Thursday, September 6, 2012

ሲኖዶሱ ለ15 ቀን የሚቆይ የምህላ አዋጅ አወጀ!

ምንጭ፤ ዓውደምህረት ብሎግ 

ሲኖዶሱ 15 ቀን የሚቆይ የምህላ አዋጅ አወጀ  

በትናትናው ዕለት ለጋዜጠኞች በተሰጠ የጽሁፍ መግለጫ ሲኖዶሱ ከጳጉሜ 1 አስከ መስከረም 10 የሚቆይ የምህላ አዋጅ አውጇል፡፡ በብጹዕ አቡነ ሕዝቅኤል ፊርማ በተለቀቀ የጽኹፍ መግለጫ እንደሚያመለክተው ምህላው ጾምን አያካትትም፡፡ ዋነኛ አላማውም የተሻለ አባት ለቤተክርስቲያን እንዲያስነሳ ነው፡፡ የሰላም አምላክ አግዚዘብሔር ለቤተክርስቲያን የሚበጀውን ያምጣልን፡፡ 

የሱባኤው ዓላማ ተገቢ እና አስፈላጊ ቢሆንም ቀጥታ ፓትርያርክ ምርጫ ጋር ከማተኮር ሁለቱ ሲኖዶሶች የሚዋሀዱበትን ሁኔታዎችን እና እርቁ የሚቀላጠፍበትን ሁኔታ የሚያመቻች ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡ ከዚህ በፊት እርቅ እንዳይፈጸም እንቅፋት የሆኑት አቡነ ጳውሎስ ናቸው እየተባልን ኖረናል፡፡ አሁንስ ታድያ ምን እየተደረገ ነው? ምህላ አዲስ ፓትርያርክ ለመምረጥ ከሆነ እርቁ ለምን ያስፈልጋል? ከአሜሪካ መጥተው የሀዘኑ ጊዜ እስኪያልፍ ጠብቁ የተባሉት ሰዎችስ ምን ሊባሉ ነው? እውን አሁን ያሉት አባቶቻችን እርቁን ይፈልጉታል? ይህንን ጉዳይ በተመለከተ አባቶቻችን አንድ ብትሉን መልካም ነው፡፡


 የጸሎተ ምህላውን ደብዳቤ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

Wednesday, September 5, 2012

ጌታም ወደ እግዚአብሔር ፍቅር ወደ ክርስቶስም ትዕግሥት ልባችንን ያቅናው 2ኛ ተሰ 3፤5


ስለትዕግስትና ታጋሽነት ብዙ ብዙ ሰምተናል። ትዕግስት መራር ናት ፍሬዋ ጣፋጭ ነው፤ በለሷን የጠበቀ ፍሬዋን ይበላል ፤ የመሳሰሉት ጥቅሶች የትዕግስትን አስፈላጊነት የሕይወታችን አንድ ክፍል የማድረግን ነገር የሚያሳስቡን ኃይለ ቃሎች ሆነው አገልግለውናል ወይም ለተገልጋዮች ተናግረናቸዋል። ትዕግስትን ብዙ ምሁራን፤ሊቃውንትና መሪዎችም በገባቸው መጠን በማሳያነት ጠቅሰው ከትበውልናል።
ሚልን የተባለው ምሁር ትዕግስትን በወንዝ ጉዞ ስዕላዊ መንገድ ሲነግረን  «ወንዞች እንዴት እንደሚፈሱ ስለሚያውቁ ቁልቁል ይፈሳሉ፤ ብዙውን ጠመዝማዛ መንገድ በረጅም ትዕግስት አቋርጠው ከመጨረሻቸው ይደርሳሉ» ይለናል። ሚልን ስለትእግስት በምሳሌ የነገረን ነገር በእርግጥም ትልቅ እውነት ነው። ዓባይን የሚያክል ወንዝ በእርጋታ ከጣና ተነስቶ በረሃውንና ቁልቁለቱን አቋርጦ፤ ሀገራትን አካልሎ ከሜዲተራንያን ገብቶ እረፍት ለማድረግ ብዙ ትዕግስት ማድረጉ በእርግጥም አስገራሚ ነገር  ነው።
«The book thief» የተባለውን መጽሐፍ የደረሰው ማርከስ ዙሳክ ደግሞ ስለትዕግስት እንዲህ ብሏል። «ትዕግስት የሌለው ሰው የራሱን ምስል በጥቁር ቀለም የሳለ የእአእምሮ ንክና  ዓለምን ማሸነፍ ያልቻለ ሰው ነው» ሲል ገልጾታል።
«ፓውሎ ኮልሆ» ደግሞ ስለትዕግስት አስፈላጊነት እንዲህ ሲል ይመከረናል። «ትዕግስት ለምን እንደሚያስፈልግ ታውቃላችሁ?» በማለት ይጠይቅና ለጥያቄው ምላሽ ራሱ እንዲህ ሲል ይሰጣል።  «ምክንያቱም የትዕግስት ማጣት ለነገሮች ተገቢውን ትኩረት እንዳናደርግ ይከለክለናል» ሲል አስቀምጦታል።
ጃሮክ ክኒትዝ ደግሞ  የትዕግስትን አስፈላጊነት ሲገልጸው« ወንድሜ! ውሃው ሳይፈላ፤ እንፋሎት አይወጣምና ታገስ» ሲል እጥር ምጥን ባለ ቃል ገልጾታል።
እነዚህንና እነዚህን የመሳሰሉ የዘመኑ ምሁራንና ፈላስፎች ስለትዕግስት አስፈላጊነት በየመድረኩ ሳይናገሩ የቀሩበት ጊዜ የለም።  ጥቅሶቻቸውን ከማነብነብ ውጪ ምን ያህላችን የትዕግስትን አስፈላጊነት ገላጭ ምክሮቻቸውን በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ እንዳደረግን ቤቱ ይቁጠረው። ይሁን እንጂ ትዕግስት አስፈላጊ ስለመሆኗ ሁላችንም በአንድ ቃል እንስማማለን። አባቶቻችንም የትዕግስትን አስፈላጊነት ሲገልጹ «ለዚሁ ነው በሬዬን ያረድኩት» ያለውን ሰው ምሳሌ የሚያቀርቡት የመታገስ አቅምን ከማጣት ጋር አስተሳስረው ሲነግሩን ኖረዋል። በትዕግስት ማጣት ብዙ ችግር ሊመጣ እንደሚችል ሳይታለም የተፈታ ነው። ግን የትዕግስት መጠኑ እስከየት ድረስ ነው? ይሄም ብዙ ያነጋግራል። ስለዚህም ብዙ የተባለ እንደሆነ ይታወቃል።  የርእሳችንን መነሻ ያሰፋዋልና ትተነዋል።
የዚህ ጽሁፍ ዓላማ በምሁራን የትዕግስትን ገላጭ ቃላትና የትዕግስትን የገደብ ጣሪያ እስከየትነት ለመተንተን ሳይሆን በሕይወት ዘመናችን ውስጥ ዓለማውያን ሊቃውንቶች ምክርና ተግሳጽን በመስጠት ትዕግስትን ገንዘብ እንድናደርግ የለገሱንን በማንሳት፤ ዓለም የዚህን ያህል ተራምዳ ስለትዕግስት አስፈላጊነት ከተናገረች መንፈሳዊ ሕይወትስ እንዴትና እስከየት እንደተናገረችን ለመዳሰስ በመሻት መንደርደሪያ ይሆን ዘንድ አስቀምጠነዋል።
ወደ ርእሳችን ስንመለስ እንዲህ ይላል።
«ጌታም ወደ እግዚአብሔር ፍቅር ወደ ክርስቶስም ትዕግሥት ልባችንን ያቅናው» 2ኛ ተሰ 3፤5
ወደ ክርስቶስም ትዕግስት እግዚአብሔር እንዲያቀናው የሚፈለገው ትዕግስት ምን ዓይነት ይሆን?
በመንፈሳዊው ዓለም ከክርስቶስ የሆነ ትዕግስት የሌለው ሰው ክርስቲያን ሊሆን አይችልም።  በመባልና በመሆን መካከል ትልቅ ልዩነት እንዳለ ልናስተውል ይገባል። ብዙ ሰዎች ክርስቲያኖች ሊባሉ ይችላሉ። ክርስቲያኖች የተባሉ ሁሉ ግን ክርስቲያን ሆነዋል ማለት አይደለም። የሚወዷቸውን የሚወዱ ክርስቲያኖች ሞልተዋል፤ ነገር ግን የሚጠሏቸውን የሚወዱ ክርስቲያኖች ማግኘት አዳጋች ነው።  እነዚህ ክርስቲያኖች ይባላሉ ግን ክርስቲያን መሆን ያልቻሉ ቀራጮች ናቸው። ወንጌል እንዲህ ካለ እነዚህ ሰዎች ቀራጭ ክርስቲያኖች የማይባሉበት ምክንያት የለም።
የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ማቴ 5፤46
ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ክርስቶስም ትዕግስት ልባችንን ያቅናው ያለበት ምክንያት መውደዳችን በክርስቶስ ክርስቲያን የተሰኘንበትን ምስጢር ከቀራጭነት ሚዛን እንድናወጣው መሆኑ ግልጽ ነው። ክርስቶስ እኛን የወደደበት ትዕግስት ሚዛን የለውምና ነው።
የክርስቶስ የፍቅሩ ትዕግስት እኛን ለማዳን መፈለጉ ብቻ አልነበረም። እኛን ለማዳን ከመጣና ከኃጢአት ብቻ በቀር  በሥጋ  ከተዛመደን በኋላ ማዳኑን በደስታ ለመቀበል ከእኛ የተገባ ማንነት የሚጠበቅ ሆኖ ሳለ ሊያድነን የመጣበት ትዕግስት ሳያንስ እንዲያድነን መግደላችንን መታገስ መቻሉ እጅግ አስገራሚ ያደርገዋል።
ማንም ሰው መልካም ስጦታ ይዞለት የመጣውን ሰው በድሎት ሲያበቃ ከተበዳዩ ሰው ፍቅርን መጠበቅ አስቸጋሪ እንደሚሆንበት መገመት አይከብድም። ክርስቶስ ኢየሱስ ሌላ መድኃኒት በስጦታ አላመጣም፤ ይልቁንም ራሱን ሞት ለሚገባው ሰው፤ ምትክ ሆኖ ለመሞት ፍቅሩ ፍጹም በሆነ ትዕግስት የመጣ መድኃኒት ነበር። ለዚህ የሞት ምትክ መድኃኒት የቀረበለት መስዋእት የደስታ ምስጋና ሳይሆን እስከሞት የሚያደርስ መከራ ነበር። የሚገርመው ነገር ይህ ሁሉ ሆኖ ትዕግስቱ ምን ጊዜም ሞት በሚገባቸው ሰዎች ላይ የጸና መሆኑ ነው።
«ኢየሱስም፦ አባት ሆይ፥ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው አለ» ሉቃ 23፤34 እንደዚህ ዓይነት ትዕግስት ከወዴት ይገኛል?
ዛሬ አንዱን ክርስቲያን በቅጽበታዊ ንዴት ሌላውን ክርስቲያን፤ ጉንጩን በጥፊ ቢመታው  ከመ ቅጽበት አጸፋዊ ምላሹን ከመንጋጋው ወይም ዓይነ ስቡን በተጠናከረ ምት የማይሰጥ ለማግኘት  ከተአምር ቢቆጠር አይገርምም። እግዚአብሔር ይቅር ይበልህ ወይም ወንድምህ ሆኜ ሳለሁ እንደዚህ የመታኸኝ ምን በደልኩህ? የሚል ቢኖር በእውነት ክርስቲያን ማለት እሱ ነው።
በየሚዲያው፤ በየጉባዔውና በየመድረኩ  የምንወራወራቸው የቃላት ናዳዎች ያልፈነከቱት ወይም ያላሳመሙት ለማግኘት ከባድ ነው። እንደዚያም ሆኖ በማስተዋል ላይ ሆነን ነገሮችን ከክርስቶስ ትዕግስት አንጻር ባለመመልከት ናዳዎቹ ከየአእምሮአችን ጓዳ እየተፈነቀሉ ቀጥለዋል። ከሁሉም የሚከፋው እኔ ያልኩትና የተናገርኩት ብቻ ትክክል ነው የሚለው ናዳዎች እየተፈነቀሉ መወርወራቸውን አለማቋረጣቸው ነው።  እንደዚያም ሆኖ ክርስቲያኖች እንባላለን። ግን እስከመቼ?

Monday, September 3, 2012

በጉጂ ቦረና ሀገረ ስብከት ጉዳይ የመንግሥትና የቤተክርስቲያን አደራ ተበላ!


የምዕመናንና የቤተክርስቲያን መብት ተጨፍልቆ ለሕገወጡ ግለሰብ የ"ይጽና" ደብዳቤ እየተረቀቀለት ነው።
source;http://dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com
ለዓመታት የዘለቀው የጉጂ ቦረና ዞን ሀገረ ስብከት ችግር አሁንም የሚፈታው አጥቶ፣ ምዕመናኑ በከፍተኛ ችግር ላይ መውደቃቸውን በዚያ ያሉ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ በነጌሌ ቦረና፣ በክብረ መንግሥት (አዶላ ወዩ) ከተማ፣ በሀገረ ማርያም እና በሌሎችም ከተሞች የሚገኙ ምዕመናንን ችግሮች አስመልክቶ ከዚህ በፊት በተከታታይ እንደዘገብንላችሁ የሚታወስ ሲሆን፣ በተለይም በክብረ መንግሥት ከተማ የ"ማኅበረ ቅዱሳን"ና የጥቂት ጥቅመኛ ግለሰቦች ጥምረት ባሳደረው ተፅዕኖ በዓመታዊው የቅድስት ኪዳነ ምሕረት በዓለ ንግሥ እንኳን ታቦት ሳይወጣ ምዕመናን በደረሰባቸው ሁከት አዝነው ወደየቤታቸው መመለሳቸውን መግለጻችን ይታወሳል፡፡
ችግሩን ለማባባስ የግል ፍላጎታቸውን በቤተክርስቲያን ላይ በመጫን ከክብረ መንግሥት ከተማ እንደ እነ ዘውዴ አበሩ ያሉ ግለሰቦች ለ25 ዓመታት ከሰበካ ጉባዔ አንወርድም በማለት ቤተክርስቲያንን ለግል ገቢያቸው ተጣብተዋት ያሉ ሲሆን፣ ሲያምር ተክለ ማርያም የተባለ ግለሰብም ነጌሌ ቦረና ላይ ቁጭ ብሎ በሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ስም ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" ጋር በመመሳጠር በማመስ ላይ መሆኑን
በወቅቱ በዝርዝር ገልጸናል፡፡ በተለይም ሲያምር ተክለ ማርያም በፈጸመው የዲስፕሊን ጥፋት ከሥራ አስኪያጅነቱ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ ትንሣኤ ዘጉባዔ ማተሚያ ቤት የተዛወረ ሲሆን፣ ይህንኑ ውሳኔ የሚያስፈጽም ጠፍቶ በእምቢ ባይነት አሻፈረኝ በማለት ይኸው ከአንድ ዓመት በላይ መቆየቱን በተጨማሪ ዘግበናል፡፡ ይኸው ግለሰብ በሕገ ወጥነት በመፋነን የሀገረ ስብከቱን መኪና እና ማኅተም ጭምር ይዞ በመሰወር ምዕመናንን ሲያንገላታ፣ ከጠቅላይ ቤተክህነትም ሆነ ከኦሮሚያ ክልል መንግሥት አቅም በላይ እየሆነ መምጣቱን አብራርተናል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ምዕመናን ያለ መታከት በተከታታይ አዲስ አበባ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት ድረስ በመመላለስ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ሰባት አባላት ያሉት አጣሪ ቡድን በነሐሴ ወር 2004 ዓ.ም መጀመሪያ ሳምንት ወደ ሥፍራው ተልኮ ነበር፡፡ እነርሱም:-
  1. አቶ ተስፋዬ ውብሸት የጠቅላይ ቤተክህነት ምክ/ሥራ አስኪያጅ
  2. አቶ ፍስሐ ከጠቅላይ ቤተክህነት ቁጥጥር ክፍል
  3. አቶ እስክንድር ከጠቅላይ ቤተክህነት ሕዝብ ግንኙነት
  4. ሊቀ ስዩማን ፋንታሁን ሙጬ ከጠቅላይ ቤተክህነት ሰበካ ጉባዔ
  5. አቶ ሰሎሞን ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር
  6. አቶ ጣሰው ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር
  7. አቶ ፈቃዱ ከኦሮሚያ ክልል ፍትሕና ፀጥታ ናቸው፡፡