Saturday, September 29, 2012

በሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ የሃይማኖት ብሔርተኝነት አደገኛ ነው!

«መጪውን ጊዜ በሃይማኖት ብሔርተኝነት መዋጀት» ይገባል። (ማኅበረ ቅዱሳን )

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 1 2005 ዓ.ም.
ሃይማኖታዊ ብሔርተኝነት ማለት ምን ማለት ነው?
በሳንዲያጎ ግሮስሞንት ኰሌጅ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶ/ር ጆን ኦክስ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን በተነተኑበት ጽሁፋቸው እንዲህ ሲሉ ያስቀምጣሉ። የሃይማኖት ብሔርተኝነት /Religious Nationalism/ የሚከተሉትን አራት ባህርያት ያሟላ ወይም ለማሟላት የሚሰራ ሲሆን በአንድ ሀገር ውስጥ ህልውናው ይረጋግጣል ይላሉ።
1/ የሀገሪቱ መንግሥት ለአንድ የተለየ  የሃይማኖት ተቋም ብቻ የእለት ከእለት እንቅስቃሴ የገንዘብ ድጋፍ የሚሰጥ ከሆነ፣
2/ የሃይማኖቱ ተቋም፦ ሞራልን፤ ግብረ ገብንና ሥነ ምግባርን በተመለከቱ በመንግሥታዊው ጉዳዮች ላይ ጫና ማሳረፍ ከቻለ፤
3/  በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ሌሎች ሃይማኖቶች በመንግሥት የሚደገፈውን ሃይማኖት መብት መጠበቅ ከተገደዱ፤
4/ መንግሥታዊ ድጋፍ ያለው ይህ ልዩ ሃይማኖት በፖለቲካው መስክ የመንግሥቱ ደጋፊ ሲሆን  በአንድ ሀገር ውስጥ የሃይማኖት ብሔርተኝነት አለ ማለት ይቻላል በማለት ያብራራሉ።
ለምሳሌ ኢራን፤
በኢራን ውስጥ ክርስቲያኖች፤ ቡድሂስቶችና አይሁዳውያን ያሉ ቢሆንም መንግሥታዊው ሃይማኖት ግን እስልምና ነው። እስልምናው በመንግስት በጀት ይደገፋል፤ ሃይማኖታዊውን ተቋም የሚጻረር አንድም ሕግ አይወጣም፤ ሌሎች ሃይማኖቶች የእስልምናን ብሔራዊነት የበላይነት የመጠበቅ ግዴታ አለባቸው ( ከእስልምና ሰው ሰብከው ቢወስዱ ይቀጣሉ፤ እስልምና ግን ከእነሱ ሰብኮ ቢወስድ አይጠየቅም)፤ መንግሥታዊው ሥልጣን  ከእስላም ሰዎች እጅ እንዳይወጣ ሃይማኖቱ ድጋፍ ይሰጣል።
ግሪክና፤ ራሺያም በተወሰነ መልኩ ተመሳሳይ ሃይማኖታዊ ብሔርተኝነት ይታይባቸዋል። በሀገሪቱ ውስጥ ብዙ ሃይማኖታዊ ሰዎች ቢኖሩም የመንግሥቱን ስልጣን የሚረከበው ሰው ቃለ መሃላ የሚፈጽመው በመንግሥቱ ተቀባይነት ባለውና በሚደገፈው የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እጁን ጭኖ እንጂ በፌዴራሉ ዳኛና በዱማው ፊት ብቻ አይደለም።
የሃይማኖት ብሔርተኝነት /Religious Nationalism/ በራሱ ሃይማኖታዊ ተቋም ውስጥ የተለየ ሃሳብና ጥያቄን ለማስተናገድ በፍጹም ቦታ አይሰጥም ብቻ ሳይሆን ባለው የኃይል ተደማጭነት የተነሳ ልዩ ሃሳብና ጥያቄ ወይም ተቃውሞ አቅራቢዎችን የመጨፍለቅና የማስጨፍለቅ አቅም አለው።
ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ወደ ሃይማኖት ብሔርተኝነት ጎዳና እያዘገመ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን የተለየ ሃሳብና አቋምን የማይቀበልና እንደነዚህ ዓይነት ልዩነቶች ለማስተናገድ ስለማይችል የሚወስደው እርምጃ  ማስደብደብ፤ ማሳሰር ብሎም ከተመቸው ማስገደል ነው። በመምህር ጽጌ ስጦታውና በዲ/ን ሙሉጌታ ወ/ገብርኤል ላይ የደረሰውን ድብደባ ማስታወስ ይሏል።
ብሔር ማለት በቁሙ ወሰን፤ ክልል፤ድንበር፤ ጠረፍ ያለው  ሀገር ማለት ነው። የሃይማኖት ብሔርተኝነት ማለትም የራሱ ድንበር፤ አጥር፤ክልል ወሰን ያለው የሃይማኖት ተቋም  ማለት ነው። የኮርኔል ዩኒቨርሲቲ የስነ ሃይማኖት ሌክቸረር ማይክል ኤሪክ ዳይሰን ስለሃይማኖት ብሔርተኝነት እንደዚህ ይላሉ። "No religion has a particular right on the nation»  በሀገሪቱ ውስጥ የተለየ መብት ያለው ሃይማኖት የለም»
ታዲያ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን ማኅበረ ቅዱሳን የሚያቀነቅነው ለምንድነው? ምናልባት ከአባ ጳውሎስ በኋላ የፓትርያርክነቱ  ተራ የወሎዬዎች ነው እየተባለ የሚዘፈነውን በመስማቱ ሃይማኖታዊ ብሔር እንጂ ጎጣዊ ብሔር በቤተክርስቲያን የለም ለማለት ፈልጎ ይሆን?  የብሔር ድጋፍና ጥላቻ እንግዳ ነገር አልነበረምና ሹመቶቹን ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ላይ ማላከክ ተገቢ አይደለም። የእግዚአብሔርን ፈቃድና እውቅና ማቀላቀል አይገባም። ሰዎች የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሲከተሉ፤ ፈቃዱ ይፈጸምላቸዋል። የልባቸውን አሳብ ሲከተሉ ደግሞ  የልባቸውን መንገድ እንዲሄዱ እግዚአብሔር እውቅና ይሰጣቸዋል እንጂ በሁሉም ሹመቶች ላይ የእግዚአብሔር ፈቃድ የለም።
እንደ ልባቸው ሥራ ተውኋቸው፥ በልባቸውም አሳብ ሄዱ» መዝ 81፤12
እስራኤላውያን ሳኦል ይነግስ ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይሆንም የልባቸውን አሳብ አይቶ ሳሙኤል ቀብቶ እንዲያነግስላቸው እግዚአብሔር እውቅናውን ሰጥቷል።
« እግዚአብሔርም ሳሙኤልን አለው። በእነርሱ ላይ እንዳልነግሥ እኔን እንጂ አንተን አልናቁምና በሚሉህ ነገር ሁሉ የሕዝቡን ቃል ስማ» 1ኛ ሳሙ 8፤7
ስለዚህ ሰዎች በቡድንና በጎጥ እየተደራጁ የሚያደርጓቸውን ሹመቶች ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደተፈጸመ ለማድረግ ቢሞክሩ ከእግዚአብሔር ቃል አንጻር ሚዛን አይደፋም።  እንደማኅበረ ቅዱሳን ዜና ዘገባ ከዚህ በፊት በቡድንና በፖለቲካ ድጋፍ የተደረገ የፓትርያርክ ሹመት እንዳልነበረ  በመቁጠርና ዛሬ እንደዚህ ዓይነት አስተሳሰብ መከሰቱን በሚያሳብቅ መልኩ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን ወደማራገብ መሸጋገሩ ጉንጭ አልፋ ስነ ሞገት ከመሆን አያልፍም። ምክንያቱም በሁላችንም ዘንድ ያለው እውቀት ያንን አያሳይምና ነው። ያለን መረዳት ከዚህ በፊት የቡድን ወይም የፖለቲካ ድጋፍ እንደነበረ ሲሆን የከዚህ በፊቱ የቡድንና የፖለቲካ ድጋፍ ምርጫ መቀጠል የለበትም ነው ሊባል የሚችለው። ይህ እውን ሊሆን የሚችለው ደግሞ በእግዚአብሔር ላይ በመታመን እንደ ሐዋርያው ማትያስ ምርጫ በመንፈስ ቅዱስ እጣ ሰጪነት  ላይ በመጽናት ብቻ ነው። (ሐዋርያም ማትያስ አልኩኝ እንጁ አባ ማትያስ ዘካናዳ ወይም አባ ማትያስ ዘአሜሪካው አላልኩም)። ምርጫ ምንም ዓይነት «የሃይማኖት ብሔርተኝነት» ሳይጨመርበት መሆን ይገባዋል። ሃይማኖታዊ ብሄርተኝነት የሚታመነው በሃይማኖታዊ ወግና ባህል ላይ እንጂ በእግዚአብሔር አሠራር ላይ ስላይደለ የከዚህ በፊቶቹ  ስህተቶች እንዳይደገሙ ለማድረግ ዋስትና አይሰጥም።
ከዚህ አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን በሃይማኖት ብሔርተኝነት እንቁም በማለት ጥሪ ሲያቀርብ ምን ማለቱ ነው?
ሁሉም ሃይማኖት የየራሱን እምነት አጥብቆ መያዝና መከተል ባህርያዊ ነው። ነገር ግን ችግሩ የሚመጣው «የኔ ብቻ» የሚል ጽንፍ ሲከተለው ነው። እግዚአብሔር አሜሪካና ሕዝቧን ይባርክ ማለት ለራስ የማሰብ አንድ አካል ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር አሜሪካና ሕዝቧን ባርኳል ማለት ሌላ ነገር ሲሆን ይህም «እኔ ብቻ» የሚለው ጽንፍ «ኢራንን አልባረከም» እንደማለት በመሆኑ ራስን በሁሉን ዓቀፍነት ዓይነት ማየት አደገኛ ነው በማለት የኮርኔሉ ሌክቸረር ዳይሰን ያሰምሩበታል።
« Religious nationalism can also give a sense of exclusivity»

Wednesday, September 26, 2012


ውድ የደጀ ብርሃን ብሎግ ተከታታዮች፤

በፅሑፍ፤በሃሳብ፤ በገንቢ አስተያየት፤ ትችትና ነቀፋ አብራችሁን ለዘለቃችሁ ሁሉ በእግዚአብሔር ስም እጅግ በጣም እናመሰግናለን።

"....ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን?

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ስለ ራሳቸው፣ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን…?

ይህ መጣጥፍ በሪፖርተር ጋዜጣ የእሁድ እትም በፍቅር ለይኩን የተባሉ ጸሐፊ ካስነበቡት ጹሑፍ ለጦማራችን በሚመስማማ መልኩ መጠነኛ ማሰተካከያ ተደርጎበት የተወሰደ ነው፡፡

 ‹‹እግዚአብሔር ሆይ ሁሉንም ነገር ለአንተ እተዋለሁ. . . አሜን!›› (በቅርቡ የሞቱት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ ከመሞታቸው በፊት ከተናገሩት የተወሰደ፡፡)
ሞት የሰው ልጆች ሁሉ አይቀሬ የሆነ የሕይወት ዕጣ ፈንታ ነው፡፡ ትልቁ ቁም ነገር በምድር ላይ በኖርንበት ወይም እንድንኖርበት በተሰጠን ዘመን የሠራነው ደግ/መልካምም ሆነ ክፉ ሥራችን ግን ሁሌም ከመቃብር በላይ ቋሚ ሀውልታችን ወይም ቅርሳችን ሆኖ እንድንታወስ ሊያደርገን እንደሚችል በቅጡ ማሰብ ይመስለኛል፡፡
ሰዎች ስለ ሞት የተለያየ አመለካከት አላቸው፡፡ ለአንዶንዶች ሞት ትርጉም የለሽ ጸጥታ ነው፡፡ ለሌሎች ደግሞ ሞት ዘላለማዊ እረፍት ነው፡፡ ለአንዳንዶች ሞት ምስጢራዊ እና ረቂቅ ነገር ነው፡፡ በክርስትናው ዓለም ውስጥ ላለን በርካቶች ደግሞ ሞት ወደ ዘላለማዊው፣ ፍፁም ሰላም እና እረፍትን ወደ ተሞላው ሰማያዊ ዓለም እንደ መሸጋገሪያ ድልድይ የሚቆጠር ነው፡፡
ስለ ሞት ያለን ግንዛቤ፣ ትንታኔ እና ፍልስፍና እንዳለንበት እና እዳደግንበት ማኅበረሰብ የኑሮ ልማድ፣ ባሕል እና እምነት/ሃይማኖት የተለያየ ፍቺ ይሰጠዋል፡፡ ሞት የቅርባችን እና የዕለት ተዕለት ክስተት የመሆኑን ያህል በአንፃሩ ደግሞ መቼም የማይለመድ እንግዳ ክስተት ሆኖ መቀጠሉ ለብዙዎቻችን እንቆቅልሽ ነው፡፡ ምነው በአዲሱ ዘመን፣ በወርኻ አደይ፣ ምድር፣ ተራሮች እና ሜዳዎች፣ ጋራ እና ሸንተረሩ በአበቦች አምረውና ተውበው በሚያጌጡበት፣ ሰዎች ሁሉ በአዲስ ራእይ ሕይወትን ውብ እና ፍቅርን የተሞላች ለማድረግ ብሩህ ተስፋን ሰንቀው ‹‹ጉልበቴ በርታ በርታ!›› በሚሉበት ውብ እና ተወዳጅ በሆነችው በወርኻ መስከረም ምን ነክቶህ ነው እንዲህ ሞት ሞት የሚሸት ጹሑፍ ምነው!? እረ…! ደግም አይደል የሚሉኝ ሰዎች አይጠፉም ብዬ እገምታለሁ፡፡
ግና ወደድንም ጠላንም መራሩ እውነታ ሞት ለሁላችንም የማይቀር ዕዳ መሆኑ ነው፡፡ ሞት የሁላችንም ዕጣ ፈንታ መሆኑ ማንኛችንም ብንሆን ለአፍታም ያህል ቢሆን እንዘነገዋለን ብዬ ለመናገር አልደፍርም፡፡ ስለዚህም ሞት ሲመጣ አማክሮ፣ ጊዜ እና ወቅትን ተከትሎ አይደለምና ስለ ሞት ለማውራት ምቹ ጊዜ፣ የተመረጠ ሰዓት ሊኖር ይችላል ብዬ አላስብም፡፡ ሞት አዲስ ዘመን፣ ወርኻ ክረምት፣ በጋ ወይም ጸደይ፣ ትንሽ፣ ትልቅ፣ መሪ ተመሪ፣ ንጉሥ፣ አገልጋይ፣ ሕጻን፣ አዛውንት… ወዘተ አይልምና፤ ለዚህም ነው በለመለመ ብሩህ ተስፋ እና ራእይ ሕይወትን ውብ እና ጣፋጭ ለማድረግ መልካም ምኞታችንን በምንገልጽበት በአዲሱ ዘመን መባቻ ስለ ሞት ለማውራት መጨከኔ፡፡
    የዕብራውያን ጸሐፊ የሆነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱም በኋላ ፍርድ ተመደቦባቸዋል፡፡›› (ዕብ ፱፣፳፯) በማለት የሞትን አይቀሬነት ያስገነዝበናል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገናም በሮሜ መልእክቱ፡- ‹‹በአዳም ኃጢአት ምክንያት ሞት በሰው ልጆች ሁሉ ላይ መንገሱን እና የዚህ የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ ሞት ድል መነሳቱን እና በክርስቶስ ሞት ምእመናን የዘላለም ሕይወትን እንደታደሉ›› እንዲህ ይተርካል፡- ‹‹በአንዱም (በአዳም) በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፣ ይልቁን የጸጋን ብዛት እና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ፡፡›› (ሮሜ ፭፣፲፯) ይለናል፡፡

   ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በወንድሟ በአልዓዛር ሞት እጅጉን ልቧ ተሰብሮ እና ሁለንተናዋ በሀዘን ደቆ በእግሩ ሥር ተደፍታ እያነባች፡- ‹‹ጌታ ሆይ አንተ በዚህ ኖረህ ቢሆን ኖሮ ወንድሜ ባለሞተ ነበር!›› ላለችው ለማርታ፡- ኢየሱስም፡- ‹‹ትንሣኤ እና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳን ሕያው ይሆናል፡፡›› በማለት በእርሱ (በሕያው እግዚአብሔር ልጅ) የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዳላቸው በቃሉ አረጋገጦላታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በቅዳሴው ‹‹ሞትን ይሽረው ዘንድ ሞተ!›› በማለት የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሞት ለዘላለም መሻሩን ይመሰክራል፡፡
ሞት በክርስቶስ ላመኑ በፍፁም የሚያስፈራ እና የሚያስጨንቅ ነገር አይደለም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለእኔስ ወደ ጌታዬ መሄድ ይሻለኛል ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡›› ሲል ሞቱን ወደ ጌታው እና አምላኩ የሚሻገርበት ድልድይ እንደሆነ ለፊሊጵስዩስ ክርስቶሳውያን የወንጌል ልጆቹ በላከላቸው መልእክቱ በግልፅ ነግሯቸዋል፡፡ እናም ሞት በክርስቲያኖች ዘንድ አስፈሪ እና አሳፋሪ አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፣ ሆኖም አያውቅም፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን የወንጌል አርበኞች፣ ጻድቃን እና ሰማዕታት ሞታቸውን እግዚአብሔር አምላካቸውን በዝማሬ እያመሰገኑ፣ እያመለኩ፣ በታላቅ ደስታ እና በጸጋ ነው የተቀበሉት፡፡
ወደ ተነሳሁበት ወደ ርዕሰ ጉዳይ ስመለስ 2004 ዓ.ም በሀገራችን በሃይማኖት፣ በሥነ ጥበብ እና በፖለቲካው መስክ አንቱ የተባሉ ሰዎችን ያጣንበት ዘመን ነው፡፡ በተለይም ደግሞ ወርኻ ነሀሴ ከሕይወት ጋር ግብ ግብ የገጠመ በሚመስል አስገራሚ ጥድፊያ፣ ዓመቱ ከማለቁ በፊት ሳልቀደም ልቅደም ያለ ይመስል በዓመቱ መጨረሻ በወርኻ ነሀሴ ሁለት ታላላቅ መሪዎችን በሳምንት ልዩነት ውስጥ ያጣንበት እንደ አየሩ ጠባይ ሁሉ ጨፍጋጋ እና አስደንጋጭ ወር ሆኖ አልፏል፡፡    
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን አባት እና መሪ የሆኑት ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እና የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚ/ር አቶ መለስ ዜናዊ የተከታተሉበት የሞት መርዶ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን ከዳር እስከ ዳር ያነጋገረ እና የሀዘን ከል ያለበሰ ክስተት ሆኖ አልፏል፡፡
በዚህ የሞት ክፉ ዜና የተነሳ በሀገራችን ያረበበው የሀዘኑ ድባብ እንደ ሰማዩ ደመና ገና ሙሉ በሙሉ የተገፈፈ አይመስልም፡፡ አሁንም ድረስ የእነዚህ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ መራኅያን ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ለብዙዎቻችን ባሰብነው ቁጥር እንቆቅልሽ እንደሆነብን ዘልቋል፡፡ ለአንዳንዶች በተመሳሳይ ወቅት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ የተከሰተው ይህ ያልተጠበቅ የሞት ጥሪ ‹‹የእግዚአብሔር ቁጣ ነው›› እኛም ንስሀ እንግባ ዘንድ ያስፈልገናል በማለት የእግዚአብሔርን ታላቅነት እና ኃያልነት ዳግም እንዲያስቡ እና እንዲያስተውሉ እንዳደረጋቸው ሲናገሩ በአደባባይ ተደምጠዋል፡፡
ለሌሎች ወገኖቻችን ደግሞ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ የሞት መርዶ ያው እንደተለመደው ተራ የፖለቲካ ጉንጭ አልፋ ወሬ ከመሆን አላለፈም፡፡ እናም አንዳንዶች ለሰሞኑ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ያልተገባ የስንፍ እና የፍርድ አስተያየት ከመሰጠት ባለፈ ሌላ አንድምታ እንዳልሰጡት በሰሞኑ ከሚነገሩ ወሬዎች፣ በማኅበረሰብ ድረ ገጾች እና በየብሎጉ ከሚጻፉ በርካታ ፍርድ አዘል ጹሑፎች እና አስተያየቶች ታዝበናል፡፡ እንዲያም ሲል ደግሞ እሰይ ስለቴ ሰመረ በሚል የሚያዜሙ እና ፍፁም ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እና ባሕል በጎደለው ሁኔታ በእነዚህ መሪዎች ሞት ጮቤ እየረገጡ ያሉ ወገኖችንም እረ ምን ጉድ ነው እያልን ለመታዘብም በቅተናል፡፡ 
እንዲሁ እንደ ዋዛ ለህክምና በሚል ሰበብ እንደ ወጡ እስከ ወዲያኛው የተለዩንና ከአሁን ከአሁን ጤንነታቸው ተመልሶ ይመጣሉ በሚል ተስፋ የጠበቅናቸው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በስተመጨረሻ ለብዙዎቻችን ጆሮ የማይታመን የሆነውን የሞታቸውን መርዶ ዜና ለማመን እየቸገረንም ቢሆን ለመስማት ነበር የተገደድነው፡፡ ደህና ናቸው፣ ከህመማቸው እያገገሙ ነው፣ በአዲሱ ዓመት ሥራቸውን ይጀምራሉ የተባለላቸው ጠቅላይ ሚ/ር በድንገት በተከሰተ ኢንፌክሽን ምክንያት በድንገት ሞቱ መባላቸው አሁንም ድረስ ለብዙዎቻችን ኢትዮጵያውያን የጠቅላይ ሚ/ሩ ህመማቸው እና አሟሟታቸው ምስጢር ነው፡፡
በዚህ ጽሑፌ ለመዳሰስ የፈለግኩት የቤተ ክህነቱ እና የቤ መንግሥቱ መሪዎች በሕይወታቸው እስትንፋስ መጨረሻ ምን እንደተናገሩ በመጠየቅ የተነሳው የመጣጥፌ ርዕሰ ጉዳይ እንደ አለመታደል ሆኖ አትኩሮቱን ያደረገው በውጩ ዓለም ባሉ መሪዎች እና ታላላቅ ሰዎች ላይ ነው፡፡ የዚህ ዐቢይ ምክንያት ደግሞ በቅርብ በሞት የተለዩን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስም ሆነ ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ ምን እንዳሉ፣ ምን እንደተናገሩ እና ለሕዝባቸው ምን ዓይነት የመጨረሻ መልእክት እንዳስተላለፉ የነገረን ሰው ወይም እኔ ምስክር አለሁ የሚለን ሰው እሰካሁን አለመገኘቱ ነው፡፡
ፍቅርን፣ ይቅር ባይነትን/እርቅን፣ ግልፅነትን፣ ታማኝነትን… ወዘተ በቃላቸውም ሆነ በተግባራቸው የሚሰብኩ መሪዎች ድርቅ ክፉኛ የመታት እናት ኢትዮጵያ መሪዎቿ እና ሕዝቦቿ በቅጡ ሳይተዋወቁ እና በፍቅር ሳይቀራረቡ ማዶ ለማዶ እንደተያዩ በሞት እስከ ወዲያኛው የሚሸኙባት ምድር የመሆኗ ምስጢር ማብቂያው መቼ እንደሆነ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡
በምስኪኗ ኢትዮጵያ መሪዎቻችን ብዙ ነገራቸው ለሕዝባቸው ምስጢር ነውና እነዚህ ለሁለት አሥርት ዓመታት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ መሪዎች ሆነው ያስተዳደሩ ፓትርያርክ አባ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ምን እንዳሉ ምን መልእክት እንዳስተላለፉ ለማወቅ አልታደልንምና ሳንወድ በግድ ቁጭት እና እልህ እየተፈታተነንም ቢሆን በጀመርኩት ርዕስ ስለ ባሕር ማዶዎቹ መሪዎችና ታላላቅ ሰዎች የመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ መልእታቸው ላምራ፡፡
ከጠቅላይ ሚ/ር መለስ ከጥቂት ሣምንታት በፊት በሞት የተለዩት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ በጉሮሮ ካንሰር በሽታ ምክንያት በአሜሪካ አገር ህክምና ያደረጉ ቢሆንም በቅርቡ ህመማቸው አገርሽቶ ወደ ሀገራቸው የጦር ኃይሎች ሆስፒታል ገብተው ሕክምና በመከታተል ላይ እያሉ ነበር ያረፉት፡፡ Web Ghana የተባለው ድረ-ገጽ ‹‹Mills’ Last Words Before He Died/የፕሬዝዳንት ሚልስ እልፈት እና ከመሞታቸው በፊት የተናገሩት የመጨረሻ ቃላቸው›› በሚል ርዕስ ባስነበበው ጹሑፍ ፕ/ር ሚልስ ከሞታቸው በፊት ካጠገባቸው የነበሩትን ወንድማቸውን ዶ/ር ካድማን ሚልስን በመጥቀስ የሚከተለውን ዘገባ አስነብቦ ነበር፡-
"Before my brother (Mills) died, the last words that he said that I clearly remember is that, he raised his hands in the air and he said ‘God, I leave it all to you, Amen’. I’ve no doubt that God heard his call. I’ve no doubt that he is now in the bosom of the Lord. I’ve no doubt that he’ll find eternal peace. Pray for him, and May God be with you, Fiifi," Dr Cadman Mills said.