‹የዓለም የሥልጣኔ ምንጭ ኢትዮጵያ ናት›፤ ማንስ ነው አይደለችም የሚል?
26
Mar 2012 በካሳሁን ዓለሙ
መቼም እንዳልኳችሁ ዋና የማስረጃ ምንጮቻችን የጥንት ታሪክ ሊቆች ናቸው፡፡ እናንተም በእነዚህ ሊቃውንት ዘገባና ማስረጃ እንደምትስማሙ እገምታለሁ፡፡ ከዚያ ውጭ አምጣ ካችሁኝ ግን ‹እንዴት ብዬ?› ነው መልሴ፡፡ በዚህም ቢሆን መጀመሪያ ልትጠይቁ የምትችሉት ‹ለመሆኑ ዓለም አንድ የጋራ የሥልጣኔ ምጭ አላት ወይ?› የሚል ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ ልገምት የቻልኩትም ሊቃውንቱም ይህንን ጥያቄ ስለሚያነሱት ነው፡፡ ሆኖም እነሱ በመጨረሻ የደረሱበት መደምደሚያ ‹የዓለማችን ሥልጣኔ ከአንድ የጋራ መነሻ ፈልቆ ወደ ተለያየ አቅጣጫ ፈሷል› የሚል ነው፡፡ እዚህ መደምደሚያ ላይ ለመድረስም ያስቻሏቸውን የተለያዩ ማስረጃዎችም አስቀምጠዋል፡፡ ከእነዚህ ማሰረጃዎች መካከልም የሥልጣኔ ቅሪቶች፣ የሥነ ተረት ማሳያዎችና የታሪክ ፍሰቶች ወደ አንድ አቅጣጫ በመምራት ቅድሚያውን ይይዛሉ፡፡
በሥነ ምድር ጥናት የዓለማችን ሥልጣኔ ከአንድ ከተወሰነ አካባቢ ከሚኖሩ ማኅበረሰቦች መነሣቱን ማረጋግጥ የሚያስችሉ ብዙ ማስረጃዎች ማግኘት ተችሏል፡፡ በዚህም የጥንት ዘመን ሥልጣኔ ማሳያዎች የሆኑት የሐውልት አሠራር፣ የግብርና አጀማመር፣ የአምልኮ ሥርዓት፣ የጊዜ አቆጣጠር፣ የባህል ውርርስ፣ የልምድ ድርጊት … ተመሳሳይነት የሥልጣኔ መነሻ አንድ ስለመሆኑ መስካሪዎች ሆነው ተገኝተዋል፡፡