Saturday, March 26, 2016

ቀሲስ የ“ክብረት ልጅ”፥ ምነው በስድብ ቃል በጣም ጮኸ?!


ምንጭ፦ የአቤኔዘር ተክሉ ገጽ http://abenezerteklu.blogspot.com/
የክብረት ልጅ እይታዎቹን በሚያቀርብበት ብሎጉ፥ “ፓትርያርኩ፦ ለኢትዮጲያ የደኅንነት ፣ ለምእመናን የድኅነት ሥጋት” በሚል አንድ ጽሁፍ፥ ዛሬ አስነብቦ ድንገት ያየ ሰው ጠቆመኝና ወደጡመራው መድረኩ ገብቼ አነበብኩት፡፡ ዳንኤል በዚህ ጽሁፉ “100% ማኅበረ ቅዱሳን ሊያዘጋጀው ከጫፍ የደረሰውን ዐውደ ርእይ የከለከሉት ፤ ያስከለከሉት ፓትርያርኩ ናቸው”፥ ብሎ ደምድሞ አስቀምጦታል፡፡ የዐውደ ርእዩ ባለቤት ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ፥ በዋናው ጸሐፊው አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ በኩል ትላንት ማምሻውን ለጋዜጠኞች በሰጠው ጋዜጣዊ “መግለጫ”፥ “ለመታገዱ ፓትርያርኩ እንደሌሉበትና በመንግሥት አካላት መመሪያ መታገዱን”ይፋዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡

ዳንኤል ፓትርያርኩን ከሰይጣን እኩል ነበር የሳላቸው ፤ “... ፓትርያርክ ማለት በግሪክ “ታላቅ አባት” ማለት ነው፡፡ የታላቅ አባት ተግባር የልጆቹን ሥራ ማፍረስ አይደለም ፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፤ ...” በማለት፡፡ እንደከዚህ ቀደም ልማዱ ዳንኤል ሌሎች ማስጮኺያዎችንም በዚህ ጽሁፍ ለማካተት ጥሯል፡፡ አዳዲስ ስድቦችንም ለፓትርያርኩ እንደእጅ መንሻ አቅርቦላቸዋል፡፡

ቅዱስ ቃሉ ግን እንዲህ ይላል፥ “ፈራጆችን አትስደብ፥ የሕዝብህንም አለቃ አትርገመው።” (ዘጸ.22፥28) የሕዝብ አለቃ ወይም መሪ የሆነ ገዥ በምድር ላይ የእግዚአብሔር ተወካይ ፤ እንደራሴም ነው፡፡ ስለዚህ ልናከብረው ፤ በመውደድም ከሁሉ በፊት ልንጸልይለት ይገባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሳያስበው ይህን ቃል በመተላለፉ ምክንያት ወዲያው ተጸጽቶ ተመለሰ ፤ አለማስተዋሉንም ተናገረ፡፡ (ሐዋ.23፥4-5) ፍትሐ ነገሥቱም “በእነርሱ ላይ የተሾመውን ጳጳስ ... እንደትልቅ ወንድም ያክብሩት መሪና አስተዳዳሪ እንደመሆኑ መጠን ሊታዘዙለት ይገባል” ይላል፡፡ (አን.4 ቁ.53) ዳኒ! ይህ የሕግ ቃል አንተን አይመለከትም ይሆን?!

የቤተ ክርስቲያን የቀኖና መጽሐፍ ፍትሐ ነገሥት በአንቀጽ.6 ስለቀሳውስት ድርሻ ባሰፈረበትና ቀሳውስት ከማዕረገ ክህነታቸው ስለሚሻሩበት ሁኔታ ሲዘረዝር “... ሕግን አውቆ የማይሠራባት ... ቄስ ይሻር፡፡” በማለት በግልጥ ያስቀምጣል፡፡ ዳኒ! እንኳን መንፈሳዊውን ሥጋዊውን የዚህን አለም ምድራዊ ሕግ መጣስህን አውቀኸዋል? ማኅበሩ ፓትርያርኩ አልከለከሉኝም እያለ፥ አንተ ግን ለፓትርያርኩ የስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍተሃል፡፡ እንደቤተ ክርስቲያን ቀኖና ከቅስናህ ትሻር ይሆን? እውነታው ግን አይመስልም፡፡

ፓትርያርኩ ቢያጠፉ እንኳ የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ምን ነበር የሚለው? ጅል ፣ ሰይጣን ፣ የክፋት አነሳሽ ... እያሉ በአደባባይ ፓትርያርክን መዘርጠጥ አለበት የሚል “ቀኖና” አለን?! ለመሆኑ ስድብ ከማን ነው? የሕዝብን አለቃ አለማክበርስ? ያንን ሁሉ መጽሐፍ የጻፈው “ደራሲና ተመራማሪ” ምነው ምራቅ እንዳልዋጠ “ፍንዳታ”(የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴራችን ቃል ናት) ደርሶ ቱግ አለ?! እንዴ ይህ ነበር እንዴ በውስጡ የነበረው?!

ውድ ወንድሜ ቀሲስ ዳንኤል፦ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አላት ፤ በየትኛውም የቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና ሽቅብ ፓትርያርክን እንዲህ መዘርጠጥ አይደለም ምእመንን መናገር አጸያፊ ነው፡፡ ተግሳጽ ነው ብትለኝ፥ ለመሆኑ ተግሳጽ መቼ ነው የሚመጣው? ደርሰህ ከመገሰጽህ በፊት ስንቴ ይሆን የመከርካቸው? ስንቴ ይሆን የወቀስካቸው? ስንቴ ይሆን ካሉበት ነቀፌታ እንዲርቁ በሚራራ ልብ አዝነህላቸው እንደእግዚአብሔር ቃል በጸሎት ቃል ወደጌታ የማለድክላቸው? ... ደጋፊ ስላገኙ ብቻ ብዙ ማለት፥ ከማያዳላ ኅሊና ጋር ያፋጥጣል፡፡ ወንድምን ሰባት ጊዜ ሰባ ይቅር ማለትና መቀበል እኮ ከአባት ባሻገር ወንድም ለሚሆነን ፓትርያርክንም ያካትታል ፤ ለመሆኑ ይህን ታውቀዋለህን?!

ፓትርያርኩ ቢያጠፉ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አላት፡፡ “...የአገሩ ሁሉ ኤጲስ ቆጶሳት ስለእርሱ የሚገባውን ይመረምሩ ዘንድ እርሱንም ለማየት በየዓመቱ ሁለት ጊዜ ከጳጳሳቸው (ፓትርያርካቸው) ዘንድ ይሰብሰቡ፡፡ ስለተሰጣቸው ሥልጣን በምታስፈራዪቱ ቀን መልሳቸው የጸናች ትሆን ዘንድ፡፡” (አን.4 ቁ.55) የሚል፡፡ የሚያዩት ፊቱን ብቻ አይደለም ፤ ሥራውን በማየት ያመሰግኑታል ፤ ነቀፌታም ካለ ይነቅፉታል፡፡ ዳኒ! ይህችን አላነበብካት ይሆን?! ፓትርያርኩን መውቀስና መምከር ፤ መገሰጽም ካለብህ መንገዱን አልሳትከው ይሆን? ይህን ያህል ግን ለምን ይሆን የጠላሃቸው? ዳኒ! ወንድምን ስለመጥላት ቃሉ በትክክል ይወቅስሃል፡፡

በእርግጥ ዳንኤልና ማኅበሩ መንገድ ሲተላለፉ ይህ የመጀመርያው አይደለም፡፡ ግን እውነት ለመናገር ባልተጣራ ወሬ ፤ በተራ አሉባልታ ያውም ስንት ሽልማት ያግበሰበሰው ሰው ይቺን ትንሿን ነገር ከማጣራት ቸኩሎ “በሚቆረቆርላት” ቤተ ክርስቲያን መሪ ላይ የስድብ ናዳ ያወርዳል ብሎ ማን ይጠብቃል?! ከዚህ ስህተቱ ይማር ይሆን ዳንኤል? ወይስ ወደፊትም ሌላ የስድብና የመዘርጠጥ ጽሁፍ ያስነብበን ይሆን? ወይስ እንደጳውሎስ በግልጥ የይቅርታ ልብ ይዞ “የሕዝብን አለቃ” ስለተሳደበበት ስድቡ ንስሐ ይገባ ይሆን? የምናየው ይሆናል፡፡ ፈጥነህ ንስሐ ብትገባ ግን ማሰናከያን ታስወግዳለህና እስኪ ቀድመህ ወደራስህ እይ!!!

ጌታ ማስተዋሉን ያብዛልን፡፡ አሜን፡፡

Tuesday, March 22, 2016

እነሆ ሁለቱ ኪዳናት!!!


ከእውነቱ (ክፍል ሁለት)

መግቢያ

ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ስለ ትምህርተ ድነት በኛ ቤተ ክርስቲያን ተረስቶ ኖሯል፤ አሁንም እንደ ተረሳ ነው፡፡ አምስቱ አዕማደ ምስጢር የሚባል የዶግማ ትምህርት አለ፡፡ ግን እንኳንስ ለህፃናትና ላልተማሩ ሰዎች ዕድሜ ልኩን በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ኖርኩ ለሚልም በቀላሉ ሊረዳ አይችልም፡፡ ዋናውና የሕይወት ትምህርት ወደ አንድ ጎን ተጥሎ ነው የኖረው፤ አሁንም ቢሆን ያሰበበት የለም፡፡ ከቃል ትምህርቱ ከዜማው፣ ከቅኔውና ከአንድምታው መቅደም የነበረበት የክርስቶስ ቤዛነት ትምህርት ነው፡፡ ትምህርተ መለኮትን (ቲኦሎጂን) ተማረ ቢባል ትምህርቱ ተንሳፋፊ ነው፡፡ መሠረቱን ለቆ አየር ላይ እየተንጠለጠለ የሚሄድ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የአመራር መንፈሳዊ አገልግሎትና በምእመናን መካከል እውነተኛው የእግዚአብሔር ፍቅር ፈጽሞ ተረስቷል፡፡ እኔነት፣ ትዕቢት፣ ትምክሕት፣ መናናቅ፣ መገፋፋት፣ መጠላላትና ርኩሰት በክርስቲያኖች መካከል ሰፍኗል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የወንበዴዎች ዋሻ ሆናለች (በጌታችን እንደ ተነገረው)፡፡ ከላይ በጥቂቱ እንደተጠቆመው ከህፃናት ጀምሮ በየዕድሜ ክልሉ ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ትምህርተ ድነት መስጠቱ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ፈጽሞ አይታወቅም፡፡ ባሁኑ ጊዜ ሰባክያን ተብዬዎች በየደብሩ ተቀጥረው ምንም ፍሬ የሌለው ጩኸት ያስተጋባሉ፡፡ በሌላ በኩል እያወቁ ዝም ከማለት አሁንም ቢሆን በየደረጃው ትምህርት ለመስጠት የሚያስችል ትምህርትን ብናዘጋጅ ኃላፊነታችንን እንድንወጣ ያስችለን ነበር (ገብረዮሐንስ 2002፡ መግለጫ)፡፡ ይህንን መልእክት የጽሑፌ መንደርደሪያ እንዲሆን የመረጥኩት በውስጤ የሚመላለሰውን የ‹‹ችላ ተብሏልና ወደ እግዚአብሔር ሃሳብና ዓላማ እንመለስ›› ጥያቄ አጭርና ግልጽ በሆነ መንገድ ስለሚያስረዳልኝ ነው፡፡
 ደግሞም ቤተ ክርስቲያናችን ያለችበትን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ድክመት እንዲሁም በሰባክያኑ ውስጥ ሳይቀር ተንሰራፍቶ የሚገኘውን ፍሬ አልባነት በማሳየቱ ረገድ በዐይን ያየንና በውስጡ አልፎ ያገናዘበን ሰው ያህል ማስረዳት ስለሚያስቸግር፥ ከእኔ ይልቅ ረዘም ላለ ዘመን ባለፉበት የሕይወት ተሞክሮ ውስጥ ያከማቹትን እምቅ ትዝብት እጥር ምጥን አድርገው ያስተላለፉልንን የእኚህን አባት ቃል ቃሌ አድርጌ መናገር የተሻለ ብቻ ሳይሆን ተገቢም ነው ብዬ ስላመንኩ ነው፡፡ ይህም የሆነው እንደተባለው በውስጡ ላለፉት ሳይቀር ግልጥ ያልሆነ የትምህርት አቅርቦትን፣ ትኩረት ያልተሰጠውንና ወደ አንድ ጎን ተጥሎ የኖረውን ደግሞም አሁንም እንኳ ያሰበበት የሌለውን መንገድ እየተከተልን ይህን ያህል አማኝ አለን እያሉ መመካቱ ገበናችንን ሊሸፍንና በትምህርትና በአስተዳደር ዘርፍ ያለብንን ሥር የሰደደ መንፈሳዊ ችግር ሊሸሽግልን ባለመቻሉ በብዙ ወገኖች ተደጋግሞ እየተነሳ ያለውን ‹‹የትምህርትና የአስተዳደር ተሐድሶ›› ያስፈልጋል ጥያቄ ተገቢነት የበለጠ ትኩረት እንድሰጠውና እኔም እንዳስተጋባው በመገደዴ ነው፡፡ ይህ እንደ ተጠበቀ ሆኖ በክርስቲያናዊ ትምህርት ተኮትኩቶ ያላደገውን ምእመን ግራ እያጋቡ እነርሱ ጭምር በውል ወዳልተረዱትና በምናልባት ወደሚጓዙበት ፍልስፍና ሲጎትቱት የሚስተዋሉት ‹‹ፍሬ የሌለው ጩኸት የሚያስተጋቡት ሰባኪያን ተብዬዎች›› ሁኔታዎች ያስገኙላቸውን ክፍተቶች ተጠቅመው እየዘሩት ያለውን የትምህርት እንክርዳድ ነቅቶ ሊጠብቅና በወቅቱ ሊያስተካክል የሚችል ቢያንስ አንድ መንፈሳዊ አባት ማጣት ያስከተለው ችግር ውስብስብነትም ምንቸገረኝ የሚያሰኝ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡

ከዚህ የተነሳ የእነዚያ ‹‹የሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍ ጸሐፊ፣ አርታኢና አሳታሚ ማኅበር ቅንጅታዊ ተግባር ይህንን ለዘመናት እውነቱን እንዳያይና በዕውቀት እንዳይመራ የተደረገ ሕዝብ በባሰ የጨለማ ሕይወት እንዲዳክር ለማድረግ በቃልና በጽሑፍ የሚከናወን ጥረት አካል በመሆኑ ይህንኑ ለማሕበረሰባችን ገልጦ በማሳየት የደረሰውንና ሊደርስ ያለውን ብርቱ ችግር መከላከል አስፈላጊ ሆኗል፡፡ በእኔ እምነት ትውፊትንና ልማድን መከለያ አድርጎ የእግዚአብሔርን ቃል መቃወም ከተወቃሽነትና ከተጠያቂነት አያድንም፡፡ በክርስትና ስም ተሰባስቦና ታሪክና ቅርሳ ቅርስ እንጠብቃለን ወደሚል ዝቅታ ዝቅ ብሎ ለባሕልና ለቅርሳ ቅርስ በመወገን የእግዚአብሔር ሃሳብና ፈቃድ እንዳይፈጸም መከላከልም ተቀባይነት የለውም፡፡ ቅርሳ ቅርስ መጠበቁና ማስጠበቁ የሚያስከፋ ባይሆንም ከታሪክና ከቅርሳ ቅርስ በፊት ለእነርሱ መገኘት ምክንያትና ባለቤት የሆነው ክርስቶስ የሞተለት ሕዝብ መንፈሳዊ ሕይወት ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ትኩረት የተነፈገው ምእመን ከሁሉ አስቀድሞ የእምነቱን ቀዳሚ ፍሬ (ድኅነተ ነፍሱን) እንዲያረጋግጥ የሚያስችለውን እውነተኛ የክርስትና ትምህርት ሊገነዘበው በሚችለው መንገድ ግልጥልጥ አድርጎ ማስተማር ያስፈልጋል፡፡ አቡነ መልኬ ጼዴቅ እንዳሉት ሕዝባችን በእምነቱ ፍጹም መታመን ኖሮት ‹‹… ኢየሱስ ክርስቶስ ብለን ጌታችንን ስንጠራው የዳንን ወገኖች መድኅንም ያለን ሕዝቦች መሆናችንን፤ ክርስቶስ ከግብርናተ ዲያቢሎስ ነጻ ያወጣን መሆናችንን ማመናችንና መናገራችን ነው›› ወደሚልበት እውቀትና ድፍረት መድረስ አለበት (መልከ ጼዴቅ 1984፡37)፡፡
 የክርስቲያን መመዘኛው የተጠለለበት ተቋም ህንጻ ውበት አሊያም ተቋሙ የኖረበት ዘመን ርዝማኔና የምእመናን ብዛት ሳይሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በማመኑ ያገኘውን ዘላለማዊ ድኅነትና የሕይወት ዋስትና በእርግጠኛነት ተገንዝቦ እንደ ቀደሙት አባቶቹ፡- ከሰማይ የመጣ የእግዚአብሔርን ቃል በሥጋው ብቻውን ከሙታን ተቀድሞ እንደ ተነሳ እናውቃለን፤ በተነሳ ጊዜ አባቱ በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ ለእርሱ የሰጣቸው ምእመናን በትንሳኤ ይመስሉት ዘንድ እንግዲህ ወዲህ በቀድሞው ሰው አዳም ትእዛዝ ማፍረስ ምክንያት ፈርሰው በስብሰው አይቀሩም፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እሺ በጄ ብሎ እስከ ሞት በመድረሱ እነርሱ ፈጽመው ይድናሉ እንጂ (ዘቄርሎስ 1982፡309 ቁጥር 52) እና ያን ጊዜ በዚያ ወራት ነፍሳት ከሥጋቸው በተለዩ ጊዜ ከምድር በታች ወደ ሲዖል ይወርዱ ነበር፤ የሞት ቤቶችም እስኪመሉ ድረስ ወደ ገሃነም ይሄዱ ነበር፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባቱ ሥልጣን ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ግን ወደ መንግስተ ሰማያት ለመግባት አዲስ መንገድ አዘጋጀልን፤ እንግዲህ ወዲህ ወደ ገሃነም አንሄድም፤ ፈጣሪያችንን እንከተለዋለን እንጂ … (ዘቄርሎስ 1982፡80 ቁጥር 17)፡፡ እያለ በሚያውጀው የእምነት ቃሉ፥ በሚመራበት የክርስቶስ መንግሥት ትምህርትና ሥርዓት በመኖሩ (በፍሬው) (ዮሐ 15፥16) እንዲሁም የመንግሥቱን ዜጎች በማብዛት ሥራው ሊሆን የተገባ ነው (ማቴ 28፥20፤ ማር 16፥15)፡፡ ለዚህ መጽሐፍ መጻፍም ድምር ምክንያቶቹ እነዚሁ እንደ ዘመን አመጣሽ ትምህርት እየተቆጠሩ ያሉትና ቸል የተባሉ የእምነት ቃሎችና ፍሬዎች አማኝ በሚባለው ሕዝብ ውስጥ ስፍራ ማጣታቸው የፈጠረው ስጋት ነው፡፡ ‹‹ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ስለ ትምህርተ ድነት በኛ ቤተ ክርስቲያን ተረስቶ ኖሯል፤ ዋናውና የሕይወት ትምህርት ወደ አንድ ጎን ተጥሎ ነው የኖረው አሁንም ቢሆን ያሰበበት የለም፤ በቤተክርስቲያን የአመራር አካላትና በምእመናን መካከል እውነተኛው የእግዚአብሔር ፍቅር ፈጽሞ ተረስቷል፤ ከህፃናት ጀምሮ በየዕድሜ ክልሉ ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔርና ትምህርተ ድነት ትምህርት መስጠቱ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ፈጽሞ አይታወቅም፤ ባሁኑ ጊዜ ሰባክያን ተብዬዎች በየደብሩ ተቀጥረው ምንም ፍሬ የሌለው ጩኸት ያስተጋባሉ›› በሚለው የገብረ ዮሐንስ ገለጻ ተስማማንም አልተስማማን፥ ነቀፍነውም ደገፍነው በእኔ እምነት ደግሞም እውነትን በሚፈልጉና በሚከተሉ ዘንድ ያለንበትን ተጨባጭ ሁኔታ ገልጦ የሚያሳይና የዘነጋነውን የቀደመችውን ቤተ ክርስቲያን ሕይወትና ተልዕኮ እንድናስብ የሚያነቃ ደወል ነው፡፡ በቅንነትና ሽንገላ በሌለበት ኅሊና ከመዘንነው የተጠራንበትን ትክክለኛ ተግባር መፈጸም በሚያስችለን የትምህርት፣ የአስተዳደር፣ የሥርዓትና የአምልኮ ሂደት ላይ አለመሆናችንን የሚያስገነዝብና ልባዊ ተሐድሶ እንድናደርግ የሚያሳስብ ሕያው መልእክት ነው፡፡ ‹‹ማን ያርዳ …›› እንዲሉ ከነበሩትና አሁንም ካሉት በላይ አስረጅ አይገኝምና መስማት ለሚችልና እውነትን ለሚፈልግ ሁሉ የ‹‹ተሐድሶ››ን ማለት የእምነት ለውጥ ሳይሆን እውነቱን ፈልጎ የማግኘትን፣ በፈጸሙት በደል ተጸጽቶ ንስሃ የመግባትንና በከበረው እውነትና መሠረት ላይ ጸንቶ የመኖርን አስፈላጊነት የሚያሳይ ፋና ነው፡፡

 ይህንን የተንደረደርኩበትን የገብረ ዮሐንስን አባባል የትምህርት ተሐድሶ አያስፈልግም በሚለው ግትር አቋሙ የሚታወቀው ማኅበረ ቅዱሳን ሳይቀር ይጋራዋል፡፡ ይህንንም በራሱ መንገድ እንዲህ በማለት ይገልጸዋል፡፡ … በሥነ ምግባር የተዋበ ዜጋን የማፍራት አቅሙ እያላት አልሰራችበትም (እንዲያውም ምግባረ ብልሹነት፣ ሙስና ወዘተ አሁን አሁን በቤተ ክርስቲያን ተንሰራፍቷል) የሚሉ ትችቶችና ዘለፋዎች ከየማዕዘኑ ሲሰነዘሩ ተደምጠዋል፡፡ ትችቱ የተጋነነ ቢሆንም እውነትነት የጎደለው ግን አይደለም፡፡ … ከዚህም በተጨማሪ ቤተ ክርስቲያን ወጣቱን በትምህርትና በሥነ ምግባር ኮትኩታ ለማሳደግና ለመያዝ አለመቻሏ ሳይነሳ የሚታለፍ አይደለም፡፡ … እንደዚሁም በ1982 እና በ1983 ዓ.ም በመናፍቃን (በተሐድሶ) እንቅስቃሴ ምክንያት በቤተ ክርስቲያን በቅንዓት የተሰበሰበውን ወጣት ተገቢውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት በመስጠት በሃይማኖትና በምግባር እንዲጎለምስ፣ አገልግሎቱም እንዲፋጠን አልሆነም፡፡ … ለእረኛነት ተመርጠው በጎቹን በለመለመ መስክ እንዲያሰማሩና ከተኩላ እንዲጠብቁ የተላኩ ካህናት ከተኙበት እንዲነሱ በየዕለቱ ከሚተረከው ዓለም አቀፋዊነት ሌላ የተሻለ ቀስቃሽ ከቶ ሊመጣ አይችልም፡፡ (ሐመር 1999፡53-54) የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሀብተ ብዙ በመሆኗ ብዙ ሥራዎች ይጠብቋታል፡፡ … በዚህ መሠረት ቢያንስ ሁለት መሠረታዊ ሥራዎች ይጠብቁናል፡፡ አንደኛ እውነተኛውን ትምህርት መስጠት … የዋሕ ልጆቿም በእምነት ቢቀበሉትም ዕውቀቱ አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ በዕውቀት ያልተደገፈ እምነት ደግሞ እየቆየ መላላቱ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ ለአማኞቿ የሚሆንና ችግሮቿን የሚፈታ ለሚጠይቋቸውም መልስ በመስጠት የሚያስጨንቁበት አንዳንዶችንም ከእሳት የሚያድኑበት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ይጠበቃል፡፡ ሁለተኛ መለየትና ማዘጋጀት፡- ምንም እንኳ ቀደም ብለን እንዳየነው የአዋልድን ቁጥር መወሰን ባይቻልም የመለየትና ለአገልግሎት የመለየት ሥራው ግን ለአራተኛው ሺህ ዓመት ሊገፋ አይገባውም፡፡ … እኛ ደግሞ በመግለጽ ጊዜ ስርዋጽ የገባባቸው ካሉ በማጥራት የተጓደሉትን በማሟላት ዲቃሎቹንና እውነተኞቹን አዋልድ በመለየት ለአገልግሎት ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ … ጌታ በሚገለጥ (ዳግመኛ በሚመጣ) ጊዜ በቀኝ የሚቆም መጽሐፍና ቅርስ የለም፡፡ የሚቆሙት ሰዎች ናቸው፡፡ …ካለበለዚያ ቆፍሮ በመቅበር መጠየቃችን አይቀርም፤ እንደ ገብረ ሀካይ (ሐመር 1999፡71)፡፡

ይህንን መሠረተ ሃሳብ መነሻው አድርጎ ትክክለኛውንና ቸል የተባለውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ገልጦ ለማሳየትና ከአጥፊዎች ለመከላከል የተዘጋጀው ይህ መጽሐፍ በሰባት ምዕራፎች የተከፈለ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኪዳናት›› የሚል ርዕስ የተሰጠው የመጀመሪያው ምዕራፍ ስለ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኪዳናት ምጥን፣ ነገር ግን አሁን ለደረስንበት አዲስ ኪዳናዊ ሕይወት መሠረት የሆኑ ሃሳቦችን ያስዳስሳል፡፡ ኪዳናቱ ከአንዱ ወደ ሌላኛው እየተሸጋገሩ ፍጹም ወደ ሆነው የመጨረሻው ኪዳን (አዲስ ኪዳን) እንዴት እንደ ደረሱ ያሳያል፡፡ በተለይም ሁለቱ ኪዳናት (ብሉይና ዐዲስ) ከተሰጡበት ዓላማና ከተመረቁበት ደም አንጻር በክብርም ሆነ በአገልግሎት እንደሚበላለጡ (አንዱ ከሌላው እንደሚለይ) ማሳየት የምዕራፉ ዋነኛ ዓላማ ነው፡፡ ምዕራፍ ሁለት ‹‹የሁለቱ ኪዳናት ቅኝት›› በሚል ርዕስ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡
ምዕራፉ ከዚህ በፊት ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ በማኅበረ ቅዱሳን ታትሞ ለሕዝብ በተሰራጨ መጽሐፍ መግቢያ ውስጥ የሚገኙ የእውነተኛው ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ትምህርት ይዘት የሌላቸው ሁለት ሃሳቦችን ነቅሶ በማውጣት በመጽሐፍ ቅዱስና በቀደሙት አባቶች አስተምህሮ የሚመዘንበት ክፍል ነው፡፡ በተለይም የመጽሐፉ አርታኢና የመግቢያው ጸሐፊ የ‹‹ሁለቱ ኪዳናት››ን (የብሉይና የአዲስን) ውሕደት አስመልክቶ ያስተላለፈውን መልእክት መነሻ በማድረግ ኪዳናቱ ሊዋሐዱ የማይችሉበትን መሠረታዊ ነጥቦች በስፋት ይዳስሳል፡፡ የማይዋሐዱትን ለማዋሐድ የሚደረገውንም መደፋፈር በብርቱ ይሞግታል፡፡ ድርጊቱም ክርስቲያናዊ ተግባር እንዳልሆነ ያስገነዝባል፡፡ ምዕራፍ ሦስት ‹‹ታሪካዊ ስህተትን ላለመድገም›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህ ክፍል መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት ያደረጉ ውሳኔዎች የተላለፉባቸውን የመጀመሪያዎቹን ሦስት ዓለም አቀፍ ጉባኤያት መንስዔና የተደረሱባቸውን ውሳኔዎች ያስታውሳል፡፡ በዚህ ክፍል የሚነሳው ሃሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን እውነት በ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍና መሰል የኅትመት ውጤቶች እየተሰራጩ ከሚገኙት ኢ-ክርስቲያናዊ ትምህርቶች ጋር በማነጻጸር ያሳያል፡፡ ይህም አንባቢው ትክክለኛውን መሠረተ እምነት ተገንዝቦ ትክክለኛ ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያስችል ዕድል ይፈጥራል፡፡ ለመግለጽ እንደሞከርኩት ይህ ክፍል ይህንን መጽሐፍ ጨምሮ ማናቸውንም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ስም ተጠልለው የሚሠራጩ ትምህርቶችን በተለይም በቀጣዩ ምዕራፍ የሚዳሰሱትን ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጎልተው የታዩትን ሦስት ቡድኖች አስተምህሮ ለመመዘንና የየትኛው ወገን ትምህርት ከሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ውሳኔዎች ጋር እንደሚስማማና እንደማይስማማ ለመለየት ያስችል ዘንድ እንደ ቱንቢ ሆኖ ተቀምጧል፡፡ እነዚህ ሶስት ዋነኛ ጉባኤያት ሲነሱ ሊታለፉ የማይገባቸው ሁለተኛው የኤፌሶን ጉባኤ (ምዕራባውያን የወንበዴዎች ጉባዔ የሚሉት) እና በምዕራባውያኑ አራተኛው ዓለም አቀፍ ጉባኤ በመባል የሚታወቀው የኬልቄዶን ጉባኤ (በኦርየንታሎቹ ጉባኤ ከለባት የሚባለው) የመጀመሪያዎቹ ሶስቱ ጉባኤያት ያስተላለፏቸውን የእምነት ድንጋጌዎች በግልጽ ለመረዳት ከሚያደርጉልን እገዛ አንጻር ጥቂት ስፍራ ተሰጥቷቸዋል፡፡ በዚህም ከእነዚሁ ጉባኤያት ጋር የተያያዙ ዋና ዋና ሃሳቦች ይዳሰሳሉ፡፡ ምዕራፍ አራት ‹‹የግጭቶቻችን ማጠንጠኛዎች - ቅባት፣ ካራ፣ ጸጋ›› በሚል ርዕስ የቀረበ ነው፡፡ ይህ ክፍል ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አንስቶ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የርስ በርስ ግጭቶችና ደም መፋሰስ ያስከተሉትን ሦስት በአመለካከት የተለያዩ ቡድኖች አስተምህሮ አስመልክቶ ምጥን፥ ነገር ግን ጠቃሚ መረጃዎችን የያዘ ነው፡፡ ክፍሉ ዛሬ ዛሬ የ‹‹ተዋሕዶ›› አማኝ ነኝ የሚሉን ቡድኖች አስተምህሮ (ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ) ከእነዚህ ከሦስት ቡድኖች (ካራ፣ ቅባት፣ ጸጋ) ቢያንስ ከአንዱ ተቀድቶ አለበለዚያም የአንዱ ቡድን ትምህርት ከሌላው ቡድን ትምህርት ጋር ተዳቅሎ ሲወርድ ሲወራረድ የመጣ በመሆኑ አስተምህሯቸውን አዳምጦና መዝኖ ከየትኛው ወገን እንደሆኑ መገምገም እንደሚያስችል ይታመናል፡፡ በተለይም በቀዳሚው ምዕራፍ የተዳሰሱትን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ውሳኔዎችና ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶች ከእነዚህ ቡድኖች አስተምህሮ ጋር በማነጻጸር የትክክለኛውን ተዋሕዶ ባህለ ትምህርት ለመገንዘብ የሚኖረው ጠቀሜታ ከፍ ያለ ነው፡፡ በምዕራፍ አምስት ‹‹ልዩነቶቻችን በመጽሐፍ ቅዱስ ሲዳኙ›› የሚል ሃሳብ ይነሳል፡፡ የዚህ ክፍል ዓብይ ዓላማ በዘመናት ሁሉ ለተነሱት ሃይማኖታዊ ችግሮች (ልዩነቶች) መንስኤው ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ያለን አመለካከት መለያየት መሆኑን በማስቃኘት የ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› መጽሐፍ አዘጋጅ መሪጌታ ኃየሎምና አሳታሚው ማኅበር ማኅበረ ቅዱሳን የሚያራምዱት የእምነት አቋም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው የእግዚአብሔር ሃሳብ የሚቃረንና ጤነኛ የተዋሕዶ ትምህርት አለመሆኑን ማስረጃዎች ጠቅሶ ያሳያል፡፡
በአንጻሩም ቤተ ክርስቲያናችን የምትቀበላቸው ቀደምት ኦርቶዶክሳውያን አባቶች ያስተላለፉትን ትምህርት በእማኝነት በማቅረብ ጥንታዊውንና እውነተኛውን የተዋሕዶ ትምህርት ያስገነዝባል፡፡ ምዕራፍ ስድስት ‹‹ሕግና ትእዛዝ›› በሚል ሃሳብ ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ ሕግጋትና ትእዛዛት ለጸጋ ስፍራቸውን እንዳልለቀቁና እነርሱን መጠበቅ የጽድቅ ምንጭ እንደሆነ ሊሰብኩን ለሚሞክሩት ‹‹የሙሴ ደቀ መዛሙርት›› ሕግን የምንጠብቀው ገና ለመጽደቅ እያሰብን ሳይሆን በክርስቶስ ኢየሱስ የመስቀል ላይ ሥራ ስለ ጸደቅን መሆኑን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ እያቀረበ ያስረዳል፡፡ ምዕራፍ ሰባት ‹‹መቅደስ - የእግዚአብሔር መገለጫ›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህም መቅደስ የተባለውና ክርስቶስ የገባበት ሰማያዊ ስፍራ ‹‹መስቀል›. ነው ለሚለው የስህተት ትምህርታቸው መልስ የተሰጠበት ክፍል ነው፡፡ ከብሉይ ኪዳን የቤተ መቅደስ ጅማሬ አንስቶ ክርስቶስ የገባባት ተብላ እስከ ተገለጸችው ቤተ መቅደስ ድረስ ያለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሃሳብ በአጭሩ በማቅረብ ‹‹ቤተ መቅደስ የተባለው ጌታ የተሰቀለበት መስቀል ነው›› የሚለውን ኢ-ክርስቲያናዊ ፍልስፍና ይፋለማል፡፡ በአጠቃላይ መጽሐፉ ጤናማውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ባህለ ትምህርት ከጥፋት ለመከላከልና እውነቱን ገልጦ ለማሳየት መጽሐፍ ቅዱስንና የቀደሙ አባቶችን ትምህርት መሠረት አድርጎ የተጻፈ በመሆኑ ስለ እምነቱ ተገቢውን ግንዛቤ ለማግኘትና እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር የሚፈልግ ሁሉ ጠቃሚ ትምህርት እንደሚያገኝበት እምነቴ ነው፡፡

Sunday, March 20, 2016

በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት!

መዝ 150
ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ አመስግኑት፤ በኃይሉ ጠፈር አመስግኑት።
በችሎቱ አመስግኑት፤ በታላቅነቱ ብዛት አመስግኑት።
በመለከት ድምፅ አመስግኑት፤ በበገናና በመሰንቆ አመስግኑት።
በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት።
ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑት፤ እልልታ ባለው ጸናጽል አመስግኑት።
እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን፦ ሃሌ ሉያ።



Saturday, March 19, 2016

ያገር ያለህ ወይም የዳኛ ያለህ!!!


ከእውነቱ /ለውይይት የቀረበ/

 1/ መግቢያ

በድሮ ጊዜ ሰው በሰው ሲበደልና ፍትሕ ሲጓደል ‘ያገር ያለህ’ ወይም ‘የዳኛ ያለህ’ በማለት ይጮህ ነበር፤ ይህ ዓይነቱ የተበዳይ ጮኸትም ለትውልድ መርገም እንዳይሆን ተብሎ በአካባቢው በሚኖሩ እድሜና ልምድ ጠገብ ሺማግሌዎች ገላጋይነት/ዳኝነት የበደለ እንዲክስ የተበደለ ደግሞ እንዲካስ በማድረግ ጉዳዩ እልባት እንዲያገኝ ይደረግ ነበር፤ እኔም ዛሬ በዲሞክራሲ ስም በምድራችን ውስጥ እየሆነ ያለውን አጠቃላይ እንቅስቃሴ /በተለይ ባለውለታ በሆነችው በኦርቶዶክስ ቤ/ክ ውስጥ/ ቀረብ ብየ ስመለከት ይህ እውነተኛ የፍትህ ፈላጊዎች ያገር ያለህ ጩኸት ትዝ ብሎኝ ለኢትዮጵያውን በሙሉ ለውይይትና ለመፍትሄው ፍለጋ ጭምር የሽማግሌ ዳኞች ያለህ በማለት ጮኸቴን ላቀርብ ተገደድኩ። መቸም ለተወሰኑ ዓመታት ከአገሩ ራቅ ብሎ ለኖረ ኢትዮጵያዊ የአዲስ አባባ ገጽታ ቀየር እንደምትልበት ይታመናል፤ በርካታ ሕንጻዎችና መንገዶች ተሠርተዋል፤ ባቡርም ተጀምሮ ሕዝቡ እየተጠቀመበት መሆኑን በግልጽ ማየት ይቻላል፤ ለራሴ ሕሊና ታማኝ መሆን ስላለብኝ የሚታዩትን መልካም ነገሮች እሰየው በማለት፣ ደስ የማይሉትንና ደካማ የሆኑትን ደግሞ ለእርምት በግልጽነት ብጠቁም ሰውነቱን የሸጠ ካልሆነ በስተቀር ቅር የሚሰኝ እውነተኛ ሰው የሚኖር አይመስለኝም። እዚህ ላይ የሕንጻዎችና የመንገዶች መገንባት መልካም ቢሆንም፤ በራሳቸው ግን ያንድ አገር እድገት ዋና መስፈርቶች ናቸው ብሎ መውሰዱ ተገቢ አይመስለኝም፤ ሕንጻ ያለሰው ከንቱ የድንጋይ ክምር ብቻ ስለሚሆን! በሌላ መልኩ ደግሞ አብዛኛው ሕዝብ በኑሮ ችግር እየተጠበሰና ያገሪቱ ሃብት በጥቂቶች እጅ ውስጥ ሆኖ እያለ ኢኮኖሚስቶች በነፍስ ወከፍ የገቢ ስሌት ተመስርተው አድገናል ማለታቸው በሕዝቡ አጠቃላይ የኑሮ ምጥ ላይ የሚታየውን የህይወት ማቃሰት በግልጽ መካድ ነው የሚሆነው፤ የተመጣጠነ የሃብት ክፍፍል በሌለበት አገር ውስጥ ይህ ዓይነቱ የሂሳብ ቀመር እንዴት ሆኖ እውነተኛ ሚዛን እንደሚሆን ፈጽሞ አይገባኝም። ማየት ከመስማት የበለጠ ጥሩ መረጃ እንደሆነ ይታመናል፤ በመሆኑም አገራችን ኢትዮጵያ ምን እየሆነችና ወዴት እየተጓዘች እንደሆነ ከዚህ በፊት በጆሮዬ የሰማሁትን ዛሬ በዓይኔ አይቼ ለራሴ ህሊና ያገኘሁትን መረዳት በሚከተሉት ርእሶች ላይ ያለኝን ስጋት በትንሹ ላካፍል፡

 1. ፖለቲካውና ኢኮኖሚው በሕዝቡ ኑሮ ላይ ያስከተለው አውንታዊና አሉታዊ ተጽእኖ፣ /በሁለተኛ ደረጃ የሚታይ ይሆናል/

 2. በሐይማኖታዊ ተቋማት /በተለይ አብዛኛው ሕዝብ ችግሩን ለፈጣሪው የሚያቀርብባትና ለመጽናናት የሚሞክርባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን/ ውስጥ እየሆነ ያለው መተራመስ፤ በምድራችን ውስጥ በርካታ የሃይማኖት ተቋማት ይገኛሉ፤ ሆኖም ግን ከአገሪቱ ታሪክ ጋር ከፍተኛ ትስስር ያላትና በበርካታ ጠንካራ ጎኗ ጉሉህ ስፍራውን ይዛ የምትገኘው ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስለመሆኗ የሚክድ ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለኝም፤ ካለ ግን ልሟገተውና ጣሊያንን በምስክርነት ጠርቸ ላስመሰክርበት እችላለሁ፤ ይህ የሚሆነውም በራሳቸው ሙያ የሚተማመኑ እውነተኛ ዳኞች ከተገኙ ብቻ ነው። ስለዚች ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊ አጀማመር፣ ላገር ስላበረከተችው መልካም አስተዋጽኦ፣ በረጅም የታሪክ ሂደቷ ውስጥ ስለገጠሟት በርካታ ተግዳሮቶችና ስለከፈለችው ከፍተኛ መስዋትነት ማወቅ ለሚፈልግ /የራሱን ታሪክ ማወቅ ለሚፈልግ/ ወደ ኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ጎራ እንዲል እየጠቆምኩ፤ የዛሬውን መልእክቴን ግን በቤተ ክርስቲያኒቷ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ በስፍራው ላይ ተገኝቼ ያየሁትን እውነት ብቻ ጥንቃቄ ባለው መልኩ በዚህ የመጀመሪያ ጽሑፌ ላይ ለማቅረብ እሞክራለሁ።

   በዚች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከላይ ከፓትሪያሪኩ ጀምሮ በተዋረድ ወደታች የሚፈስ ያስተዳደር መዋቅር አለ፤ በተጨማሪ በርካታ መንፈሳዊ የትምህርት ማሰልጠኛዎች እያስመረቁ የሚያወጧቸው ወጣቶች ዐውደ ምህረቱን ሞልተውት የሰንበት ትምህርት የማስተማሩን ሥራ በሰፊው ተያይዘውታል፤ እኔን የገረመኝና የማላውቅበትን ብእር እንዳነሳ ያደረገኝ ግን በዚህ ግራና ቀኙን በማያውቅና እግዚአብሔርን በሚፈራ የዋህ ወገናችን መካከል በተለያየ መንፈሳዊ ስያሜ ተመስርተው የሚያካሂዱት የእርስ በርስ ጦርነት ነው፤ በዘመናት መካከል እኔ ‘አውቅልሃለሁ የሚልለት ተቆርቋሪ አጥቶ የማያውቅ’ አሳዛኝ ሕዝብ፤! በዚህ መሰረት ለዛሬ ማህበረ ቅዱሳንን እና ኦርቶዶክስ ተሐድሶ የሚባሉትን መንፈሳዊ ማህበራትን ከሥራቸውና ከሚያራምዱት ዓላማ አኳያ በማየት ፍርዱን ለእውነት ፈላጊዎችና ለወገን ተቆርቋሪ ወገኖች ስተወው፤ ለበለጠ መፍትሄ ፍለጋ ግን ቤተ ሰብ ከቤተሰብ፣ ጓደኛ ከጓደኛ፣ ባል ከሚስት፣ ጎረቢት ከጎረቢት፣ አንዳችን ከሌላው ጋር በእውቀትና በቅንነት ግልጽ ውይይት በማድረግ ለአገርና ለሕዝብ የሚጠቅመውን መደገፍ ለሁላችንም ይበጃል።

1/ ማህበረ ቅዱሳን ማነው?

ከማሕበረ ቅዱሳን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ሁላችንም ልንማረው የሚገባ ቁምነገር እንዳለ አምናለሁ፤ ዋና ዓላማው ግልጽ ባይሆንልኝም የአባላቱ ስብጥር፣ አባላት ለማህበራቸው የሚከፍሉት ዋጋና የርስ በርስ መደጋገፍ ይበል የሚያሰኝ ነው። እንዲሁም በየደብሩና በየገዳማቱ ለወደቁ ምስኪን ወገኖቻችን ከሚያደርገው መልካም ሥራ ባሻገር /እውተኛው ክርስትና የመስቀሉ ሥራ ውጤት እንጂ የመልካም ሥራ ውጤት አይደለም ወይም በሌላ አባባል የጽድቅ ሥራ ለመሥራት በመጀመሪያ በጸጋው አምኖ መጽደቅ አለበት ይላሉ ተሐድሶዎች/ ለባህልና ለቅርስ ጥበቃው ሥራ የሚከፍለው ዋጋም በቀላሉ የሚታይ ጉዳይ አይደለም። የዚህ ማህበር ሌላ መገለጫ ባህሪው የተለያየ የጉዞ ፕሮግራም በማዘጋጀት ሕዝቡ ገንዘቡን ከፍሎ በነጭ ልብስና በኢትዮጵያ ባንዲራ ከቦታ ቦታ እንዲንቀሳቀስ በማድረግ የሕዝቡ ማህበራዊ ትስስር እንዲበረታታ ያደርጋል፤ ሌላው አብዛኛው ሕዝብ አዲስና ልዩ ፈዋሽ ጸበል ተገኘ በተባለበት ስፍራና በየገዳማቱ ሁሉ አብዝቶ እንዲንቀሳቀስ ያደርጋል።
ማህበሩ በተጨማሪ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል ጥቂቶቹ፡- ሕንጻ መገንባትን፣ ንግድ መነገድን፣ የራሳቸውን አባላት ማሰልጠንን፣ አዳዲስ ታቦታት መትከልንና ስነጽሁፎችን በሰፊው አውጥቶ ማሰራጨት ሲሆኑ በእነዚህ ጽሁፎቻቸውም ላይ በዋናነት ተሐድሶን የሚያጥላላና የሚያወግዝ መልእክት በትኩረት ያወጣል። የማህበሩን እንቅስቃሴ ለማጠቃለልም፡  የውስጣቸውን/የልባቸውን ባላውቅም አለባበሳቸው በባንዲራ የታጀበ ነጭ ልብስ በመሆኑ የየዋሁን ሕዝባችንን ልብ ለዓላማቸው በቀላሉ ማማለል ይችላሉ፤ ችለዋልም፣  ለቅርስና ባህላዊ እሴቶቻችን ከፍተኛ ትኩረት በመስጠታቸውም ለአገር ብቸኛ ተቆርቋሪ ከነሱ ሌላ ፈጽሞ የሌለ አስመስሏቸዋል፣  ባህላዊ የቆሎ ትምህርት ቤቶች የበለጠ እንዲጠናከሩ ድጋፍ ያደርጋል፣ የገዳምና የምንኩስናን ኑሮ በማበረታት ምሁራን ሳይቀሩ ወደገዳም እንዲገቡ ያበረታታል፤ እንዲያውም ከውጭ አገር ኑሯቸው ተመልሰው ገዳም እንዲገቡ የተደረጉ እንዳሉ ይነገራል፣  ዘርዓ ያዕቆብን የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለወለታ በማድረግ ያወድሱታል፤ታሪኩንም ሕዝቡ እንዲያውቀው ለማድረግ የተደጋገመ ወርክሾፕ በስሙ አድርገውለታል/እያደረጉለትም ነው፣  መጽሐፍ ቅዱስ የማያውቃቸውን አዳዲስ ቅዱሳንን ሳይቀር ሕዝቡ እንዲያውቃቸውና ጽላት/ታቦት እንዲቀረጽላቸው ያደርጋል፤ አድርጓልም /ምሳሌ አርሴማ የምትባልን ነጭ ሴት/፣  ለአባላቱ ሁለንታዊ ድጋፍና ስልጠና በትጋት ከማድረጉም ባሻገር በምረቃና በሰርግ ላይ ከበሮና ጸናጽን ይዞ በመገኘት በሚያደርገው ሞቅ ያለ የሽብሸባ አምልኮ ከጴንጤዎች ጋር ውድድር የገባ አስመስሎታል፣  ሕንጻ ይገነባል፣ ንግድ ይነግዳል፣ ገንዘብ ይሰበስባል፣ አባላትን ያደራጃል /ከቀን ሰራተኛ እስከ ምሁር ባለስልጣናት ድረስ/፣  በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ የሚማሩትን ተማሪዎች በማሰልጠንና በእረፍታቸው ወቅት ወደየቤተ ሰቦቻቸው በመላክ ዓላማቸውን በሰፊው እንዲያስተዋውቁላቸው ያደርጋል //ይህን በተመለከተ አንድ በመንፈሳዊም ሆነ በታሪክ በቂ እውቀት የሌለው /ከስሜታዊነት በስተቀር/ የወንድሜ ልጅ መሳተፉን አጫውቶኛል//፣  ማህበሩ በሚያደርገው አጠቃላይ እንቅስቃሴ አባላቶቹንና የዋሁን ሕዝብ ፍጹም የጉልበት ሃይማኖተኛ እያደረገው እንደሆነ በአንዳንድ ደብር በስሜታዊ አባላቱ በኩል የሚታዩት የደም መፋሰስ ግጭቶች ይመሰክራሉ፣  አዳዲስ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ሥራ ላይ በሙያተኞቹ በኩል በሰፊው ይሳተፋል፣  ጎልቶ የሚታየው ሌላው ሥራው በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ ከሚገኙ አገልጋዮች መካከል አንዳንዶችን በመክሰስና ከሥራ በማሳገድ እስከ ቤተሰባቸው ችግር ላይ እንዲወድቁ ያደርጋል /ይህ በደል የደረሰባቸውን አንድ ሊቅ ይህ ጸሐፊ አናግሯል/፣  ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተሃድሶ ያስፈልጋታል የሚሉትን ጳጳሳት፣ ካህናት፣ መሪጌቶች፣ መነኮሳት፣ ዲያቆናትና አባላትን በሙሉ የፕሮቴስታንት ቅጥረኞችና ጸረ ኦርቶዶክስ ናቸው በማለት በመጽሄታቸው፣ በጋዜጣቸውና በአውደ ምህረት ላይ በማውጣት ከፍተኛ ዘመቻ ያደርጋል።
ይቀጥላል


Sunday, March 13, 2016

እነሆ ሁለቱ ኪዳናት!

መቅድም
 ‹‹እነሆ ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀው ይህ መጽሐፍ በ2002 ዓ.ም ‹‹ሁለቱ ኪዳናት›› በሚል ርዕስ በመሪጌታ ሃየሎም ተዘጋጅቶ በማኅበረ ቅዱሳን አሳታሚነትና አከፋፋይነት በተሠራጨው መጽሐፍ ውስጥ ለተላለፉት ኢ-ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮዎች መልስ ለመስጠት ቢሆንም በችግሮቹ ላይ ብቻ ከማትኮር ይልቅ አንባቢያን ሃሳቤን በቀላሉ እንዲረዳልኝ ያስችላሉ ያልኳቸውን መሠረታዊ የመጽሐፍ ቅዱስና የታሪክ እውነታዎች በማሰባጠር በማስረጃ አስደግፌ ለማቅረብ ሞክሬያለሁ፡፡ የዚህን ጽሑፍ ረቂቅ ያሳየኋቸው አንዳንድ ወንድሞች የሁለቱ ኪዳናትን ጸሐፊ፣ አርታኢና አሳታሚ ማኅበር የእምነት አቋም ተወራራሽነት ለመግለጽ የተጠቀምኩባቸውን የወል ዐረፍተ ነገሮች ባስተካክላቸውና በጸሐፊው ላይ ብቻ አትኩሬ መልእክቴን ባስተላልፍ እንደሚሻል አስተያየት ሰጥተውኛል፡፡ ሃሳባቸውን በሃሳብነቱ ብቀበለውም እንዳሉት ሶስቱን አካላት ነጣጥዬ ማየት ግን አልሆነልኝም፡፡ ለዚህም ምክንያቴ አርታኢው ከአርትዖት ተግባሩ ባሻገር የመጽሐፉን መግቢያ በማዘጋጀትና በመጽሐፉ የተካተተውን አስተምህሮ ‹‹ትክክለኛነት›› አጽንኦት ሰጥቶ በማስተጋባት እንዲሁም ማኅበሩ በሐመረ ተዋሕዶ 2001 ዓ.ም ልዩ እትሙ‹‹እቅበተ እምነት (አፖሎጂ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን›› በተሰኘ አምድ ሥር ‹‹ሁለቱ ኪዳናት ማኅበረ ቅዱሳን በተለያየ ጊዜ በመጻሕፍትና በመጽሔት በቃል ትምህርትም መናፍቃን ለዘሩት የጥርጥር ትምህርት መልስ የሰጠበት መጽሐፍ›› ነው ብሎ መገለጹ በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኘው የእምነት አቋም የጸሐፊው ብቻ ሳይሆን የአርታኢውና የማኅበሩ ጭምር መሆኑን የሚያረጋግጥ መሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ መጽሐፍ በተገለጠው የትምህርት አቋማቸው ብርሃኑ፣ ሐየሎምና ማኅበረ ቅዱሳን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸውና ብርሃኑንም ሆነ ሐየሎምን ሳመሰግን ሶስቱንም ማመስገኔ፣ እንዲሁም የብርሃኑንም ሆነ የሐየሎምን ሃሳብ ስቃወም ሁሉንም መቃወሜ መሆኑን ማስገንዘብ ተገቢ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ በእኔ እምነት ብርሃኑ ስለማያምንበት ነገር መንደርደሪያ አልጻፈም፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የእምነት አቋሙ ያልሆነን ትምህርት አሳትሞ አላሰራጨም፤ ለመናፍቃኑ የተሰጠ መልስ ነው እያለም አልፎከረምና ከምስጋናውም ሆነ ከወቀሳው ሊጎድሉ አይገባም ብዬ ሁሉንም ያለ ልዩነት እንዲጋሩት አድርጌያለሁ፡፡

እንደማምነው ካራ፣ ቅባት እና ጸጋ ሁሉም የተዋሕዶ አማኞች ናቸው፡፡ እንግዳ አመለካከት ሊመስል ቢችልም እንኳ ንስጥሮስ፣ አቡሊናርየስ፣ አውጣኬና ፓፓ ሊዮም ሳይቀሩ የዚሁ የተዋሕዶ ጽንሰ ሃሳብ አራማጆች ናቸው፡፡ ልዩነቱ የተፈጠረው ተዋሕዶን ለመግለጽ በተጠቀሙበት ቃል ትንታኔ ላይ ነው፡፡ አውጣኬ ተዋሕዶውን ያስረዳበት መንገድ መለኮት የሥጋን ባሕርይ መጥጦታል የሚል በመሆኑ መጠፋፋትን እንጂ የሁለቱን ባሕርያት መገናዘብ አያስረዳም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትም የለውም ተብሎ ተወገዘ፡፡ አቡሊናርየስ ክርስቶስ የሰው ነፍስ የለውም፤ በነፍሱ ምትክ ነፍስ የሆነለት መለኮት ነው አለ፡፡ በዚህም የክርስቶስን ፍጹም ሰውነት አጎደለ ተብሎ ተተቸ፤ ተለየ፡፡ ንስጥሮስም በበኩሉ የቃልና የሥጋ ተዋሕዶ ሁለቱ አካላት የየግል አቋማቸውን ጠብቀው የየራሳቸውን ሥራ እየሠሩ የሚኖሩበት ስምምነት (moral union) ነው አለ፡፡ እንደ እርሱ አባባል መለኮት በሥጋ ውስጥ አደረ እንጂ ባሕርያዊም ሆነ አካላዊ ተዋሕዶን አላስከተለም፡፡ ታዲያ ይህም ቢሆን የክርስቶስን አሐዱነት በተገቢው መንገድ አይገልጥም ተብሎ ተነቀፈ፡፡ በግልጥ እንደሚታወቀው የፓፓ ሊዮ አቋም ሁለት ባሕርያት በአንድ አካል የሚል ነው፡፡ ይህም ቢሆን ተዋሕዶን ምሉዕ በሆነ መንገድ አይገልጥም፡፡ አካል ያለ ባሕርይ ባሕርይም ያለ አካል ሊኖሩ አይችሉምና አንዱ የክርስቶስ አካል የማን ነው? የሚል ውዝግብ አስነሳ፡፡ ይህም አስተምህሮው በኦርየንታሎቹ ዘንድ ጥያቄ ላይ ወደቀ፡፡ በዚህም እንደሚታየው ፓፓ ሊዮም በሁለቱ ባሕርያት መኖር ላይ ከማትኮሩና የክርስቶስ አካል የመለኮት ነው ከማለቱ በቀር ተዋሕዶን አልተቃወመም፡፡ በመጀመሪያው የኤፌሶን ጉባኤ ተቀባይነት ያገኘው የቅዱስ ቄርሎስ የ‹‹ተዋሕዶ›› አስተምህሮ (ምንም እንኳ ምዕራባውያኑ በትክክል ባይረዱትና ከፓፓ ሊዮ የአንድ አካል ሁለት ባሕርይ፣ አልፎ ተርፎም ከአውጣኬ የመጠፋፋት ትምህርት ጋር ሊያመሳስሉት ቢሞክሩም) ሁለቱ አካላትና ሁለቱ ባሕርያት ሳይጠፋፉ፣ ሳይነጣጠሉ፣ ሳይቀላቀሉ አንዱ የሌላውን አካልና ባሕርይ ገንዘብ የተደራረጉበትን ከሁለት አንድ የመሆን ምስጢር (አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ ፈቃድ፣ አንድ ግብር) የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ይህም በተዋሕዶ የተገለጠው ኢየሱስ ክርስቶስ ያከናወናቸው ተግባራት ሁሉ ይህ የሥጋ ነው ያኛው ደግሞ የመለኮት ነው ተብለው ሳይከፈሉ በአንዱ በክርስቶስ (ሥግው ቃል) የተከናወኑ ናቸው የሚል ነው፡፡ በዚህ አስተምህሮ መሠረት እንደ ንስጥሮሳውያንና እንደ ኬልቄዶናውያን (ፓፓ ሊዎ) ድካሙን ለሥጋ ብርታቱንና ማዳኑን ለመለኮት የመስጠት ሙከራ በብርቱ የተነቀፈ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ከአውጣኬያውያንና ከነፓፓ ሊዮ የተዋሕዶ ሃሳብ በእጅጉ ይለያል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም በአቋም ደረጃ ይህንን ትቀበላለች፡፡

እንግዲህ በቤተክርስቲያናችን የሚታወቁት ሶስት ቡድኖች ምንም እንኳ ‹‹ተዋሕዶ›› ነን ቢሉም የተዋሕዶ አስተምህሯቸው ከላይ ከተገለጹት ተዋሕዶ ነን ባዮች ከየትኛው ምንጭ እንደተቀዳ በጥንቃቄ መፈተሽ ቀዳሚውንና ትክክለኛውን የተዋሕዶ እምነት ተገንዝቦ ለመከተልና ያለ እውቀት ከሚሰነዘር ትችት ለመታቀብ ያስችላል፡፡ ከዚህ የተነሳ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያው የኤፌሶን ጉባኤ ያጸደቀችውን የተዋሕዶ ጽንሰ ሃሳብ ከነአውጣኬና ከነንስጥሮስ የተዋሕዶ ትርጓሜ ለመለየትና አንባቢያንን ከድንጋሬ ለመጠበቅ ‹‹ትክክለኛው›› የሚል ገላጭ ቃል ተጠቅሜያለሁ፡፡ በኢትዮጵያውያኑ የእምነት ጎራዎች (ካራ፣ ቅባት፣ ጸጋ) አስተምህሮዎች ላይ የመጻፉ ጉዳይ ብዙም አልታየኝ ነበር፡፡ ሆኖም የአንዳንድ ጊዜ የገጠማቸው ግለሰቦችና ቡድኖች አስተምህሮ ምንጭ በብዙሃኑ ስለማይታወቅ ከነሰባልዮስና ከነአውጣኬ ወገን ተሰልፈው የነቄርሎስን እምነት እንከተላለን እያሉ እውቀቱ የሌለውን ምእመን ከማደናገር አልፈው በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጠውን የእግዚአብሔር ቃል በመቃወም ላይ ስላሉና የእነርሱን ፈለግ ያልተከተሉትን ሁሉ እያሳደዱ እውነተኛ መስለው ለመታየት ሌት ከቀን እየተጣጣሩ ስለሚገኙ የአሳዳጆቹም ሆነ ተሐድሶ ናቸው በሚል ሽፋን እየተሳደዱ ያሉት ወገኖች ማንነት በግልጽ ይታወቅ ዘንድ እንዳልኩት ብዙም ትኩረት ላደርግባቸው የማልፈልጋቸውን ሶስት ቡድኖች አስተምህሮ ከመረጃ መጻሕፍት አሰባስቤ ለማቅረብ ተገድጃለሁ፡፡ በተለይ ማኅበረ ቅዱሳን የነቄርሎስን የተዋሕዶ ለምድ ለብሶ የሚያቀነቅነው ‹‹ሰባልዮሳዊ›› እና ‹‹አውጣኬያዊ›› ተዋሕዶ ፍንትው ብሎ ይታይና ትክክለኛው ማንነቱ ይገለጥ ዘንድ ይህንን ማድረጌ ተገቢ እንደሆነ አምናለሁ፡፡ በተረፈ ወደ መሠረታዊው ሃሳቤ ለመሸጋገር አንድ ጸሐፊ በተናገሩት ቁም ነገር ሃሳቤን ልቋጭ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህ ትውልድ የሚፈልገውን እውነት በውስጧ ይዛለች፡፡ ነገር ግን እውነቷን ባልተዛባና ትውልዱ በሚፈልገው መንገድ ገልጣ ልታቀርብ አልቻለችም አብዛኛዎቹ የስብከት መድረኮቿ የተሞሉት ሌላውን በመንቀፍ ወግና ሥርዓትን ታሪክን በመተረክ ላይ በተመሠረቱ ስብከቶች ነው፡፡ በማኅበርና በግል ደረጃ በጽሑፍ የሚተላለፉ መልእክቶችም ይኸው ገጽታ ነው ያላቸው፡፡ ያለባትን ችግር በመረዳት በሚፈለገው ሁኔታ ወንጌልን የሚሰብክ አንድ ሰው ቢነሳ እንኳ በጥርጣሬ መንፈስ እየታየ በተለያዩ ውንጀላዎች ከመድረክ የሚወገድበት መንገድ ይፈለጋል (አግዛቸው ቀ.አ፡5)፡፡

ለእኔም እውነታው ይኸው ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ የአውጣኬያዊውና የሰባልዮሳዊው ተዋሕዶ ትምህርት በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ሠርጎ መግባቱ ነው፡፡ እንደ ተባለው የከበረ እውነት አለን፤ ነገር ግን በዘመናት ሂደት ውስጥ ተቀብሯል፡፡ ስለዚህ የተቀበረው እውነት ተፈልፍሎ ሊወጣና ምእመኑ በግልጥ እንዲያውቀው ሌሎችም ቢሆኑ መሠረታዊውን የተዋሕዶ አስተምህሮ ተገንዝበው አጓጉል ነቀፋዎችን ከመሰንዘር እንዲቆጠቡ ማድረግ ይገባል፡፡ ለዚህም ብርቱ ትግል፣ ለመታገልም እውነቱን ከሃሰቱ መለየት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከጥላቻ በጸዳ መንፈስ ከማንበብና ከመወያየት የተሻለ መንገድ የለም፡፡ አለመደማመጥና ምን ያመጣሉ ለሮም ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያንም እንዳልበጃት ከታሪክ መማር ይገባል፡፡ ስለዚህ ንባብዎ እውነቱን ለመፈለግና በመመካከር መልካሙን መንገድ ለመከተል ይሆን ዘንድ ከልቤ እመኛለሁ፤ እጸልያለሁም፡፡ ሌላው ምናልባት ላሳውቀው የሚገባኝ መልሱ የዘገየበትን ምክንያት ነው፡፡ እንደ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ጊዜ እስኪደርስ ነው ብዬ ባስብም ይህ ጽሑፍ ከታሕሣስ 2003 ዓ.ም ጀምሮ እስከዚህ ጊዜ ድረስ በእጄ ላይ እየተንከባለለ ድፍን አምስት ዓመታት ማስቆጠሩን ሳስበው በጥቂቱ አዝናለሁ፡፡ በሌላ መልኩ ምንም እንኳ እንዲታተም ብዙ ጊዜ ተመኝቼ ባይሳካልኝም እንደ ቀልድ ባለፉት በእነዚያ ዓመታት ውስጥ እኔ ባደግሁበት ዕድገት ልክ የማደግና የመብሰል ዕድል አግኝቷልና ደስ ይለኛል፡፡ ምናልባትም ቀድመውና ዘግይተው ከተጻፉ ጓደኞቹ ይልቅ የመታተሙን ቅድሚያ እንዲያገኝ የረዳው ይኸው ሳይሆን አይቀርም፡፡ እንዲህም ሲሆን ፍጹም ነው ማለቴ አይደለም፡፡ ይልቁንም ገና ‹‹ሁ›› ስለሆነ ከስህተትና ከችግር የጸዳ ላይሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ አንብባችሁ በምትሰጡኝ ምክርና ተግሳጽ ታግዤ ስህተቴን በማረም የተሻሉ ሥራዎቼን ይዤ እንደምቀርብ ተሥፋ አደርጋለሁ፡፡ እስከዚያው መልካም ንባብ!!!
                         ጸሐፊው

Thursday, March 10, 2016

የተሸጠ ብኩርና!

(መነሻ ሃሳብ በደግፌ ጃክሰን)

  ነጠላ ያስረዘሙ ፈሪሳዊ ሰልፈኞች ከመጻሕፍቱ ጀርባ በኦርቶዶክሳዊ አቋቋም አደግድገው ቆመዋል። ከድንኳኑ ውጨኛው ክፍል "5ኛው የማኅበረ ቅዱሳን የመጻሕፍት ኤግዚቢሽን"የሚል ጽሑፍ በጉልህ ተጽፎ ተሰቅሏል። ሰይጣንም፣ ክፉውም፣ ጠማማውም፣ ነፍሰ ገዳዩም፣ ወንበዴውም፣ ሟርተኛውም ሰው "ቅዱስ ነኝ"ቢል በዚህ ዘመን የሚጠይቀው ስለሌለ (አሁን ጥያቄ የለም ማለት እስከመጨረሻው ጥያቄ የለም ማለት አይደለም) በቅድስና ማኅበር ስም የተጻፈውን ማስታወቂያ ካነበብኩ በኋላ ስለቅድስናው የሚመሰክር ፍንጭ ፍለጋ ወደድንኳኑ ጎራ አልኩ።  እዚህ ላይ አንባቢን ላስገነዝብ የምፈልገው ነገር እኛ ለራሳችን የምንሰጠው ስም ሳይሆን የምንሰራው ሥራ ነው የዋጋችንን ሚዛን ሊወስን የሚችለው። ጠንቋይ ቤት የሚካኤልና የማርያም ስዕል ተሰቅሎ መገኘቱ ወይም የገብርኤልን ዝክር እንድትደግስ በማለት ባለሀድራው በማጓራቱ ጠንቅ ዋይነቱን ወደቅድስና ማዕረግ አይለውጠውም።
ወደፍሬ ነገሩ ስመለስ፣ ከቅዱሳኑ ማኅበር ድንኳን ጎራ ብዬ የእግዚአብሔርን ቅድስና የሚያውጁ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን መድኃኒትነት የሚናገሩ፣ ዓይን ሁሉ ወደቀራንዮ እንዲመለከት የሚያሳስቡ መጻሕፍት ፍለጋ አማተርኩ። ጠላታችሁ ይፈር፣ አንድም መጽሐፍ በማጣቴ አፈርኩ። ይልቁንም እልክ የተጋቡ በሚመስል መልኩ ከዚህ በተቃራኒ የሰዎችን እይታ ከቀራንዮ በማስኮብለል ወዳልሆነ ቦታ የሚነዱ፣ ክርስቶስን በሰዎች ማንነትና ትልቅነት የሚጋርዱ ሆነው አገኘኋቸው። ካየሁት የመጻሕፍት ዐውደ ርእይ የተረዳሁት ነገር የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ ብቸኛ አዳኝነት፣ መንገድና ሕይወትነት ከመስበክ ይልቅ ቅጠልም፣ አፈርም፣ ዳቦም፣ ንፍሮም፣ ጠላም፣ ቅራሪም፣ አተላም፣ ተራራ ለተራራ መዞርም ሳማ ሰንበትም፣ አርሴማም፣ የግሼኗ ማርያምም፣ ኩክየለሽ ማርያምም፣ ግንድ አንሳውም፣ ሺህፈጁም፣ ጭሱም፣ ጠበሉም፣አመዱም፣የባህር ዛፍ ቅጠሉም፣ ጥንጁቱም፣ ቅርንፉድ መታጠንም፣ ቅማልና አይጥ ስእለት ማድረስም ገነት፣ መንግሥተ ሰማያት ሰተት አድርገው ያስገባሉ ትባላለህ። በቃ ያስገባሉ ከተባልክ አሜን ብለህ መቀበል ነው።  የኢየሱስስ ማዳን ምን ሊሆን ነው? ብሎ መጠየቅ፣ ማጉረምረም አይቻልም። መናፍቅ፣ ተሀድሶ፣ ጴንጤ ገለመሌ ካልሆንክ በስተቀር በክርስቶስ ላይ ተጨማሪ ልዩ ልዩ ተስፋዎች ሲቀርቡልህ አልቀበልም ማለት አትችልም።  "መንፈስን ሁሉ አትመኑ፣ ነገር ግን መንፈስ ከእውነት እንደሆኑመርምሩ"  የሚለውን ትምህርት ከማንበብ ውጪ ወደተግባር መለወጥ ክህደት ነው። ይህንን በመቃወም ፉከራው የገፋው ሰይጣን፣ አሹልኮ ያስገባቸውና በዘመናት ሂደት ጠፍተውና ቁጥራቸው ተመናምኖ የቆዩ መጻሕፍትን ይኼ ቅዱስ ነኝ የሚለው ማኅበር በባትሪ ፈልጎ በማሰባሰብ አራብቶና አባዝቶ አገልግሎቱን ማጠናከሩን በአግራሞት ተመለከትኩ። ሰይጣን በዚህ አገልግሎት ከመቼውም በላይ ደስተኛ ሳይሆን አይቀርም።  ማንነቱን መርምረው እንዳያውቁ በዘመቻ እየደፈቀ፣ ክህደቱን ለማግነን የሰራባቸው እንደዚህ የሰራባቸው ዘመናት አልታዩም። ኢየሱስ ክርስቶስ የንፍሮ ውሃ የጠጣልህን እስከ ዐሥር ትውልድ እምርልሃለሁ የሚል ቃል በ33 ዘመነ መዋዕለ ሥጋዌው ለማንም አላስተማረም። ይልቁንም ሌላ የመዳኛ መንገድ እንደሌለ አስረግጦ መናገሩን እናውቃለን።
ዮሐንስ 14፣6
"ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም"
ማኅበረ ቅዱሳን ግን የለም፣ ወደአብ መግባት የሚቻልባቸውንና ሰዎች በቀላሉ ከፈፀሟቸው የሚድኑባቸው ልዩ ልዩ ብልሀቶች አሉኝ የሚሉ መጻሕፍትን በአደባባይ ይሸጣል።  በዚያ ኤግዚብሽን ላይ ከተደረደሩት መጻሕፍት መካከል  “ወናሁ ትመውት በሕማመ ብድብድ እኩይ ሞት፣ ወእሬሲ ለከ ኪያሃ ከመ ስቅለትየ ወከመ ደመ ሰማዕት እለ እምቅድሜከ አኮ ለባሕቲትከ አላ ደቂቅከኒ እለ ይወውቱ በሕማመ ብድብድ በውስተ ዛቲ ገዳም እኌልቆሙ ምስለ ሰማዕታት ወአወፍዮሙ ለከ መንግሥተ ሰማያት”
ትርጉም፦ “እነሆ በክፉ ሞት በተቅማጥ ትሞታለህ፣ እሷንም እንደ ስቅለቴና ከአንተ በፊት እንደነበሩት ሰማዕታት ደም እቆጥርልሃለሁ ነገር ግን ለብቻህ አይደለም በዚች ገዳም በተቅማጥ በሽታ የሚሞቱትን ልጆችህንም ቁጥራቸውን ከሰማዕታት ጋራ አደርጋለሁ፣ መንግሥተ ሰማያትንም እሰጣቸዋለሁ” የሚለው ገድለ ተክለ ሃይማኖትን ገለጥ አድርጌ እንደገዢ ሰው አየሁት። ስድስት ክንፍ እንደተተከለለት የተቆረጠ እግር አለፍ ብሎ ወድቆ በስዕል ይታይ ነበር።
አቡነ አረጋዊ በዘንዶ ሲንሸራሸሩ፣ ለማርያም ድግስ የተቆላ አሻሮ የሸተተው ገነት እንደገባ፣ የሴት ብልት ስሞ ማርያም አፈወርቅ እንዳለችው የሚያትት፣ እግዚአብሔርን ክዶ በማርያም እንደዳነ የሚተርክ፣ ሰይጣን መነኮሰ፣ 30 ትውልድ ተማረ፣ ሎጥን ያዳነችው ማርያም ናት፣ መርቆሬዎስ ፀሐይና ፈረቃን ፈጠረ፣ ገብርኤልና ሚካኤል ሠለስቱ ደቂቅን አዳኑ፣ ሲኦልን የሞሉት ጋላና ሻንቅላ፣ የአርሴማ ድንግል ድንጋይ መካን አስወለደ፣ የአድዋን ጦርነት ጊዮርጊስ አሸነፈ ወዘተ ወጎችን የሚጠርቁ መጻሕፍት እንደጉድ ሲቸበቸቡ ተመለከትኩ። የሆኖስ ሆኖ ጊዮርጊስ አድዋ ላይ ከተዋጋ ጀግኖች አርበኞች ምን ሰሩ ሊባል ነው? የሞቱትና የቆሰሉት ምን ሲያደርጉ ኖሯል? ነው ወይስ መቁሰልና መሞት አልነበረም?
"የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል" እንዲሉ ሰዎቹ ጊዮርጊስ ባይኖር ጣልያንን ባላሸነፍንም ነበር ይሉናል። ኢህአዴግ ደርግን ያሸነፈው ማንን ይዞ ይሆን?
ማኅበሩ እያራባ ከሚሸጣቸው መጻሕፍት አብዛኛዎቹ ወንጌልን የሚቃወሙ፣ ባዶ ተስፋ የሚሰጡ፣ ሰው ከወንጌል ይልቅ እነዚያን እንዲያነብ የሚገፋፉ፣ የክርስቶስ ኢየሱስን የማዳን ሥራ አስትተው በትርኪ ምርኪ ቃል ኪዳን ላይ እንዲታመኑ የሚያበረታቱ መጻሕፍት ብቻ ድንኳኑን ሞልተው አይቻለሁ። ታዲያ ይህንን የስሁታንን ሥራ የሚሸጠው ማኅበር ራሱን "የቅዱሳን" ሲል ያሞካሸዋል።
ሰይጣን አስርጾ ያስገባቸውና በዘመናት ብዛት ተቀዳደውና ተመናምነው የሚያባዛለት አጥቶ በደነገጠበትና ተስፋ በቆረጠበት ሰዓት ማኅበሩ ድንገት ደርሶ እንደታደገው ማረዳት አይከብድም። ሊወገዙ የሚገባቸው የባዶ ተስፋ መጻሕፍትን ከወንጌል በላይ አሳትሞ ማሰራጨት ከቶ ምን ይባላል?
ከኤግዚቢሽኑ መጻሕፍት እንዲህ የሚል ቃል ያለበት መጽሐፍም ነበር።
«ወሶቤሃ አውስአ  ወይቤላ ንስኢ ወሐብኩኪ ዐሥራተ ብዙኀ ነፍሳተ መጠነ ነጠብጣብ ዝናም ዘ፬ቱ አውራኅ ለእለ አሐዱ ዕለት»
ትርጉም «ጌታም እንዲህ አላት። በዐራት ወራት ውስጥ በየቀኑ የሚወርደውን የዝናም ነጠብጣብ ያህል ነፍሳትን ዐሥራት አድርጌ ሰጥቼሻለሁ» ገድለ ክርስቶስ ሰምራ
 በዓለም ላይ በየቀኑ የሚዘንበውን የአራት ወራት ያህል የዝናብ ነጠብጣብ ውሃ ያህል ሰው ከአዳም ጀምሮ አልተፈጠረም። ገድሉ የተፈጠረውንም፣ ያልተፈጠረውንም ክርስቶስ ሰምራ ታድን ዘንድ ቃል ተገብቶላታል ይለናል።  በዚህ ቃል መሠረት ኦርቶዶክስ በክርስቶስ ሰምራ በኩል የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ናት ማለት ነው።
በሮሜ 10፣3 እንደተመለከተው
"የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም" የሚለው ቃል ከሚፈፀም በቀር እንኳን ለዓለሙ አዳኝ ልትሆን ቀርቶ ራሷም ከቆመችበት የአበው አስተምህሮ ተንሸራታ ተስፋ በሌለው ተረታ ተረት ተሸፍናለች።  ማኅበሩ የመጋረጃውን አገልግሎት በማስፋት ሰዎችን ወደጥፋት እንዳይነዳ  እንደሄሜዎስና እስክንድሮስ ለሰይጣን ተላልፎ የተሰጠ ይሁን! ብኩርናውን ለጥቅም፣ ትጋቱን ለስሁት አገልግሎት፣ ሐዋርያትም ከሰበኩት ስብከት የተለየውን የሰበከ የተረገመ ይሁን! አሜን።

Saturday, February 27, 2016

የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም!

አንዳንዶች ከአበው የተረከብነው አስተምሕሮና ሕግ በማለት ሁሉን ነገር እንደወረደ እንድንቀበለው ይፈልጋሉ። አዎ፣ አበው ብዙ ነገር አስተላልፈውልናል። ነገር ግን የተላለፈልን ነገር ሁሉ ጠቃሚ ነው ማለት አይደለም። ለእግዚአብሔር ይቀርብ የነበረ የቤተመቅደሱ መስዋእት በመቅደሱ ሚዛን ይለካ እንደነበረው ሁሉ የተላለፈልን የአበው አስተምሕሮ ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል ሚዛን መሰፈር አለበት። ምክንያቱም ከኛ በፊት ያለፉ ሁሉ በእድሜ አበው ቢሆኑም በአስተምሕሮ ግን በአበው ከለላ የስሕተት አስተምህሮ በስማቸው ሊገባ ይችላልና ነው። ስለሆነም በጅምላ አባቶቻችን ማለት ብቻውን ከስሕተት አያድንም። የአባቶች ትምሕርት ከመጻሕፍት ውጪ እንዳይኾኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በአንድ ወቅት አይሁዳውያን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምሕርት እንዲኽ እንደዛሬው የተቃወሙት እኛስ ከአባታችን ከአብርሃም ነን እያሉ ነበር። አብርሃም አባታቸው መሆኑን ቢናገሩም በአብርሃም ስም ከመነገድ በስተቀር የአብርሃምን ስራ የማይከተሉ ነበሩ ተግባራቸው ይመሰክር ነበር።

ዮሐንስ 8፣39
መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው፡ አሉት። ኢየሱስም፦ የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር፣ ብሏቸዋል።
ዛሬም ከሙሴ የተቀበልነው የታቦት ሕግ አለን የሚሉ አሉ። ነገር ግን ለሙሴ የተሰጠውንና ያደረገውን ሥራ አያደርጉም። ግን በሙሴ ስም ይነግዳሉ፣ ያታልላሉ፣ ይዋሻሉ። ሙሴን አውቀውትማ ቢኾን ኖሮ ሙሴ ያደረገውን ባደረጉ ነበር። ሙሴ የታዘዘውና ያደረገውን ይኽንን ነበርና።

ዘጸአት 25፣10
ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን።
ሙሴ ለጽላቱ ማኅደር ይሆን ዘንድ እንዲሰራ የታዘዘውና የሰራውም ታቦት ልኩ ይኼው የተጠቀሰው ሆኖ ቤተመቅደሱ ፈርሶ አገልግሎቱ እስከተቋረጠበት እስከ 70 ዓ/ም ድረስ ለ 2000 ዘመን ይህ ልኬታ ተሻሽሎና ተቀይሮ ስለመገኘቱ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ላይ አልተጻፈም። ነገር ግን ዛሬ የጽላቱ ማደሪያ የሆነው ታቦት አለን የሚሉ ወገኖች በሙሴ ሽፋን የሚሰሩት ታቦት ርዝመቱም፣ ቁመቱም፣ ወርዱም እንደጠራቢው ችሎታና እንደአስጠራቢው ፍላጎት እንጂ የተወሰነ መጠን በሌለው ልቅ ፍላጎት ሲጠቀሙ ይታያሉ። የእግዚአብሔርን የመሥፈሪያ ሚዛን ሊጠቀሙ ይቅርና ለሚሰሩት የስሕተት ሥራ እንኳን አንድ ወጥ የሕግ ሚዛን ለራሳቸው የላቸውም። ጠራቢዎቹም የእግዚአብሔር መንፈስ እንደሞላባቸው በሙሴ እንደተመረጡት አልያብና ባስልኤል ሳይሆን ቤተክርስቲያን አነውራ የምትጠራቸው፣ ቆብና ቀሚስ የጣሉ መነኮሳት፣ ያፈረሱ ቄሶችና ደጋሚ ደብተራዎች፣ የሚያስገኘውን ገቢ የቀመሱ አወዳሾች መሆናቸው የአደባባይ ምስጢር ነው።   በመኖሪያ ቤቱ የእንጨት ማሽን ተክሎ፣ ከጣውላ አቅራቢዎች ምንነቱ ያልታወቀ ጥርብ እየገዛ በሚቀርቡለት የፈላጊዎች ትእዛዝ መሠረት ጽላት የሚባለውን የዘመኑን የሰዎች መሻት እየቀረጸ የሚያከፋፍል ሰው የዚኽ ጽሑፍ አቅራቢ ያውቃል። ከሥራዎቹም የተወሰነውን ለማየት ችሏል። ከታች በገብርኤል ስም ከጣውላው የተቀረጸ ምስል ለአብነት ይመለከቷል።   እግዚአብሔር በሚሰራውና ጥንት ባደረገው ነገር ሁሉ ከመረጣቸው ሰዎች ማንነት ጀምሮ የተለዩና በሚሰሩትም ሥራ ጥንቃቄና ትእዛዙን የጠበቀ ስለመሆኑ ለአፍታ የሚዘነጋ ጉዳይ አይደለም።  ዛሬስ? በ 0% የቀደመ ሥርዓት ላይ ሆነው በሙሴ ሕግ ሥር የመደበቅ ዘመን አብቅቷል። በትውልዱም የተሸፈነው መገለጡ አይቀርም። በስተመጨረሻም የእግዚአብሔርም ትእግስት ሲሞላ ውርደት መከተሉ ሳይታለም የተፈታ ነው። በዋጋ መሸጪያ ተመን ገበያ ወጥቶለት በገንዘብ የሚገዛ ጽላት በጭራሽ ሊኖር አይችልም።
እንደእውነቱ ከሆነ በዚህ ዘመን በአባቶች እያሳበቡ የእግዚአብሔርን ቃል በመቀየር በትውልድ ላይ ለመጫን መሞከር ማብቃት አለበት።
 ሙሴ የዕንቁውን ጽላት አሮን ባሰራው የጥጃው ጣኦት ላይ ከሰበረ በኋላ አስመስለኽ ቅረፅና አምጣ ተብሎ በእግዚአብሔር ሲነገረው ለጽላቱ ማደሪያ ተብሎ አስቀድሞ የተሰጠው የታቦቱ ርዝመት፣ ቁመትና ወርድ ላይ የተሰጠ የለውጥ ትእዛዝ አልነበረም። ምክንያቱም የተሰበረው ጽላቱ እንጂ ታቦቱ አይደለምና።  ስለዚህ "ቀር ከመ ቀዳሚ"  የተባለው ጽላቱን እንጂ ማደሪያውን ታቦት ካልሆነ ሙሴ ያላሻሻለውን ታቦት ዛሬ ያሻሻሉት ከየት ባገኙት አምላካዊ ትእዛዝ ነው?  ውሸታቸውን ለማጽደቅ የፈረደበት የሙሴን ስም አቅርበው ሊሞግቱን ይዳዳሉ።
ስለማኅደሩ መሻሻል የተነገረ ካልነበረ እነዚህኞቹ በራሳችን ሥልጣን አሻሽለናል ይበሉን እንጂ ሙሴን ለሐሰት ምስክርነት አይጥሩብን።
ከዚያም ሌላ ሙሴ የፊተኞቹን ጽላቶች አስመስሎ ከቀረጸ በኋላ ይዞ የሄደው ወደሲና ተራራ ነው። በዚያም እግዚአብሔር በጣቶቹ 10ቱን ትእዛዛት ጻፈባቸው እንጂ ሙሴ በጭራሽ አልጻፈም።

ዘዳግም 10፣3-4
ከግራርም እንጨት ታቦትን ሠራሁ፥ እንደ ፊተኞችም ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረብሁ፤ ሁለቱንም ጽላቶች በእጄ ይዤ ወደ ተራራው ወጣሁ።
ስብሰባ ተደርጎ በነበረበትም ቀን እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳት ውስጥ ሆኖ የተናገራችሁን አሠርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደ ነበረ በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ።
ይለናል መጽሐፍ ቅዱሳችን።

እዚህ ላይ እንደምናነበው ጽላቶቹ ላይ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ሆኖ ሳለ ሙሴ እንደጻፈ አድርጎ በሙሴ ላይ መዋሸት ለምን አስፈለገ?  አስመስለኽ ቅረጽና አምጣ መባሉን ልክ እራስኽ እየጻፍክባቸው አባዛ የተባለ ማስመሰል በእግዚአብሔር ላይ መዋሸት አይደለምን? ያልተባለውን እንደተባለ፣ ያልተነገረውን እንደተነገረ አድርጎ በማቅረብ የራስኽንም ስሕተት እንደማጽደቂያ መሳሪያ አድርጎ መጠቀም የከፋ ክሕደትና ሕዝቡን በስሕተት መንገድ መንዳት ነው።  ሙሴን ያላደረገው ነገር አድርገኻል ማለት መሳደብ ነው፣ እግዚአብሔርንም ለሙሴ አንተው ጻፍባቸው ያላለውን እንዳለ ማስመሰልስ ዋሾ ማድረግ አይደለምን?
 ጽላቶቹ ላይ የተጻፈባቸውና ሙሴ የተቀበላቸው 10ቱን ትእዛዛት ሆኖ ሳለ የሰው ስም ወይም የሰው ምስል ያለበት አድርጎ በማቅረብ በዚህ ዘመን እኛ የምንፈልገውን የልባችን ፈቃድ ለማሳካት ማጭበርበርስ ለምን ይሆን? በየትኛውስ ቃል እንደገፋለን? የምናስደስተው ሰውን ወይስ እግዚአብሔርን? መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ያላለውን ብለኻል በሚሉ ዋሾዎች ተደስቶ አያውቅም። ሊደሰትም አይችልም። ከራሱ አንቅቶ የሚናገረው የሐሰት አባት የሆነው ዲያብሎስ ብቻ ነው።
እግዚአብሔር የሰጠውን ሕግ የሚያጸናውና የሚሽረው ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ሰው እንዴት የኪዳኑን ሕግ ራሱ ለራሱ ስሜት ያሻሽላል?
የሙሴን ታቦተ ሕግ ተከትለናል ማለት እግዚአብሔር ያላለውን በራስ ፍላጎት እንደሚመች አድርጎ ማቅረብ ነው እንዴ?
ሌላው መነሳት ያለበት ነገር፣ ዛሬ የኪዳኑን ጽላት እንጠቀማለን የሚሉ ሰዎች የኦሪቱ የጽላት ሕግ፣ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለማነው? የሚለው ነው።

 በማያከራክር መልኩ የቃልኪዳኑ ታቦት ሕግ የተሰጠው ለእስራኤል ዘሥጋ ብቻ ነው። ይኽ ሆኖ ሳለ እናንተን ያ የኪዳን የሕግ ውል የጨመራችሁ በየትኛው የብሉይ ኪዳን ቃል ላይ ነው?  እግዚአብሔር ውሉን በሙሴ ፀሐፊዎች አማካይነት በአራቱ ብሔረ ኦሪት ጽፎ ሰጥቷቸዋል። የእናንተስ ውል በነማን በኩል፣ መቼና የት ቃል ተገባላችሁ? ብለን እንጠይቃቸዋለን።
ምክንያቱም እስራኤላውያን አፋቸውን ሞልተው እንዲህ ሲሉን እናገኛቸዋለን።
ዘዳግም 5 ፣2
አምላካችን እግዚአብሔር በኮሬብ ከእኛ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ።

ያ ቃልኪዳን ከፈረሰና የመስዋእቱ አገልግሎት ከተቋረጠ 2ሺህ ዘመን አልፎታል። ከዚያ በኋላ ከእስራኤላውያን ውጪ እግዚአብሔር የታቦት ቃልኪዳን የገባላቸው ሌላ ሕዝቦች የሉም። ኧረ በጭራሽ አይኖርምም። ምክንያቱም ያ ውል የተገባው ለተወሰነ ሕዝብ ብቻ ስለሆነ ሁሉን ያካተተ አዲስ ውል ያስፈልግ ስለነበር ለተወሰነ ሕዝብ በድጋሜ ቃል የሚገባበት ምክንያት የለም።
ሮሜ 9፣4
እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና"

ነገር ግን ሕዝቤ ያልተባለን ሕዝቤ ለማለት አህዛብ ሁሉ ወደመጠራቱ እንዲገቡ አዲስ ቃል ኪዳን አስፈልጓል።
ሮሜ 9፣26 እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ስፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሔር ልጆች ተብለው ይጠራሉ፥ ይላል።

በዚህም ምክንያት ለአንድ ሕዝብ ብቻ ተሰጥቶ የነበረው ሕግ ቀርቶ ሁሉን የሚመለከት ሕግ እንዲመጣ ማስፈለጉን በአዲስ ኪዳን የኦሪቱ የመስዋእት አገልግሎት ከእንግዲህ አይታሰብም ተብሎ ትንቢት ተነግሯል።

ኤርምያስ 31፣31
እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር።

 ለምን አዲስ ቃልኪዳን መግባት አስፈለገው? ምክንያቱም፣

ኤርምያስ 31፣32
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም፤ እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር።

ስለዚህ በሰማያዊው መስዋእት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተሻለ ኪዳን ስለተገባልን አሁን ልንናገርበት ጊዜው ባልሆነ የዚህ ምድር ሥርዓት አይደለንም። ጳውሎስ ድሮ ነበረ፣ አሁን ግን የለም ይለናል።

ዕብራውያን 9፣5
በላይዋም ማስተስሪያውን የሚጋርዱ የክብር ኪሩቤል ነበሩ፤ ስለ እነዚህም ስለ እያንዳንዳቸው ልንናገር አሁን አንችልም።
ምክንያቱም፣
ዕብራውያን 7፣22
እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።
ስለዚህ አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ መሪያችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን በማለት ለስሕተት መሸፈኛ አድርጎ ማቅረብ አያድነንም። አብርሃም አባታችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን ይሉ የነበረ፣ ነገር ግን የሚነገራቸውን ቃል እኛ ከሁሉ ቀድመን ያወቅን ነን በሚል ትምክህት ለመቀበል ያልፈለጉትን ሊቃውንተ አይሁድን እንዲህ ብሏቸዋል።

ዮሐንስ 8፣47
ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።

ስለዚህ በዚህ ዘመንም የቀደመችው ሃይማኖት በማለት ራስን በመካብ ብልጫ አይገኝም። ከአይሁድ የቀደመ ሃይማኖት የለምና። ነገር ቀድሞ በመገኘት አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ ፈለጋችን ነው፣ ማለት ከስህተት አያርቅም። ምክንያቱም አብርሃምና ሙሴ የተቀበሉትንና የፈፀሙትን ሕገ እግዚአብሔር ሳይሸራርፉና ሳያሻሽሉ በማድረግ እንጂ የነሱ ተከታይ መሆን የሚቻለው በስማቸው በመነገድ ግን በሕጉ በሌሉበት ሁኔታ የሙሴ ተከታዮች በማለት ራስን ካልሆነ ማንንም ማታለል አይቻልም።
ስለሆነም የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም። እንዲቀየርና እንዲሻሻል ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሕግ አልነበረም። ፊተኛውና ኋለኛው ጸሐፊ ራሱ እግዚአብሔር፣ ጽሕፈቱም ሕግጋቶች ነበሩ። የተጻፈውም በሲና ተራራ ነጎድጓዳማ ድምጽ መካከል እንጂ በጥቃቅንና አነስተኛ የእንጨት መላጊያ ውስጥ አልፎ የዚህ ምድር በሆነች እጅ ብልሃት አይደለም።
የእጅ ብልሃት ይኽ ነው።

Tuesday, February 23, 2016

ቃል ኪዳን!


“ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” (መዝ. 88/89፥3)።
በዚህ ቃል ሽፋንነት የገባው የስሕተት ትምህርት፥ የክርስቶስን የመካከለኛነት ስፍራ ለፍጡራን አሰጥቷል። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ከተለያዩ ቅዱሳን ጋር ስለ ልዩ ልዩ ጕዳዮች የገባውን ቃል ኪዳን መነሻ በማድረግና፥ “ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” የሚለውን ቃል በመታከክ፥ በዐዲስ ኪዳንም ኀጢአተኞች ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡበትን የተለያየ ቃል ኪዳን ለቅዱሳን ሰጥቷል የሚሉ አሉ።
በቅዱሳን ስም በተደረሱት ገድላትና ድርሳናት ውስጥ፥ ከራስ ዐልፈው ሰባትና ከዚያም በላይ ያለውን ትውልድ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገቡ ቃል ኪዳኖች እንዳሉ ተገልጧል። ቃል ኪዳኖቹ የተመሠረቱትም በቅዱሳን ስም የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ ነው። ሌላው ቀርቶ የአንዱን ቅዱስ ገድል የጻፈ፥ ያጻፈ፥ ያነበበ፥ የተረጐመ፥ የሰማ፥ ያሰማ እንኳ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርስ ተስፋ የሚሰጡ ገድላት በርካታ ናቸው። ይህም በራእ. 1፥3 ላይ፥ “ዘመኑ ቀርቧልና፥ የሚያነብበው የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁ ብፁዓን ናቸው” ከሚለው የተኰረጀ ሊኾን ይችላል።
በመዝሙረ ዳዊት 88/89፥3 ላይ የተገለጠው፥ እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንጂ ሌሎችን አይወክልም። በቍጥር 4 ላይ፥ “ለባሪያዬ ለዳዊት ማልኹ፤ ዘርኽን ለዘላለም አዘጋጃለኹ፤ ዙፋንኽንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለኹ” ማለቱም ይህንኑ ያስረዳል። ቃል ኪዳን የገባው የማይዋሽ እግዚአብሔር በመኾኑ፥ “ኪዳኔንም አላረክስም፤ ከከንፈሬም የወጣውን አልለውጥም። ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልኹ። ዘሩ ለዘለዓለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሓይ ይኖራል። ለዘለዓለም እንደ ጨረቃ ይጸናል። ምስክርነቱ በሰማይ የታመነ ነው” ብሎ ነገሩን እንዳጻናለት ይናገራል (ቍጥር 34-37)።
ይህ ስለ ዙፋኑ መጽናት የተገባው ቃል ኪዳን ለጊዜው ጥላነቱ በሰሎሞን ሲታይ፥ በክርስቶስ ግን ተፈጽሟል (2ሳሙ. 7፥12-16፤ ሉቃ. 1፥32፤ ዕብ. 1፥5፡8፤ ራእ. 22፥11)። እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ አምላክ በመኾኑ፥ ዳዊት ከሞተ በኋላ ልጁ ሰሎሞን በቃል ኪዳኑ ውስጥ የነበረውን ውል አፍርሶ በመገኘቱ መንግሥቱ መቀደድ ቢኖርበትም፥ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት የገባውን ቃል ኪዳን ዐስቦ ይህን በሰሎሞን ዘመን አላደረገበትም (ዳን. 9፥4፤ 1ነገ. 9፥5-7፤ 11፥1-13)።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ (በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት) ቃል ኪዳን ከተገባላቸው መካከል ዋናዎቹ፥ አዳም፥ ኖኅ፥ አብርሃም፥ ሙሴና ዳዊት ናቸው። ለአዳም የተሰጠው ቃል ኪዳን መልካሙንና ክፉውን በሚያስታውቀው ዛፍ ምልክትነት፥ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ተስፋን የያዘ ነበር። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች አዳምና ሔዋን በኪዳኑ ስላልጸኑ ሞት ገዛቸው (ዘፍ. 2፥8-17፤ ሆሴ. 6፥7)።
ከአዳም ቀጥሎ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለኖኅ ሲኾን፥ ምድር ዳግመኛ በጥፋት ውሃ እንዳትጠፋ የቆመ ኪዳን ነው። ይህ በምድር ላይ የመኖርን ተስፋ የያዘው ኪዳን፥ በቀስተ ደመና ምልክትነት ተገልጦ ለዓለም ሕዝብ ኹሉ ያገለግላል (ዘፍ. 9፥1-17)።
እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው ቃል ኪዳን፥ በብሉይ ኪዳን ጐላ ያለ ስፍራ ከተሰጣቸውና በዐዲስ ኪዳን ፍጻሜ ካገኙት ቃል ኪዳኖች መካከል ይጠቀሳል። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች ለጊዜው ምድራዊቱን ከነዓንን የወረሱት አብርሃምና በይሥሐቅ በኩል የተቈጠሩት ዘሮቹ ኹሉ ሲኾኑ፥ ፍጻሜው ግን አይሁድ፥ አሕዛብ ሳይባል አብርሃምን በእምነት በመምሰላቸው የአብርሃም ልጆች የኾኑት ኹሉ ናቸው (ገላ. 3፥7-9፡29፤ ሮሜ 4፥11-12፤ 9፥7-8)። የዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ግዝረት፥ የቃል ኪዳኑ ተስፋ ደግሞ በዘሩ የአሕዛብ መባረክና ከነዓንን መውረስ ነው (ዘፍ. 17፥1-21፤ ሮሜ 4፥11)።
የምድር አሕዛብ ኹሉ የተባረኩበት የአብርሃም ዘር ክርስቶስ፥ የምድራዊቱ ከነዓን አማናዊት የኾነችውን ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን የሚያወርስ በመኾኑ፥ ለቃል ኪዳኑ ፍጻሜን ሰጥቷል (ገላ. 3፥16)። እግዚአብሔር በክርስቶስ ያደረገው ኹሉ ለአብርሃም በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መኾኑንም ቅዱሳን መስክረዋል (ሉቃ. 1፥54፡73)።
በመቀጠል ደግሞ ለሙሴ የተሰጠውን ቃል ኪዳን እናገኛለን (ዘፀ. 19፥5-6፤ 24፥7-8)። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች የኾኑት ሕዝበ እስራኤል፥ የአብርሃምን የቃል ኪዳን ምልክት ተከትለው ሰንበታቱን መጠበቃቸው ለዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ኾኗል (ዘፀ. 31፥13፤ ሕዝ. 20፥10-17)። በቃል ኪዳኑ የተሰጣቸው ተስፋ በአገራቸው ሕይወትን ማግኘት ነው። ይህንም ገና ከምድረ ግብጽ ሳይወጡ በነበረው ዕለት ምሽት ላይ ያረዱት የፋሲካ መታሰቢያ በግ ደም አረጋግጦላቸዋል (ዘፀ. 12፥21-28)።
ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ሲና ተራራ ሲደርሱ፥ ሕጉን በድንጋይ ጽላት ጽፎ ይጠብቁትና በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል ቃል ኪዳን ይኾን ዘንድ ለሙሴ ሰጠው። ይህም ብሉይ ኪዳን ተብሎ የተጠራው ነው (ዘፀ. 19፥20፤ 31፥18፤ 20፥1-17፤ 34፥28፤ ዘዳ. 4፥13)። በእንሰሳት ደም የቆመው ብሉይ ኪዳን ወደ ፊት ለሚመጣው ዐዲስ ኪዳን መንገድ ጠራጊ እንጂ በራሱ ቋሚነት አልነበረውም። የጽላቱ ተሰብረው መተካታቸው፥ የማደሪያው ድንኳን ሰሎሞን በሠራው ቤተ መቅደስ መተካቱ፥ የመሥዋዕት መደጋገምና የመሳሰሉት ኹኔታዎች ለጊዜያዊነቱ ምልክቶች ተደርገው ይወሰዳሉ። ይበልጥ ደግሞ ትንቢቱ ይህን አረጋግጧል (ዘዳ. 18፥15፤ ኤር. 31፥31)።
ቃል ኪዳን የሚጸናው ኹለቱም ወገኖች ሲጠብቁት ብቻ ነው። ከኹለቱ አንዱ ጠብቆ ሌላው ቢያፈርሰው ቃል ኪዳን መኾኑ ይቀራል። ብሉይ ኪዳን ጊዜያዊነቱ ሳያንስ ሕዝቡ ሊጠብቀው ባለመቻሉ ቃል ኪዳንነቱ ቀረ። እግዚአብሔርም ከዚህ በብዙ መንገድ የተሻለውን ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚገባ ተናገረ (ኤር. 31፥31-34)። ይህም ስለ ዐዲስ ኪዳን የተነገረ ትንቢት በመኾኑ፥ በዕብራውያን 8 ላይ ተፈጻሚ ኾኖ ተጠቀሰ። ዐዲስ ኪዳን የተሻለና የበለጠ ኪዳን በመኾኑ ብሉይ ኪዳን ከነጓዙ ፍጻሜ አግኝቶ እንደሚቀርና የሚጠቀምበት ቀርቶ የሚያስበው እንኳ እንደማይኖር እግዚአብሔር በአጽንዖት ተናገረ (ኤር. 3፥16)።
እግዚአብሔር እስከዚህ ድረስ ለተለያዩ ቅዱሳንና ለአጠቃላዩ የእስራኤል ሕዝብ ገብቶ የነበረውን ቃል ኪዳን ኹሉ በመጠቅለል፥ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ዐዲስና ለዘላለም የማይፈርስ፥ ተጨማሪ የማያስፈልገው ቃል ኪዳን ገባ። እርሱም በገዛ ደሙ የመሠረተው ዐዲስ ኪዳን ነው (ሉቃ. 22፥19-20፤ ኢሳ. 42፥6-7)። ይህ ኪዳን በክርስቶስ ለሚያምኑ ኹሉ የተሰጠ ሲኾን፥ የዘላለም ሕይወትን ተስፋ የያዘ ቃል ኪዳን ነው። የተስፋው ምልክቶችም ጥምቀትና ቅዱስ ቍርባን ናቸው (ማር. 16፥16፤ 1ቆሮ. 11፥23-26፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 80)።
ዐዲስ ኪዳን ብሉይ ኪዳንን በከፊል ሳይኾን ሙሉ በሙሉ ተክቷል። ዐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ክብሩ የጸናበት፥ ኹሉ የተፈጸመበት ታላቅ ቃል ኪዳን መኾኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍትም መስክረዋል፤ “ወበምክረ ዚኣከ ወልድከ ዋሕድ ኢየሱስ ዘተሰቅለ በእንተ መድኀኒትነ ዘበቃለ ኪዳንከ ቦቱ ገበርከ ሠሚረከ ቦቱ። - ለድኅነታችን በተሰቀለው በአንድያ ልጅኽ በኢየሱስ በባሕርይኽ ምክር ደስ ተሰኝተኽበት ቃል ኪዳንኽን ኹሉ በእርሱ አድርገኻል” (መጽሐፈ ቅዳሴ 1984፣ ገጽ 65)።  
እንዲሁም በእልመስጦአግያ፥
“ከመ ታእምሩ ፈቃዶ ለኢየሱስ ክርስቶስ ወትሌብዉ ምስጢረ መድኀኒትክሙ ኦ አንትሙ እደው ወአንስት ቅዱሳት እለ ሀሎክሙ ውስተ ተመክሖ በክርስቶስ፥ ወኩኑ አሐደ ምስለ ብእሲ ዘውስጥ አንትሙኬ እለ አጽንዐ እግዚአብሔር ኪዳኖ ምስሌክሙ ወሤመ መንፈሶ ውስቴትክሙ፡፡”
ትርጓሜ፥ “የኢየሱስ ክርስቶስን ፈቃድ ታውቁ ዘንድና የደኅንነታችኹን ምስጢር ታስተውሉ ዘንድ፥ በክርስቶስ ትምክሕት ያላችኹ እናንተ ወንዶችና ቅዱሳት ሴቶች ሆይ፥ ከውስጣዊ ሰውነት ጋር አንድ ኹኑ፤ እግዚአብሔር ኪዳኑን ከእናንተ ጋር ያጸና መንፈሱንም በውስጣችኹ ያሳደረ እናንተ ናችኹ እኮ” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 24)።
የእግዚአብሔር የባሕርይ ምክርና ሐሳቡ ለአንዴም ለመጨረሻ ጊዜም በክርስቶስ በኩል በገባው ዐዲስ ኪዳን በኩል ተፈጽሟል። እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ጋር ባለው ታሪክ የገባው የመጨረሻው ቃል ኪዳን ዐዲስ ኪዳን ብቻ ነው። በዚህ ኪዳን ያልተፈጸመለት ወይም የቀረው ነገር ኖሮ፥ በሌላ ቃል ኪዳን ለመፈጸም በማሰብ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ሌላ ቃል ኪዳን ገብቷል የሚለው ትምህርት ልብ ወለድ ከመኾን አይዘልም፤ ምክንያቱም የዘመን ፍጻሜ በኾነው ባለንበት ዘመን፥ እግዚአብሔር ለማድረግ ያሰበው፥ ነገሮችን ኹሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል እንጂ ሌላ ቃል ኪዳን ለመግባት አይደለም (ኤፌ. 1፥10)።
ከላይ ለማሳየት እንደ ተሞከረው፥ ለቀደሙት አበው የገባው ቃል ኪዳን፥ ከወቅቱ ኹኔታ ጋር በተያያዘ መንገድ፥ ወይም ስለ ወደ ፊቱ ተስፋ ነበር እንጂ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ቃል ኪዳን አልነበረም፤ እንዲህ ያለውን ቃል ኪዳን ከማንም ፍጡር ጋር አልገባም። ምናልባት ለአዳም የገባው ቃል ኪዳን በአዳም ባይፈርስ ኖሮ፥ ለዘላለም በሕይወት መኖርን የሚያስገኝ ቃል ኪዳን ይኾን ይኾናል። ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበትን ቃል ኪዳን የገባው ግን በክርስቶስ በኩል ብቻ ነው።
በሐሰት ለቅዱሳን በዐዲስ ኪዳን ተገባ በሚባለው ቃል ኪዳን መሠረት፥ እንዲህና እንዲያ ያደረገ ይህንና ያን ያገኛል የሚል ተስፋ በብዙ አዋልድ መጻሕፍት በስፋት ተጽፎ እናነባለን። አብዛኛው ቃል ኪዳን ተሰጠ ተብሎ የሚተረከው ቅዱሳኑ ሊሞቱ ሲሉ በመጨረሻዋ ሰዓት ላይ ነው። እንዲህ ከኾነ ታዲያ በዐዲስ ኪዳን መጥምቁ ዮሐንስ፥ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ፥ እና ያዕቆብ በግፍ የተገደሉ ቅዱሳን ናቸው፤ ሊሞቱ ሲሉም ኾነ ከዚያ በፊት ቃል ኪዳን እንደ ተገባላቸው በሐዲስ ኪዳን ውስጥ አናገኝም (ማቴ. 14፥10-12፤ ሐ.ሥ. 7፥6 12፥2)። ለነዚህ ቅዱሳን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ሰዎች ከልባቸው አንቅተው (አመንጭተው) በደረሱላቸው ድርሰትና ገድላት ውስጥ ግን፥ የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን ጻጽፈው ሊያስነብቡን ቢከጅሉም አንድም እውነትነት የለውም።
ዛሬ ብዙዎቹ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባልኾነ ቃል ኪዳን ተታለዋል። ስለዚህ በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ከመጽደቅና በእርሱ ኖረው መልካም የሥራ ፍሬን ከማፍራት ይልቅ፥ በኀጢአት ላይ ኀጢአትን በመጨመር ከእግዚአብሔር ባልኾነው ቃል ኪዳን እየተኵራሩ፥ ‘በእገሌ ቃል ኪዳን መሠረት እንዲህ ካደረግኹ አልኰነንም’ ብለው ራሳቸውን ይሸነግላሉ። የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ይላቸዋል፤ “ለዐመፀኞች ልጆች ወዮላቸው፥ ይላል እግዚአብሔር። ከእኔ ዘንድ ያልኾነ ምክር ይመከራሉ። ኀጢአትንም በኀጢአት ላይ ይጨምሩ ዘንድ ከመንፈሴ ዘንድ ያልኾነውን ቃል ኪዳን ያደርጋሉ።” (ኢሳ. 30፥1)።
ምንጭ፦ የተቀበረ መክሊት 3ኛ ገጽ 106

Sunday, February 14, 2016

የቫላንታይን ዴይ ከክርስትና አንፃር!


ስንቶቻችን ይሆን የቫለንታይን ቀን (የፍቅረኞች ቀን ብለን የምናከብረው) የሚከበርበት ምክንያትና መነሻው የምናውቀው? ወይስ ሰው ስለ አከበረውና የስልጣኔ መገለጫ መስሎን ነው የምናከብረው? ክርስቶስ ከመወለዱ ከብዙ ክፍለ ዘመናት በፊት አረማዊ ሮማውያን የካቲት 14 ማታና የካቲት 15 "የተኩላ አዳኙ" ለሚሉት ሉፐርኩስ (Lupercus) ክብር በማለት በጣኦት አምልኮ ያከብሩት ነበር። ሮማውያን ይህ በዓል ሉፐርካልያ (Lupercalia) ይሉታል።
ንጉሥ ቆንጠንጢኖስ ክርስትና የሮማውያን ይፋዊ ሃይማኖት መሆኑ በማወጁ ማንኛውም የጣኦት አምልኮ እንዲቀር ቢያስጠነቅቅም የተወስኑ ሮማውያን ሰዎች ግን በዓሉን ማክበር አልተዉም።
ይህንን አረማዊ በዓል ማለትም ሉፐርካልያ የሮማው ጳጳስ ገላስዮስ ክርስትያናዊ በዓል ሆኖ እንዲከበር አደረጉ። ጳጳስ ገላስዮስ ለካቲት 15 ሲከበር የነበረው በዓል የቅዱስ ቫለንታይን ቀን በሚል አዲስ ስያሜ የካቲት 14 እንዲከበር አደረጉ።
እንዴት ይህ አረማዊ በዓል የቅዱስ ቫለንታይን ቀን የሚል ስያሜ ተሰጠው?
ቫለንታይን የሚል ስም በሮማውያን ዘንድ የተለመደ ስያሜ ነው። ቫላንታይን ጥንታዊው ታዋቂው ሉፐርኩስ ነው። ሉፐርኩስ በግሪካውያን ፓን (pan) ተብሎ ይጠራል። በጥንታውያን አይሁድ ደግሞ ይህ ፓን በአል (Baal) በሚል ስያሜ ይታወቃል። በአል በመጽሓፍ ቅዱስ ዘፍጥረት 10-9 ላይ ታላቁ አዳኝ ተብሎ ለተገለጸው ኒምሮድ ሌላኛው መጠርያው ነው። ኒምሮድ የሮማውያን የተኩላ አዳኙ ሉፐርኩስ ነበር። በዚህ መሠረትም የቅዱስ ቫለንታይን ቀን የአረማውያን ለኒምሮድ ክብር የሚያከብሩት የጣኦት አምልኮ ነው።
ቫለንታይን የሚል ቃል ቫለንቲኑስ (valentinus) ቫለንስ ከሚል የላቲን ቃል የመጣ ነው። ቀጥተኛ ትርጉሙ ጠንካራ፣ሃይለኛ ታላቅ ማለት ነው። ዘፍጥረት10-9 ላይ እንደምናነበው " እርሱም በእግዚአብሔር ፊት አዳኝ ነበረ። ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት ሃያል አዳኝ እንደ ኒምሮድ ተባለ።  ኒምሮድ የሮማውያን ጀግና ሃይለኛ ሰው ቫለንታይን ነበር።
ሌላኛው የኒምሮድ ስም ሳንክቱስ (Sanctus) ወይ ሳንታ (santa) ነው። ሳይንት (saint) የሚል የእግሊዝኛ ትርጉም አለው ማለትም ቅዱስ። የሮማውያን ሉፐርካልያ በመጨረሻ ቅዱስ ቫለንታይን የሚል ስያሜ ያዘ ማለት ነው።
ጥንታውያን ሮማውያን ከባቢሎናውያን በቀዱት አረማዊ የልብ (heart) ምልክት ይጠቀማሉ። በባቢሎናውያን በአል (baal) ልብ የሚል ፍቺ ነው ያለው። በአሁኑ ጊዜ ይህ አረማዊ የልብ ምልክት ለቫለንታይን ቀን (የፍቅረኛሞች ቀን የምንለው) መገለጫ እንጠቀምበታለን። በአል የባቢሎናውያን የጣኦት ጌታ ነበር። በሌላ መንገድም ኒምሮድ ወይም ቅዱስ ቫለንታይን ሳተርን ተብሎ ይጠራል። ሳተርን የሮማ-ባቢሎን ከአባራሪዎቹ ለመሸሽ በምስጥራዊ ቦታ የሚደበቅ ጣኦት ነው። ሳተርን የሚል የላቲን ቃል ሴሜቲክ (አይሁድ) ቋንቋ ከሚናገሩ ባቢሎናውያን የተገኝ ነው። መደበቅ፣ ራስን መደበቅ የሚል ፍቺ አለው።
በጥንታዊ እምነትም ኒምሮድ (ሳተርን) ከአባራሪዎቹ በመሸሽ ወደ ጣልያን እንደተጓዘ ይነገራል። የአፐኒን ተራራ ስያሜው ወደ ኔምብሮድ ወይም ኒምሮድ ተቀየረ።ይህ ተራራ ኒምሮድ በጣልያን የተሸሸገበት ቦታ ነበር። ሮማም በዚህ ተራራ ላይ እንደ ተመሰረተች ይታወቃል። ሮም ፈርሳ እንደገና ከመሰራትዋ 753 ዓ/ዓ በፊት ሳቹርንያ (ሳተርን፡ኒምሮድ የተደበቀባት ቦታ) የሚል ስያሜ ነበራት። ኒምሮድ በዚህ ቦታ ተይዞ በፈጸመው ወንጀል ተገደለ። በንጉሥ ቆስንጠንጢኖስ ጊዜም ክርስቲያናዊ ሰማዕት የሚል የውሸት ክብር ተሰጥቶት በሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስትያን መዘከር ጀመረ። ኒምሮድ፣ ባል፣ ቫለንታይን፣ ታላቁ አዳኝ፣ ፋውኑስና ሉፐርክስ 31ኛ፣ 32ኛና 33ኛና ደረጃ (ዲግሪ) ላይ ያሉ ፍሪማሶኖሪዎች ከሚያመልኩት ባፎሜት (የሜንደዝ ፍየል) አምልኮ አጋንንት ጋር የሚስተካከል ነው።
እንግዲህ በሰላቢ እጆች (ኢሉሚናቲ) ሴራ ዘመናዊነት ተላብሶ ድብቅ ጣኦት የሚመለክበት የቅዱስ ቫለንታይን ቀን እኛ ደግሞ የፍቅረኛሞች ቀን በማለት እያከበርን ማለትም እያመለክን ነው። አንድ በአል የሚከበርበትን ምክንያትና አስፈላጊነት ሊኖረው ግድ ነው። ሆኖም የምናከብረውን በአል የምናከብርበትን ምክንያትና አስፈላጊነት ሳናውቅ ከሴረኞች ድብቅ አላማ ማስፈጸሚያ ከመሆን መቆጠብ ይበጀናል፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር ነዉ!