Sunday, May 26, 2013

የክርስቲያኖች ሰንበት የሚል ሕግ አለ?


 ታሪክ፤
እሁድን እንደመንፈሳዊ የእረፍት ቀን መቁጠር ከመጀመሩ በፊት ቀደምት ሕዝቦች የፀሐይ ቀን አድርገው ያከብሩት ነበር። በእንግሊዝኛው/ Sun- day / የሚለው ቃል ትርጉም የሚያመለክተው ያንን ሲሆን መነሻ ስርወ ቃሉም  የአንግሎ ሳክሶን ቃል ከሆነው / sunnandei/ ከሚለው የመጣ ቃል ነው። ትርጉሙም የፀሀይ ቀን ነው።  እሁድ ወይም /ዮም ርሾን יום ראשון/ ማለት የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን ማለት ነው። ዮም ርሾን እንደአንድ ቁጥር/ 1/  ሆኖም ያገልግላል። የአይሁድ ሰንበት፤ ሰባተኛው ቀን እንደመሆኑ መጠን የእሁድን የመጀመሪያ ቀን መሆንን ከአንድ ተነስተን ብንቆጥር ያረጋግጥልናል። ይህ የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን/ እሁድ/ በጥንት ሮማውያን ዘንድ ከሥራ ሁሉ የእረፍት ቀን ሆኖም አገልግሏል። ቆስጠንጢኖስ ንጉሥ መጋቢት 10/ 313 ዓ/ም ይህንን ቀን የሮማውያን ግዛት እረፍት ቀን ይሆን ዘንድ በአዋጅ አጽድቆታል።  ስለእሁድ የመጀመሪያ ቀን መሆንና በጥንታዊው ስያሜ ዙሪያ ታሪካዊ ዳራውን በአጭሩ ካመላከትን መንፈሳዊ አመጣጡን ደግሞ በጥቂቱ እንመልከት።
1/ ሰባተኛ ቀን፤
ሰንበት የሚለው ቃል ከእብራይስጡ Shabbat (שַׁבָּת) ከሚለው ቃል የመጣ ሲሆን ቀጥተኛ ትርጉሙም ከድካም ማረፍ ወይም ሥራን ማቆም (to cease or to desist from exertion) ማለት ነው። ሰንበት እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ለእስራኤል ከሰጠው አሥርቱ ትእዛዛት ውስጥ አንዱ ነው።
 ኦሪት ዘጸአት 20:8-11  የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ።ስድስት ቀን ሥራ ተግባርህንም ሁሉ አድርግ:: ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክህ ሰንበት ነው አንተ፥ ወንድ ልጅህም፥ ሴት ልጅህም፥ ሎሌህም፥ ገረድህም፥ ከብትህም፥ በደጆችህም ውስጥ ያለ እንግዳ በእርሱ ምንም ሥራ አትሥሩ:: እግዚአብሔር በስድስት ቀን ሰማይንና ምድርን፥ ባሕርንም፥ ያለባቸውንም ሁሉ ፈጥሮ በሰባተኛው ቀን ዐርፎአልና ስለዚህ እግዚአብሔር የሰንበትን ቀን ባርኮታል ቀድሶታልም።
የቃሉ ትርጉምና እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ሰንበት ከድካምና ከሥራ ሰዎችና እንስሳት የሚያርፉበት የእረፍት ቀን ነው። በተለይ ከሰንበት ጋር ተያይዞ የተጠቀሱት ሎሌዎች፣ የቤት ሠራተኞች፣ ባሪያዎችና ከብቶች በዚያን ጊዜ እጅግ አድካሚ ሥራ ይሠሩና ይለፉ የነበሩ ናቸው። ሰለዚህ ሰንበት በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ከሠራው ሥራ በሰባተኛው ቀን እንዳረፈ ሁሉ ከሥራና ከድካም ማረፍ ጋር የተያያዘ ነው። ለዚህ ነው ሰውን ብቻ ሳይሆን የአምልኮ ፕሮግራም ማድረግ የማይችሉትን ከብቶችንም የሰንበት ትእዛዝ የሚያጠቃልለው።
ከዚህ በተጨማሪ ሰንበት በእግዚአብሔርና በእስራኤል ሕዝብ መካከል የተደረገ የምልክት ቃል ኪዳን ነው። እንደማናቸውም የብሉይ ኪዳን ሕግ ሰንበትም በማያከብሩት ላይ መርገምና ፍርድ የሚያመጣም ትእዛዝ ነው።
ኦሪት ዘጸአት 31:12-17 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው። ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብለህ ንገራቸው። እኔ የምቀድሳችሁ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቁ ዘንድ በእኔና በእናንተ ዘንድ ለልጅ ልጃችሁ ምልክት ነውና ሰንበቶቼን ፈጽሞ ጠብቁ። ስለዚህ ለእናንተ ቅዱስ ነውና ሰንበትን ጠብቁ የሚያረክሰውም ሰው ሁሉ ፈጽሞ ይገደል፥ ሥራንም በእርሱ የሠራ ሰው ሁሉ ከሕዝቡ መካከል ተለይቶ ይጥፋ። ስድስት ቀን ሥራን ሥራ ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር የተቀደሰ የዕረፍት ሰንበት ነው በሰንበት ቀን የሚሠራ ሁሉ ፈጽሞ ይገደል። የእስራኤልም ልጆች ለልጅ ልጃቸው ለዘላለም ቃል ኪዳን በሰንበት ያርፉ ዘንድ ሰንበትን ይጠብቁ። እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን በስድስት ቀን ስለ ፈጠረ፥ በሰባተኛውም ቀን ከሥራው ስላረፈና ስለ ተነፈሰ፥ በእኔና በእስራኤል ልጆች ዘንድ የዘላለም ምልክት ነው።
ብዙ ጊዜ ሰንበት ተብሎ በልማድ የሚታወቀው ሥራ የማይሠራበትንና የአምልኮ ፕሮግራሞች የሚካሄዱበትን ቀን ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ግን ሰንበት የሚባለው በእስራኤልና በእግዚአብሔር ብቻ የተገባን ቃል ኪዳን ነው። በዚያ ቀን "የአምልኮ ፕሮግራም የማይካፈል ይሙት" ሳይሆን ትእዛዙ የሚለው "በሰንበት ቀን የሚሠራ ሁሉ ፈጽሞ ይገደል" የሚል ፍርድና ቅጣት ያለው ነው። በብሉይ ኪዳንም ይሁን በአሁኑ ዘመን እስራኤላውያን ሰንበትን የሚጠብቁት ቅዳሜ ነው፡፡
2/ የመጀመሪያው ቀን
ክርስቲያኖች የአይሁድ ሰንበትን ይጠብቁ ዘንድ አልታዘዙም። በእርግጥ እስራኤላዊ ሆነው ወደ ጌታ እምነት የሚመጡ ሰንበትን መጠበቅ ይችላሉ አልተከለከሉም። ነገር ግን ሰንበት ለክርስቲያኖች የተሰጠ ትእዛዝ አይደለም። እስራኤላዊ ባልሆኑ አህዛብ ክርስቲያኖችም ዘንድ በአዲስ ኪዳን ሰንበት ሲጠበቅ ይሁን ሰንበትን እንዲጠብቁ ሲታዘዙ አናነብብም። ይህ ብቻ አይደለም፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ክርስቲያኖች ይጠብቁትና ያከብሩት ዘንድ የተሰጠ ምንም ዓይነት ቀን ወይም በዓል የለም። ክርስትና የቀኖችና የበዓላቶች አክብሮ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ የሆነ ሕይወት ነውና።
ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2:16-17 እንግዲህ በመብል ወይም በመጠጥ ወይም ስለ በዓል ወይም ስለ ወር መባቻ ወይም ስለ ሰንበት ማንም አይፍረድባችሁ። እነዚህ ሊመጡ ያሉት ነገሮች ጥላ ናቸውና፥ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው።
በአዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች በዚያን ዘመን የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን በሆነው እሁድ እሁድ ይሰበሰቡና ጌታን እያመለኩ የጌታን እራት ይካፈሉ እንደነበር ተጽፎአል፦
የሐዋርያት ሥራ 20፥7 ከሳምንቱም በመጀመሪያ ቀን እንጀራ ለመቁረስ ተሰብስበን ሳለን፥ ጳውሎስ በነገው ሊሄድ ስላሰበ ከእነርሱ ጋር ይነጋገር ነበር፥ እስከ መንፈቀ ሌሊትም ነገሩን አስረዘመ።
ይህ የሳምንቱ መጀመሪያ የሆነው እሁድ ቀን ጌታ ኢየሱስ ከሙታን የተነሳበትም ቀን ሰለ ነበር አንዳንዴም የጌታ ቀን ተብሎ ይጠራል፦
የሉቃስ ወንጌል 24:1-5 ነገር ግን ከሳምንቱ በመጀመሪያው ቀን ያዘጋጁትን ሽቱ ይዘው ከእነርሱም ጋር አንዳንዶቹ ወደ መቃብሩ እጅግ ማልደው መጡ። ድንጋዩንም ከመቃብሩ ተንከባሎ አገኙት፥ ገብተውም የጌታን የኢየሱስን ሥጋ አላገኙም። እነርሱም በዚህ ሲያመነቱ፥ እነሆ፥ ሁለት ሰዎች የሚያንጸባርቅ ልብስ ለብሰው ወደ እነርሱ ቀረቡ፤ ፈርተውም ፊታቸውን ወደ ምድር አቀርቅረው ሳሉ፥ እንዲህ አሉአቸው። ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቶአል እንጂ በዚህ የለም።
የዮሐንስ ራእይ 1፥10 በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፥ በኋላዬም የመለከትን ድምፅ የሚመስል ትላቅ ድምፅ ሰማሁ፥
አዲስ ኪዳን የሚሰጠው ፍንጭ ክርስቲያኖች ጌታ ኢየሱስ በተነሳበት ቀን እሁድ እግዚአብሔርን እንደሚያመልኩና የጌታን እራት እየቆረሱ ሕብረት እንደሚያደርጉ ያመለክታል። ይሄንን ሲያደርጉ ግን ሰንበትን እያከበሩ አይደለም፡፡ ሰራተኞቻቸውንና ከብቶቻቸውን ወዘተ ቀኑን ሙሉ ከድካማቸው እያሳረፉና ሰው ቢተላለፈው ፍርድ ያለበትን በሕግ የተደነገገውን ሰንበትን እያከበሩ አይደለም። በአዲስ ኪዳን የቀንና የምግብ እርኩስና ቅዱስ የለም! የምግብና የበዓላት ትእዛዛት ሁሉ በሕግ ውስጥ ካለ የሥርዓት ሸክምና ለጽድቅ የሚደረግ ልፋት ሊያሳርፈንና ወደ እረፍቱ ሊያስገባን የመጣው የክርስቶስ ጥላዎችና ምሳሌዎች ብቻ ናቸው። የክርስቶስ የሆኑትስ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ እነርሱም ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብና እርሱን ለማግኘት ከሚደረግ የሥርዓት ጥረትና ድካም እርሱን አግኝተው አርፈዋል። ወደ እግዚአብሔር ሰንበትም ገብተዋል።
ወደ ዕብራውያን 4:9-10 እንግዲያስ የሰንበት ዕረፍት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ቀርቶላቸዋል። ወደ ዕረፍቱ የገባ፥ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ፥ እርሱ ደግሞ ከሥራው አርፎአልና።
ስለዚህ ክርስቲያኖች ምንም እንኳን ታሪካዊ አመጣጡ ለብዙ የታሪክ ተመራማሪዎችም እንኳን ግልጽ ባልሆነ እሁድ እሁድ የመሰብሰብና እግዚአብሔርን የማምለክ ልምድ ቢኖራቸውም፤ ይሄን ግን እንደ ሰንበት መውሰድ ወይም ይባስ ብሎ ሰንበት ከቅዳሜ ወደ እሁድ እንደተቀየረ ማሰብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የለውም። እሁድ የክርስቲያኖች ሰንበት አይደለም። የብሉይ ኪዳኑን ሰንበትን የመጠበቅ ትእዛዝ ለአዲስ ኪዳን አማኞች አልተሰጠም። ማንም ግን ሰንበትን ማክበር ቢፈልግ፤ ሰንበት ሕግ ነውና ሕጉ ደግሞ ያለ መርገም አልመጣምና በሰንበት ምንም አይነት ሥራ ቢሠራ ራሱን ከሕግና ከእርግማን በታች እያደረገ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግና ከእርግማን በታች ሳንሆን ከጸጋ በታች ሆነን በነጻነት እንድንኖር ከሕግ እርግማን ሊያመጣን መጣ እንጂ እንደገና ለሥርዓትና ለበዓላት ባርነት አልጠራንም።
ወደ ገላትያ ሰዎች 3፦11-13  ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸውና፤ በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና።ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎአልና ማንም በእግዚአብሔር ፊት በሕግ እንዳይጸድቅ ግልጥ ነው። ሕግም ከእምነት አይደለም ነገር ግን፤ የሚያደርገው ይኖርበታል ተብሎአል። በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን፤
3/ ማጠቃለያ፣
የአይሁድ ሰንበት በእግዚአብሔር በራሱ ከፍጥረት ሥራው በማረፍ ለአይሁዳውያን የተሰጠ የተለየ ቀን ነው። በኋለኛው አዲስ ዘመን ደግሞ ዓለሙን ሁሉ በልጁ ደም ካዳነ በኋላ የመጀመሪያውን ቀን ወይም የጌታ ቀን የተባለውን ዕለት በአይሁዳውያን ሰንበት መልኩ በማረፍ፤ እናንተም ዕረፉ በማለት ሕግን አልሰጠም። ስለዚህም የክርስቲያን ሰንበት የሚባል ቀን የለም። ትንሣዔውን፤ ዕርገቱን፤ ቅዱሳን በጌታ ቀን ሲጸልዩ መታየታቸው በራሱ የዕረፍት ቀን የመሆንን ሕግ ሳይሆን የሚያመለክተው መንፈሳዊ ተግባራትን በማድረግ፤ ቃሉን በማሰብና በመጸለይ ብናሳልፍ መልካም እንዲሆንልን የሚያመለክት ነው። ለጸሎት፤ ለቅዳሴ፣ ለጾምና ጸሎት መፋጠን የተለየ ድንጋጌ መሰጠቱን አያመለክትም። ቅጠል በመበጠስ፤ ከአንድ ምዕራፍ በላይ መንገድ በመሄድ ወይም ሥራ በመስራታችን ለቀኑ ከተሰጠ ድንጋጌና የውግዘት እርግማን ለመጠበቅ ተብሎ አይደለም። እንደአይሁድ ሰንበት የሚያከብሩ ሰዎች  አልፈው ተርፈው፤ የእመቤታችንን 33 በዓላተ ቀኖቿን እንደእሁድ ሰንበት ያላከበረ ፈጽሞ የተወገዘ ይሁን በማለት ብዙ ሰንበታት ፈጥረውልን ይገኛሉ። /መቅድመ ተአምር/ ከዚያም  ባለፈ ሰንበተ ክርስቲያን ተብላ በሰዎች የተሰየመችው ይህች ቀን በሰው አምሳል ከመጥራት ተጀምሮ መልሷን እስከመፈለግም ተደርሷል።«ሰዓሊ ለነ ሰንበተ ክርስቲያን ቅድስት፣ለውሉደ ሰብእ መድኃኒት፣ ወእስከ ለዓለም ሰፋኒት» ትርጉም--ለሰው ልጆች መድኃኒትና እስከዘለዓለም ገዢ የሆንሽ፣ ቅድስት የክርስቲያን ሰንበት ሆይ ለምኝልን ማለት ነው። ሰንበት የተባለው ክርስቶስ ራሱ ነው የሚሉ ደካማዎች ቢኖሩም ክርስቶስን « ለምኝልን» ሊሉ ቢመኙ እንዴትና ከማን? በሚል ጥያቄ ማጣደፋችን አይቀርም። ይልቁንም ይህ የክርስቲያን ሰንበት እንዳለ ከሚያስብ አእምሮ የመነጨ ትምህርት ነው። አንዲቱን ቀን በሰው አንደበት እያናገሩ፤ ከሷ ምላሽ መጠበቅ ክርስቲያናዊ ትምህርት አይደለም።
ብዙ አይሁዶች ከይሁዲነት ወደክርስትና ሲመለሱ ቀዳሚት ሰንበትን በነበራቸው ልምድ ዓይነት የክርስቲያን ሰንበት አድርገው ያከብሩ ነበር። የቀዳሚት ሰንበትን የማክበር ባህል በሀገራችን እስካሁን ድረስ በብዙ ቦታዎች አልተቀየረም። ቀዳሚት ሰንበት የአይሁድ በዓል እንጂ የክርስቲያኖች እንዳልሆነ በ363 ዓ/ም የላኦዲቂያ ጉባዔ አንቀጽ 29 ላይ ተደንግጎ ነበር።  የክርስቶስ ሞትና ትንሣዔ የተለየች ቀንን ለመባረክና የእረፍት ቀን ለማድረግ ሳይሆን ክርስቲያኖች ከነበረን የሕግ ሸክም ሊያሳርፈን መሆኑን ልንረዳ ይገባል። እሁድን በጸሎት፤ በምሥጋናና በቅዳሴ ብናከብር ለክርስቲያን የተሰጠ ልዩ ቀንና ሰንበት ስለሆነ አይደለም። ምክንያቱም በእግዚአብሔር ቀናት ውስጥ ርጉምና ቅዱስ የሚባል የለም።

Wednesday, May 22, 2013

የጤና መረጃ ( በሰውነታችን ከመጠን ያለፈ ስኳር መከማቸት ችግር )

ጣፊያ የተባለው የሰውነታችን ክፍል ለደም ዝውውር የሚያገለግለውን ኢንሱሊን የተባለውን ንጥረ ነገር ማምረት ሳይችል ሲቀር ወደ ደም ሴል መሄድ የሚገባው ስኳር ክምችት ይፈጠራል። ከመጠን በላይ የስኳር መገኘት ችግርም «የስኳር በሽታ» ወይም /Diabetes/ ይባላል። ቁጥር 1 ተብሎ የሚጠራው የስኳር በሽታ በዘር ሊወረስ እንደሚችል ሲነገር፤ ቁጥር 2 ተብሎ የሚጠራው የስኳር ህመም ግን በአብዛኛው ከኑሮ ምቹነትና ከሰውነት እንቅስቃሴ ጉድለት የሚመጣ ነው። ሰዎች በተፈጥሮአችን በመንቀሳቀስ፤ በመውጣት፤ በመውረድ፤ ላብና ወዛችንን አንጠፍጥፈን በመስራት እንድንኖር ተደርገን ወደዚህ ምድር የመጣን ቢሆንም ኑሮአችን ምቹና ድካም በማይጠይቅ ሁኔታ ውስጥ እንድንኖር በሚያደርግ ቅንጦት ውስጥ በዕለታዊ ምግባችን ውስጥ በስብና ቅባት ክምችት የተነሳ የደም ዝውውራችንን እንዲዛነፍ እናደርገዋለን። ስለሆነም ለሰውነታችን ሥርዓተ ዑደት /metabolism/ በስራ ወይም በአካል እንቅስቃሴ እናስተካክል። ከመጠን በላይ በሆነ የሰውነት ግዝፈትና ድሎት ራሳችንን ከምንጎዳ በማጣት ሰው ለተራቡ ያለንን እናካፍል።

Tuesday, May 21, 2013

«እግዚአብሔርን ወደማወቅ መድረስ


የሥነ አእምሮ፤ የፍልስፍናና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ሪቻርድ ፕራት ሃይማኖትን ሰዎች የሚጠቀሙት ከሚመጣባቸው ቁጣና ቅጣት በማምለጥ ሰላምና ዘላለማዊ ዋስትና አገኝበታለሁ ብለው ለመጠለያነት ነው ይላሉ። ከዚያ ተቋም ውጪ ዋስትና አለ ብለው አያስቡም። ሰላምና ዋስትና መፈለግ በራሱ ጥሩ ቢሆንም ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት በራሳቸው መንገድ የተገለጸውን ሰላምና ዋስትና መስጠት ወይም ማሰጠት አለመቻላቸው እውነት ነው። እንደሃይማኖቶቹ ልዩነት የተለያየ የደኅንነት መንገድ የለም። ምክንያቱም ዋስትናና ሰላም በተቋም ደረጃ ለተከታዮች የሚከፋፈል ስጦታ ሳይሆን  መስጠት ከሚችልና ዋስትና ካለው የሰላም ባለቤት ከራሱ ከእግዚአብሔር ለጠየቁትና ለለመኑት በቀጥታ የሚሰጥ እንጂ እግዚአብሔር ለሃይማኖት ተቋማት በተለይ አድሎ፤ እነርሱ ደግሞ በተናጠል ወደእነሱ ለመጣ እንዲያድሉ የተደረገበት መንገድ በፍጹም የለም። እግዚአብሔርን አባት ብለው ለሚጠሩት አማኞች ሁሉ አባት  የሚሆነው ልጅ የመባልን ጸጋ በነጻ ማግኘታቸውን አምነው ለተቀበሉ ብቻ ነው ይላሉ ዶ/ር ፕራት።
« በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና» ገላ 3፤26
በማመን የሚገኘውን ጸጋና ልጅነትን በሃይማኖት ተቋም በኩል መቀበል አይቻልም። ዛሬ በዚህ ዓለም ላይ የሃይማኖት ተቋማት መብዛት ዋናው ምክንያት ከሌላው የተሻለ ሰላምና ዋስትናን ለተከተለን ሁሉ እናድላለን ብለው ስለሚሰብኩ ብቻ ነው። በየድርጅቶቹ ውስጥ ያሉ ተከታዮችም በዚያ ተቋም በኩል ሰላምና ዋስትና ያገኙ ስለሚመስላቸው እኔ ኦርቶዶክስ ነኝ፤ እኔ ካቶሊክ ነኝ፤ እኔ ይሁዲ፤ እኔ እስላም፤ እኔ ፕሮቴስታንት ነኝ፤  ጴንጤ ነኝ፤ እኔ ደግሞ ሙሉ፤ ጎዶሎ፤ ቤዛ፤ መሠረት፤ሞርሞን፤ ወዘተ ነኝ እያሉ መታመኛና ዋስትና ያለበት የራሳቸውን ተቋም ትክክለኛነት ይናገራሉ። ሁሉም ራሱን ከሌላው የተሻለ የዋስትናና የሰላም ምንጭ የሆነውን ፈጣሪ ለመስጠት ብቃቱና ውክልናው አለኝ ብሎ ለራሱ ይመሰክራል።  እንዲያውም አንዱ ሃይማኖት የሌላውን ጉድለት በራሱ መንገድ እየዘረዘረ ራሱን ከማንም የተሻለ የእግዚአብሔርን ጎዳና መሪ አድርጎ በመደስኮር ወደእሱ ለመምጣት እንዲሽቀዳደሙ ሲሰብክ ይታያል። እግዚአብሔር ሰዎችን የሚመዝነው ባሉበት የእምነት ተቋም ያለውን ህግና ደንብ ማክበራቸውን በማየት ሳይሆን እግዚአብሔርን አውቀው ከእርሱ ጋር ያደረጉትን እምነትና ኅብረት በመመዘን ብቻ መሆኑ እውነት ነው። አማኞች ያሉበት ሃይማኖት የሰራላቸውን አጥር አልፈው እግዚአብሔርን ለማወቅና ለማግኘት፤ ከእኔነት አዙሪት ወጥተው ለአንዱ እግዚአብሔር መገዛት ቢችሉ ኖሮ የሃይማኖት ተቋማት ባልኖሩም ነበር።  የመጀመሪያይቱ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። ዛሬም ከድርጅትነት የተለየች የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። የየሃይማኖቶች ጥምቀት፤ ጌታና አባት የለም። ሃይማኖቶች ግን የየራሳቸውን ጌታ፤ አባትና ጥምቀት ሲሰጡ ይታያሉ። ይህም የመጽሐፉ ተቃራኒ ነው።
«አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ»  ኤፌ 4፤5-6
 ይሁን እንጂ ያለው እውነት አንድ ብቻ በመሆኑ እኔ፤ እኔ ያለው ሁሉ እውነተኛ ሊሆን አይችልም። በዚህም ይሁን በዚያ የማይናወጥና የማያጠራጥር እውነት፤ ሰላምና ዋስትና ያለው ከምንጩ ባለቤት ከኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ክርስቶስም  ሰላምና ዋስትናን በውክልና እንዲሰጥ ያቋቋመው አንድም ተቋም እና ድርጅት በዚህ ምድር ካለመኖሩም በላይ ክርስቶስ በአማኞች ልቦና ላይ ሰላምና ዋስትናን ሊመሰርት መጣ እንጂ ድርጅት ሊያቋቁም አይደለም። ክርስቶስ ያቋቋመው እኔን ነው ማለት የሚቻለው  ባለሰርቲፊኬት ተቋም ባለመኖሩ ሁሉም እኔ ከሌላው የተሻልኩ ለክርስቶስ ቅርብ ነኝ እያለ ራሱን አጽዳቂ ከመሆን ውጪ ሰላምና ዋስትናን በዚህ ምድር ማምጣት አይችልም።
ሳይካትሪስትና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ዶ/ር ሪዩበን ዴቪድ  ደግሞ እንዲህ ይላሉ። ሁሉም ሃይማኖቶች እግዚአብሔርን የሚገልጹበት የየራሳቸው ዶግማና አስተምህሮ፤ የእግዚአብሔር ወዳጅ ለመሆን የሚያስችልም የየራሳቸው ሕግና ደንብ አላቸው። ያንን ዶግማና አስተምህሮ፤ ሕግና ደንብ በመጠበቅ ብቻ ትክክለኛው እግዚአብሔር ይገኛል ስለሚሉ  እያንዳንዱ የሚያምነውና ከእርሱ ዘንድ ብቻ በትክክል እንዳለ የሚገልጽበት የራሱ እግዚአብሔር አለው  ሲሉ  ያብራራሉ።  ዶ/ር ሪዩበን ማብራሪያቸውን ሲቀጥሉ ትክክለኛው እውነት ግን እግዚአብሔር ራሱን የገለጸበትና የሚለካበት መንገድ እያንዳንዱ ሃይማኖት በጻፈው ዶግማ፤ አስተምህሮ፤ ሕግና ቀኖና መሠረት አለመሆኑ ነው።  የእስላሞች ፈጣሪ «አላህ» ይባላል። እስላሞች ራሳቸው የተረጎሙትን ያንን «አላህ» ሰው ማመን ካልቻለ አይድንም ይላሉ። አላህ የሚገኘውም ቁርአን በተባለ መጽሐፋቸው ውስጥ ነው። ከዚያ ውጪ አላህ የለም።ካቶሊኮች የራሳቸው የሆነና ካቶሊካዊ ትርጉም  የተሰጠው እግዚአብሔርን የማወቅ ዐለምዓለቀፋዊነት አስተምህሮ፤ ዶግማና ቀኖና አላቸው። ሰዎች ትክክለኛውን እግዚአብሔርን ለማግኘት እነዚያ መጽሐፍቶች ውስጥ ገብተው በተተረጎመው ተቋማዊ እምነት ውስጥ መነከር አለባቸው። ካቶሊክ መሆን ካልቻሉ እግዚአብሔርን አያገኙትም፤ ወይም በተሳሳተ ጎዳና ላይ ናቸው ይላሉ።  ገሚሱም የቀደመችው መንገድ በዚህ አለች ይላሉ። አንዳንዶቹም ኢየሱስን ከእኛ ዘንድ ተቀበሉ፣ እንደግል አዳኝ ካልወሰድክ አትድንም ይላሉ። እርግጥ ነው፤ እምነት የግል ነው። የክርስቶስ የማዳን አገልግሎት የተሰጠው ግን ለግል አይደለም። ላመኑ ሁሉ እንዲያው የተሰጠ ጸጋ ነው። አንድ ሰው በግሉ ክርስቶስን ማመኑ ክርስቶስን የግል አዳኝ አያደርገውም። ማንም ለመዳን በዚህ የግል አዳኝነቱ መስመር ውስጥ የግድ ማለፍ የሚሉ እንደብቸኛ ወኪልነት ራሳቸውን  የሚቆጥሩ ናቸው።  ዶ/ር ሪዩበን፤ በእርግጥ ማንም ሰው ስለክርስትና መሠረታዊ የመዳን ትምህርትና ሕይወት የሚገኝበትን የመንፈስ ቅዱስ ምሪት እውቀት ያስፈልጉታል። «ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል» 2ኛ ጢሞ 3፤5   «እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው» ሮሜ 10፤17
ቅዱሱን መጽሐፍ መማርና ማንበብ ሕይወት የሚገኝበትን ቃል ለማግኘት እንጂ የድርጅት አባል በመሆን ለእግዚአብሔር ያሉበትን ተቋም እንደትክክለኛ ሥፍራ የማቅረብ ዓላማ አይደለም። ሐዋርያትም ወንጌልን እየተዘዋወሩ ሕዝቡን እያስተማሩና እያጠመቁ ወደ ሕይወት መንገድ መመለስ ቻሉ እንጂ  ድርጅትና የእምነት ተቋም በመመስረት ስለማገልገል አንድም ቦታ ወንጌል ላይ አልነገሩንም በማለት ያብራራሉ ዶ/ር ሪዩበን።  ሰው በመጠየቅ፤ በማንበብ፤ በመማር፤በመጸለይና በእግዚአብሔር ፈቃድ እውነቱን ወደማወቅ  ሊያደርስ ይችላል። በአንድ ድርጅት ውስጥ ተወትፎ መኖር ግን እውነት ምን እንደሆነ ከማወቅ ይከለከላል። ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ የአይሁድ እምነት ተከታይ እንደነበረ የኦሪቱን ሕግ ሊፈጽም ኢየሩሳሌም የመገኘቱ ታሪክ ይነግረናል። ወደሀገሩ ሲመለስ ያልገባውን በመጠየቅ በሐዋርያው ፊልጶስ የኢሳይያስ መጽሐፍ ትርጉም ሲነገረው  እውነቱን ወደማወቅ ደረሰ፤ አመነ ተጠመቀም። ከአይሁዳዊ የእምነት ተቋም ወደክርስትና የመዳን ሕይወት ወዲያው ተሸጋገረ። በሕይወቱ ላይ የመጣው አዲስ ለውጥ ከአይሁድ ሕግና መመሪያ ድርጅታዊ ትእዛዝ ነጻ በመሆን ክርስቲያን የመባል የሐዋርያት እምነትጋር ኅብረት አደረገ እንጂ ከድርጅት ወደድርጅት አልተዘዋወረም። ያለኝ ኦሪታዊ ሕግና ደንብ ይበቃኛል፤ መዳን በዚያ ነው ያለው ብሎ በተቋማዊ ሕግጋቱ ላይ በድርቅናው ጸንቶ ቢሆን ኖሮ እውነቱን ወደማወቅ ባልደረሰም ነበር።  ክርስትና ማለት በክርስቶስ የተገለጠውን እውነት ማወቅና በዚያ ሕይወት ውስጥ መኖር በመሆኑ ጃንደረባው ከዚህ አዲስ እምነት ጋር ለማወቅ ባለው ትጋት ልክ ሊገባ በቃ።  የሃይማኖት ተቋማት አባል ሆኖ መቅረት ማለት በተቋሙ ጣሪያ ስር ተደፍኖ መቅረት ማለት ነው። በጣሪው ከተዘጋ ልቡና ወጣ ብሎ እውነቱን ለማወቅ ሰው ቢፈልግ ኖሮ እንደጃንደረባው ወደእውነቱ መድረስ በቻለ ነበር። ዛሬ በዓለማችን ላይ ያሉ ሃይማኖቶች ሁሉ በተለይም በክርስትናው ስም የሚንቀሳቀሱት በየራሳቸው ጣሪያ ስር ሚሊዮኖችን ነፍሳት ደፍነው በመያዝ ከዚያ እንዳይወጡ በሕግ፤ በመመሪያ፤ በደንብና በትዕዛዝ አጥር  እውነቱን ወደማወቅ እንዳይደርሱ ከልክለው ይገኛሉ።  እስልምና የተባለው እምነት ተከታዮቹን በሃይማኖት መጽሐፉ ላይ ከየትኛውም  ሌላ እምነት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርጉና በእምነት ከማይመስሏቸው ሰዎችም ጓደኝነትን እንኳን እንዳይዙ በጥብቅ ያስጠነቅቃል።  (ሱረቱ አል ኢምራን 3፤28) ከዚህ ጥብቅ መመሪያ የተነሳ ከዚህ እስር ለመውጣት አይችሉም። ከዚህም የተነሳ እውነት ምን እንደሆነ ወደማወቅ ለመድረስ ሊደርሱ አይችሉም። ኢየሱስ ክርስቶስ  በትንሣኤ ዘለሙታን ዳግም ሲመጣ በእሱ ላይ የነበረንን እምነትና ምግባር ይመዝናል እንጂ በነበርንበት የሃይማኖት ተቋም ልክና ማንነት አይፈርድልንም ወይም አይፈርድብንም።  እኔ ቀጥተኛይቱ ስላልን ቀጥተኛ አንሆንም። ቀጥተኛው የት እንዳለ በቃሉ ስንመረምር ብቻ እውነቱን ማወቅ ይቻለናል። አስተዋይ ልብም  በእውቀት፤ ጠቢብም በመሆን ሰሚ ጆሮ ካለን መንገዳችንን ያሰፋዋል፤ በታላቅም ሥፍራ ያደርሰናል። 
«የአስተዋይ ልብ እውቀትን ያገኛል፥ የጠቢባንም ጆሮ እውቀትን ትፈልጋለች፣ የሰው ስጦታ መንገዱን ታሰፋለታለች፥ በታላላቆችም ፊት ታገባዋለች» ምሳሌ 18፤15-16
መንፈሳዊ ሰው መሆን ማለትም ያሉበትን ድርጅት ዓላማ መቀበልና መፈጸም ሳይሆን እግዚአብሔርን ማወቅ፤ እንደትእዛዙና ፈቃዱ መኖር ማለት ነው። ስለዚህ ከድርጅት በላይ እግዚአብሔርን ወደማወቅ አዲስ ሕይወት ልንሻገር ይገባል ።
1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2፥3-4
ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው።