጠርቸ ላስመሰክርበት እችላለሁ፤ ይህ የሚሆነውም በራሳቸው ሙያ የሚተማመኑ እውነተኛ ዳኞች ከተገኙ ብቻ ነው። ስለዚች ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊ አጀማመር፣ ላገር ስላበረከተችው መልካም አስተዋጽኦ፣ በረጅም የታሪክ ሂደቷ ውስጥ ስለገጠሟት በርካታ ተግዳሮቶችና ስለከፈለችው ከፍተኛ መስዋትነት ማወቅ ለሚፈልግ /የራሱን ታሪክ ማወቅ ለሚፈልግ/ ወደ ኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ጎራ እንዲል እየጠቆምኩ፤ የዛሬውን መልእክቴን ግን በቤተ ክርስቲያኒቷ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ በስፍራው ላይ ተገኝቼ ያየሁትን እውነት ብቻ ጥንቃቄ ባለው መልኩ በዚህ የመጀመሪያ ጽሑፌ ላይ ለማቅረብ እሞክራለሁ።

   በዚች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከላይ ከፓትሪያሪኩ ጀምሮ በተዋረድ ወደታች የሚፈስ ያስተዳደር መዋቅር አለ፤ በተጨማሪ በርካታ መንፈሳዊ የትምህርት ማሰልጠኛዎች እያስመረቁ የሚያወጧቸው ወጣቶች ዐውደ ምህረቱን ሞልተውት የሰንበት ትምህርት የማስተማሩን ሥራ በሰፊው ተያይዘውታል፤ እኔን የገረመኝና የማላውቅበትን ብእር እንዳነሳ ያደረገኝ ግን በዚህ ግራና ቀኙን በማያውቅና እግዚአብሔርን በሚፈራ የዋህ ወገናችን መካከል በተለያየ መንፈሳዊ ስያሜ ተመስርተው የሚያካሂዱት የእርስ በርስ ጦርነት ነው፤ በዘመናት መካከል እኔ ‘አውቅልሃለሁ የሚልለት ተቆርቋሪ አጥቶ የማያውቅ’ አሳዛኝ ሕዝብ፤! በዚህ መሰረት ለዛሬ ማህበረ ቅዱሳንን እና ኦርቶዶክስ ተሐድሶ የሚባሉትን መንፈሳዊ ማህበራትን ከሥራቸውና ከሚያራምዱት ዓላማ አኳያ በማየት ፍርዱን ለእውነት ፈላጊዎችና ለወገን ተቆርቋሪ ወገኖች ስተወው፤ ለበለጠ መፍትሄ ፍለጋ ግን ቤተ ሰብ ከቤተሰብ፣ ጓደኛ ከጓደኛ፣ ባል ከሚስት፣ ጎረቢት ከጎረቢት፣ አንዳችን ከሌላው ጋር በእውቀትና በቅንነት ግልጽ ውይይት በማድረግ ለአገርና ለሕዝብ የሚጠቅመውን መደገፍ ለሁላችንም ይበጃል።

1/ ማህበረ ቅዱሳን ማነው?

ከማሕበረ ቅዱሳን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ሁላችንም ልንማረው የሚገባ ቁምነገር እንዳለ አምናለሁ፤ ዋና ዓላማው ግልጽ ባይሆንልኝም የአባላቱ ስብጥር፣ አባላት ለማህበራቸው የሚከፍሉት ዋጋና የርስ በርስ መደጋገፍ ይበል የሚያሰኝ ነው። እንዲሁም በየደብሩና በየገዳማቱ ለወደቁ ምስኪን ወገኖቻችን ከሚያደርገው መልካም ሥራ ባሻገር /እውተኛው ክርስትና የመስቀሉ ሥራ ውጤት እንጂ የመልካም ሥራ ውጤት አይደለም ወይም በሌላ አባባል የጽድቅ ሥራ ለመሥራት በመጀመሪያ በጸጋው አምኖ መጽደቅ አለበት ይላሉ ተሐድሶዎች/ ለባህልና ለቅርስ ጥበቃው ሥራ የሚከፍለው ዋጋም በቀላሉ የሚታይ ጉዳይ አይደለም። የዚህ ማህበር ሌላ መገለጫ ባህሪው የተለያየ የጉዞ ፕሮግራም በማዘጋጀት ሕዝቡ ገንዘቡን ከፍሎ በነጭ ልብስና በኢትዮጵያ ባንዲራ ከቦታ ቦታ እንዲንቀሳቀስ በማድረግ የሕዝቡ ማህበራዊ ትስስር እንዲበረታታ ያደርጋል፤ ሌላው አብዛኛው ሕዝብ አዲስና ልዩ ፈዋሽ ጸበል ተገኘ በተባለበት ስፍራና በየገዳማቱ ሁሉ አብዝቶ እንዲንቀሳቀስ ያደርጋል።
ማህበሩ በተጨማሪ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል ጥቂቶቹ፡- ሕንጻ መገንባትን፣ ንግድ መነገድን፣ የራሳቸውን አባላት ማሰልጠንን፣ አዳዲስ ታቦታት መትከልንና ስነጽሁፎችን በሰፊው አውጥቶ ማሰራጨት ሲሆኑ በእነዚህ ጽሁፎቻቸውም ላይ በዋናነት ተሐድሶን የሚያጥላላና የሚያወግዝ መልእክት በትኩረት ያወጣል። የማህበሩን እንቅስቃሴ ለማጠቃለልም፡  የውስጣቸውን/የልባቸውን ባላውቅም አለባበሳቸው በባንዲራ የታጀበ ነጭ ልብስ በመሆኑ የየዋሁን ሕዝባችንን ልብ ለዓላማቸው በቀላሉ ማማለል ይችላሉ፤ ችለዋልም፣  ለቅርስና ባህላዊ እሴቶቻችን ከፍተኛ ትኩረት በመስጠታቸውም ለአገር ብቸኛ ተቆርቋሪ ከነሱ ሌላ ፈጽሞ የሌለ አስመስሏቸዋል፣  ባህላዊ የቆሎ ትምህርት ቤቶች የበለጠ እንዲጠናከሩ ድጋፍ ያደርጋል፣ የገዳምና የምንኩስናን ኑሮ በማበረታት ምሁራን ሳይቀሩ ወደገዳም እንዲገቡ ያበረታታል፤ እንዲያውም ከውጭ አገር ኑሯቸው ተመልሰው ገዳም እንዲገቡ የተደረጉ እንዳሉ ይነገራል፣  ዘርዓ ያዕቆብን የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለወለታ በማድረግ ያወድሱታል፤ታሪኩንም ሕዝቡ እንዲያውቀው ለማድረግ የተደጋገመ ወርክሾፕ በስሙ አድርገውለታል/እያደረጉለትም ነው፣  መጽሐፍ ቅዱስ የማያውቃቸውን አዳዲስ ቅዱሳንን ሳይቀር ሕዝቡ እንዲያውቃቸውና ጽላት/ታቦት እንዲቀረጽላቸው ያደርጋል፤ አድርጓልም /ምሳሌ አርሴማ የምትባልን ነጭ ሴት/፣  ለአባላቱ ሁለንታዊ ድጋፍና ስልጠና በትጋት ከማድረጉም ባሻገር በምረቃና በሰርግ ላይ ከበሮና ጸናጽን ይዞ በመገኘት በሚያደርገው ሞቅ ያለ የሽብሸባ አምልኮ ከጴንጤዎች ጋር ውድድር የገባ አስመስሎታል፣  ሕንጻ ይገነባል፣ ንግድ ይነግዳል፣ ገንዘብ ይሰበስባል፣ አባላትን ያደራጃል /ከቀን ሰራተኛ እስከ ምሁር ባለስልጣናት ድረስ/፣  በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ የሚማሩትን ተማሪዎች በማሰልጠንና በእረፍታቸው ወቅት ወደየቤተ ሰቦቻቸው በመላክ ዓላማቸውን በሰፊው እንዲያስተዋውቁላቸው ያደርጋል //ይህን በተመለከተ አንድ በመንፈሳዊም ሆነ በታሪክ በቂ እውቀት የሌለው /ከስሜታዊነት በስተቀር/ የወንድሜ ልጅ መሳተፉን አጫውቶኛል//፣  ማህበሩ በሚያደርገው አጠቃላይ እንቅስቃሴ አባላቶቹንና የዋሁን ሕዝብ ፍጹም የጉልበት ሃይማኖተኛ እያደረገው እንደሆነ በአንዳንድ ደብር በስሜታዊ አባላቱ በኩል የሚታዩት የደም መፋሰስ ግጭቶች ይመሰክራሉ፣  አዳዲስ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ሥራ ላይ በሙያተኞቹ በኩል በሰፊው ይሳተፋል፣  ጎልቶ የሚታየው ሌላው ሥራው በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ ከሚገኙ አገልጋዮች መካከል አንዳንዶችን በመክሰስና ከሥራ በማሳገድ እስከ ቤተሰባቸው ችግር ላይ እንዲወድቁ ያደርጋል /ይህ በደል የደረሰባቸውን አንድ ሊቅ ይህ ጸሐፊ አናግሯል/፣  ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተሃድሶ ያስፈልጋታል የሚሉትን ጳጳሳት፣ ካህናት፣ መሪጌቶች፣ መነኮሳት፣ ዲያቆናትና አባላትን በሙሉ የፕሮቴስታንት ቅጥረኞችና ጸረ ኦርቶዶክስ ናቸው በማለት በመጽሄታቸው፣ በጋዜጣቸውና በአውደ ምህረት ላይ በማውጣት ከፍተኛ ዘመቻ ያደርጋል።
ይቀጥላል


Sunday, March 13, 2016

እነሆ ሁለቱ ኪዳናት!

መቅድም
 ‹‹እነሆ ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀው ይህ መጽሐፍ በ2002 ዓ.ም ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ በመሪጌታ ሃየሎም ተዘጋጅቶ በማኅበረ ቅዱሳን አሳታሚነትና አከፋፋይነት በተሠራጨው መጽሐፍ ውስጥ ለተላለፉት ኢ-ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮዎች መልስ ለመስጠት ቢሆንም በችግሮቹ ላይ ብቻ ከማትኮር ይልቅ አንባቢያን ሃሳቤን በቀላሉ እንዲረዳልኝ ያስችላሉ ያልኳቸውን መሠረታዊ የመጽሐፍ ቅዱስና የታሪክ እውነታዎች በማሰባጠር በማስረጃ አስደግፌ ለማቅረብ ሞክሬያለሁ፡፡ የዚህን ጽሑፍ ረቂቅ ያሳየኋቸው አንዳንድ ወንድሞች የሁለቱ ኪዳናትን ጸሐፊ፣ አርታኢና አሳታሚ ማኅበር የእምነት አቋም ተወራራሽነት ለመግለጽ የተጠቀምኩባቸውን የወል ዐረፍተ ነገሮች ባስተካክላቸውና በጸሐፊው ላይ ብቻ አትኩሬ መልእክቴን ባስተላልፍ እንደሚሻል አስተያየት ሰጥተውኛል፡፡ ሃሳባቸውን በሃሳብነቱ ብቀበለውም እንዳሉት ሶስቱን አካላት ነጣጥዬ ማየት ግን አልሆነልኝም፡፡ ለዚህም ምክንያቴ አርታኢው ከአርትዖት ተግባሩ ባሻገር የመጽሐፉን መግቢያ በማዘጋጀትና በመጽሐፉ የተካተተውን አስተምህሮ ‹‹ትክክለኛነት›› አጽንኦት ሰጥቶ በማስተጋባት እንዲሁም ማኅበሩ በሐመረ ተዋሕዶ 2001 ዓ.ም ልዩ እትሙ‹‹እቅበተ እምነት (አፖሎጂ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን›› በተሰኘ አምድ ሥር ‹‹ሁለቱ ኪዳናት ማኅበረ ቅዱሳን በተለያየ ጊዜ በመጻሕፍትና በመጽሔት በቃል ትምህርትም መናፍቃን ለዘሩት የጥርጥር ትምህርት መልስ የሰጠበት መጽሐፍ›› ነው ብሎ መገለጹ በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኘው የእምነት አቋም የጸሐፊው ብቻ ሳይሆን የአርታኢውና የማኅበሩ ጭምር መሆኑን የሚያረጋግጥ መሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ መጽሐፍ በተገለጠው የትምህርት አቋማቸው ብርሃኑ፣ ሐየሎምና ማኅበረ ቅዱሳን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸውና ብርሃኑንም ሆነ ሐየሎምን ሳመሰግን ሶስቱንም ማመስገኔ፣ እንዲሁም የብርሃኑንም ሆነ የሐየሎምን ሃሳብ ስቃወም ሁሉንም መቃወሜ መሆኑን ማስገንዘብ ተገቢ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ በእኔ እምነት ብርሃኑ ስለማያምንበት ነገር መንደርደሪያ አልጻፈም፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የእምነት አቋሙ ያልሆነን ትምህርት አሳትሞ አላሰራጨም፤ ለመናፍቃኑ የተሰጠ መልስ ነው እያለም አልፎከረምና ከምስጋናውም ሆነ ከወቀሳው ሊጎድሉ አይገባም ብዬ ሁሉንም ያለ ልዩነት እንዲጋሩት አድርጌያለሁ፡፡

እንደማምነው ካራ፣ ቅባት እና ጸጋ ሁሉም የተዋሕዶ አማኞች ናቸው፡፡ እንግዳ አመለካከት ሊመስል ቢችልም እንኳ ንስጥሮስ፣ አቡሊናርየስ፣ አውጣኬና ፓፓ ሊዮም ሳይቀሩ የዚሁ የተዋሕዶ ጽንሰ ሃሳብ አራማጆች ናቸው፡፡ ልዩነቱ የተፈጠረው ተዋሕዶን ለመግለጽ በተጠቀሙበት ቃል ትንታኔ ላይ ነው፡፡ አውጣኬ ተዋሕዶውን ያስረዳበት መንገድ መለኮት የሥጋን ባሕርይ መጥጦታል የሚል በመሆኑ መጠፋፋትን እንጂ የሁለቱን ባሕርያት መገናዘብ አያስረዳም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትም የለውም ተብሎ ተወገዘ፡፡ አቡሊናርየስ ክርስቶስ የሰው ነፍስ የለውም፤ በነፍሱ ምትክ ነፍስ የሆነለት መለኮት ነው አለ፡፡ በዚህም የክርስቶስን ፍጹም ሰውነት አጎደለ ተብሎ ተተቸ፤ ተለየ፡፡ ንስጥሮስም በበኩሉ የቃልና የሥጋ ተዋሕዶ ሁለቱ አካላት የየግል አቋማቸውን ጠብቀው የየራሳቸውን ሥራ እየሠሩ የሚኖሩበት ስምምነት (moral union) ነው አለ፡፡ እንደ እርሱ አባባል መለኮት በሥጋ ውስጥ አደረ እንጂ ባሕርያዊም ሆነ አካላዊ ተዋሕዶን አላስከተለም፡፡ ታዲያ ይህም ቢሆን የክርስቶስን አሐዱነት በተገቢው መንገድ አይገልጥም ተብሎ ተነቀፈ፡፡ በግልጥ እንደሚታወቀው የፓፓ ሊዮ አቋም ሁለት ባሕርያት በአንድ አካል የሚል ነው፡፡ ይህም ቢሆን ተዋሕዶን ምሉዕ በሆነ መንገድ አይገልጥም፡፡ አካል ያለ ባሕርይ ባሕርይም ያለ አካል ሊኖሩ አይችሉምና አንዱ የክርስቶስ አካል የማን ነው? የሚል ውዝግብ አስነሳ፡፡ ይህም አስተምህሮው በኦርየንታሎቹ ዘንድ ጥያቄ ላይ ወደቀ፡፡ በዚህም እንደሚታየው ፓፓ ሊዮም በሁለቱ ባሕርያት መኖር ላይ ከማትኮሩና የክርስቶስ አካል የመለኮት ነው ከማለቱ በቀር ተዋሕዶን አልተቃወመም፡፡ በመጀመሪያው የኤፌሶን ጉባኤ ተቀባይነት ያገኘው የቅዱስ ቄርሎስ የ‹‹ተዋሕዶ›› አስተምህሮ (ምንም እንኳ ምዕራባውያኑ በትክክል ባይረዱትና ከፓፓ ሊዮ የአንድ አካል ሁለት ባሕርይ፣ አልፎ ተርፎም ከአውጣኬ የመጠፋፋት ትምህርት ጋር ሊያመሳስሉት ቢሞክሩም) ሁለቱ አካላትና ሁለቱ ባሕርያት ሳይጠፋፉ፣ ሳይነጣጠሉ፣ ሳይቀላቀሉ አንዱ የሌላውን አካልና ባሕርይ ገንዘብ የተደራረጉበትን ከሁለት አንድ የመሆን ምስጢር (አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ ፈቃድ፣ አንድ ግብር) የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ይህም በተዋሕዶ የተገለጠው ኢየሱስ ክርስቶስ ያከናወናቸው ተግባራት ሁሉ ይህ የሥጋ ነው ያኛው ደግሞ የመለኮት ነው ተብለው ሳይከፈሉ በአንዱ በክርስቶስ (ሥግው ቃል) የተከናወኑ ናቸው የሚል ነው፡፡ በዚህ አስተምህሮ መሠረት እንደ ንስጥሮሳውያንና እንደ ኬልቄዶናውያን (ፓፓ ሊዎ) ድካሙን ለሥጋ ብርታቱንና ማዳኑን ለመለኮት የመስጠት ሙከራ በብርቱ የተነቀፈ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ከአውጣኬያውያንና ከነፓፓ ሊዮ የተዋሕዶ ሃሳብ በእጅጉ ይለያል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም በአቋም ደረጃ ይህንን ትቀበላለች፡፡

እንግዲህ በቤተክርስቲያናችን የሚታወቁት ሶስት ቡድኖች ምንም እንኳ ‹‹ተዋሕዶ›› ነን ቢሉም የተዋሕዶ አስተምህሯቸው ከላይ ከተገለጹት ተዋሕዶ ነን ባዮች ከየትኛው ምንጭ እንደተቀዳ በጥንቃቄ መፈተሽ ቀዳሚውንና ትክክለኛውን የተዋሕዶ እምነት ተገንዝቦ ለመከተልና ያለ እውቀት ከሚሰነዘር ትችት ለመታቀብ ያስችላል፡፡ ከዚህ የተነሳ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያው የኤፌሶን ጉባኤ ያጸደቀችውን የተዋሕዶ ጽንሰ ሃሳብ ከነአውጣኬና ከነንስጥሮስ የተዋሕዶ ትርጓሜ ለመለየትና አንባቢያንን ከድንጋሬ ለመጠበቅ ‹‹ትክክለኛው›› የሚል ገላጭ ቃል ተጠቅሜያለሁ፡፡ በኢትዮጵያውያኑ የእምነት ጎራዎች (ካራ፣ ቅባት፣ ጸጋ) አስተምህሮዎች ላይ የመጻፉ ጉዳይ ብዙም አልታየኝ ነበር፡፡ ሆኖም የአንዳንድ ጊዜ የገጠማቸው ግለሰቦችና ቡድኖች አስተምህሮ ምንጭ በብዙሃኑ ስለማይታወቅ ከነሰባልዮስና ከነአውጣኬ ወገን ተሰልፈው የነቄርሎስን እምነት እንከተላለን እያሉ እውቀቱ የሌለውን ምእመን ከማደናገር አልፈው በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጠውን የእግዚአብሔር ቃል በመቃወም ላይ ስላሉና የእነርሱን ፈለግ ያልተከተሉትን ሁሉ እያሳደዱ እውነተኛ መስለው ለመታየት ሌት ከቀን እየተጣጣሩ ስለሚገኙ የአሳዳጆቹም ሆነ ተሐድሶ ናቸው በሚል ሽፋን እየተሳደዱ ያሉት ወገኖች ማንነት በግልጽ ይታወቅ ዘንድ እንዳልኩት ብዙም ትኩረት ላደርግባቸው የማልፈልጋቸውን ሶስት ቡድኖች አስተምህሮ ከመረጃ መጻሕፍት አሰባስቤ ለማቅረብ ተገድጃለሁ፡፡ በተለይ ማኅበረ ቅዱሳን የነቄርሎስን የተዋሕዶ ለምድ ለብሶ የሚያቀነቅነው ‹‹ሰባልዮሳዊ›› እና ‹‹አውጣኬያዊ›› ተዋሕዶ ፍንትው ብሎ ይታይና ትክክለኛው ማንነቱ ይገለጥ ዘንድ ይህንን ማድረጌ ተገቢ እንደሆነ አምናለሁ፡፡ በተረፈ ወደ መሠረታዊው ሃሳቤ ለመሸጋገር አንድ ጸሐፊ በተናገሩት ቁም ነገር ሃሳቤን ልቋጭ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህ ትውልድ የሚፈልገውን እውነት በውስጧ ይዛለች፡፡ ነገር ግን እውነቷን ባልተዛባና ትውልዱ በሚፈልገው መንገድ ገልጣ ልታቀርብ አልቻለችም አብዛኛዎቹ የስብከት መድረኮቿ የተሞሉት ሌላውን በመንቀፍ ወግና ሥርዓትን ታሪክን በመተረክ ላይ በተመሠረቱ ስብከቶች ነው፡፡ በማኅበርና በግል ደረጃ በጽሑፍ የሚተላለፉ መልእክቶችም ይኸው ገጽታ ነው ያላቸው፡፡ ያለባትን ችግር በመረዳት በሚፈለገው ሁኔታ ወንጌልን የሚሰብክ አንድ ሰው ቢነሳ እንኳ በጥርጣሬ መንፈስ እየታየ በተለያዩ ውንጀላዎች ከመድረክ የሚወገድበት መንገድ ይፈለጋል (አግዛቸው ቀ.አ፡5)፡፡

ለእኔም እውነታው ይኸው ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ የአውጣኬያዊውና የሰባልዮሳዊው ተዋሕዶ ትምህርት በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ሠርጎ መግባቱ ነው፡፡ እንደ ተባለው የከበረ እውነት አለን፤ ነገር ግን በዘመናት ሂደት ውስጥ ተቀብሯል፡፡ ስለዚህ የተቀበረው እውነት ተፈልፍሎ ሊወጣና ምእመኑ በግልጥ እንዲያውቀው ሌሎችም ቢሆኑ መሠረታዊውን የተዋሕዶ አስተምህሮ ተገንዝበው አጓጉል ነቀፋዎችን ከመሰንዘር እንዲቆጠቡ ማድረግ ይገባል፡፡ ለዚህም ብርቱ ትግል፣ ለመታገልም እውነቱን ከሃሰቱ መለየት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከጥላቻ በጸዳ መንፈስ ከማንበብና ከመወያየት የተሻለ መንገድ የለም፡፡ አለመደማመጥና ምን ያመጣሉ ለሮም ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያንም እንዳልበጃት ከታሪክ መማር ይገባል፡፡ ስለዚህ ንባብዎ እውነቱን ለመፈለግና በመመካከር መልካሙን መንገድ ለመከተል ይሆን ዘንድ ከልቤ እመኛለሁ፤ እጸልያለሁም፡፡ ሌላው ምናልባት ላሳውቀው የሚገባኝ መልሱ የዘገየበትን ምክንያት ነው፡፡ እንደ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ጊዜ እስኪደርስ ነው ብዬ ባስብም ይህ ጽሑፍ ከታሕሣስ 2003 ዓ.ም ጀምሮ እስከዚህ ጊዜ ድረስ በእጄ ላይ እየተንከባለለ ድፍን አምስት ዓመታት ማስቆጠሩን ሳስበው በጥቂቱ አዝናለሁ፡፡ በሌላ መልኩ ምንም እንኳ እንዲታተም ብዙ ጊዜ ተመኝቼ ባይሳካልኝም እንደ ቀልድ ባለፉት በእነዚያ ዓመታት ውስጥ እኔ ባደግሁበት ዕድገት ልክ የማደግና የመብሰል ዕድል አግኝቷልና ደስ ይለኛል፡፡ ምናልባትም ቀድመውና ዘግይተው ከተጻፉ ጓደኞቹ ይልቅ የመታተሙን ቅድሚያ እንዲያገኝ የረዳው ይኸው ሳይሆን አይቀርም፡፡ እንዲህም ሲሆን ፍጹም ነው ማለቴ አይደለም፡፡ ይልቁንም ገና ‹‹ሁ›› ስለሆነ ከስህተትና ከችግር የጸዳ ላይሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ አንብባችሁ በምትሰጡኝ ምክርና ተግሳጽ ታግዤ ስህተቴን በማረም የተሻሉ ሥራዎቼን ይዤ እንደምቀርብ ተሥፋ አደርጋለሁ፡፡ እስከዚያው መልካም ንባብ!!!
                         ጸሐፊው