Saturday, June 9, 2012

ማኅበረ ቅዱሳን እንዲህም ነበር! በቀሲስ መልአኩ


ካለፈው የቀጠለ.................ክፍል 4
በድንጋይ መስታወቱን አንዴ ሲያደቁት በበሩ የነበረው ታጣቂ (ቦታው የአስተዳደር አዳራሽ ሰለነበር ነው ) ወደ ሰማይ ለመተኮስ ቢሞክርም አልቻለም።  መጨረሻ ላይ ነፍስ አውጭኝ ብሎ ሸሸ።  ከዚያ በኋላ መራኮት ሆነ።  «ዋናው እሱ ነው፤ እርሱን ያዙት!  የሚል ጩኸት ብሰማም የማላውቃቸው ሰዎች መጥተው ስለሸፋፈኑኝ እኔን ለመግደል ለሞከሩት ሰዎች አልሆነላቸውም ነበር።  «ስለ እመ አምላክ ተዉኝ» ከምትለው ነፍሰ ጡር ጀምሮ «እማዬ የት ነሽ»  እያለ እስከሚያለቅሰው ሕጻን ድረስ ታላቅ ጩኸት በአዳራሹ ውስጥ ሞላ።

መግቢያና መውጫውን እነርሱ ስለያዙት በየትም መውጫ አልነበረም። የአካባቢው ጸጥታ ኃይሎች እስኪመጡ ድረስ ሰዎቹ ይዘዉት በመጡት መምቻ ሁሉ መቱት።  ማን  ምን እንደሆነ ለማወቅ ግን አልቻልንም ነበር። በመጨረሻ የጸጥታ ሰዎች በመጡ ወቅት ግን የተወሰነው እነርሱን ጥግ አድርገን ለማምለጥ ቻልን።  ከአካባቢው እየሮጥኩ ስወጣ ታክሲ ስላገኘሁ የማልረሳውን ቃል ተናገርኩ «ከዚህ ቦታ ወደ ፈለግህበት ውሰደኝ» ምንም እንኳን ለጊዜው ለባለ ታክሲው የተናገርኩት ቢሆንም በዚያ ወቅት ግን ለአምላኬም የተናገርኩት ነበር።  «ብቻ ከዚህ ቦታ ወደ ፈልግህበት ውሰደኝ»  ወንድሞቼ በምላቸው የገዛ ወገኖቼ የአንዲት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ስንደበደብ ምን ልበል ? ካሳደገችኝ ቤተ ክርስቲያን ሽሚዜ በደም ጨቅይቶ እንደሌባ በገዛ ሀገሬ ወገኔ ፊት ስሸሽ  ምን ልበል ? (ከልለው ባወጡኝ ሰዎች ደም ጭምር ነበር የዳንኩት! እኔ ብቻ ሳልሆን  እነርሱ ለኔ ደሙልኝ ) የደማሁት ቀላል ቢሆንም  በታክሲ የተቻልኝን ያህል ራቅሁ።  የራቅሁት ግን ሕይወቴን በሙሉ ከሰጠሁበትም ቦታ ነበር።
 
ከድሬዳዋ ድብደባ በኋላ ወዲያው ሐረር ነበር የተመለስኩት። በሐረር ሁኔታው ተሰምቶ ስለነበር ሕዝቡ ሁል አንድ ነገር የሆንን መስሎት ነበር።  በሰላም መመለሳችን ደስታ ቢሆንም የእኛን እግር ተከትሎ አንድ አስደንጋጭ ዜና ደረሰ።  ከተደበደቡት መካከል ሦስቱ በአሳሳቢ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙና በተለይም አንደኛው በኮማ ውስጥ እንዳለ ተነገረን።  ሁላችንም አለቀስን።

Friday, June 8, 2012

ቁም ነገር በፈገግታ!

 ቸልተኝነት እና አስተዋዩ ውሻ!

ከውል ውጩ በሚደርስ ኃላፊነት ህግ ውስጥ የቸልተኝነት ጥያቄ ከተነሳ ምላሹ ለብዙ ፍርድ ቤቶች ብዙውን ጊዜ አስቸጋሪ ነው፡፡ በብዙ የህግ ስርዐቶች ውስጥ ተቀባይነት ያገኘው የቸልተኝነት መለኪያ “የአንድ አስተዋይ ሰው ሚዛን” ሲሆን ይህም አንድ አስተዋይ ሰው በተመሳሳይ ሁኔታዎች ውስጥ ቢሆን ኖሮ ምን እንደሚያደርግ በመላምታዊ ፍሬ ነገር ላይ ተመስርቶ ማሰላሰልና ድምዳሜ ላይ መድረስን ይጠይቃል፡፡ እንግዲህ ቸልተኝነትን በአንድ አስተዋይ ሰው እይታ መዝኖ መወሰን አስቸጋሪ ከሆነ ይህን መለኪያ ለአንድ አስተዋይ ውሻ ተፈፃሚ ማድረግ ደግሞ በጣም ፈታኝ ብቻ ሳይሆን አስገራሚም ጭምር ነው፡፡

በአሜሪካም ኢሊዮኒስ ግዛት በኪርካም እና ዊል (Kirkham Vs. Will) መካከል በታየ አንድ የይግባኝ ክርክር ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት በጉዳዩ የተነሳው ጭብጭ የአንድ አስተዋይ ውሻ መለኪያ በመጠቀም እልባት ሰጥቶበታል፡፡ ክሱ የተጀመረው “የተከሳሽ ውሻ በንክሻ ላደረሰብኝ ጉዳት የውሻው ባለቤት የሆነው ተከሳሽ ካሳ ሊከፍለኝ ይገባል፡፡” በሚል ከሳሽ ባቀረበው ክስ ሲሆን ተከሳሹም በበኩሉ ከሳሽ የተነከሰው ውሻውን በመተናኮሉ ስለሆነ በራሱ ጥፋት ለደረሰበት ጉዳት ልጠየቅ አይገባም በማለት ተከራክሯል፡፡ ክሱ በስር ፍርድ ቤት ውድቅ ከተደረገ በኋላ በይግባኝ ክርክሩ ላይ በዋነኛነት የተነሳው ጭብጥ “መተናኮል አለ ወይስ የለም?” የሚለው ጥያቄ ነበር፡፡ ውሳኔውን የሰጡት ዳኛ ይህንን ጭብጥ ለመወሰን እንደመመዘኛ ወይም መስፈርት የተጠቀሙት የተለመደውን የአስተዋይ ሰው ሚዛን ሳይሆን የአንድ አስተዋይ ውሻ መለኪያ ነበርር፡ በዚህ ሚዛን ወይም መለኪያ መሠረት መተናኮል አለ ወይስ የለም የሚለውን ጥያቄ ለመወሰን በተመሳሳይ ሄኔታዎች ውስጥ አንድ አስተዋይ ውሻ ተከሳሽ ካሳየው እንቅስቃሴ አንጻር ምን ዓይነት ምላሽ ይሰጣል? የሚል መላምታዊ ጥያቄ አንስቶ ድምዳሜ ላይ መድረስን ይጠይቃል፡፡ ፍርድ ቤቱ ተፈጻሚ ባደረግው መለኪያ መሰረት የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ አጽንቶታል፡፡

source:  http://abookmedhin.wordpress.com/

Wednesday, June 6, 2012

ጽዮንን ባሰብናት ጊዜ/መዝ.136፡1/

                                    ቤተ ጳውሎስ ረቡዕ ግንቦት 29 2004 ዓ.ም.
ለብዙ ጊዜ ዱርዬ ማለት ቀጥተኛ ትርጉሙን፣ ገላጭ ፍቺውን አላውቀውም ነበር፡፡ ዱርዬ ማለት የቆሸሸ ልብስ የለበሰ፣ ሥራ አጥቶ ድንጋይ ላይ የተቀመጠ፣ ለማኅበረሰቡ ስጋት የሆነ ብለን እንፈታው ይሆናል፡፡ ነገር ግን ያማረ ልብስ የለበሱ፣ ለፕሮቶኮላቸው የሚጠነቀቁ፣ ብዙ ፋብሪካ የተከሉ፣ ብዙ ሥልጣን የተሸከሙ፣ በጌትነት ወንበር ላይ የሚቀመጡ፣ በክብር አልባሳት የተንቆጠቆጡ፣ ወደ ስማቸው ቶሎ የማይደረስ ብዙ ቅጽል ያላቸው፣ ማኅበረሰቡ ተስፋችን ባልቴቶቹ ቀባሪያችን የሚሏቸው … ብዙ ዱርዬዎች አሉ፡፡ ትልቁ ችግራችን ሰውን በልብስ፣ ሰውን በንግግር ችሎታ፣ ሰውን በገንዘብ፣ ሰውን በመዐርግ፣ … መለካታችን ነው፡፡ ሰው በዲግሪ፣ ሰው በኒሻን አይለካም፡፡ የሰው መለኪያው የኑሮ ምርጫው ወይም ቀጥተኛነቱ ነው፡፡ ብዙ የዓለም ክብሮች የታሪክ አጋጣሚዎች ናቸው፡፡ በአጋጣሚ ግን ቅን መሆን አይቻልም፡፡ ቅንነት ወይም እውነተኛነት ምርጫ ነው፡፡
ዱርዬ ማለት ምን ማለት ነው? አሁንም ፍችውን ማሰስ አለብን፡፡ ዱርዬ ሁሉም ልብስ ልክ የሚሆነው ብዬ በራሴ መዝገበ ቃላት ፈትቼዋለሁ፡፡ ሲዘፍን እንደርሱ ሲዘምር እንደርሱ የሌለ፣ ሲጾም እንደርሱ ሲበላ እንደርሱ የሌለ፣ ሃይማኖታዊ ልብስ ሲለብስ እንደርሱ ሲዘንጥ እንደርሱ የሌለ፣ … ሁሉም ልብስ ልክክ የሚልበት፣ ጎበዝ ተዋናይ እርሱ ዱርዬ ይባላል፡፡ ይህን ፍቺ ያገኘሁት ተጨንቄ ሳይሆን ዓይቼ ነው፡፡ ከስድስት ወር በፊት በአንድ ሠርግ ላይ ተገኝቼ ከሚዜዎቹ አንዱ የማውቀው ሰው ነበር፡፡ ይህ ወንድም ጠበል ሲጠጣ እንደ እርሱ ሥርዓት ያለው ዓይቼ አላውቅም፡፡ ውስኪ ሲጠጣም እንደ እርሱ ጎዝጉዞ የሚጠጣ ያለ አይመስልም፡፡ ታዲያ እዚያ ሠርግ ላይ ትግርኛውን ሲጨፍር፣ ጉራጊኛውን ሲጨፍር ያደጉበት እንኳ እንደ እርሱ አልተዋሐዳቸውም ብል ሐሰት አይደለም፡፡ ታዲያ ልቤ በድንገት፡- “ወይ ዱርዬነት” አለ፡፡ ወዲያው ከሠርጉ ጫጫታ በአሳብ ወጣሁና ዱርዬ ማለት ሁሉም ነገር ልኩ የሆነ፣ ትክክለኛ ማንነቱ ግን ኃጢአት የሆነ ብዬ ማሰብ ጀመርኩ፡፡