Tuesday, February 26, 2013

የሻርለት ቅ/ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በአቡነ መርቆሬዎስ የፓትርያርክ አስተዳደር ሥር ለመጠቃለል ወሰነች!



በአሜሪካ ኖርዝ ካሮላይና  በ9400  መንገድ ላይ የምትገኘው የሻርለት ቅ/ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ራሷን ችላ የቆየችበትን ጊዜ ከግምት ውስጥ በማስገባትና አሁን እየታየ ባለው መንፈሳዊውን ሥልጣን ወደቡድናዊ ሽኩቻ የማውረድ እንቅስቃሴ በመገምገም  በአቡነ መርቆሬዎስ ሲኖዶስ ሥር ለመጠቃለል መወሰኗን የቤተክርስቲያኒቱ ሊቀ መንበር ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶ/ር ዮሐንስ ጉግሳ በተለይ ለሚዲያ  ገልጸዋል።


በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን የቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ በቅርበት እየተከታተሉ እንደቆዩና ጉዞው ሁሉ ከድጡ ወደማጡ እየሆነ በመሄዱ ለዚህ ውሳኔ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት እንዳደረሳቸውም የገለጹ ሲሆን ከእንግዲህ ወዲያ በኢትዮጵያ ላለው ሲኖዶስ እውቅና ባለመስጠት ውሳኔ ላይ በመድረሳቸው የአቡነ መርቆሬዎስን ፕትርክና ለመቀበል ሁኔታዎች እንዳስገደዷቸውም አብራርተዋል።

ዶ/ር ዮሐንስ ማብራሪያቸውን በመቀጠል፤ የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነትና ሰላም እንዲጠበቅ የፖለቲካው አመራር እጁን ማስገባት እስካልተወ ድረስ ችግሮች መቼም ሊያበቁ እንደማይችሉ የገመገምን ሲሆን ከእንግዲህ አዲስ አበባ ባለው ሲኖዶስ የሚነሳውን ክርክር እያዳመጥን ምን አዲስ ነገር ይመጣ ይሆን? በማለት ጊዜ ማጥፋት እንደሌለብን በማመናችን ወደዚህ ውሳኔ ደርሰናል ሲሉ ገልጸዋል። ስለሆነም ከእንግዲህ ወዲያ የኖርዝ ካሮላይና ቅ/ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ለአቡነ መርቆሬዎስ አመራር እውቅና በመስጠት ፓትርያርካችን አድርገናቸው ተቀብለናል በማለት አጠቃለዋል።